Thursday, July 20, 2023
ፕሪቴሪዝም፣ የተፈጸመው ሥነ-መለኮት: በታሪካዊ መዛግብት ከተረጋገጡ አንዳንድ ምልክቶችና ምስክሮች ጋር
Friday, June 30, 2023
የብልጥግናና የጤንነት "ወንጌል"
የጥፋት ወንጌል
"ስለዚህም በመገለጥ ታላቅነት እንዳልታበይ የሥጋዬ መውጊያ፥ እርሱም የሚጎስመኝ የሰይጣን መልእክተኛ ተሰጠኝ፤ ይኸውም እንዳልታበይ ነው። ስለዚህ ነገር ከእኔ እንዲለይ ሦስት ጊዜ ጌታን ለመንሁ። እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ። ስለዚህ ስለ ክርስቶስ በድካም በመንገላታትም በችግርም በስደትም በጭንቀትም ደስ ይለኛል፤ ስደክም ያን ጊዜ ኃይለኛ ነኝና።" 2 ቆሮ 12፥ 7-10
፩.
እንደ መነሻ የጠቀስኩትን ይህንን የንባብ ክፍል ኋላ ላይ እመለስበታለሁ። ልንሰማው በሚያስፈልገን የመዳን ወንጌል ጤናማ ቃልና እኛ ልንሰማው በምንፈልገው "ጥሩ ዜና" መካከል ልዩነት አለ። እንደሚታወቀው ሰዎች የሆንን ሁሉ ልንሰማው የሚያስፈልገን መልካሙ የምስራች አንድ ነው። ነገር ግን በዚህ አለም ብዙ አይነት ጥሩ ዜናዎች ሊኖሩ ይችላሉ። እስቲ ሰው ሁሉ ሊሰማው የምፈልገውን ጥሩ ዜና ላሰማችሁ። ምናልባትም ይህ አንዳንዶቻችሁ ሰምታችሁት የማታውቁት፣ ብዙዎቻችሁ ግን አሁንም ድረስ እንደ እግዚአብሔር መልዕክት የምትቆጥሩት ስሜት ኮርኳሪ ምርጥ ዜና ሊሆንላችሁ ይችላል። ልትሰሙት ዝግጁ ናችሁ?
"እነሆ እግዚአብሔር ሁላችሁም ጤናማ እንድትሆኑ፣ በሽታም እንዳያገኛችሁ፣ ሀብታም እንድትሆኑ፣ ድህነትም እንዲርቃችሁ፣ ከሥቃይ ነፃ እንድትሆኑ እና በምትሠሩት ሁሉ እንድትበለጽጉና በብዙ እንድትከናወኑ ፈቃዱ ነው፤" የሚል ዜና ነው። ይህ ታዲያ ጥሩ ዜና ነው ወይስ መጥፎ? ይህ እኛ መስማት እጅጉን ደስ የሚለን ዜና ነው፣ አይደል? ይህ ታዲያ ምን ክፋት አለው? እንዲህ ያለው ዜና የያዘውን መልእክት መስማት አትወዱምን? በርግጥም ትወድዳላችሁ እንጂ ለምን አትወዱም? እግዚአብሔር ሁላችሁም ጤናማ እንድትሆኑ፣ ሀብታም እንድትሆኑ፣ ከሥቃይ ነፃ እንድትሆኑ እና በምትሠሩት ሁሉ እንድትበለጽጉ የሚፈልግ መሆኑ መልእክቱ አሪፍ ዜና ካልሆነ ታዲያ ምን ሊሆን ይችላል?
የዚህ መልእክት ብቸኛው ችግር ግን እውነት አለመሆኑ ነው። እውነት ደግሞ መስማት ደስ ከሚለንና ከምንፈልገው ነገር በላይ ዋና አስፈላጊ ነው። አዎን፣ በተለይም ይህ ስለ እግዚአብሔር እና ስለ መጽሐፍ ቅዱስ እውነቱን ስንናገር የሚሰራ ነው።
እስቲ ልጠይቃችሁ፣ ስለ ጤንነት/ብልጥግና ወንጌል ምን ይሰማችኋል? እንዲህ ላለው ጉዳይ ግድ የለሾች ናችሁን? እሱንስ ሳይጎረብጣችሁ ታግሶ ለመስማት አቅም አላችሁን? ሲሰሙት ለጆሮ የሚጥም ከመሰለ፣ ቃሉን እያጣመመ ከሚሰራ እንዲህ ካለ ትምህርት ጋር በጽኑ ካልተጣላችሁ፣ እንዲህ ያለው ትምህርት በንዴት ካላቃጠላችሁ፣ ከሁለት ነገሮች አንዱ በህይወታችሁ እውነት ነው ማለት ነው፦ 1ኛ. የብልጽግና ወንጌል የሚያስተምረው ግልሙትና ምን እንደሆነ አልገባችሁም ወይም ጨርሶ አታውቁትም ማለት ነው፤ አልያም 2ኛ. ወንጌል ራሱ ከመሰረቱ አልገባችሁም። ወንድሜ ሆይ፣ ወንጌልን በአግባቡ ተረድተኸው ከሆነ ያኔ ሕያው ሆነህ የጤንነት/ብልጥግና ወንጌል አስተማሪዎች የሚሰብኩትን አደጋ በንቃት ታውቃለህ፤ ራስህንም ሆነ በአጠግብህ ያለውን ክርስቲያን ከአደጋው ለመጠበቅም ትተጋለህ። ካልሆነ ግን ሞት በመሰለ ከባድ እንቅልፍ ተይዘሃል፣ ሳትቀበር በፊት ፈጥነህ መንቃት አለብህ። ዝም ብለን ተጎልተን አገሩን የሞላው የሀሰት ወንጌል ህዝባችንን እየጠራረገው ነው። "ሰይፍ ከዋጠው ሕዝብ ሁሉ ይልቅ ዱር ብዙ ዋጠ" (2ሳሙኤል 18፥ 8) እንደተባለ ኮምኒዝምና መከራው ካደረሰው ጥፋት በላይ የነጻነቱ ዘመን የትምህርት አሰስ ገሰስ ብዙዎችን ውጧል።
እኔ እንደማስበው ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን የተናገረው ቃል ዛሬ እኛን የሚመለከት ይመስለኛል፡-
"ይሁን እንጂ፥ መጥቼ ባያችሁ ወይም ብርቅ፥ በአንድ ልብ ስለ ወንጌል ሃይማኖት አብራችሁ እየተጋደላችሁ፥ በአንድ መንፈስ እንድትቆሙ ስለ ኑሮአችሁ እሰማ ዘንድ፥ ለክርስቶስ ወንጌል እንደሚገባ ኑሩ።" (ፊልጵስዩስ 1፥ 27)
ጳውሎስ ለእነዚህ አማኞች "ጸንታችሁ ቁሙ" የሚል ምክር ይሰጣቸዋል። ይህም ስቴኮ (Steko) ከሚለው የግሪክ ቃል የተተረጎመ ነው። ይህ ቃል የሚልቴሪ ሳይንስ ሙያዊ ቃል ሲሆን፣ ትርጉሙም "በጦርነት ውስጥ ያለመናወጥ መቆም፣ መረጋጋት" ማለት ነው። የገጠመው ጦርነት የቱንም ያህል ቢከፋ ስፍራውን ለማይለቅና ከቦታው የማይነቃነቅ ወታደርን ለመግለጥ ጥቅም ላይ ይውላል።
ጳውሎስ በተሰጣቸው የወንጌል ባላደራነታቸው፣ ከስህተት ወይም ከኃጢአት ጋር ባላቸውም ተጋድሎ ጸንተው እንዲቆዩ፣ በትምህርታቸውም ሆነ በምግባራቸው ሳይነቃነቁ እንዲቆሙ እየነገራቸው ነው። ይህ ወታደራዊ የሆነ ያነጋገር ዘይቤ በከፍተኛ ጥቃት ውስጥ እያሉ ቢሆን እንኳ ገዢ ቦታን ሳይለቁ ገትሮ ከመያዝና ወጥሮ ከመዋጋት ጋር የተያያዘ ነው። “ጸንታችሁ ቁሙ” ሲልም በአእምሮው ውስጥ በአስተምህሮ እና በሥነ ምግባራዊ ጉዳዮች ላይ የማመቻመች ፈተናን የመቃወም ነገር አለው።
ጳውሎስ “ለወንጌል እምነት አብራችሁ ተጋደሉ” በማለት ይነግራቸዋል። “በአንድነት መጋደል” የሚለው የግሪክ ቃል "ሱናትሊዮ" (sunathleo) ከሚለው ሁለት ቃል የተገኘ ሲሆን፣ እሱም sun “በጋራ” እና athleo "ውድድርን ወይም ፉክክርን መሳተፍ" ማለት ነው። አትሌቲክስ የተሰኘው ስፓርታዊ ውድድርም ስያሜውን ያገኘውን ከዚሁ የግሪክ ቃል ነው።
ይህ ተጋድሎ በጦር ግንባር እና በጨዋታ ሜዳ ላይ እንደሚደረግ የሕይወትና የሞት ሽረት ትግል እንዳለበት የግላዲያተር ፍልሚያ ከውድድርና ከፉክክር ጋር የተያያዘ ነው። ይህም አብሮ መጋደል በቡድን ተጣምሮ ለማሸነፍ ጥረትን ሁሉ የማሳየት ጥሪ ነው። በወንጌል የመጋደልን ጥሪ እና አደራ ያላወቀ አማኝ የወንጌልን እውነት እያመቻመቸ ለአለም የሚመች ማህበረረባዊ ወንጌል (social gospel) አቀንቃኝ ይሆናል። እኛ የወንጌል አማኞች ግን፣ “በአንድ መንፈስ ጸንተን በአንድ ልብ ለወንጌል እምነት አብረን የምንጋደል” መሆን አለብን። በዛሬው ዘመን ክርስትና ግን የወንጌል መልእክት ምንነት ግልጽ አይደለም፣ ማንኛውም ሰው ወንጌል ምን እንደሆነ የብልጭታን ያህል ፍንጭ ቢኖረው በጤንነት/ብልጥግና ወንጌል ላይ አሰላለፉን ባስተካከለ ነበር።
ወንጌል እግዚአብሔር በልጁ ሞት በኩል ለኃጢአተኛው ሰው ቤዛ ሆኖ እንዳቀረበ የሚታወጅ የምስራች ነው። ይህ ቤዛነት ለሚያምኑ ሁሉ በጸጋ ይታደላል። በክርስቶስ ላይ የሚያርፈው እምነት በአእምሮው፣ በአካሉና በመንፈሱ የተበላሸውን ኃጢአተኛ ወስዶ ከኃጢአቱ ሁሉ ያነጻዋል፣ በእግዚአብሔርም ፊት ጻድቅ ያደርገዋል፣ የዘላለምንም ሕይወት ይሰጠዋል። ያ ነው እንግዲህ መልካም ዜና ነው የምንለው።
፪.
ክርስቶስ የኃጢያት እዳዬን እንደከፈለልኝ አምናለሁ ከዚህ የተነሳ ኑሮዬና ደረጃዬ ፍጹም ተለውጦ ከችግር ሁሉ ተላቅቄ ሁሉ መልካም ይሆናል ብሎ ማሰብ ግን ፈጽሞ አይሰራም፤ እስቲ አሁን የምኞትና የቅዠት ጥግ ካልሆነ በቀር የኃጢአት ዕዳ ክፍያና የኑሮ ደረጃ ለውጥ ምን ያገናኛቸዋል? እንዲህ ያለው እብደት ፈጽሞ የክርስቶስ ወንጌል አይደለም። በክርስቶስ የሙስቀል ሞት የተገኘው የኃጢአት ዕዳ ክፍያ ከዘላለም ኩነኔ መዳኛ እንጂ ከችግር ነጻ ሆኖ የመኖር ዋስትና አይደለም። አሁንም የእለት ጉርስ ማጣት፣ የመኖሪያ ቤት እጦት፣ ያለቀ ጫማና የተቀደደ እራፊ፣ የተኛ የመኪና ጎማ፣ የተሰበረ አጥንት፣ የታመመ አካል ሊኖረኝ፣ የትዳር ጭቅጭቅ፣ የገንዘብ እጥረት ትግል ሊኖርብኝ ይችላል፤ እውነታው ደግሞ ይኸው ነው። የአገር ቀበኞች የደኃውን ገንዘብ ከመመዝበር እጆቻቸውን ካልሰበሰቡና በላብ ሰርቶ በኢኮኖሚ ከመለወጥ ውጪ ህይወት እንደሁ ሁልጊዜ ትግል ናት!
ነገር ግን የጤንነት/ብልጥግና ወንጌል አቀንቃኞች ደረጃው እየጨመረ በሚያድግ እምነት እግዚአብሔር በከፍተኛ ጤና እና ሀብት አትረፍርፎ እንደሚከፍል ደፍረው ያስተምራሉ። ሲናገሩም እግዚአብሔር የዘላለም ሕይወትን ብቻ ሳይሆን ብራንድ ሀብታም እና ህመም የማያውቀው ፍጹም ጤናማ እንድትሆኑ፣ እንዲሁም ከየትኛውም ስቃይና መከራ ነፃ እንድትሆኑ፣ ከችግር ተላቃችሁም እንድትኖሩ ይፈልጋል ሲሉ በአዎንታዊ ማነቃቂያ እያባበሉ ያስተምራሉ።
እንዲህ ያለ ከመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ያፈነገጠ ነገር "ወንጌል አማኝ" ነን በሚሉት ዘንድ እንዴት ሊታሰብ ቻለ? እንዴትስ ስር ሰዶ በመሰራጨት "ወንጌላውያን አማኞችን" ከክርስቶስ ወንጌል ሊያርቃቸው ቻለ? በእውነቱ ይህ ጥሩ ጥያቄ ነው። ይህንን ለማስተዋል እንዲቻለን በአገራችን እንደ ጉድ የፉሉትን አነስተኛና ጥቃቅን እባብ የብልጥግና ሰባኪዎች ላይ ጊዜ ከምናጠፋ ዘንዶ እና አናኮንዳ የሆኑ አባቶቻቸውን፣ ትምህርቶቻቸውንና ልምምዶቻቸውን ነቅሰን እያወጣን ስለ ብልጽግና ወንጌል ታሪካዊ ዳራ ጥቂት ነገር ለማለት እንሞክራለን። ከምዕራባውያን የቴሌቪዥን ሰባኪዎች በተቀዳ ትምህርትና በተኮረጀ ስታይል የሚያቅራሩብንን የአገራችንን የብልጥግናና የስኬት እርኩስ ወንጌል ሰባክያንን ተውት አድርገን ምንጫቸውን እንመርምር።
እንደ ቅደም ተከተላቸው የመጀመሪያዎቹ የአዎንታዊ አስተሳሰብ አራማጆች፣ ፊኒያስ ፒ. ኩዊቢ እና ሜሪ ቤከር ኤዲ፣ የመሰሉ የአዲስ አስተሳሰብ እንቅስቃሴን እና የክርስቲያን ሳይንስ መንፈሳዊ አስተሳሰብ መስራቾች ቀደምት ፈጣሪዎች ነበሩ። በ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መባቻ ላይ የቤቴል መጽሐፍ ቅዱስ ተቋም መሥራች እና መጋቢ ኤሴክ ዊልያም ኬንዮን ስለ ክርስቶስ የተጠናቀቀ ሥራ በሚሰብክበት ጊዜም ተመሳሳይ የሆኑ የአዎንታዊ ሐሳቦችን አካትቶ ያስተምር ነበር። ኬንዮን ክርስቲያኖች ስሜታዊ እና አካላዊ የሆኑ ፍላጎቶቻቸውን ለማሟላት “አዎንታዊ ኑዛዜ” (positive confession) ሊያደርጉ እንደሚችሉ ጽፏል። ሲናገርም "እኔ የተናዘዝኩትን (ያልኩትን) ነኝ/አለኝም" ይል ነበር።
በ1930ዎቹ ኬኔት ሀገን የቃል-እምነት እንቅስቃሴን ሲጀምር የኬንዮንን ትምህርት እንዳለ በመቅዳት ከጴንጤቆስጤ እምነትና አስተምህሮ ጋር ቀይጦ ማስተማርን ጀመረ። የእግዚአብሄር ማኅበረ ቅዱሳን የተባለ ቤ/ክ መጋቢ የነበረው ይህ ኬኔት ሀገን ክርስቲያኖች በቂ እምነት በማሰባሰብ ሀብታም መሆን እንደሚችሉ ሲያስተምር ይደመጣል። "በእምነት በለው፣ አድርገው፣ ተቀበለው፣ አውራው" የሚሉ የቃል እምነት መርሆዎችን ፈብርኮ ክርስቲያኖችን በቅዠት አለም ያሰክራችው ነበር። በእምነት የሚነገሩ ቃላቶች መሟላት እንዳለባቸው የሚገልጽ “ጥራው" እና "በይገባኛል ውረሰው” የሚሉ መፈክሮችን ያስከተለውን “የሬማ አስተምህሮ” አስፋፍቷል። ይህን ተከትሎ በ1960ዎቹ የኦራል ሮበርትስ ወጣት ተባባሪ ኬኔት ኮፕላንድ እምነት “ኃይል” እንደሆነ ማስተማር ጀመረ፤ እሱም ጮክ ባለ ድምጸት በይሆናል አይነት ስሜት ሲናዘዝ (ሲመሰከር) የተጠበቀውን ቁሳዊ ውጤት ያመጣል፣ ይል ነበር። በሁለት አስርት አመታት ውስጥ፣ ይህ Word-Faith ልክ እንደ ካንሰር ሆኖ ወደ ትልቅ የካሪዝማቲክ እምነት ዘር አድጓል።
የእነዚህን ሰዎች አስተምህሮ እንደሚከተለው ማጠቃለል ይቻላል፡- እግዚአብሔር ሰውን የፈጠረው እንደ ሉዓላዊ ፍጡራን “የእግዚአብሔር ዓይነት እምነት”ን በመጠቀም ነገሮችን በመጥራት ወደ መኖር እንዲያመጣቸው፣ በብልጽግናና በስኬት የመኖር ችሎታ ያለው አድርጎ “በእግዚአብሔር ደረጃ” (ወይንም እንደ “ትናንሽ አማልክት”) እንዲሆን ነው። ነገር ግን በገነት ውስጥ በእግዚአብሔር ላይ በማመፅ እና የሰይጣንን ተፈጥሮ በመያዝ ይህንን እድል አጥተናል። ይህንን ሁኔታ ለማስተካከል፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆነና፣ በመንፈስ ሞተ (በዚያም የሰይጣንን ባሕርይ ለብሶ/ ሰይጥኖ)፣ ወደ ሲኦል ወረደ፣ “በሲኦልም ዳግመኛ ተወለደ”፣ እንደገናም በእግዚአብሔር ባሕርይ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፣ ከዚያም መንፈስ ቅዱስን ላከ። በዚህም ትስጉዑቱን በአማኞች ውስጥ ሊያባዛ ይችላል፣ ከዚህም የተነሳ አማኞች እንደ እርሱ ትናንሽ አማልክት የመሆን ጥሪያቸውን ይፈጽማሉ። አሁን የተጠራነው እንደዚህ አይነት ህይወት እንድንለማመድ ስለሆነ በሁሉም የህይወታችን ዘርፍ ስኬታማ መሆን ይኖርብናል። እንግዲህ እነዚህ ሰዎች ብዙውን ጊዜ እንደሚያስተምሩት በዕዳ የመያዝ ሁኔታ ቢሆን፣ ወይም ጤና የማጣት ጉዳይ፣ ወይም ትዳርን የማጣትና የቤተሰብ መበተን ሁኔታ፣ እንዲሁም ማናቸውም እነዚህን የመሳሰሉ ችግሮችን በተመለከተ የእግዚአብሔርን ተስፋዎች "በማወጅ" መፍትሄን አለማግኘት ያው የእምነት ማነስን ያሳያል፣ ይላሉ። ከላይ ያለው አስተምህሮ አንዳንድ ገጽታዎች ከአስተማሪ ወደ አስተማሪ ሊለያዩ ቢችሉም ቅሉ፣ አጠቃላይ ዝርዝሩ ግን በእያንዳንዱ ጉዳይ ላይ ያው አንድ አይነት ነው።
የዚህ ዓይነቱ ሥነ-መለኮት ከምዕራቡ አለም እየናኘ ድንኳኖቹን በማስፋት ካስማዎቹንም በማርዘም ወደሩቅ ደርሷል። መላውን የሩቅ ምስራቅ ክርስትናና የአፍሪካን ምድር እያጥለቀለቀ በተለይ ከኮምኒዝም ስደት በኋላ በምድራችን በኢትዮጵያ ያለቅጥ ተሰራጭቷል። ይህ ትምህርት በእርግጥ ሰዎችን በጤናና በስኬት እያባበለ ይማርካል፣ ትምህርቱና ልምምዱ ከእምነት በስተቀር ምንም ስለማይፈልግ እርሱም ደግሞ በቂ እምነት ከሆነ፣ ከዚህ የተነሳ ሰዎች ባለጠጋና ጤናማ ሊሆኑ እንደሚችሉ ተስፋ ይሰጣል። እንዲህ ያለው መልዕክት "በህልሙ ቅቤ እንደሚጠጣ ደሀ" ሰዎች ሊሰሙት የሚፈልጉት አይነት ስለሆነ በብዙዎች ዘንድ ተወዳጅ መልእክት ሆኖላቸዋል።
የዚህ ጠማማ ወንጌል አንዳንድ አስተማሪዎች የሚሉትን ስሙ፦ "እኔ ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ ነኝ --እስከፍጻሜዬም እንደዚያም ነው ብዬ ማንም አማኝ በብሽታ እንዳይታመም በኢኮኖሚም እንዳይቸገር፣ እያንዳንዱም አማኝ በዚህ ምድር ላይ እድሜው ሳይቀጠፍ ሙሉ ህይወቱን ቆይቶ እንዲኖር፤ በታላቅ ፍቅሩ እና በታላቅ ምህረቱ የተገለጠ የአባታችን የእግዚአብሔር እቅድ ነው ብዬ በዚሁ እምነት እሞታለሁ፤ እያንዳንዱም አማኝ በመጨረሻ በኢየሱስ ሆኖ መተኛት አለበት" (ኬኔት ኢ ሃጊን፣ ስለ መለኮታዊ ፈውስ ማወቅ ያለብህ ሰባት ነገሮች፣ ገጽ 21)።
ኬኔት ኮፕላንድ "የብልጽግና ህጎች" በተሰኘው መጽሃፉ በገጽ 51 ላይ "እንዲያበለጽግህ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሆነ መገንዘብ አለብህ። ይህም ለአንተ ተዘጋጅቶ የሚጠብቅህ ነው፣ እውነቱን ለመናገር እስካሁንም ከሱ አለመካፈልህ ትልቅ ሞኝነት ነው" ይላል።
የብልጽግና ወንጌል ዋና ስህተት አንዱ ማዕከላዊ መርህ ፦ እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ክርስቲያን በገንዘብ ባለጸጋ እንዲሆን ፈቃዱ ነው፣ ስለዚህም አማኝ በድህነት መኖሩ እግዚአብሔር ካሰበለት ፈቃዱ ውጭ መኖር ነው የሚለው ነው። በተለምዶም ራሱን የሸሸገበት አንዳች ቦታ፦ እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ስለሆንን ሁል ጊዜም ቢሆን የመጀመሪያውንና የታላቅነትን ደረጃ መያዝ አለብን፣ ራስ እንጂ ጅራት ስላልሆንን ከሁሉ ከፍ ያለውና መልካም የሆነው ሁሉ ሊኖረን ይገባል። ለእግዚአብሔር ክብር የሚያመጣውም ይህ ብቻ ነው! የሚለው ማረጋገጫው ነው። ሰሞኑን እንደውም አንዱ ያገራችን ጉድ ድህነት አርነት መውጣት የሚጠይቅ ሰይጣናዊ እስራትና እርግማን ነው እያለ ጣቃውን ሲቀደድ በሶሻል ሚዲያ ሰማሁት። እንዲህ ያለው ሰባኪ ነኝ ባይ በጥልቅ ድህነት ውስጥ ይኖሩ የነበሩትን የሜቄዶንያን ቅዱሳን ምን ሊላቸው ነው? ምነው ጳውሎስስ ቢሆን ከዚህ እስራት ሳይፈታቸው ቀረ?
እነዚህ የሐሰት ወንጌል አስተማሪዎች በአብዛኛው የእግዚአብሔርን ቃልና ተገቢነት ያለውን አተረጓጎም ችላ ቢሉም፣ ያንን እርኩስ ትምህርታቸውን ግን እዚህም እዚያም በተቆነጠረ የቅዱሳት መጻሕፍት ጥቅሶች ለማስደገፍ ይሞክራሉ። መቼም የቃል እምነት መልእክትን የሚያስተላልፉ ማናቸውም የሕትመት ሥራ ሆነ ወይም አስተማሪ ነኝ ባይ ከ3ኛ ዮሐንስ መልዕክት ቁጥር 2 መጥቀስ ቋሚ ልማዱ ነው፤ ጥቅሱም "ወዳጅ ሆይ፥ ነፍስህ እንደሚከናወን፥ በነገር ሁሉ እንዲከናወንልህና ጤና እንዲኖርህ እጸልያለሁ።" ይላል።
የብልጽግና ወንጌል አስተማሪዎች ይህን ጥቅስ ልክ የአዲስ ኪዳን ዶክትሪን የሆነ ያህል፣ ክርስቲያኖች ሁልጊዜ ከነፍሳቸው የመከናወን ሁኔታ ጋር ተመጣጣኝ በሆነ መጠን እንደሚበለጽጉ በእርግጠኝነት ያሳያል ሲሉ ይተረጉሙታል። በሌላ አነጋገር፣ በአካሄድህ ከእግዚአብሔር ጋር የምትራመድ ከሆነ፣ ማለትም ነፍስህ ከተከናዋወነ፣ በውጤቱ ኑሮ የተከናወነለት ባለጠጋና የማይታመም ጤነኛ ሰው ትሆናለህ። በድህነት ውስጥ የምትኖር ከሆነ ግን ገና አሁንም በኃጢአትህ ውስጥ መሆን አለብህ፤ እንደ ማለት ነው፣ ይላሉ።
ይህ ጥቅስ ዮሐንስ ለወዳጁ ለጋይዮስ ያቀረበው ሰላምታና የጸሎት ዘገባ ብቻ ነው እንጂ ከእግዚአብሔር ዘንድ ለክርስቶስ አካል ሁሉ የተሰጠ የእምነት መግለጫ ወይም አቋም አይደለም፤ ዶክትሪን ሆኖ እንደ ተስፋ ቃል ወይም እንደ እምነት እንቀጽ መቆጠርም የለበትም። ሰላምታንና የጸሎት ርዕስን ሁሉ እየሰበሰቡ ዶክትሪን ለማድረግ መሞከር በእውነቱ አለመማር ብቻ ሳይሆን፤ ሁሉም የተጻፈው ለእኔ ነው የሚል ብልጣብልጥነትና ራስ ተኮርነትም ጭምር ነው። የብልጥግና ወንጌል ክፋቱ ሰዎችን ራስ ወዳድና ስግብግብ ማድረጉ ነው
ተመልከቱ፣ ይህ መልእክት የተቀረጸው በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን በነበረው የተለመደ የደብዳቤ አጻጻፍ ቅርጽ ነው። ዊልያም ባርክሌይ ይህንን በ3ኛ ዮሐንስ 2 ላይ ያለውን የተለመደ የደብዳቤ አጻጻፍ ቅርጽ እውነታ የሚመለከተው አንድ የመርከብ ካፒቴን ሸኝዎቹን ሲሰናበት ከሚጠቀምበት የስንብት ቃልና አብረውት የሚጓዙትን ሲያበረታታ ከሚጠቀምበት ማበረታቻ አረማዊ የመልካም ምኞት መግለጫ ጋር ተመሳሳይ የሆኑ ሐረጎችንና ቃላትን በመጥቀስ ነው። ሃዋርድ ማርሻልም፣ በኒው ኢንተርናሽናል የመጽሐፍ ቅዱስ ማብራሪያው ውስጥ፣ ሽማግሌው (ዮሐንስ) ለወዳጁ ለጋይዮስ መልካም ምኞቶችን በመግለጽ በጊዜው የነበረውን ባህላዊ ወግ እና እሴት እንደሚከተል በመግለጽ የባርክሌይን አስተያየት ያረጋግጣል። ይህ ልክ በሃገራችን ልማድ "ጤና ይስጥልኝ" ብሎ በመልካም ምኞት መግለጫ ሰላምታ የማቅረብ ሁኔታ እንጂ "የመከናወንና የጤንነት" ዶክትሪን ፈጽሞ አይደለም። ለሁሉም አማኞች ፈቃዱን በተመለከተ ከእግዚአብሔር የተሰጠ ሁለንተናዊ መግለጫም አዋጅም አይደለም። እንደዚያ ነው ብሎ መገመት ግን ከሥነ-ጽሑፋዊው እና ታሪካዊው አውድ ውጭ መሆን ነው።
አስተውሉ፣ መጽሐፍ ቅዱስ ስለእኛ ተጽፎልናል እንጂ በቀጥታ ለእኛ አልተጻፈም። ጳውሎስ እስክንድሮስን በአይነ ቁራኛ እንዲጠብቅ ለጢሞቴዎስ የሰጠው ትዕዛዝ፣ እንዲሁም ከክረምት በፊት በርኖሱን ይዞለት እንዲያመጣ፣ ቲቶም በቀርጤስ እንዲኖር የተሰጠው መመሪያ፤ ወይም ጌታችን ኢየሱስ "ሽሽታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ" ያለው፣ ወይም "በአንዲቱ ከተማም መከራ ቢያሳዩአችሁ ወደ ሌላይቱ ሽሹ" ያለው፣ አልያም "በይሁዳ ያሉት ወደ ተራራዎች ይሽሹ" ያለው እና ይህን የመሰለ ነገር ሁሉ በእርግጥም የእግዚአብሔር ቃል አካል መሆኑ እሙን ነው፥ ዳሩ ግን እንዲህ ያለው ትዕዛዝ በቀጥታ ለእኛ የተጻፈ አይደለም። ብዙዎች ግን ይህንን መለየት ተስኗቸዋል። የብልጽግና ወንጌል መምህራንም ይህን በተመለከተ በያዙት ግንዛቤ ግለሰብን ጠቅሶ በአድራሻው በተጻፈለት ሰላምታን በያዘ የመልካም ምኞት መግለጫና ለሁሉ በሚሆን ሉል አቀፍ ዶክትሪናል የተስፋ ቃል መካከል ያለውን ልዩነት አደባልቀዋል።
፫.
አሁን እንግዲህ ታዲያ ይህ ምንአለበት፣ በእኛ ላይስ ምን ጉዳት ሊያደርስ ይችላል? ተብሎ ይጠየቅ ይሆናል። በእርግጠኝነት ለመናገር የእግዚአብሔርን ቃል እየተማርን የምናድግ ማናችንም ብንሆን በዚህ የውሸት ወንጌል ልናምን የምንችልበት ምንም መሰረት እንደሌለን ይህንን አንድ ነገር እገነዘባለሁ፤ ይሁንና ግን ልታስተውሉት የሚገባችሁ ነገር እንዲህ ያለ የተሳሳተ ትምህርት በቤተ ክርስቲያን ላይ እየናኘ የብዙወችን ልብ እየወሰደ መሆኑን ነው። በኢንተርኔት በተደረገ ጥናት 61 በመቶ የሚሆኑት የአሜሪካ ጰንጤቆስጤ አማኞች እግዚአብሔር ሰዎች እንዲበለጽጉ እንደሚፈልግ ያሚያምኑ ናቸው። "የእርስዎ ምርጥ ህይወት አሁን"፣ በሚል ርዕስ መጽሐፍ አሳትሞ ከ4 ሚሊዮን በላይ ቅጂዎች የሸጠው የጆኤል ኦስቲን ድርሰት ይህንን ያሳያል። በግሌ መጽሐፍ ተራ ጎራ ብዬ አይኔን ሳማትር በየመደርደሪያው ላይ እዚህም እዚያ በርከት ብሎ አይኔን የሚያደናቅፈኝ እንደ ዚህ ሰውዬ ድርሳን ሌላ መጽሐፍ ብዙ አልገጠመኝም።
ይህ እምነት የጰንጤቆስጤ መሰረቱን እያሰረገ ወደ ወንጌል አማኝ አብያተ ክርስትያናት ሁሉ ዘልቆ ግብቷል። በአገራችንም የወንጌል እምነት ታሪክ ውስጥም የቃል እምነት ህጸጹን አሹልኮ በማስገባት የአንበሳውን ድርሻ የሚወስደው ጰንጤቆስጤ ነው። እኔ በበኩሌ እንደ ጰንጤቆስጤ ከጤንነትና ከብልጽግና ወንጌል ጋር እርኩስ ጋብቻን የፈጸመ ሌላ እምነት አላየሁም፤ ይህም ግልሙትና እንደ ወረርሽኝ ወንጌላውያንና ካርዝማውያን ነን ሲሉ ራሳቸውን የሚጡሩትን እያዳረሰ በሁሉም ቤት እንደ ቀኖና የሚታመን እየሆነ ለመምጣት ጥቂት ስብከቶቻቸውንና መዝሙሮቻቸውን መታዘብ ብቻ ይበቃል።
እንደሰሜን አሜሪካ ባሉ አገሮች ውስጥ ትላልቆቹን ጉባኤያት ከሚመሩና ብዙሃኑ ካደነቃቸው ዝነኛ ሰባክያን ጋር በሥነ-መለኮታዊ ጉዳዮች አለመስማማት በተለይም በአሁኑ ጊዜ እንደ ሞኝነት እንደ እብደትም ሊመስል ይችላል። ተመልከቱ ሠላሳ ሺህ የሚሆኑ ጎልማሶች በየእሁዱ የጆኤል ኦስቲንን ስብከት ለመስማት በቤተክርስቲያኑ ይገኛሉ። በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተጨማሪ ሰዎች ደግሞ በየቤታቸው ሆነው የእሱን ብሔራዊ እና የዓለም አቀፍ የቴሌቪዥን ስርጭቶችን በቻናሎቹ ይከታተላሉ። በእርግጠኝነት ይህ ለቁጥር የሚያታክት ተከታይ ያለው ሰው በትክክለኛው መንገድ ላይ የመሆኑ ምልክት ነው ብሎ ማንም ሰው መገመት ይችላል። እውነታው ግን ይህ አይደለም! ቢከፍቱት ተልባ የሆነ ይህ ሰው ኃሰተኛ የምኞት ወንጌል እየሰበከ ያለ የስህተት አስተማሪ ነው።
ጆኤል ኦስቲን ያተረፈው እንዲህ ያለ እውር ተወዳጅነት በእውነት በአሜሪካ ውስጥ ላለው አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን ሁኔታ አይነተኛ ማረጋገጫ ነው። ይህ ሰው በሚያቀርበው ዲስኩር የሚደመጠው አነቃቂ ንግግሩ በእውነት ስለ ኃጢአታቸው የማይወቀሱና ሊወቀሱ የማይወዱ ሰዎችን ጆሮ ይማርካል። እነዚህም ንስሃ መግባት እና ኃጢአታቸውን መጥላት የማይፈልጉ ናቸው። ስለዚህም ጆኤል ኦስቲን፣ ሆነ ብሎ የእግዚአብሔርን እውነት ርዕሰ ጉዳዮች በሙሉ በስብከቱ ሜኑ ውስጥ አያካትታቸውም። በዚህም ምክንያት ከእግዚአብሔር ክብር ወይም ክርስቶስ ለኃጢያታችን ከከፈለው የኃጢአት ዕዳ ክፍያ ጋር የማይገናኝ ሁለመናው ራስን ስለ ማሻሻል የሆነ፣ የተዛባና፣ ከረሜላ ከረሜላ የሚል "የምኞት ወንጌል" ያቀርባል። ይህ የምኞት ወንጌል ፈጽሞ ወንጌል አይደለም፤ እውነት እላችኋለሁ ግማሹንም ያህል እንኳ ወንጌል አይደለም። ለዚያም ነው በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የሚፈልጉትን የምኞት ወንጌል ለመመገብ ወደ ስፍራው የሚጎርፉት፣ እንዲሁም በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሌሎች በቲቪ የሚመለከቱት። አስተውሎ ለተከታተለው ሰው፣ የዚህ ሰው ወንጌል ቅዱስና የተፈራ አምላክ የለውም፣ አስፈሪውን መለኮታዊ ፍርድም አያቀርብም፣ የስርየት አስፈላጊነትንም አያሳይም። ምናልባት በእርሱ ስብከት የሚነቃቃ ይኖር ይሆናል እንጂ ንስሃ የሚገባና ከክፉ ስራው ተጸጽቶ የሚመለስ አንድ ሰው የለም። በስብከቱም ራስን ስለመውደድ እንጂ ለራስ ወዳድነት ስለመሞት ፈጽሞ አይናገራትም፣ በእኔነት ላይ ያተኮረ፣ እኔ፣ እኔ የሚለው ስብከቱ ሲደመጥ እውነተኛውን ወንጌል በሚያውቁ ሰዎች ዘንድ እንጨት እንጨት ይላል።
የሰው ሃይማኖተኛ ዝንባሌ ሁል ጊዜ ለገዛ ራሱ ጥቅም ሲል የገዛ ፍላጎቱን የሚያሟላለትን አማላክ ይፈበርካል። ወንጌል ካልገባህ የፈለግኸውን የሚሰጥህንና የአንተ አገልጋይ የሆነ አምላክ ለመፈልሰም አትቦዝንም። ይህ ሰዎችን በምኞት የሚያጠፋ የጤናና የብልጥግና ነገረ መለኮት ወንጌላዊውን ክርስትና ከደረጃው አውርዶ ዝቅተኛ ከሆነው የሰው ሀይማኖቶታዊ ዝንባሌ የማይለይ ተራ የከልት ስርዓት አድርጎታል። አምላክ በሰዎች ምርጫ እጁ የሚጠመዘዝ፣ ፈቃዱን ለመለወጥ የሚገደድ፣ በሰዎች አቀራረብ የሚታለል፣ በማባበያ የሚሸነገል፣ ሰዎች ሊቆጣጠሩትና ወደፍላጎታቸው ሊስቡት የሚችሉትና ክርስቲያኖች ለጥቅማቸው የሚበዘብዙት አይነት ከሆነ እንዲህ ያለው አምላክ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አባትና አምላክ አይደለም። እንዲህ ያለውን የተፈበረከ አምላክ የተቀበለ ክርስትና ደግሞ አፍሪካዊ ተፈጥሮ ያለውን የቩዱ ሃይማኖት ዓይነት ጣዖታዊ መልክ አለው።
ጆኤል ኦስቲን ምን አይነት ወንጌል እንደሚያስተምር መረዳት እንድንችል 30,000 ለሚሆኑ አባል ቤተ ክርስቲያኑ ከላከላቸው መልእክቶች አንዱን ወስደን እንመልከት፡-
"እርሱ ከከፈለው ዋጋ የተነሳ በድል አድራጊነት የመኖር መብት አለን። ጥሩ ቤተሰብ መመስረት፣ ጥሩ ጤንነት ማግኘት ወደቻልንበት ግማሽ ድል ውስጥ ገብተንም ሊሆን ይችላል፣ በገንዘብ አቅማችን ውስጥ ግን ያለማቋረጥ እየታገልን እንኖራለን፤ ይሄ ግን ፈጽሞ ሙሉ እና አጠቃላይ ድል አድራጊነት አይደለም። እግዚአብሔር በአንዱ ዘርፍ መልካም ካደረገላችሁ በሌላው ዘርፍም መልካም ሊያደርግላችሁ ይወዳል። እንዲህ ላለው ስኬት ግን ራዕይ ይኑራችሁ። በግሌ ብዙ ገንዘብ ያላቸውን ሰዎች አውቃለሁ፣ ጥሩ ጤንነትም አላቸው፣ በቤተሰባዊ ግንኙነቶቻቸው ውስጥ ግን እርስ በርስ መግባባት አይችሉም። በቤታቸው ውስጥ ሁል ጊዜ ጠብና ጭቅጭቅ አለ ፣ ይህ በእውነት ሙሉ በሙሉ ድል አይደለም። ምናልባት ደግሞ እግዚአብሔር ባርኮህ ጥሩ ቤተሰብ እና ጥሩ ስራ ይኖርህ ይሆናል፣ ነገር ግን በሰውነትህ ላይ ለዓመታት እና ለዘመናት የሚታገልህ ህመም ያለብህ ልትሆንና፣ እርሱንም እየተቃወምህ ስትጸልይ ምናልባትም ከህመምህ ነፃ እንደምትወጣ ታምን ነበር። አሁን ግን ይህ በህይወቴ ውስጥ ዕጣ ፈንታዬ ነው…ብለህ ተቀብለኸው መኖር ከወሰንክ በጣም ብዙ ጊዜ አልፎታል፣ አንድ ነገር ግን እወቅ ሙሉ በሙሉ ነፃ እንድንሆን ኢየሱስ ዋጋ ከፍሏል። ይህ ማለት ከመጥፎ ልማዶች እና ከሱሶች ሁሉ፣ ከተስፋ መቁረጥ እና ከጭንቀት ሁሉ፣ ከድህነት እና ከእጦት ሁሉ፣ ነፃ እንድትሆን፣ ለራስህም ከፍ ያለ ዋጋ እንዳትሰጥ ከሚያደርግህ የዝቅተኛነት ስሜት ነፃ እንድትሆን ማለት ነው። እግዚአብሔር ፍጹም ነፃ እንድንሆን ይፈልጋል። ቅዱሳት መጻሕፍት ክርስቶስ የሞተለትንና የተነሣበትን ሁሉ እንድንቀበል ይነግሩናል። እግዚአብሔር ጤናማ እና ሙሉ አድርጎሃል፣ የእኛ ቀዳሚ ስፍራም ሙሉ ነፃነት ነው... አማካኝ ቦታ ላይ እንድትሆን አለመፈጠርህን አረጋግጥልሃለሁ። በጭንቅ ውስጥ እንድታልፍ እና ክፉንም ደጉንም ሁሉንም አይነት ነገሮች እንድትቀበል አልፈጠረህም። ትክክለኛውን የህይወት ራዕይ ማግኘት አለብህ። እግዚአብሔር የፈጠረህ ፍፁም ነፃ እንድትሆን፣ በአእምሮህ ሰላም እንዲኖርህ፣ በመለኮታዊ ጤንነት እንድትመላለስ፣ ጥሩ ቤተሰባዊ ግንኙነት እንዲኖርህ፣ የብድር ዕዳህን እንድትከፍልና ከብድር ህይወት ነጻ እንድትሆን፣ እንድትበዛና እንድትትረፈረፍ ነው። ይህ ሁሉ የሚገባህና ልዩ መብትህ ነው። ከነዚህ መብቶችህ ውስጥ አንዱ አጠቃላይ ድል ነው። ነፃ ሆኖ መኖር ያለ ጥርጥር ይገባናል፣ ይህም ማለት በአእምሯችን ነፃ ሆነን ከጭንቀት ሁሉ የጸዳን መሆን ማለት ነው። የባንክ ሂሳባችን ምንም አይነት ቢመስልም፣ ከድህነት እና ከእጦት የጸዳ መሆን ማለት ነው። አመለካከታችንም ተለውጦ እኔ እንደተባረኩ አውቃለሁ፣ የተረገምሁ ልሆንም ፈጽሞ አልችልም። እኔ የነካሁት ሁሉ ይበለጥጋል ይሳካለታልም እንድንል ነው"።
ይህ እንግዲህ የጆኤል ኦስቲን ንግግር ነው። የእግዚአብሔርን ቃል በወጉ ላልተማሩ ሰዎች ይህ ንግግር ምንም ችግር የሌለበት ሆኖ ይሰማቸዋል። የክርስቶስን ወንጌል ተፈጥሮ ስታውቀው ግን ይህ ንግግር ወንጌልን የሚበርዝ በማር የተለወሰ መርዝ መሆኑን አስተውለህ ራስህንና የሚሰሙህን ከዚህ የጥፋት ወንጌል ለማዳን ትናጠቃለህ። ልብ አድርጉ፣ በዚህ ሰው ትርጓሜ መሰረት ከእግዚአብሔር ጋር በመንፈሳዊ ብስለት መሄድ ማለት ባለጠጋ መሆን ማለት ነው፣ ጤናማ፣ የማይታመም፣ ጥሩ ቤተሰባዊ ግንኙነት ያለህ፣ ሁልጊዜ ያለ ህመምና ያለ ጭንቀት በድል አድራጊነት እየኖርክ በሁሉ ቀዳሚና አንደኛ ሆነህ እንደ ባለ መብት መኖር አለብህ ማለት ነው። የዚህ አመለካከት ችግሩ ግን ኢየሱስ የኖረውን ህይወትና መላው የአዲስ ኪዳንን ቤተ ክርስቲያን ያለፉበትን የህይወት ትግል ያገለለ መሆኑ ነው።
የዚህን ሰባኪ ንግግር ካደመጣችሁ በኋላ፣ ኢየሱስና በወንጌሉ የምናውቀው ኑሮው ከዚህ ሰው አሳብ ጋር እንዴት ነው ሚስማሙት? ብላችሁ ጠይቁ። በውኑ ወንጌሉ የሚያስተዋውቀን ኢየሱስ ባለጠጋ ነበርን? ደልቶትስ ይኖር ነበርን? ፈጽሞ እንደዚያ አልነበረም! በሶስት ዓመት ተኩል አገልግሎቱ፣ የሚጠለልበት እንኳን ሳይኖረው በምድር ላይ እየተንከራተተ በድህነት ኖረ (ሉቃስ 9፥ 58)፤ የሚያርፍበት ቤት አልነበረውም፣ መሠረታዊ ፍላጎቶቹን ለማግኘት ሁልጊዜም ቢሆን የሌሎች ድጋፍ አስፈልጎት ነበር። ብዙዎች የብልጥግና ወንጌል አጋፋሪዎች ግን ይህንን የእግዚአብሔር ልጅ ኑሮ "ድህነት" ነው ብሎ ለመጥራት ይፈተናሉ።
ኢየሱስ በማበራዊ ግንኙነቱ ላይ ችግር ነበረበትን? ተመልከቱ ሁሉም የሃይማኖት መሪዎች ይጠሉት ነበር፣ የገዛ ቤተሰቦቹ ንቀውት ነበር፣ ጴጥሮስ ክዶታል፣ ይሁዳ አሳልፎ ሰጥቶታል፣ ሕዝቡም ሁሉ "ስቀለው ስቀለው" እያሉ ጮኸዋል። ጌታ ኢየሱስ በማህበራዊ ግንኙነቱ ውስጥ ጆኤል ኦስቲን በሚናገርለት አይነት በድል አድራጊነት እየኖረ እንዳልነበር አስባለሁ። ብዙዎች ተወዳጅነትና ከበሬታን ነፍገውታል። ከከበሩትም ሰዎች መካከል የሚበዙት በቀንና በአደባባይ ከእርሱ ጋር መታየትም ሆነ ሊተባበሩት አይፈልጉም ነበር። ኢየሱስ የህማም ሰው ነበር። ከባድ ሥቃይ ደርሶበታል። ተገርፏል፣ ጉሰማና ድብደባ ደርሶበታል። አዋርደው ተፍተውበታል፣ እርሱ በመከራ እንጨት ላይ ተሰቅሎ እንዲገደል በእግዚአብሔርም በሰውም የተተወ የህማም ሰው ነው። ስለዚህ ጆኤል ኦስቲን እየተናገረለት ያለው ይህ አይነቱ የድል ሕይወት በኢየሱስ አልተኖረም። መፅሃፍ ቅዱስም በግልጽ ሲያስተምረን እርሱን መስለን መኖር እንዳለብን ይናገራል።
1ዮሐንስ 2፥ 6 "በእርሱ እኖራለሁ የሚል እርሱ እንደ ተመላለሰ ራሱ ደግሞ ሊመላለስ ይገባዋል።"
እንግዲህ ይህን ካደረግንና እንደ ኢየሱስ የምንኖር ከሆነ ኢየሱስ ያጋጠመውንና ያለፈበትን ዓይነት የህይወት ውጣ ውረድ እኛም ያጋጥመናል። ክርስቶስ እንደኖረ ከኖርን ጆኤል ኦስቲን የሚሰጠውን ሃሰተኛ የድል ሕይወት ተስፋ አናይም። የኢየሱስ ነኝ የምትሉ ሁሉ ስሙኝ፣ በጤንነት ብልጥግና ወንጌል ኃሰተኛ ተስፋ ተታላችሁ ኢየሱስ በስጋው ወራት ያልኖረውን የቅምጥል ህይወት ለመኖር አታስቡ።
የጌታችን ደቀመዛሙርትስ እንዴት ነበር የኖሩት? በአጠቃላይ የድል ኑሮ የሚኖሩ ህመም የማያውቃቸው ፍጹም ጤነኛ ነበሩን፣ ባለጠጎችስ የነበሩና በምድራዊ ፍላጎቶቻቸው ጉድለት ያላዩ ነበሩን? በጭራሽ ቅምጥሎችም አልነበሩም ያንንም ተስፋ አድርገው አልተመኙም! ተመልከቱ ከሐዋርያት መካከል አንዳቸውም ባለጠጋ አልነበሩም። ሁሉም ሊታመን የማይችል ፈተናና መከራ ነበረባቸው፣ ቢያንስ የጳውሎስን ጉዳይ እንኳ ብናነሳ መሰረታዊ የቁሳዊ ጉዳዮች እጦት እና ከባድ የጤና ችግሮች ለህይወቱም አስጊ የነበሩ ተስፋ አስቆራጭ ከፍተኛ ፈተናዎች ደርሰውበታል።
ሐዋርያው ጳውሎስን ከእግዚአብሔር ጋር በመልካም ኅብረት የተራመደ፣ ነፍሱ የተከናወነለት የእግዚአብሔር ሰው ነበርን? አዎ በሚገባ ነበር። እግዚአብሔር ራሱ በጳውሎስ እጅ የሚያስገርም ተአምራት እያደረገ፣ ለድውዮችም ከአካሉ ላይ ጨርእቅ ወይም ልብስ ይወስዱ እንደነበር እናውቃለን። አብዛኛውን አዲስ ኪዳንን እንዲጽፍ እግዚአብሔር ጳውሎስን በብዙ ተጠቅሞበታል። ጳውሎስ ግን በማህበራዊ በግንኙነት ላይ ችግር አጋጥሞት ያውቃልን? አዎ። በእርግጥም እንዲህ ያለው ታላቅ የእግዚአብሔር ሰው በሰዎች መተውና መረሳት ደርሶበት ያውልቃ፤ አመዛኙን ህይወቱን ያሳለፈውም ወህኒ ቤት ውስጥ እንደነበር እናውቃለን፦
2ጢሞቴዎስ 4፥ 16 "በፊተኛው ሙግቴ አንድ ስንኳ አልደረሰልኝም፥ ሁሉም ተዉኝ እንጂ፤ ይህንም አይቍጠርባቸው፤"
አካላዊ ሕመምን በተመለከተስ? ፣ ጳውሎስ የአካላዊ ጤና ችግር ነበረበትን?
2ቆሮንቶስ 12፥ 7 "ስለዚህም በመገለጥ ታላቅነት እንዳልታበይ የሥጋዬ መውጊያ፥ እርሱም የሚጎስመኝ የሰይጣን መልእክተኛ ተሰጠኝ፤ ይኸውም እንዳልታበይ ነው።"
እዚህ ላይ ጳውሎስ አካላዊ የጤንነት ዕክል የነበረበት መሆኑን እናያለን። ይህን ችግር ያጋጠመው ለምን እንደሆነም የእግዚአብሔር ቃል ይነግረናል። በጠቅላላ ህይወቱ በድል ስላልተራመደ ወይም መንፈሳዊ የሕይወት ድካም ስለነበረበት ሳይሆን ይልቁንም ትህትናውን ጠብቆ ለማቆየት እግዚአብሔር የተጠቀመበት መንገድ ነበር። "እግዚአብሔር ለትሑታን ጸጋን ይሰጣልና" ያ ደግሞ መልካም ነገር ነው።
2ቆሮንቶስ 12፥8 "ስለዚህ ነገር ከእኔ እንዲለይ ሦስት ጊዜ ጌታን ለመንሁ።"
ይህንን ችግር እግዚአብሔር እንዲወስድለት ጳውሎስ በጸሎት ጠየቆ ነበር። እግዚአብሔር ግን የሰጠውን መልስ ልብ በሉ፦
2ቆሮንቶስ 12፥ 9 "እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ።"
ጳውሎስ በድህነቱና በሥቃዩ ላይ ስለተቀዳጀው አጠቃላይ ድል ይመካ ነበርን? ደስታውስ ይህ የጤናና የኢኮኖሚ ችግር ከእርሱ ስለተለየ ነበርን? ፈጽሞ ደስታውም ትምክህቱም በዚያ አልነበረም! ይልቁንም በነዚያ ድክመቶቹ ሲመካ ይታያል። ይህ ለምን እንደሆነ ልብ አድርጉ፦
2ቆሮንቶስ 12፥ 10 "ስለዚህ ስለ ክርስቶስ በድካም በመንገላታትም በችግርም በስደትም በጭንቀትም ደስ ይለኛል፤ ስደክም ያን ጊዜ ኃይለኛ ነኝና።"
ልብ አድርጉ፣ ይህ የጤና/ብልጥግና ወንጌል የተባለ የትምህርት አረም ይህንን እውነት ሙሉ በሙሉ ስቶታል። ጳውሎስ፣ “ስደክም፣ ማለትም በዚህ አካላዊ ሕመሜ፣ በማልፍበት እጦትና ድህነት፣ በሚገጥመኝ የማህበራዊ ተቀባይነት እጦት፣ በመከዳቴ እና በሰዎች በመረሳቴ እመካለሁ፣ ደስ ይለኛል” ሲል ተናግሯል። አያችሁ፣ በሕይወታችን ውስጥ ችግሮች ሲያጋጥሙን ያኔ ነው እንደ ጳውሎስ ወደ ክርስቶስ የምንዞረው እና በኃይሉ የምንታመነው።
የጳውሎስን የግል የህይወት ምስክርነት ተመልከቱ እና ምን ያህል ከጆኤል ኦስቲንን አጠቃላይ የድል ኑሮ ሃሳብ እና አስተምህሮ ጋር መስማማት አለመስማማቱን መዝናችሁ እዩ፦
2ቆሮንቶስ 11፥ 23-27 "እንደ እብድ ሰው እላለሁ፤ እኔ እበልጣለሁ፤ በድካም አብዝቼ፥ በመገረፍ አብዝቼ፥ በመታሰር አትርፌ፥ በመሞት ብዙ ጊዜ ሆንሁ። አይሁድ አንድ ሲጎድል አርባ ግርፋት አምስት ጊዜ ገረፉኝ። ሦስት ጊዜ በበትር ተመታሁ፤ አንድ ጊዜ በድንጋይ ተወገርሁ፤ መርከቤ ሦስት ጊዜ ተሰበረ፤ ሌሊትና ቀን በባሕር ውስጥ ኖርሁ። ብዙ ጊዜ በመንገድ ሄድሁ፤ በወንዝ ፍርሃት፥ በወንበዴዎች ፍርሃት፥ በወገኔ በኩል ፍርሃት፥ በአሕዛብ በኩል ፍርሃት፥ በከተማ ፍርሃት፥ በምድረ በዳ ፍርሃት፥ በባሕር ፍርሃት፥ በውሸተኞች ወንድሞች በኩል ፍርሃት ነበረብኝ፤ በድካምና በጥረት ብዙ ጊዜም እንቅልፍ በማጣት፥ በራብና በጥም ብዙ ጊዜም በመጦም፥ በብርድና በራቁትነት ነበርሁ።"
ጆኤል ኦስቲን ይህን ምስክርነት አንብቦ ያውቃልን? እንጃ። ለክርስቶስ መኖር እና እግዚአብሔርን በመታዘዝ መመላለስ ለጳውሎስ ይህን ይመስል ነበር። ምን ያህሎቻችሁ ለእንደዚህ አይነት የህይወት ስርአት መፈረም ትሻላችሁ? ጆኤል ኦስቲን ይህንን ህይወት የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው ብሎ ለአማኞች ሰብኮ ቢሆን ኖሮ እንዲህ ያለ ትልቅ የሕንፃ ካቴድራል ባልኖረውም ነበር።
፬.
ያለህባት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር ሀብት ሰጥቶ ባለጠጋ ሊያደርግህ እንደሚፈልግ የምታምን ከሆነ፣ ፓስተርህም ይህንንው እየደጋገመ ሲሰብክ፣ አንተ ግን "በእምነትህ ማነስ " ምክንያት ከዚህ እንደጎደልህ ማወጅና ማስተማር ሲጀምር፣ እንዲህ ያለው ይህ የትምህርት እብደት በተለይ በድህነት ውስጥ ለሚኖሩ በሚሊዮን ለሚቆጠሩ እግዚአብሔርን ለሚፈሩ ሰዎች ምን ማለት ይሆን?
ተመልከቱ በገጠራማዋ የኢትዮጵያ መንደሮች በየእሁዱ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ለማምለክ 3 በ 5 ስፋት ባላት አነስተኛ "የጸሎት ቤት" ውስጥ ወይም በዛፍ ጥላ ስር ይሰበሰባሉ። ያቺ ቤተመቅደስ በሰዎች አይን የምታምር አይደለችም፣ ነገር ግን በምድር ላይ ካሉት በጣም ድሆች ከሆኑ አማኞች ጥቂቶቹን በአባልነት ያቀፈች ቤተክርስቲያን ናት። ነገር ግን የእነዚህ ሰዎች ኢኮኖሚያዊ ዝቅተኛነት ያለባቸውን መንፈሳዊ የበታችነት አያመለክትም። እርግጥ ነው እነዚህ ሰዎች እንደብዙዎቹ ምዕራባውያን የጤና እንክብካቤ ዋስትና የላቸውም፣ ነገር ግን በህመማቸው ጊዜ ጌታ እንዲፈውሳቸው በጸሎት ይጠይቃሉ። ምናልባትም ከብዙዎቻችን በተለየ በእግዚአብሔር ሉዓላዊነት ላይ የመተማመን እጅግ የላቀ ደረጃ ያላቸው ናቸው። እነዚህ ሰዎች "የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን" ብለው ሲጸልዩ - በእርግጥ ለማለት ያህል በልማድ ሳይሆን የምራቸውን መለመናቸው ነው። በጣም መሠረታዊ የሆኑ ፍላጎቶቻቸውን ሊሰጣቸው እንደሚችልም በእግዚአብሔር እየታመኑ ውሱን በሆኑ ግብአቶቻቸው በገዛ እጃቸው ለሥራ ይተጋሉ እንጂ አይለግሙም።
የሚቀጥለው ምግብ እንዴትና ከየት እንደሚመጣ የማያውቁ ነገር ግን መንፈሳዊ ኃያላን የሞሉባት እንዲህ ያሉ ታናናሽ መንጋ ያሏቸውን ታናናሽ የቅዱሳን ማህበራት ኢትዮጵያን ከመሰሉ የአፍሪካ ገጠራማ መንደሮች ማግኘት የተለመደ ነው። ሆኖም በድህነታቸውና በሥቃያቸው መካከል እግዚአብሔርን በደስታ ውዳሴ ሲያመልኩት ነፍስ አይቀርላቸውም። እኔ ከወንጌል እንደምረዳው ጆኤል ኦስቲን ከሚደሰኩረው ኃሰተኛ የድልና የስኬት ህይወት ይልቅ ፍጹም ድል ይህ ነው።
ምእመናን አጥብቀን ልንረዳው የሚገባን እውነት እዚህ አለ፤ ክርስቲያኖች በዚህ ዓለም ውስጥ መኖር እንደሚገባው ያህል በጽድቅ ሕይወት በሚኖሩበት ጊዜ ሁሉ ወንጌልን በኃይል ለማስፋፋት እና ሰዎችን ደቀ መዛሙርት ለማድረግ እየተጋደሉ ለጽድቅ ሲቆሙ የዚህ ተፈጥሮዋዊ ውጤት መከራ መቀበል ይሆናል። ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ ይህንን እንዲረዱ ይፈልጋል፣ መከራንም እንዲጠብቁ ያስተምራል። ጳውሎስም እንዲሁ ሲያመለክተን፡-
2ጢሞቴዎስ 3፥ 12 "በእውነትም በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ።" ይላል።
ይህ ጥቅስ ክርስቲያኖች ሁሉ በጅምላ ስደትን መጠባበቅ ይችላሉ አይልም። ይልቁን ምን ይላል? "በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ።" ነው የሚለው። መከራንና ስደትን ወዳለንበት ስቦ የሚያመጣው እግዚአብሔርን የመምሰል ሕይወት ነው። ማለትም ከእግዚአብሔር ጋር ስትቆም፣ ኃጢአትን ስትቃወም፣ ውርጃን፣ ግብረ ሰዶማዊነትን፣ ተመሳሳይ ጾታዊ ጋብቻን ስትነቅፍ እና የስነምግባር ዝቅጠትን ተቃውመህ ስትናገር፣ ያኔ በዚህ ምክንያት ስደት ሊደርስብህና መከራን ልትቀበል እንደምትችል ጠብቅ!
ጳውሎስ በብዙ መልዕክቶቹ የንባብ ክፍሎች ላይ መከራና ስቃይ የሐዋርያዊ አገልግሎት አስፈላጊ አካል እንደሆ በማሰብ ጽፏል። በሌሎች ክፍሎች ግን ጳውሎስ መከራን እና ስቃይን በሐዋርያት አገልግሎት ላይ ብቻ አልወሰናቸውም። ይልቁንም አለፍ ብሎ የደቀመዝሙርነት ኑሮ አስፈላጊ አካል እንደሆነም ያመለክታል። ይህም ትምህርት በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ወጥነትና ቀዋሚነት ያለው አጽንዖት ነው። ችግሮችና ፈተናዎች፣ ተግዳሮቶችና ግጭቶች ህመምም ከደቀመዝሙርነት ኑሮ ጋር የማይነጣጠሉ ሆነው የተቆራኙ ናቸው።
ምእመናን፣ ልንረዳው የሚገባን አንድ ጉዳይ ህመምና ስቃይ ድኅነትም የዚህ ሕይወት ሥርአትና አካል ናቸው፤ ክርስቲያን መሆናችንም ሆነ የድል ኑሮ መኖር ደግሞ ሁሉም ከህይወታችን እንዲወገዱ አያደርጋቸውም። ጥበበኛ፣ ቅዱስ እና አፍቃሪ የሆነው አምላካችን በህመማችን እና በመከራችን ውስጥ የማይመረመር አላማ አለው። ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች የሚነገራቸውን ልብ አድርጉ፦
2ቆሮንቶስ 1፥ 8 "በእስያ ስለ ደረሰብን መከራችን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ታውቁ ዘንድ እንወዳለንና፤ ስለ ሕይወታችን እንኳ ተስፋ እስክንቆርጥ ድረስ ከዓቅማችን በላይ ያለ ልክ ከብዶብን ነበር፤"
ይህ ጆኤል ኦስቲን የሚናገርለትን አጠቃላይ የድል ኑሮ ፈጽሞ አይመስልም። ጳውሎስ ግን እርሱና ባልደረቦቹ መከራ ለምን እንደደረሰባቸው በግልጽ ነግሮናል፣ ተመልከቱ፦
2ቆሮንቶስ 1፥ 9 "አዎን፥ ሙታንን በሚያነሣ በእግዚአብሔር እንጂ በራሳችን እንዳንታመን፥ እኛ ራሳችን የሞትን ፍርድ በውስጣችን ሰምተን ነበር።"
ወገኖች ሆይ፣ መከራን መቀበል በራስ የመደገፍ ኃጢያትን ከላያችን ያራግፍልናል። ብዙ ወንዶች እና ሴቶች የእግዚአብሔር ልጆች እግዚአብሔር ይህን ትምህርት በህይወታቸው እንዳስተማራቸው፣ በእርሱም ላይ ጥገኛ እንዳደረጋቸው፣ በስህተት የተመኩባቸውን ነገሮቻቸውን ሁሉ ከውስጣቸው ነቅሶ በማውጣት የእርሱ ተደጋፊ እንዳደረጋቸው መስክረዋል። በአብዛኛው የሚያጋጥመን ሥቃይና መከራ አላማው በእግዚአብሔር ጸጋ እና ኃይል ላይ ብቻ የማይቋረጥ ጥገኛነትን ማምጣት ነው። መከራችን ፍጥረቱ የተነደፈውና የተሰራው በእኛ በራሳችን እንድንደገፍ ሳይሆን በእግዚአብሔር ችሎታ፣ ኃይል እና ዝግጅት እንድንመላለስ ነው። እርሱ ብቻ በገዛ ራሳችን አለን ከምንለው ሀብታችን እያላቀቀ ወደ ባለጠግነቱ ዘወር እንድንል ያደርገናል።
ምእመናን ይህን ስሙ፣ ሌሊቱ ሲነጋ፣ ፀሀይ ስትወጣላችሁ ሰማዩ ጥርት ያለ ሲሆን፣ የተነቃቃ ታላቅ ስሜት ሲሰማችሁ፣ ብዙ ገንዘብ ያላችሁና "ሀብታም ነኝና ባለጠጋ ሆኜአለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም" ለማለት ስትፈተኑ፣ ሁሉም ሰው ሲወዳችሁና ሁሉንም ሰው ስትወዱ፣ ተቀባይነታችሁና ተፈላጊነታችሁ ሲጨምር፣ ያኔ በእርግጠኝነት እግዚአብሔርን ችላ የማለት ዝንባሌ መኖሩ አይቀርም። እንዲህ ባለው ስኬት በሚመስል ውድቀት ውስጥ በራሳችን የመታመን እና እግዚአብሔርን ሙሉ በሙሉ የመርሳት ዝንባሌ በእርግጥ አለ። እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ስለ ብልጽግና አስጠንቅቋቸው የነበረው ለዚህ ነው።
ዘዳግም 8፥ 11 "ዛሬ እኔ አንተን የማዝዘውን ትእዛዙንና ፍርዱን ሥርዓቱንም ባለመጠበቅ አምላክህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ ተጠንቀቅ፤"
እግዚአብሔር እዚህ ላይ እስራኤላውያንን የሚያስጠነቀቃቸው፣ ስለ ድህነት አደጋ ሳይሆን ስለ ሀብት አደጋ ነው እያስጠነቀቃቸው ያለው።
ዘዳግም 8፥ 12-16 "ከበላህና ከጠገብህ በኋላ፥ መልካምም ቤት ሠርተህ ከተቀመጥህበት በኋላ፥ የላምና የበግ መንጋ ከበዛልህ በኋላ፥ ብርህና ወርቅህም ያለህም ሁሉ ከበዛልህ በኋላ፥ ልብህ እንዳይጓደድ፤ ከግብፅም ምድር ከባርነት ቤት ያወጣህን፥ እባብና ጊንጥ ጥማትም ባለባት፥ ውኃም በሌለባት፥ በታላቂቱና በምታስፈራው ምድረ በዳ የመራህን፥ ከጭንጫ ድንጋይም ውኃን ያወጣልህን፥ በመጨረሻም ዘመን መልካም ያደርግልህ ዘንድ ሊፈትንህ ሊያዋርድህም አባቶችህ ያላወቁትን መና በምድረ በዳ ያበላህን አምላክህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ፤"
ልባቸው እንዲጓደድ፣ በትዕቢት እንዲኮሩና ጌታን እንዲረሱ የሚያደረጋቸው ድህነታቸው ሳይሆን የሚያከማቹት ሀብት መሆኑን ልብ በሉ።
ይህንኑ ሃሳብ በምሳሌ መጽሐፍ ውስጥ እናያለን።
ምሳሌ 30፥ 8-9 "ከንቱነትንና ሐሰተኛነትን ከእኔ አርቃቸው፤ ድህነትንና ባለጠግነትን አትስጠኝ፤ ነገር ግን የሚያስፈልገኝን እንጀራ ስጠኝ፥ እንዳልጠግብ እንዳልክድህም፦ እግዚአብሔርስ ማን ነው? እንዳልል፤ ድሀም እንዳልሆን እንዳልሰርቅም፥ በአምላኬም ስም በሐሰት እንዳልምል።"
ስንጠግብ፣ ሁሉም ነገር ሲስተካከል ጌታን የመካድ አደጋም አብሮት አለ።
ቅዱሳን ስሙኝ፣ በእውነቱ ለአንድ አማኝ የዚህ ምድር ህይወቱ በጣም ከባድ ሊሆንበት የሚችል መሆኑ ነው፤ እግዚአብሔርም በእርሱ ስንታመን ጤናንና ሀብትን ሊሰጠን የገባው ቃል የለም። እግዚአብሔርን በመምሰል የምንኖር ከሆነ ግን ስደት እንደሚደርስብን ቃል ገብቷል። የወንጌል መልእክትም እነ ጆኤል ኦስቲንና መሰሎቻቸው አጣመው እንደሚያስተምሩት በድህነት እና በበሽታ ላይ፣ በማህበራዊ ግንኙነቶችም ተቀባይነት ማጣት ላይ በድል አድራጊነት ፈጽሞ ስለመኖር አይደለም። ወንጌል በብቸኝነት የሚናገረው እግዚአብሔር በእርሱ ለሚታመኑት ሁሉ የኃጢአትን ዕዳ ለመክፈል የሚወደውን አንድያ ልጁን መስዋዕት አድርጎ ስለማቅረቡ ነው። እግዚአብሔር የዘላለም ሕይወትን ሊሰጠን እንጂ የሀብትና የመጽናናት ሕይወት እንድንኖር ቃል አልገባልንም።
እግዚአብሔር በእርሱ እንድንታመንና፣ በእርሱ ላይ በመታመን ብቻ እንድንኖር ይፈልጋል፣ ያንንም ለማድረግ የሚረዱን የህይወት ፈተናዎቻችን ናቸው።
ስለዚህ ጆኤል ኦስቲን "አጠቃላይ የድል ህይወት" እያለ በሚሰብከው የቅዠት አለም ውስጥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፈጽሞ እንዳልኖረበት ወንጌሉ ነግሮናል፤ ሐዋርያትም ሆኑ የየዘመኑ ቅዱሳን ሁሉ ባለፉት ዘመናት እንዲህ ባለ ቅዠት አልኖሩም። ወደ ቅዱሳት መጻሕፍት ስትጠጉ ይህ የጤና/ብልጥግና ወንጌል ፈጽሞ መጽሐፍ ቅዱሳዊ እንዳልሆነ ታያላችሁ። ታዲያ ብዙዎች ይህንን የውሸት መልእክት በውድ ዋጋ እየገዙ ወደዚህ ትምህርት የሚሳቡት፣ የነዚህ ኃሰተኞችስ ግባኤ በብዙ ቁጥር እያደገ የመጣው ለምንድነው? በመጀመሪያ ስለ እድገታቸው መገረምና መደነቅ የለብንም ምክንያቱም ካንሰርም ያድጋል። እኔ እንደማስበው ግን የዚህ እድገት ዋናው ምክንያት የትምህርቱ ድምጸት በጣም ጥሩ ስለሚመስል ነው። መቼም ቢሆን ጤናማ ለመሆን፣ ሀብት ለማግኘት፣ ከችግርም ነጻ የሆነ ኑሮ መኖር የማይፈልግ ማን ሰው አለ? ስለዚህ የስብከቱ ድምጸት ጥሩ ስለሚመስል ብዙ ሰው ይከተለዋል። ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ በጣም ጥቂት ሰዎች ብቻ መጽሐፍ ቅዱሳቸውን በቅጡ ስለሚያውቁ፣ አብዛኛው ግን ቃሉን መማርና ማወቅ እምቢ ስላለ፣ ወይም ንጹሁን ወንጌል የሚያስተምረው ስላጣ ይህ የጤና/ብልጥግና ወንጌል እግዚአብሔር ለእነርሱ እንዲሰሙትና እንዲከተሉት የሚፈልገው ነው ብለው ስለሚያስቡ ነው። አማኞች በዚህ ኢ-መጽሐፍ ቅዱሳዊ በሆነ አጉል ትምህርት ውስጥ ሲጠመዱ ስናይ በቅዱሳን መካከል ይህንን የሚመዝን መለኪያ ድምጽ በመሆን ኃሰትን ለመጋፈጥ የእግዚአብሔርን ቃል እውነት አውቀን ልንቆም ይገባናል።
በአገራችንም እንደ አሸን የፈሉት የጥፋት ወንጌል ሰባኪዎች ቢከፍቱት ተልባ የሆነው ዲስኩራቸው ምንጩና መሰረቱ ይኸው ከላይ በስፋት የተቸነው መስቀል አልባ የትምህርት ቅዠት ነው። ስራ ጠል የሆኑ ቁጭ ይበሉዎች በኃሰተኛ ትንቢታቸው እያዋዙ ሕዝብ በሚያደነቁሩበት የትባረካላችሁ ስብከት መንጋው እየከሳ ዘርፈው የጠገቡ እነርሱው ብቻ ናቸው። "ማን መጥቶ ባሳሳተን" በሚል ክፉ ምኞት ተይዘው ላይ ላዩን የሚጋልቡና አጥብቀው የማጠይቁ ሰነፍ የቤተስኪያን ደንበኞችም ይጠፉ ዘንድ ለዚህ የተመደቡ ናቸው፤ ቃሉንም ከመማር ርቀው በዝነኞቻቸው የትምህርት ንፋስ ተጠርገዋል። ብዙ ዘመን በውሃ ውስጥ የኖረ ጥቁር ድንጋይ ውሃው ወደውስጡ እንደማይገባ ሁሉ እነዚህም ደጋግመን በወንጌል ያስጠነቀቅናቸው ሆነው ሳሉ ትምህርታችንና የምክር ቃላችን አልገባቸውም።
እንግዲህ በብዙ ዝርዝር ልናየው የሞከርነውና ይህ “የጥፋት ወንጌል” ስል የሰየምኩት የጤና/ብልጥግና ወንጌል አደገኛነቱ ሊሰማን ይገባል። የዚህ ወንጌል አራማጆች እንደሚደሰኩሩት እግዚአብሔር አማኞች ሁሉ ጤናማና ባለጸጋ እንዲሆኑ፣ ከየትኛውም አካላዊ ስቃይና መከራ ነጻ እንዲሆኑ፣ በሚያደርጉት በማናቸውም ነገር እንዲበለጽጉና እንዲከናወንላቸው ይፈልጋል ብለው ያስተምራሉ። በመግቢያዬ ላይ እንዳመለከትኩት ይህ ጥሩ ዜና ይመስላል። ብቸኛው ችግሩ ግን እውነት አለመሆኑ ነው። ይህም መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረው ወንጌል ሳይሆን ሰዎች ሊሰሙት የሚፈልጉት "ማጽናኛ" (ማዝናኛ ቢባል ይቀላል) እና ስሜትን የሚኮረኩር ማነቃቂያ ብቻ ነው።
የዚህ የጤና/ብልጥግና ወንጌል ሰባኪዎች የሚያደርጉት አንድ ክፉ ስራ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሀብት የሚናገረውን ዋና መልዕክት ገልብጠው ስሜታችን ሊሰማው የሚፈልገውን እየደሰኮሩ ባህላችን ስለ ሀብት/ብልጽግና በሚናገረው ለመተካት የሚያደርጉት እውር ጥረት ነው። እርግጥ ነው፣ “እግዚአብሔር ባለጠጋ ሊያደርግህ ይፈልጋል” የሚለውን መልእክት ስትሰብክ፣ ትርጉሙ አጠቃላዩ የወንጌል መልእክት ስለ እኛና ስለ ፍላጎቶቻችን ነው የሚል ብቻ ሳይሆን፣ ወንጌሉ እግዚአብሔር ፍላጎቶቻችንን እንዲያሟላልን የምናደርግበት መንገድ፣ በራሳችንም ላይ ብቻ እያተኮርን ራስ ተኮር በሆነ ህልማችን የምንወሰድበትም ጭምር ይሆናል። ያኔ የእኛ ትክክለኛ የህልውናችን ማእከልም የፍላጎቶቻችን መሟላት እንጂ ራሱ እግዚአብሔር አይሆንም። ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኘው ከእግዚአብሔር ልናገኘው በምንችለው ነገር ብቻ ነው ማለት ነው። ትክክለኛው የህልውና ማእከላችንም "እግዚአብሔር ስኬታማ የአኗኗር ደረጃዬን ይባርክልኝ" በሚል ምኞት የሚነዳ በራሳችን ላይ ያተኮረ የብልጽግና እና የስኬታማ የህይወት ዘይቤአችን መሆኑ ነው።
(gkr)
Friday, June 2, 2023
ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያው
ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፩)
“የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ” የሚለው ይህ በማርቆስ 14፥ 61-62 ያለው ቃል እና በዮሐንስ 21፥ 22-23፣ ያለው ቃል፣ ሊቀ ካህናቱ ቀያፋ እና ሐዋርያው ዮሐንስ የጌታን ዳግም ምጽአት በአይናቸው ለማየት በህይወት እንደሚኖሩ ኢየሱስ የተናገረው የታመነ ቃል ነው።
በማርቆስ 14፥ 61-62፣ ኢየሱስን እንዲገደል ለሮማውያን አሳልፎ የሰጠውን ሊቀ ካህናቱን ቀያፋን በተመለከተ የሰው ልጅ በሰማይ ደመና ሆኖ ሲመጣ እንደሚያየው በግልጽ ነግሮታል። እንደገናም በዮሐንስ 21፥ 22-23፣ እንደተጻፈው ሐዋርያው ዮሐንስ ኢየሱስ ተመልሶ እስኪመጣ ድረስ በሕይወት ኖሮ እንደሚቆይ ተነግሮታል። ኢየሱስም በማቴዎስ 16፥ 27-28፣ በማቴዎስ 24 እና ማርቆስ 8፥ 38-9፥ 1 ባለው ክፍል ላይ በዚያው ትውልድ እንደሚመለስ ቃል ገብቷል። ኢየሱስ ስለዳግመኛ ምጽአቱ ደጋግሞ ከተናገራቸው እንደነዚህ ካሉት ንግግሮቹ የተነሳ ደቀ መዛሙርቱም ሆኑ የጥንት ቤተክርስቲያን ምዕመናን በሙሉ ኢየሱስ በህይወት ዘመናቸው ተመልሶ እንደሚመጣ በብዙ ያምኑና ይጠባበቁ እንደነበር መላው የአዲስ ኪዳን መልዕክቶች ያሳያሉ። ይህንን በበቂ ሊያስተባብልና ሊቃወም የቻለ ሥነመለኮት ፈጽሞ የሌለ በመሆኑ ፓሮውዥያው ከፍ ሲል በተጠቀሱት አይነተኛ ሰዎችና በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ቅዱሳን ትውልድ ውስጥ ተፈጽሟል ብሎ በዚህ እምነት ለመቆም ፕሪቴሪዝም ከተረትና ከልማድ ርቆ የእግዚአብሔርን ቃል ብቻ መሰረት አድርጓል።
ፕሪቴሪዝም ይለመልማል።
አልጨረስኩም
(GKR)
ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፪)
ስለ ፓሮሺያ ቅድመ ፕሪተርስት እይታ–
“የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ”፡-
"ታያላችሁ" የተባሉት እና ይህ ሲሆን ያዩ ዘንድ የተገባቸው እነማን እንደሆኑ ካላወቅን፣ "ታያላችሁ" የተባሉት ሊያዩ የተገባቸውን ካላዩ፣ ጌታም በኃይል ቀኝ መቀመጡንና በሰማይ ደመና መምጣቱን እስካሁን ካላሳያቸውና፣ ታያላችሁ የተባሉት ሊያዩ የተገባቸውን ሳያዩ ካለፉ፣ እኛን ጨምሮ ከዚያስ በኋላ ባለው ትውልድ የኖረና ገና ወደፊት የሚመጣ ሌላ ትውልድ ይህንን ሊያይ እንዴት ይችላል? ጌታስ እንዴት ታማኝ ይሆናል? እኛ እናይ ይሆናል የምትሉ ሁሉ እውነት እላችኋለሁ፣ ታያላችሁ ከተባሉት በቀር ማንም ቢሆን ይህ ሲሆን የሚያይ ከዚህ በኋላ እንደማይኖር ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ።
ተመልከቱ፣ ዳግም ምጽአት በራእይ 19፥ 11-14 እንዴት እንደተገለጠ ተዘግቧል። በዚያም የራእዩ ክፍል ኢየሱስ የመላእክትን ሠራዊት በሰማይ ላይ ሲመራ ይታያል። እንዲህ ሲል፦
"ሰማይም ተከፍቶ አየሁ፥ እነሆም አምባላይ ፈረስ፥ የተቀመጠበትም የታመነና እውነተኛ ይባላል፥ በጽድቅም ይፈርዳል ይዋጋልም። ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ናቸው፥ በራሱ ላይም ብዙ ዘውዶች አሉ፥ ከእርሱም በቀር አንድ እንኳ የማያውቀው የተጻፈ ስም አለው፤ በደምም የተረጨ ልብስ ተጐናጽፎአል፥ ስሙም የእግዚአብሔር ቃል ተብሎአል። በሰማይም ያሉት ጭፍራዎች ነጭና ጥሩ ቀጭን የተልባ እግር ልብስ ለብሰው በአምባላዮች ፈረሶች ተቀምጠው ይከተሉት ነበር።"
ፕሪቴሪዝም ይህ ቃል በጊዜው ለዚያውም በገሃድ እንደተፈጸመ ያምናል። የዚህ ትንቢታዊ ራእይ ታሪካዊ ፍጻሜ ደግሞ የሰው ልጅ የሆነው ጌታ ኢየሱስ፣ በ66 ዓ.ም በአይሁድ ሮም ጦርነት መጀመሪያ ላይ በደመና ውስጥ በገሃድ መታየቱ ነው። ይህንን ታሪካዊ ክስተት እና ዘገባውን ከዚህ ቀደም በግርድፉ አካፍያችሁ እንደነበር ይታወሳል። በቀጣዩ ጽሁፌ ሰፋ አድርጌ በማስረጃዎቹ ላይ እመለሳለሁ። ይሁንና ግን ይህ ታሪካዊ ማስረጃ ባይኖረን እንኳ፣ ክርስቶስ በዚያ ከተማይቱና መቅደስዋ ፈጽመው በሚፈራርሱበት የአይሁድ ሮም ጦርነት ወቅት ተመልሶ ለመምጣት የሰጠውን ተስፋ እንደፈጸመ ያለጥርጥር ማመን ይቻለናል። ምክንያቱም እንደዚያ እንድናምን በእግዚአብሔር ቃል ብቻ ተይዘናልና።
ተመልከቱ፣ ዳግመኛ ምጽአቱ በራዕይ 19፥ 11-14 በዝርዝር እንደተገለጸዉ ጌታ ኢየሱስ በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ የመላእክትን ሠራዊት እየመራ በደመና ላይ የታየበት ነው። ይህ ቃል እንዴት እንደተፈጸመና የዳግም ምጽአቱ ገሃዳዊ መታየት ምን እንደሚመስል፣ ታሪክም እንዴት ዘግቦ እንዳስቀመጠው በሚቀጥለው ክፍል እናያለን።
ከዝባዝንኬ ተረትና የቆየ ልማድ ርቃችሁ የእግዚአብሔርን ቃል ብቻ ማመንና መታዘዝ ይበዛላችሁ ዘንድ እጸልያለሁ። ጌታም በነገር ሁሉ ማስተዋልን ይስጠን።
(GKR)
ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፫)
የዳግም ምጽአቱ ቀዳሚ ፍጻሜ ታሪካዊ ምስክርነት—
“የሰው ልጅም . . . በሰማይ ደመና ይመጣል”፡-
አሁን የምታነቡትን ነገር ምናልባት ከዚህ ቀደም ያልሰማችሁት ታሪክ ሊሆን ይችላል። ዳሩ ግን ይህን ታሪካዊ ዘገባ ለሚያስተውለው ሰው ከዘሙኑ ፍጻሜና ከጌታ ዳግም ምጽአት ምንነት አንጻር አእምሮን ሊይዝ የሚችል ብርቱ ምስክርነትእንደሚሆንቡት አልጠራጠርም። የዳግም ምጽአቱ ኹነት በአይሁድ ሮም የጦርነት ታሪክ ተዘግቦ ትውልድ እንዲያነበው ተቀምጧልና። አሁንም ደግሜ እላለሁ፣ ይህ ታሪካዊ ማስረጃ ፈጽሞ ባይኖረን እንኳ፣ ክርስቶስ በዚያ ከተማይቱና መቅደስዋ ፈጽመው በሚፈራርሱበት የአይሁድ ሮም ጦርነት ወቅት ተመልሶ ለመምጣት የሰጠውን ተስፋ እንደፈጸመ ያለጥርጥር ማመን ግን ይቻለናል። ምክንያቱም እንደዚያ እንድናምን በእግዚአብሔር ቃል ብቻ ተይዘናልና። ሆኖም የክርስቶስን ቃል ለሚጠራጠሩ ላልተማሩና ለሚስቱ ወገኖች ስንል ታሪካዊ ዘገባዎችን አንስተን እንይ፦
….ከዚያ ከበዓሉ ጥቂት ቀናት በኋላ፣’… በ21ኛው በአርጤምስየስ [ጂያር] ቀን… “አንድ አስደናቂ እና ሁሉንም ያስገረመ ክስተት ታየ። ይህ ክስተት ሲፈጸም ታሪኩን በገዛ አይናቸው ባዩት በነዚያ ሰዎች ህይወትና የእለት ተለት ኑሮ ውስጥ ምንም ተጽዕኖ ባይኖረውና፣ ከዚያም በኋላ ተከትለው የተፈጸሙ ድርጊቶች እንደነዚህ ያሉ ምልክቶች የሚገባቸው አይነት ትላልቅ ተፈጥሮ ያላቸው ክስተቶች ባይሆኑ ኖሮ፣ እኔ ራሴ ታሪኩ ተረት ይመስላል ብዬ ባሰብሁና ትኩረት ሰጥቼ ሳልዘግበው በተውኩት ነበር፤ የታየውና የሆነው ግን ይሄ ነው፣ ፀሐይ ከመጥለቋ በፊት ሠረገሎችና በላያቸው ላይ ተቀምጠው የሚጋልቡ የታጠቁ የሰራዊት ጭፍሮች በደመናው መካከል ወዲህና ወዲያ እየተሯሯጡ ከተማይቱን ሲከብቧት ታዩአቸው። ከዚህም በላይ በዓለሃምሳ ብለን በምንጠራው በዚያ የበዓል ቀን ካህናቱ በሌሊት እንደ ልማዳቸው ወደ ውስጠኛው የቤተ መቅደሱ ክፍል ገብተው የዘወትሩን አገልግሎታቸውን እይፈጸሙ ሳለ፣ በመጀመሪያ ለራሳቸው ብቻ የሚታወቅ መሸበርና ፍርሃት ይሰማቸው እንደነበሩ ሲገልጡ፣ በታላቅ ድንጋጤም ውስጥ ሆነው እየተንቀጠቀጡ የሰሙት ታላቅ ድምፅ "ኑ ከዚህ በኋላ ይህንን ስፍራ ለቅቀን እንሂድ” የሚል እንደ ብዙ ሕዝብ ያለ ድምፅ ነበር። (Wars, 6-5-3, አንቀጽ 297-299)
በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ይኖር የነበረው አይሁዳዊ የታሪክ ጸሐፊ ጆሴፈስ በራእይ 19፥ 11-14 ላይ ኢየሱስ ይመራው እንደነበረው ያለ ሠራዊት በደመና ውስጥ የተመመውን ሰማያዊ ሠራዊት በትረካው ገልጿል። ይህ ክስተት በሌሎች የታሪክ ተመራማሪዎችም ተዘግቧል። በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ይኖር የነበረው ሌላው አረማዊ የታሪክ ጸሐፊ ታሲተስም ይህን ክስተት ጠቅሶ "በሰማይ ውስጥ የሰራዊት ግጭትና የሚያብረቀርቅ የጦር ራእይ ታየ" ሲል ጽፏል [Tacitus The Histories 5.13.]። ፕስዩዶ ሄጌሲፐስም በዚያን ጊዜ ከኃያላን መላእክቱ ጋር የክርስቶስን በደመና ላይ መምጣቱን ሲገልጽ እንዲህ ሲል ጽፏል፦"“የአይሁድ መጻሕፍት እንደ ገለጹት ብዙዎች ያዩት እጅግ ታላቅ የሆነ ምስል በሰማዩ ላይ ታየ፤ ፀሐይም ሳትጠልቅ በደመና ውስጥ ሰረገሎችና የታጠቁ የጦር ሠራዊቶች በደመናት ላይ ሆነው ሲርዋርዋጡ ታዩ፤ የይሁዳ ከተሞችንና ግዛቶቿንም ሁሉ ወረሩ።" [Pseudo-Hegesippus 44.] የመካከለኛው ዘመን አይሁዳዊ የታሪክ ምሁር ሴፈር ዮሲፖንም በ66 ዓ.ም ሰማይ ላይ ስለነበረው የመላእክት ሠራዊት እንዲህ ሲል ገልጾታል፦ “በዚያም ወራት የእሳት ሰረገሎችና ፈረሰኞች፣ ታላቅ ሠራዊትም ሆነው በሰማዩ ላይ እየበረሩ ወደ ምድር በቀረቡ ጊዜ በኢየሩሳሌምና በይሁዳ ምድር ሁሉ ላሉ ሰዎች የእሳት ፈረሶችና የእሳት ፈረሰኞች ሲመጡ ታዩአቸው" [Sepher Yosippon A Mediaeval History of Ancient Israel በተሰኘውና Steven B. Bowman ከዕብራይስጥ ቋንቋ የተረጎመው ሲሆን በምዕራፍ 87 “Burning of the Temple” ከተሰኘው ክፍል ላይ የተጠቀሰ ነው] በተጨማሪም፦
http://fulfilledtheology.ning.com/forum/topics/historical-records-with-some (9/16/2014) በተሰኘው ድረ ገጽ ላይም ተጠቅሶ ይገኛል።
እንግዲህ ልብ ብለን ካየነው በእነዚህ ሦስት ዘገባዎች እና በራእይ 19 መካከል ያለው ተመሳሳይነት በእጅጉ አስደናቂ ነው። በመሆኑም፣ በዮሲፖን ዘገባ እንደሰፈረው 2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 ላይ ያለውና "ጌታ ኢየሱስ ከሥልጣኑ መላእክት ጋር ከሰማይ በእሳት ነበልባል ይገለጣል" የሚለው ቃል በ66 ዓ.ም ላይ በነበረው የአይሁድ ሮም ጦርነት መባቻ ላይ እንዴት ግልፅ እና ተዳሳሽ በሆነ መልኩ እንደተፈጸመ ማየት እንችላለን። ያ የመጅመርያው ክፍለ ዘመን የአይሁድ ሮም ጦርነት በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ ከተካሄዱ ጦርነቶች ሁሉ ይልቅ የከፋው ብቻ ተብሎ የሚወሰድ አይደለም። በሁለት ህዝቦች መካከል የተደረገ ግጭት ብቻም ሳይሆን፤ መለኮት ያስከተተው፣ የሰው ልጆችን ታሪክና መጻኢ እድል ሊቀይር ሰማይ ራሱ የዘመተበት፣ በአይሁድ ቅዱሳት መጻህፍት በብዙ የተነገረለት የፍጻሜው አርማጌዶን ነበር። ያ የጦርነት ታሪክ ግንዛቤ ውስጥ ሳይገባ የሚደረግ የአዲስ ኪዳን ትንቢት ትርጓሜ ሁሉ ቤተክርስቲያንንና ትምህርቷን ወደማይረባ የተረት ዝባዝንኬ ውስጥ እየዶለ እምነቷንና ተስፋዋን የአለም መሳቂያና መሰደቢያ እያደረገ፣ ሰዎችንም ከእምነት ይልቅ ለክህደት የሚጋብዝ ሆኖ መቀጠሉ አይቀርም።
በሚቀጥለው ጥሁፍ ይህ ታሪካዊ ሰማያዊ ክስተት የትንቢት ፍጻሜ ሆኖ ለመወሰድ እንዴት የመለኮታዊ መገለጥን መስፈርት እንደሚያሟላ በመጽሐፍ ቅዱሳዊ በማስረጃ እንመለከታለን።
ቸር ሰንብቱ
(GKR)
ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፬)
የዳግም ምጽአቱ ፕሪቴሪስታዊ እይታ— በቀደመው ጽሁፌ የዳሰስሁት ታሪክ ዘግቦ ያቆየልን ሰማያዊ ክስተት የትንቢት ፍጻሜ ሆኖ ለመውሰድ እንዴት የመለኮታዊ መገለጥ መስፈርትን እንደሚያሟላና፣ ያ በእስራኤል ሰማይ ላይ የታየው ትንግርት የጌታ መምጣት መሆኑን፣ እርሱም በቀደመው ኪዳን የአምላክ አመጣጥ ሁናቴ የተብራራ እንደሆነ ጨምረን እንመለከታለን፦
“የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ”
ዮሲፖን በ66 ዓ.ም የሰማይ ላይ የእሳት ሠራዊት በሰማይ ላይ መታየቱን አስመልክቶ የሰጠው ታሪካዊ ዘገባ በብሉይ ኪዳን ቀደም ሲል በኢሳይያስ 66፥ 15፤ በመዝሙረ ዳዊት 68፥ 17 እና በዕንባቆም 3፥ 1-8 የተገለጠውን የጌታን መምጣት መግለጫና መስፈርት በሚገርም የቃል በቃል ንግግር የሚያሟላ ነው። ያህዌ በጥንቱ ዘመን ወደህዝቦችና መንግስታት በፍርድ እና በምርት ይመጣ የነበረበትን መንገድ በሚመስልና በሚስተካከል አኳኋን የ66ቱ ዓ.ም ክስተትም እንዲሁ ነው።
በ66 ዓ.ም በፈረሶችና በሰረገሎች እየጋለቡ በእስራኤል ሰማይ ላይ ለታዩ እሳትማ መላእክቶች ፊት አውራሪ ሆኖ ክርስቶስ መምጣቱ በ2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 ላይ "ጌታ ኢየሱስ ከሥልጣኑ መላእክት ጋር ከሰማይ በእሳት ነበልባል ይገለጣል"" ሲል የተተነበየውን ቃል በቃል ፍጻሜ ይሰጠዋል። ይህም በኢሳይያስ 66፥ 15 ላይ "እነሆ፥ እግዚአብሔር መዓቱን በቍጣ፥ ዘለፋውንም በእሳት ነበልባል ይመልስ ዘንድ ከእሳት ጋር ይመጣል፥ ሰረገሎቹም እንደ ዐውሎ ነፋስ ይሆናሉ።" ሲል የተነገረውን የጌታን አመጣጥ በሚያስገርም ሁኔታና ቀጥተኛ በሆነ መንገድ ያንጸባርቃል። በመዝሙር 68፥ 17 እና ዕንባቆም 3፥ 1-8 ላይ የተገለጠው በፍርድ የሆነው የጌታ አመጣጥ ገለጻዎችም በተመሳሳይ መልኩ የሚታዩ ናቸው። የሚገርመው፣ በ66 ዓ.ም በእስራኤል ሰማይ ላይ ታይቶ የነበረው እሳትማ የመላእክት ፈረሰኞችና ሠረገላዎች በጥንታዊ የእስራኤል ታሪክ ውስጥ የተለመደ በመሆኑ እንደዚህ ያለ ትዕይንት ሲዘገብ ይህ የመጀመሪያው አልነበረም።
ይህ በዮሲፖን የተዘገበውና በ66 ዓ.ም በሰማይ ላይ የታየው የመላእክት የእሳት ሠራዊት መግለጫ በ2ኛ ነገሥት 6፥ 17 ላይ ከብዙ ዘመን በፊት የተገለፀውን የእሳት መላእክት ሠራዊት በትክክል ያንጸባርቃል።
በዳግም ምጽአቱ ኢየሱስን አጅበው ከእርሱ ጋር ወደ ክብሩ ለመግባት ሲጠበቁ እንደነበሩት ቅዱሳን ሁሉ በ2ኛ ነገሥት 6፥ 17 ላይ ኤልሳዕም በመላእክት ሠራዊት ይጠበቅ እንደነበር እናያለን። ይህ እሳትማ የመላእክት ሠራዊት በዮሲፖን እንደተዘገበው የፈረሰኞች፣ የፈረሶች እና የእሳት ሰረገሎች ሠራዊት ተብሎ በትክክል ተገልጿል። 2ኛ ነገ 6፥ 17 "ኤልሳዕም፦ አቤቱ፥ ያይ ዘንድ ዓይኖቹን፥ እባክህ፥ ግለጥ ብሎ ጸለየ። እግዚአብሔርም የብላቴናውን ዓይኖች ገለጠ፥ አየም እነሆም፥ በኤልሳዕ ዙሪያ ያሉት የእሳት ፈረሶችና ሰረገሎች ተራራውን ሞልተውት ነበር።" እንግዲህ በሁለቱም ሁኔታዎች ውስጥ የመላእክት ፈረሰኞች ሠራዊት እንደ ፈረሰኞችና የእሳት ሠረገላዎች መከሰታቸውን ልብ በሉ።
በሐዋርያት ሥራ 9፥ 3-6 ሳውል በአሳዳጅነት መንገዱ ላይ ተገልጦ ያየው ኢየሱስና እና በራዕይ 1፥ 13-16 በፍጥሞ ለዮሐንስ ተገለጦ በታየው መሰረት፣ ኢየሱስ በትንሳኤው ያለው አካል ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ የበለጠ የከበረ አካል እንደሆነ፣ ይህም እንደ ነበልባል እሳት የሚያበራ መሆኑን እናያለን። ይህ ዕፁብ ድንቅ ብርሃን የሳውልን አይኖች አሳውሮ በምድር ላይ ጥሎታል፤ በተለይ ለዮሐንስ ደግሞ በደረቱ ላይ ተጠግቶ ምስጢርን ከእርሱ ይሰማ እንደነበረበት ጊዜ ሳይሆን፣ ትእይንቱ በእግሩ ስር እንደሞተ ሰው አድርጎ የሚደፋው ነበር።
"ራሱና የራሱ ጠጕርም እንደ ነጭ የበግ ጠጕር እንደ በረዶም ነጭ ነበሩ፥ ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ነበሩ፤ እግሮቹም በእቶን የነጠረ የጋለ ናስ ይመስሉ ነበር፥ ድምፁም እንደ ብዙ ውኃዎች ድምፅ ነበረ። በቀኝ እጁም ሰባት ከዋክብት ነበሩት፥ ከአፉም በሁለት ወገን የተሳለ ስለታም ሰይፍ ወጣ፤ ፊቱም በኃይል እንደሚበራ እንደ ፀሐይ ነበረ።"
ማንም ሊቀርበው በማይችል ብርሃን የሚኖር እርሱ ሲገለጥ ብረቱንና ናሱን የሚያቀልጥ ሁሉን የሚበላ እሳት ይሆናል። ከሙታን ተነስቶ ወደክብሩ የገባው ይህ ኢየሱስ እንደ አባቱ ሁሉ የሚያስፈራ፣ በማንነቱ ("በተፈጥሮው") የሚባላና ማንም ሊቀርበው የማይችል የእቶን እሳት ነው። ስለዚህ ይህ የኢየሱስ አካል በ2ኛ ነገሥት 6፥ 17፣ በ2 ቆሮንቶስ 11፥ 14 እና በማቴዎስ 28፥ 2-3 ባለው መሠረት የሰማይ መላእክትን ዓይነት መልክ የያዘ ነበር።
በ2ኛ ነገሥት 6፥ 17 ላይ ያሉት መላእክት እና በ66 ዓ.ም በዮሲፖን ዘገባ የተገለጹት የእሳት ፍጡራን ተመሳስለው ለምን ተገለጡ? በ2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 ላይስ ጌታ ኢየሱስ በዳግም ምጽአቱ ወቅት የሚነድ እሳትን የመሰለ መልክ እንደሚይዝ የሚናገረው ለምንድን ነው? ምንም እንኳን የኢየሱስ የትንሳኤ አካል ከእርገቱ አስቀድሞ ገና በምድር ሳለ ከሥጋዊ አካሉ ጋር ቢመሳሰልም፣ ነገር ግን በሐዋርያት ሥራ 1 ላይ ኢየሱስ ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ ይህ የተለወጠ ይመስላል (የሐዋርያት ሥራ 9፥ 3-6፣ ራዕይ 1፥ 13-16)። ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ፣ በቀረው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ የተገለጸው የኢየሱስ አካል በሰማይ ካለው አባቱና ስለ ሌሎች ሰማያዊ አካላት ከተሰጠው መጽሐፍ ቅዱሳዊ መግለጫዎች ጋር በቅርበት ይመሳሰላል። ለምሳሌም፣ ነብዩ ሕዝቅኤል በትንቢቱ ምዕራፍ 1፥ 26-28 ባለው ክፍል የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ መልክን በራእይ አይቶ፣ "የእግዚአብሔር ክብር እንደ እሳት ምስያ ያበራል" ብሎ ሲናገር፣ በሐዋርያት ሥራ 9፥ 3-6 እና በራዕይ 1፥ 13-16 ላይ ኢየሱስን አስመልክቶ ከተሰጡት መግለጫዎች ጋር ተመሳሳይ በሆነ ሁኔታ ተነግሯል፦ "በራሳቸውም በላይ ካለው ጠፈር በላይ የሰንፔር ድንጋይ የሚመስል የዙፋን አምሳያ ነበረ፤ በዙፋኑም አምሳያ ላይ እንደ ሰው መልክ አምሳያ ነበረ። ከወገቡም አምሳያ ወደ ላይ የሚብለጨለጭ የወርቅ ምስያ አየሁ፤ ከወገቡም አምሳያ ወደ ታች እንደ እሳት ምስያ አየሁ፤ በዙሪያውም ፀዳል ነበረ። በዝናብ ቀን በደመና ውስጥ እንደ ቀስተ ደመና አምሳያ፥ እንዲሁ በዙሪያው ያለ ፀዳል አምሳያ ነበረ። የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ መልክ ይህ ነበረ። ባየሁም ጊዜ በግምባሬ ተደፋሁ፥ የሚናገርንም ድምፅ ሰማሁ።"
ተመልከቱ፣ ከዕርገቱ በኋላ ያለው የክርስቶስ ትንሳኤ አካል ብሩህነትና ግርማው እንደ ጸሐይ ብሩህነ የሚያበራ መሆኑ በሐዋርያት ሥራ 9፥ 3-6 ውስጥም ተጠቅሷል፤ ጌታ ካረገ በኋላ የነበረውንና ጳውሎስን ለጊዜው በእውርነት የመታውንና የጣለውን ታላቅ ብርሃን ክፍሉ ያመለክታል። ዮሲፖን በትረካው በሰማይ ላይ የታዩት እነዚያ ትንግርታዊ ፈረሶች ምን አይነት እንደነበሩ ሲገልጥ የእሳት ፈረሶች እንደነበሩ ይናገራል፤ በራእይ 19፥ 14 ላይ ግን መላእክቱ ነጭ ፈረሶችን ይጋልቡ እንደነበር ይናገራል፣ ይህ ታዲያ ተቃርኖ ነው ወይ? በጭራሽ አይቃረንም። ወደ ሞት የቀረቡና የዚያ ራእይ ልምምድ ያላቸው በርካታ ሰዎች ከነቁ በኋላ ስላለፉበት የሞት ጽልመት ሲናገሩ በሰማያዊው ግዛት ውስጥ ያሉ ፍጥረታት በከፍተኛ ሁኔታ የሚያብረቀርቅ ነጭ ብርሃን እንደሚፈነጥቁ ሲገልጹ በተደጋጋሚ ይደመጣሉ። ስለዚህ በዮሲፖን ትረካ የተገለጹት ፈረሶችና ፈረሰኞች በሰማይ እንዳሉት ሌሎች ፍጥረታት ሁሉ በሚያንጸባርቅ ነጭ ብርሃን ውስጥ ሆነው ሳይታዩ እንዳልቀረ ይመስላል ማለት ነው።
በዚያን ጊዜ ጌታ ኢየሱስ የዚህ ሠራዊት ፊት አውራሪና ራስ ሆኖ ተገኝቶ መሆን እንዳለበት ከታሪካዊው ዘገባ እናስተውላለን፤ ይህም ግምታችን ብቻ አይደለም። ምንም እንኳን ኢየሱስ በደመና ውስጥ ባለው በዚህ የመላእክት ሠራዊት ራስ ላይ በውል ተለይቶ ባይታወቅም፣ በዚያ ተአምራዊ ትዕይንት ውስጥ ግን ያንን ሰማያዊ ጭፍራ ድል ለመንሳት አስከትቶ በግርማው የመጣው እርሱ ራሱ መሆን እንዳለበት ግልጽ ነው ብዬ አምናለሁ። በአገልግሎቱ ዘመን ሁሉ ሲናገር እንደነበረው ጌታ ኢየሱስ በአገልግሎቱ ወቅት በነበሩት አድማጭ ተመልካቾቹ ሰዎች የህይወት ዘመን በትውልዳቸው ውስጥ የሰማይ ሰራዊትን እየመራ በደመና ላይ ሆኖ እንደሚመጣ ይተንብይ ነበርና። ኢየሱስ በዚያ ሁኔታ ተመልሶ እንደሚመጣ ተንብዮ ከነበረ፣ እኛ በትንሽዋ አእምሮአችን ታሪክንና ክስተትን አነጻጽረን ከምንደርስበት ድምዳሜ በላይ የትንቢት ቃል የጸና እውነት መሆኑን እናውቃለን። በእስራኤል ሰማይ ላይ የታየው ይህ ልዕለ ተፈጥሯዊ የሆነ ክስተት ከሆነ፣ በእርግጥም የዮሐንስ ራእይ 19፥ 14 እና ሌሎች ስለ ዳግም ምጽአቱ የተነገሩ የመጽሐፍ ቅዱስ ገለጻዎችን ሁሉ አሟልቶ የሚፈጽመውም ከሆነ፣ እንግዲያውስ ኢየሱስ በደመና ላይ ባለው በዚህ ሠራዊት ራስ ላይ ፊት አውራሪው ሆኖ ተገኝቶ መሆን አለበት ማለት ነው። እሱ ባይሆን ኖሮ ግን ይህ ተአምራዊ ክስተት በጣም የአጋጣሚ ጉዳይ ብቻ ሊሆን ይችል ነበር ብለን ከትንቢት ፍጻሜ ደረጃ ማውረድ በቀለለን ነበር፤ ያንን እንዳናዱርግ ግን በትንቢቱ ቃል ተይዘኔል። ጌታ ኢየሱስ በስጋው ወራት ባገለገለው ማህበረሰብ እና በትውልዱ ውስጥ በሰማይ ደመናና በክብር ተመልሶ ለመምጣት ከሰጠው ጽኑና ተደጋጋሚ ተስፋው አንጻር ሲታይ ይህ ታሪክ ከትቦ ያስቀመጠው ተአምራዊ ክስተት የአጋጣሚ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፤ ይልቁንም ይህ ክስተት የሰጠውን ተስፋ የሚሞላ በትክክልም የፓሮውዥያው ትንቢት ፍጻሜ ነበር። በተጨማሪም ኢየሱስ በዚህ የሰማይ ሠራዊት መሪነቱ ተለይቶ የታወቀ ከሆነ በጥቅሉ ይህ በደመና ውስጥ የታየው የሰራዊቱ ታሪካዊ ዘገባ ትንቢት መፈጸሙን ለማስረዳትና በክርስቲያናዊ መስተጋብር ውስጥ እምነታችንን ከጥቃት ለመከላከል በእጅጉ የሚረዳ ጠንካራ ማስረጃችን ተደርጎ ሊወሰድም ይችላል። ተመልከቱ፣ ክርስቲያን ያልሆኑ የታሪክ ሰዎች ስለ ክርስቲያናዊ የነገረ ፍጻሜ ጥናት ዝርዝሮች በጥልቀት ሊያውቁ የማይችሉ እንደመሆናቸው መጠን፣ እነዚያ ክርስቲያን ያልነበሩ ታሲተስ እና ጆሴፈስ የተባሉ የታሪክ ዘጋቢዎች በዘገባቸው እንዲህ ዓይነት ግልጽ መለያን ያደርጋሉ ተብሎ አይጠበቅም። በአንጻሩ ግን የታሪክ ዘገባቸው የዮሐንስ ራእይ መጽሐፍና የማቴዎ 24 ፍካሬ ማብራሪያ እስኪመስል ድረስ ታሪክ ባይነት ባይነቱ ተቀናብሮ መገኘቱን ስናይ፣ ትንቢት ለመፈጸሙ ማስረጃ የሚሆን ውጫዊ ሰነድ እግዚአብሔር በኪነ ጥበቡ እንዳሰናዳልን እናስተውላለን። ይህ ውጫዊ የታሪክ ሰነድ ደግሞ በባህርይው ውስጣዊ ለሆነው ጽኑ የትንቢት ቃል ሲገዛ እንደ ማየት ለቃሉ አማኝና ለቃሉ ተማሪ ምን የሚያስደስት ነገር ይኖር ይሆን! ታሪክ ለእግዚአብሔር ቃል ይሰግዳል። የዚህን ክስተት ታሪካዊ አስተማማኝነትና ማስረጃዎችን የበለጠ በዝርዝር ማብራሪያ ለማቅረብ የተሞከረበትን ጥናት ጊዜ ከተሰጠን ኋላ ላይ ቆየት እያልን እንመለስበታለን።
ለአሁኑ እዚህ ላይ ላብቃ፤ ቸር ሰንብቱ
(GKR)
ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፭)
“የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ”
እንደ ታሲተስ ታሪካዊ ዘገባ ከሆነ፣ ያኔ በአይሁድ አመጽ መጀመርያ ላይ መብረቅ በርቆ መቅደሱን መትቶት ነበር፤ ይህም
የማቴዎስ 24፥ 27 ትንቢትን ፍጻሜ በሚሰጥበት መልኩ በዳግመኛ ምጽአቱ ወቅት የሚጠበቅ ክስተት መሆኑን እናውቃለን።
ማቴዎስ 24፥ 27 እንዲህ ይላል፡- “መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ፥ የሰው ልጅ መምጣት እንዲሁ ይሆናልና፤"
ይህ ጥቅስ የሰው ልጅ በደመና ላይ ሲመጣ እንደ መብረቅ ሆኖ እንደሚመጣ የሚያመለክት ይመስላል። የመብረቅ መኖር ፓሮውዥያውን የሚያጅበው ክስተት መሆኑ በቃሉ እንደተገለጠ ሁሉ ከምጽአቱ ጋር ባለው ግንኙነት አብሮ ሊሆን እንደሚችል የሚያሳዩ የታሪክ ማስረጃዎች በ66 ዓ.ም የአይሁድ ዓመፅ መጀመሪያ ላይ በሮማውያን ታሪክ ጸሐፊ ታሲተስ ተመዝግቧል፦ "የጭፍሮች ግጭትና የሚያብረቀርቅ የጦር ትጥቅ፣ የፈረሶች ኮቴና የሰረገላ ድምጽ ራእይ ከፍ ብሎ በከተማይቱ ሰማይ ላይ ይታይ ነበር። ድንገትም ከደመናው መሃል በኃይል የሚያበራ የመብረቅ ብልጭታ፣ የገሞራ እሳትም በመቅደሱ ላይ አበራ። ብራቅም ሆነ፤ የቅዱሱ ቦታ በሮችም በድንገት ተበርግደው ተከፈቱ፣ አማልክት እንደሚለቁት ያለና ሰው ሊያወጣው ከሚችለው በላይ የሆነ ድምፅም ተሰማ፣ እናም በዚያው ቅጽበት በችኮላ ስፍራውን ለቅቀው መሄዳቸውን የሚያመለክት የመለከት ድምጽ ሆነ።" [Tacitus The Histories 5.13]
በማቴዎስ 28፥ 2-3 ላይ እንደተገለጸው ሰማያዊ አካላት እንደ ጸሐይ የሚያንጸባርቅ መልክ እንዳላቸው ተነግሯል፤ ስለዚህም በማቴዎስ 24፥ 27 ክርስቶስ መብረቅ በሚመስል ብሩህ፣ አንጸባራቂ መልክ እንደሚገለጥ ሲነገር በፓሮዥያውም እንዲሁ ይፈጸማል። እንደ እውነቱ ከሆነ፣ ዳግመኛ ምጽአቱ ከምስራቅ ወጥቶ በስተምዕራብ ከሚታየው መብረቅ ጋር መነጻጸሩን ስናስተውል ያ የክርስቶስ መብረቃዊ ብርሃነ መለኮት ከዕርገቱ በኋላ በፓሮዥያው ላይ ያለውን ክብር የሚገልጽ መሆኑን እናያለን። ከኢየሱስ ትንሣኤ በኋላ የታየው የጌታ መልአክም በማቴዎስ 28፥ 2-3 በተነገረው መሠረት መብረቅ በሚመስል መልክ መገለጡን አስታውሱ፡-"እነሆም፥ የጌታ መልአክ ከሰማይ ስለ ወረደ ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ፤ ቀርቦም ድንጋዩን አንከባሎ በላዩ ተቀመጠ። መልኩም እንደ መብረቅ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ነበረ።" በቀደመው የዚህ ጽሁፍ ክፍል እንደተገለጸው፣ ኢየሱስ ከዕርገቱ በኋላ በሥጋው እንደሚታወቅ አይደለም፤ ይልቁን ግን በግርማው የማይቀረብና የሚያስፈራ ሆኖ ተመሳሳይ አንጸባራቂ መልክን ይዟል፣ እርሱም ደግሞ እንደ መብረቅ ብራቅ ይመስላል።
እንግዲህ በ66 ዓ.ም በሰማዩ ላይ ታይቶ የነበረው ያ የመላእክት ሠራዊትና የተሰማው የፈረሶች ኮቴና የሰረገላ ድምጽ ስለ ዳግመኛ ምጽዓቱ የተነገሩትንና የተገለጡትን ሁሉንም የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች በበቂ ያሟላል እያልሁ ደጋግሜ አጽንዖት የሰጠሁበትን ሃሳብ ልብ አድርጉ። ይህም ማለት ከላይ በታሪክ ጸሓፍያኑ ተዘግቦ ያየነው ያ ሰማያዊ ሰራዊት ስለ ዳግመኛ ምጽአቱ በዝርዝር የተነገሩትን ሁሉንም መጽሐፍ ቅዱሳዊ መግለጫዎች ፍጻሜ ይሰጣቸዋል ማለት ነው። ከዚህ ቀጥሎ በምንመለከታቸው ስምንት ነጥቦች ወደ ማጠቃለያዬ አልፋለሁ። እነዚህን ነጥቦችና የጠቀስኳቸውን የቅዱሳት መጻህት ምንባባት ከተከፈተ መጽሐፍ ቅዱስ ጋር ልትመለከቷቸው ካልወደዳችሁ ግን ኮስታራ የቃሉ ተማሪዎች ስላልሆናችሁ እዚህ ሩም ውስጥ ለናንተ የሚሆን ምንም መነባነብ አይኖርም። ነጥቦቹን እነሆ፦
በማቴዎስ 24፣ ማቴዎስ 16፥ 28፣ ማቴዎስ 10፥ 23፣ ማርቆስ 8፥ 38-9፥ 1፣ ማርቆስ 14፥ 61-62፣ ዮሐንስ 21፥ 22 እና ራእይ 1፥ 7 የተተነበየው ይህ ክስተት የተፈፀመው በራሱ ኢየሱስ ትውልድ እና ዘመን፣ በሐዋርያቱና በጥንት ቤተክርስቲያን ዘመንና ትውልድ ውስጥ መሆኑ የታመነ ነው። ይህን አለማመን የእግዚአብሔርን ቃል አለማመን ብቻ ሳይሆን ራሱን ጌታችንን ውሸተኛ ማድረግ ነው፤ ውሸተኛ ጌታ ደግሞ እውነተኛ አዳኝ ሊሆነን አይችልም። እውነተኛ አዳኝ ከሌለን ደግሞ ክርስትና የለም። ስለዚህ አስተውሉ፣ ይህ የምጽአቱ ትንቢት የመጀመርያውን ክፍለ ዘመን ከሚሽፍነው ከዚህ የጊዜ ወሰን ውጭ በሌላ በየትኛውም ሌላ መጻኢ ዘመን ውስጥ የሚፈጸም ለመሆኑም ሆነ የፍጻሜውን ጊዜ አራዝመን ወደፊት ለመጠባበቅ ምንም አይነት የቃሉ ድጋፍ የለንም። ይህም የትንቢት ፍጻሜ ዘመን በቤተ ክርስቲያን ትውፊት ሲነገር በኖረው መሠረት እስከ ትራጃን ዘመነ መንግሥት ድረስ በህይወት እንደኖረ በሚገመተው በሐዋርያው ዮሐንስ የሕይወት ዘመን ውስጥ፣ ማለትም በአንደኛው መቶ ክፍለ ዘመን የመጨረሻዎቹ አስርት ዓመታት አልያም በሁለተኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ ማለት ነው። [Eusebius The History of the Church 3.23.]
በማቴዎስ 24፥ 30፤ ራእይ 1፥ 7 እና ማርቆስ 14፥ 62 ትንቢት መሠረት ይህ ክስተት በደመና ላይ የሚፈጸም እንደሆነ ተዘግቧል።
ይህ ልዕለ ተፈጥሯዊ የሆነና ብዙ መላእክትን እየመራ የመጣው የሰው ልጅ የሆነው ኢየሱስን የሚመስለው ሰማያዊ ትዕይንት ታሪካዊ ዘገባ በማቴዎስ 16፥ 27፣ በማርቆስ 8፥ 38፣ በ2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 እና በይሁዳ 14-15 የተጻፈውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ የትንቢት ቃል መሰረት ያደረገ መሆኑን ያሳያል። የትንቢቱ ቃል እና የታሪክ ጸሐፍያኑ ዘገባ እርስ በርሳቸው የተስማሙ ናቸው።
ይህ በማቴዎስ 16፥ 27-28፣ በማቴዎስ 24፥ 27፣ በማቴዎስ 24፥ 30፣ በማርቆስ 14፥ 62፣ በራእይ 1፥ 7 እና በሐዋርያት ሥራ 1፥ 9-11 ያለውና በታሪክ ውስጥ በገሃድ ፍጻሜውን ያገኘው ክስተትና መገለጡ የታወቀው (ቢያንስ በራእይ መልክ) ነበር።
ይህ ክስተት የመብረቅ መኖርን በሚያሟላ ይዘቱ ታጅቦ በማቴዎስ ወንጌል 24፥ 27 ላይ የተጻፈውን ፍጻሜ ይሰጠዋል።
ኢየሱስ በማቴዎስ 24፥ 27 እና በ2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 የተነገረውን ፍጻሜ በሚስጥ መልኩ በገሞራ እሳትና የመብረቅ ብልጭታን በሚመስል ደማቅ ብርሃን በሚበርቅና በሚያንጸባርቅ ሰማያዊ ሠራዊት ላይ ሆኖ ተገለጧል።
ፓሮውዥያው የተጀመረው በራዕይ 8፥ 5 እና በራዕይ 14፥ 14 ላይ እንደተገለጸው የአይሁድ ሮም ጦርነት ሲጀመር ነው። ፓሮውዥያ የሆነው በ66 ዓ.ም ነበር ወይንስ በ70 ዓ.ም? የሚለው ጥያቄ ብዙዎችን ሊያወዛግብ ይችል ይሆናል፤ ፓሮውዥያ የግሪክ ቃል ሲሆን ቀላል ትርጉሙ መገኘት ወይም መምጣት ማለት ነው። በጥቅሉ ግን ለረጅም ጊዜ ቆይታ መምጣት ማለት ደግሞ ነው። ፓሮውዥያ አጭርና፣ የአንድ ጊዜ ብቻ የክርስቶስ መገለጥ የሚመስላቸው በርካቶች ናቸው፤ ይህ ግን የቃሉን መሰረታዊ አጠቃቀም ካለመረዳት የዳበረ ተለምዷዊ አመለካከት ነው። ብዙውን ጊዜ ሰዎች ስለ ፓሮውዥያ ሲያስቡ፣ የክርስቶስን በደመና ላይ ለአንድ ጊዜ አጭር መገለጥ መምጣቱን ያስባሉ፣ ይህ ግን ልክ አይደለም። ፓሮውዥያ አጭርና፣ የአንድ ጊዜ ብቻ የክርስቶስ መገለጥ ከሆነ፣ እንግዲያውስ ፓሮውዥያ የተሰኘው ቃል ይህን ክስተት ለመግለፅ የሚጠቀምበት እንግዳ የሆነ፣ ወይም ትክክለኛና ተገቢ ያልሆነ፣ ወይም ክስተቱን የማይመጥን ቃል ይሆናል። ፓሮውዥያ አንድ ድል አድራጊ ጄኔራል፣ ወይም ንጉሠ ነገሥት ወይም ከፍተኛ ባለሥልጣን ወደ አንዲት ከተማ መምጣቱን ለማመልከት የሚያገለግል ቃል ሲሆን፣ የመንግስቱ መቀመጫ ወደሆነችው ዋና ከተማው ከመመለሱ በፊት ለብዙ ጊዜ፣ ለብዙ ወራት ወይም ረዘም ላለ ዓመታትና ጊዜ የጉብኝት ቆይታ ማድረጉን የሚያሳይ ቃል ነው። ለምሳሌ፣ የኔሮ ቄሳር ፓሮውዥያ በግሪክ ግዛቱ ውስጥ ለብዙ አመታት ተራዝሞ ቆይቷል። ኔሮ በ66 ዓ.ም ላይ ግሪክ ደርሶ ወደ መንግስቱ መቀመጫ ወደ ታላቂቱ ሮም እስኪመለስ ድረስ ማለትም እስከ 67 ዓ.ም መጨረሻ ወይም በ68 ዓ.ም መጀመሪያ ድረስ ቆይታ አድርጓል። ስለዚህ ቃሉ በመሰረታዊ ትርጉሙና ጠቀሜታው ብዙ ጊዜ ሊመጣ ያለው ተመልሶ ከመሄዱ በፊት ያለውን እና የተራዘመ መገኘቱን ወይም ቆይታውን ያሳያል። የሆነ ሆኖ፣ ፓሮውዥያ በፊልጵስዩስ 2፥ 12 ላይ ጥቅም ላይ በዋለበት መንገድ እንደሚታየው፣ ይህ ቃል ከተለመደው የብዙዎች እሳቤ በተለየ ሁኔታ በአጠቃላይ መምጣትን እና ረጅም ቆይታን ወይም መገኘትን ያመለክታል። ስለዚህ የኢየሱስ ዳግመኛ ምጽአት ወይም ፓሮውዥያም እንዲሁ ረጅም የጉብኝት ቆይታ ወይም መገኘት ያለው መምጣት እንደሆነ ይመስላል። ስለዚህም ፓሮውዥያ ከያዘው መስረታዊ ትርጉም ተነስተን በ66 ዓ.ም እንደጀመረ እና በ70 ዓ.ም እስከሆነው የእየሩሳሌም ውድቀት ድረስ እንደተራዘመ ልናምን እንችላለን።
ለ1ኛ ተሰሎንቄ 4:፥ 16 ፍጻሜ በሚሰጥ መልኩ ይህ ሰማያዊ ሠራዊት በ66 ዓ.ም በሰማዩ ላይ ታይቷል፣ በዚያው ዓመትም የሙታን ትንሣኤ መጀመሪያ በሚመስል ሁኔታ ብዙ መንፈሳዊ አካላት ከምድር ሲነሱ ታይተዋል።
[በ66 ዓ.ም የአይሁድ ዓመፅ ሲጀምርና ሠራዊቱ በደመና ውስጥ ከታዩ ጥቂት ቀናት ወይም ሳምንታት በኋላ፣ ብዙ መንፈሳዊ አካላት ከምድር ወጥተው እንደነበር ካሲየስ ዲዮ እንዲህ ሲል ጽፏል፡- “የመጀመሪያዎቹ ሠራተኞች ምድሪቱን በነኩ ጊዜ ያኔ ደም ከእርስዋ ወጣ፣ ከባድ ጩኸት እና እሪታም ተሰማ፣ ብዙ መናፍስታዊ ምስሎችም ታዩ። ኔሮ ራሱ ምንጣፉን በመያዝ ከአፈሩ የተወሰነውን እየበተነና እየነሰነሰ የተቀሩት ሁሉ እርሱን እንዲመስሉ አስገደዳቸው። ሱኢቶኒየስ ይህንን ክስተት ሲዘግብ ኔሮ መሬቱን ሲሰብር ያኔ የመለከት ድምፅ ተሰምቷል። የሙታን መናፍስት በተነሱበት ወቅት መለከት መሰማቱ ደግሞ በ1 ቆሮንቶስ 15፥ 52 ላይ ላለው ቃል ግልጽ ፍጻሜ ይሰጠዋል:- “መለከት ይነፋልና፣ ሙታንም የማይበሰብሱ ሆነው ይነሣሉ፤….” በማለት ተናግሯልና። በራእይ 15፥ 8 ላይ እንደተገለጸው፣ እነዚህ የሙታን መንፈሶች ግን ሰባቱ መቅሰፍቶች እስኪፈጸሙ ድረስ ገና ህያዋን ሆነው ወደ ሰማይ አልገቡም ነበር። ይልቁን በአይሁድ ጦርነት መጀመሪያ ላይ የተነሡት እነዚህ መንፈሶች ግን ሰይጣን ሊደርስበት ወደማይችልበት ሥፍራ ለ1260 ቀናት ተወስደዋል፤ ይህም በ66 ዓ.ም በቲሽሪ ወር (መስከረም - ጥቅምት) ሮማውያን ለወረራ በመጡበት፣ የኔሮም ፓሮውዥያ በግሪክ በጀመረበትና ጀነራል ቲቶ በመጨረሻው መለከት በኢየሩሳሌም ላይ ጥቃት እስከጀመረበት እስከ 70 ዓ.ም ፋሲካ ድረስ ባለው ጊዜ መካከል ካለው የጊዜ ክፍተት ጋር ይዛመዳል ብዬ አምናለሁ።]
ይህንን የሱኢቶኒየስ ዘገባ ከሰማእታቱ ፊተኛ ትንሳኤ ፍጻሜ ጋር ባለው ተዛምዶ የምንመለከትበት ሌላ ጥናት እድሜ ከሰጠን በሌላ ጊዜ ይዤ እቀርባለሁ። ለአሁኑ ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያን ከታሪክ መዛግብት አንጻር በመጠኑ ለማሳየት የሞከርሁበትን ጥናት በዚሁ አበቃሁ