Thursday, July 20, 2023

ፕሪቴሪዝም፣ የተፈጸመው ሥነ-መለኮት: በታሪካዊ መዛግብት ከተረጋገጡ አንዳንድ ምልክቶችና ምስክሮች ጋር

ፕሪቴሪዝም፣ የተፈጸመው ሥነ-መለኮት
በታሪካዊ መዛግብት ከተረጋገጡ አንዳንድ ምልክቶች እና ምስክሮች ጋር

መግቢያ፦ ትንቢት ተፈጽሟል ብለን ለያዝነው አቋም ቀዳሚና ብቸኛው መሰረታችን የቅዱስ ቃሉ ትምህርት መሆኑ የልብ ስፋትና የአእምሮ ዝግጅት ባላቸው፣ በቅጡ ማሰብ በሚችሉም ሁሉ ዘንድ የታወቀ ነው። ለእምነት ቤተሰብ ቃሉ ብቻ ይበቃዋል ብለን እንጂ እንደ ደመና ከበውን ያሉ እርግጠኛ የታሪክ ምንጮችን ጠቅሰን ማስረዳትም ሆነ ለሚጠይቁን መልስ መስጠት አያስቸግረንም። በመሆኑም ሊመረመሩ ይገባቸዋል ብዬ የማስባቸውን አንዳንድ ታሪካዊ የመረጃ ምንጮችን ልጠቁማችሁ እወዳለሁ። እነዚህ የመረጃ ምንጮች ለብዙዎቻችሁ ምን ማለት እንደሆኑ አላውቅም፤ ዳሩ ግን መጽሐፍ ቅዱስ  “ይህ ትውልድ አያልፍም”፣ “ጌታ በደጅ ነው”፣ “ዘሙኑ አጭር ሆኖአል”፣ “ፈጥኖ”፣ "ቶሎ" ፣ “ሊሆን ያለ” ወዘተ." ሲል ለሚገልጣቸው ጊዜ ጠቋሚ ለሆኑ ንግግሮቹ ተገቢውን ዋጋ ሰጥተን ልናያቸው ይገባናል።
 
አስተውሉ፣ መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገርለት ሊመጣ ያለው ፍርድ ከጌታ ዳግመኛ ምጽአቱ (ፓሮውዥያው) ጋር የተቆራኘና፣ በከሃዲዋ እስራኤል ላይ ሊደርስ የቀረበ ፍርድ ነበር (ማቴ. 19፡28፤ ሉቃ. 21፡22-23፣ 32፤ ሉቃ. 22፡30)፤ ይኸውም ከ66-70 ዓ.ም ባለው ጊዜ በተካሄደው የአይሁድ-ሮም ጦርነት ወቅት፣ ለ42 ወራት (3 ዓመት ተኩል) የሚቆይ ማለት ነው። ይህንን በግልጽ የሚናገሩና ትንቢት ሁሉ ተፈጽሟል ብለን ለያዝነው አቋም በቀዳሚነት ዋቢ የምናደርጋቸውን የቅዱሳት መጻህፍት ምንባባት ከብዙ በጥቂቱ በሁሉት ምድብ በዚህ ጽሁፍ መጨረሻ ላይ በዝርዝር አስቀምጫለሁ። በዚህ ጽሁፍ ግን ዋናው ትኩረቴ በተለይ የፍላቪየስ ጆሳፈስን "Wars"  እና የኢውሳብየስን "Ecclesiastical History" መጻህፍት ሳገላብጥ፣ ድረ ገጾችንም አስሼ ያገኘሁአቸውን ሰነዶች ተመልክቼ፣ ምን ያህል ከቃሉ ትምህርት ጋር የሚስማሙ እንደሆነ ግንዛቤ ከያዝሁና፣ ሰነዶችን በመጠቀም ረገድ ልምዱ ያላቸውን የተመሰገኑ ምሁራን የጽሁፍ ስራዎች አማክሬ፣ ሰነዶቹ የያዙአቸውን ታሪካዊ ማስረጃ የሚሆኑ ክስተቶችን በመጠኑ ጠቆም  ጠቆም ማድረግ ነው። እኔን ግን በእጅጉ የሚገረመኝ ነገር ቢኖር ብዙ ክርስቲያኖች፣ ባስ ሲልም ምሁራኖቻችን ስለ እነዚህ ታሪካዊ ክስተቶች ምንም ሲሉ አለመሰማታቸው ነው። እስካሁን ባለኝ ምልከታ የተለያዩ የአገራችን "ሥነመለኮት አዋቂዎች" በትምህርታቸውም ሆነ በጽሁፎቻቸው እውቅና ሰጥተው ዋቢ ሲያደርጓቸውም ሆነ ሲተቹአቸው አልሰማሁም፣ አላየሁምም። ምናልባትም እነዚህ ሰነዶች ይኖሩ እንደሆነ ስለማወቃቸውም እጠራጠራለሁ።

የአዲስ ኪዳንን ታሪክና ስነመለኮት ለመመርመር ራሱን የሰጠ ማንም አማኝ ከነዚህ ታሪካዊ መዛግብትና ሰነዶች ጋር የሚፋጠጥበት ዕድል ከሌለው ስለ አዲስ ኪዳን የሚያውቀው በግርድፉ ነው ማለት ነው። ጌታ ቢፈቅድ በአዲስ ኪዳን ጥናት ውስጥ የሰነዶቹን ዋጋ የሚያስነብብ ጽሁፍ ሌላ ጊዜ አቀርባለሁ። እነዚህ ሰነዶች በጊዜው የተፈጸሙትን ክስተቶች የአይን ምስክር ሆነው በታሪክ ድርሳናቸው ከትበው ያስቀሩልንና የእነርሱን ምስክርነት ከቃሉ ትምህርት ጋር እያመሳከሩ የጻፉ የጥንት አባቶችና ምሁራን ስራ ስለሆኑ፣ ስለ ትንቢት ፍጻሜ ከቃሉ ምስክርነት ያለፈ ውጫዊ ማስረጃ ለሚፈልጉ አይነተኛ ግብዓት በመሆናቸው፣ በቀጥታ ወደ ማስረጃዎቹ ዝርዝር አልፋለሁ፦

1ኛ/ ጆሴፈስ (በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ የኖረ፣ ስለ አይሁዶች ታሪክ እና ስለ ሮማ ግዛት በሰፊው የጻፈ አይሁዳዊ የታሪክ ምሁር ነው። የጆሴፈስ ጽሑፎች በተለይ፣ በአዲስ ኪዳን ውስጥ ለተመዘገቡና በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ለተከሰቱት ክስተቶች እና አንዳንድ ሰዎች ጠቃሚ ምስክርነት ስለሚሰጡ ጠንካራ ግንኙነት አላቸው። በአዲስ ኪዳን ውስጥ የተጠቀሱ በርካታ ስብዕናዎች እና ቡድኖች በጆሴፈስ ውስጥም አሉ። የጆሴፈስ ጽሑፎች በአዲስ ኪዳን ውስጥ ለተገለጹ ክስተቶች ውጫዊ የሆነ ታሪካዊ አውድን በማቅርብ ረገድ ያላቸው ጠቀሜታ ከፍ ያለ ነው።  ስራዎቹ በጊዜው ስለነበሩ ማህበራዊ፣ ፖለቲካዊ እና ሃይማኖታዊ እውነታዎች ብርሃንን ይፈነጥቃሉ።  ስለዚህ፣ የጆሴፈስ ጽሑፎች አዲስ ኪዳንን ለሚማሩ የቃሉ ተማሪዎች ጠቃሚ የመረጃ ምንጭ ናቸው።) ከተነሳንበት ርዕሰ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ጆሴፈስ የአይሁድ ጦርነት በተሰኘው የታሪክ ድርሳኑ መጽሐፍ 6 ምዕራፍ 5 ክፍል 2 እና 3 ላይ ያሰፈረውን ዘገባ እንመልከት፦

War 6:286 (6.5.2.286) እንግዲህ፣ በዚያን ጊዜ የተነሱ እጅግ በጣም ብዙ ሐሰተኛ ነቢያት ነበሩ፤ እኑርሱም በሕዝቡ ላይ ቀንበርን እንዲጭኑ በወቅቱ ተነስተው በነበሩ አምባገነን ገዥዎች የሚታገዙ ነበሩ። ህዝቡንም መዳንን ከእግዚአብሔር ይጠባበቁ ዘንድ በውግዘትና በእርግማን ያስፈራሩአቹው ነበር (ልክ ቃል እንዳላወጣብህ እንደሚሉት እንደ ዘመናችን ሟርተኞች ማለት ነው )፤ እነዚህ ሟርተኛ ነብያት ይህንን  ያደርጉ የነበሩት ህዝቡ በከተማይቱና በሚኖሩባት ላይ ሊመጣ ካለው ጥፋት ሸሽተው እንዳያመልጡ  ለመከላከል ብቻ ሳይሆን፣ ከዚህም በላይ፣ ከእነዚያ እየመጡባቸው ካሉ፣ ከሚፈሩአቸው እና ከሚያስጨንቋቸው ጠላቶቻቸው  እንደሚታደጉአቸው እንዲህ ያሉ አሳሳች ተስፋዎችንም ይሰጡአቸው ነበር።

War 6:288 (6.5.3.288) ስለዚህ እነዚህ የተታለሉ ምስኪን ሰዎች፣ እነዚያ በግልጽ የሚታዩትን እና የወደፊቱን መጻኢ ጥፋት በግልጽ የሚተነብዩና የሚያመለክቱ ምልክቶችን አስተውለው ሳይከታተሉ ወይም ተገቢውን ዋጋ ሳይሰጡአቸው፣ ይልቁንም፣ በዓይኖቻቸው እንዳያዩ ታውረው፣ ወይም አእምሮ እንደሌላቸው ሁሉ፣ እግዚአብሔር በእነርሱ ላይ እያወረደባቸው ያለውን ያንን ሁሉ መዓት ከግምት ውስጥ ሳያስገቡ፣ የእነዚህ አታላዮች እና እራሱን እግዚአብሔርን የካዱ ነብያቶቻቸው ሰለባ ሆኑ።

War 6:289 (6.5.3.289) ስለዚህም በከተማይቱ ሰማይ ላይ ከፍ ብሎ የቆመና የተመዘዘ ሰይፍ የመሰለ ኮከብ እና አመቱን ሙሉ የቀጠለ የኮሜት አስፈሪ ትዕይንት ነበረ።
War 6:290 (6.5.3.290) እንዲሁም ደግሞ፣ ያ የአይሁድ ዓመፃ ከመቀስቀሱ በፊትና፣ ከጦርነቱ አስቀድሞ ከነበረው የህዝብ ቁጣና ግርግር በፊት፣ በዛንቲከስ [ኒሳን] ወር በስምንተኛው ቀን እና በዘጠነኛው ሰዓት ሕዝቡ እጅግ ብዙ ሆነው ወደ ቂጣ በዓል ወጥተው ነበር፣ ገና ሌሊትም ሳለ በቀን ጊዜ እንደሚያበራ ብሩህ እስኪመስል ድረስ ታላቅ ብርሃን በመሠዊያውና በቅዱሱ ቤት ዙሪያ አበራ፤  ይህም ብርሃን ለግማሽ ሰዓት ያህል በዚያ ቆይቶ ነበር።

War 6:291 (6.5.3.291) ይህ ብርሃን ለነዚያ በዚያ ተከማችተው ለነበሩ ላልተማሩ ሰዎች እንደ አንድ ጥሩ ምልክት ተደርጎ ይታይ ነበር፣  ቅዱሳት መጻህፍትን በሚመረምሩ በጸሐፍቱ ዘንድ ግን ወዲያውኑ በእነርሱ ላይ የተከሰቱትን የጥፋት ክስተቶች ለማስረዳት አስቀድሞ እንደተሰጠ የክፉ ነገር ምልክት ተደርጎ ተተርጉሞ ነበር።
War 6:296 (6.5.3.296) ከዚህም በተጨማሪ ከበዓሉ ከጥቂት ቀናት በኋላ አርጤምስዮስ (ጂያር) በተባለው ወር ከወሩም በሃያ አንደኛው ቀን  ይህ ምልክት በእነርሱ ላይ እየደረሰ ያለውን ጥፋት እንደሚያሳይ በይፋ ተናገሩ።
  
War 6:297 (6.5.3.297)  “አንድ አስደናቂ እና ሁሉንም ያስገረመ ክስተትም ታየ፤ ያንን ክስተት በአይኖቻቸው ያዩ ምስክሮች ባይናገሩት ኖሮ ታሪኩ ተረት ይመስላል ብዬ እኔ ራሴም ባልዘገብኩት ነበር።

War 6:298 (6.5.3.298) የታየውና ያንንም ተከትለው የተፈጸሙ ድርጊቶች እንደዚህ አይነት ምልክቶች የሚገባቸው አይነት ተፈጥሮ ያላቸው ክስተቶች ነበሩ። ፀሐይ ከመጥለቋ በፊት ሠረገሎችና በላያቸው ላይ ተቀምጠው የሚጋልቡ የታጠቁ የሰራዊት ጭፍሮችም በደመናው መካከል ወዲህና ወዲያ እየተሯሯጡ ከተማይቱን ሲከብቧት ታዩአቸው። 

War 6:299 (6.5.3.299) ከዚህም በላይ በዓለ ኀምሳ በተባለው በዚያ በዓል፣ ካህናት እንደ ልማዳቸው፣ ቅዱስ አገልግሎታቸውን ለመፈጸም በሌሊት ወደ ውስጠኛው [ወደ ቤተ መቅደሱ] ገብተው ሳለ፣ በመጀመርያ ለራሳቸው ብቻ የሚታወቅ መሸበርና ፍርሃት ይሰማቸው እንደነበሩ ሲገልጡ አስከትለውም  ታላቅ ድምፅን ሰሙ።

War 6:300 (6.5.3.300) ከዚህም በኋላ በታላቅ ድንጋጤም ውስጥ ሆነው እየተንቀጠቀጡ የሰሙት ታላቅ ድምፅ "ኑ ከዚህ በኋላ ለቅቀን ከዚህ እንሂድ” የሚል እንደ ብዙ ሕዝብ ያለ ድምፅ ነበር።

2ኛ/ ኢውሳብየስ (በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የኖረ ክርስቲያን የታሪክ ጽሐፊ እና የቂሳርያ ቢሾፕ ነበር።) "የቤተክርስቲያን ታሪክ" በተሰኘ ባለ አስር ጥርዝ ስራው፣ መጽሐፍ 3፣ ምዕራፍ 8፣ ክፍል 1-6 እንደተዘገበው የጆሴፈስን ትረካ ምንጭ አድርጎ በስድስተኛው የታሪክ መፅሃፉ ላይ ያሰፈረውን ዘገባ እንመልከት፣ ቃሉም እንደሚከተለው ነው፦

94 “በዚህም ጊዜ ምስኪኑ ሕዝብ በአስመሳዮችና በሐሰተኛ ነቢያት ተሸነፈ፤ 95 ነገር ግን ሊመጣ ስላለው ጥፋት ያለውን ራእይና ምልክት አልሰሙም፤ አላከበሩምም።  በተቃራኒው ግን፣ ልክ በመብረቅ እንደተመታ ሰው፣ ዓይንና ማስተዋል እንደሌላቸው ሆነው፣ የእግዚአብሔርን አዋጅ ናቁ።

በአንድ ወቅት የተመዘዘ ሰይፍ የሚመስል ኮከብ፣ በከተማይቱ ሰማይ ላይ ቆሞ ታየ፤ ዳግመኛም ከዐመፁ በፊትና ወደ ጦርነቱ ያመራውን ግርግር ከመጀመሩ በፊት አንድ ዓመት ሙሉ የፈጀ የኮሜት ትዕይንትም ታይቶ ነበር። ሕዝቡም ለቂጣ በዓል በተሰበሰበ ጊዜ፣ በ ዛንቲከስ ወር በስምንተኛው ቀን፣ ከሌሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ላይ፣ ታላቅ ብርሃን በራ።  በመሠዊያው በቤተ መቅደሱ ሁሉ ብሩህ ቀን የሆነ ይመስል ነበር፤  ይህም ለግማሽ ሰዓት ያህል ቀጠለ። አላዋቂዎች የሆኑ ይህንን እንደ ጥሩ ምልክት አድርገው ወስደውት ነበር፣ ነገር ግን በጊዜው የነበሩ የቅዱሳት ጸሐፍት ተርጓሚዎች ጉዳዩን የተረዱት ከዚያ ወቅት ብዙም ሳይቆይ የተከናወኑትን እነዚያን ከባባድ ክፉ ክስተቶች እንደሚያመለክቱ አድርገው ነው።

በዚያም በዓል አንዲት ላም ለመሥዋዕት ልትቀርብ በሊቀ ካህናቱ ተመርታ በቤተ መቅደሱ መካከል ሳለች ድንገት ጥጃዋን ወለደች።

ከናስም የተሰራው፣ በብረትም በተሠሩ ምሰሶዎች ላይ ያረፈው፣ በመሬት ውስጥም የተተከሉ መወርወሪያዎች የነበሩት፣ በመሸም ጊዜ በሃያ ሰዎች ጉልበት በጭንቅ ይዘጋ የነበረው የውስጠኛው ቤተ መቅደስ ምስራቃዊ በር፣ ገና ከሌሊቱ ስድስተኛ ሰአት ሲሆን ድንገት በራሱ ተበርግዶ ሲከፈት ታየ።

ከበዓሉም ብዙ ሳይቆይ በአርጤምስ ወር ከወሩም በሃያ አንደኛው ቀን ለማመን የሚያስቸግር አንድ አስደናቂ ራእይ ታየ።  ይህም ራእይ ራእዩን ካዩት ሰዎች ህይወት ጋር ካልተዛመደ እና  በኋላም ራእዩን ተከትለው የተከሰቱት ጥፋቶች በእንደዚህ አይነት ተጨባጭ ምልክቶች የታዩ ባይሆን ኖሮ ጉዳዩ ተረት ሊመስል ይችል ነበር።  ፀሐይ ከመጥለቋ በፊት ሰረገሎችና የታጠቁ ጭፍራዎች በአየሩ ላይ ሆነው በየአገሩ ሁሉ በደመና ሲሽከረከሩ ከተሞችንም ሲከብቡ ታይተዋልና።

በዓለ ኀምሳ ተብሎ በሚጠራው በዓልም ካህናቱ እንደ ልማዳቸው በሌሊት ወደ ቤተ መቅደስ ገብተው ሥርዓተ አምልኮውን እየፈጽሙ ሳሉ፣ በመጀመሪያ ላይ የሆነ እንቅስቃሴ የመሰለ መታወክና ታላቅ የጩኸት ድምጽ ሆነ፤ ከዚያም በኋላ "ኑ ከዚህ ለቀን እንሂድ" የሚል እንደ ብዙ ሕዝብ ያለ ድምፅ ተሰማ።

3ኛ/ ታሲተስ (ጆሴፈስ በኖረበት በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ የኖረ ሮማዊ  የታሪክ ምሁር እና ፖለቲከኛ ነበር።) Histories, Book 5:

ይህ ሕዝብ አጉል ለሆነ እምነት የተጋለጠ ነበር፣ ነገር ግን ደግሞ ሁሉንም ሃይማኖታዊ ሥርዓቶች የሚጠላ፣ ሕጋዊ እንደሆነ በማይቆጠር መባና የመሥዋዕት ማስተስረያን የሚለማመድ ነበር።  ያኔም በሰማይ ላይ ለጦርነት የሚንቀሳቀሱና እርስ በርሱ የሚቀላቀል የሰራዊት ጭፍራ፣ የእሳታማ ክንድ ብልጭታም ታይቷል፤ ቤተ መቅደሱም ከደመና ወጥቶ በመጣ ድንገተኛ ብርሃን ወጋገን ያበራ ነበር።  የመቅደሱ የውስጠኛው በሮችም በድንገት ተበርግደው ተከፈቱ፤ ከሟች ሲቃ ቃና በላይ የሆነ ድምፅ "አማልክት ለቅቀው እየሄዱ" ነው የሚል ታላቅ ጩኸት ተሰማ።  በዚያው ቅጽበትም  ተለይቶ እንደሚሄድ አይነት የብዙ ህዝብ ግርግር ሆነ።  ጥቂቶች በእነዚህ ክንውኖች ላይ አስፈሪ ትርጉም ሰጥተዋል፣ ዳሩ ግን በጥንታዊ የካህናቶቻቸው ትንቢታዊ መዛግብት ውስጥ ከምሥራቅ የሆነው ኃይል በዚህ ጊዜ እንዴት ኃያላን ሆነው እንደሚነሱ እና ገዥዎችም ከይሁዳ እንደሚመጡ፣ መላውን አለምም የሚገዛ ኢምፓየርም እንደሚነሳ ትንቢት ተጽፎ ነበር የሚል ጠንካራ እምነት ነበራቸው። 
 
4ኛ/ ሴፈር ዮሲፖን (በመካከለኛው ዘመን የተጻፈ የጥንቷ እስራኤል ታሪክ፣ ስራዎቹም የአይሁድ እምነትን እና የጥንቷን እስራኤልን ታሪክ ለሚመረምሩ ምሁራን ጠቃሚ የሆኑ መረጃዎች አሉት) ከዕብራይስጥ ቋንቋ በስቲቨን ቢ ቦውማን የተተረጎመ ሆኖ፤  ከምዕራፍ 87 “የመቅደሱ መቃጠል” ከሚለው ዘገባ ላይ የተወሰደ።

ቬስፓሲያን ከመምጣቱ አንድ ዓመት በፊት፣ ልክ እንደሚያበራ አንድ ታላቅ ኮከብ ከሰገባው የተመዘዘ ሰይፍ የሆነ ትዕይንት በቤተ መቅደሱ ላይ ታየ።  ምልክቱ በታየበት ጊዜ በነዚያ ቀናት የፋሲካ በዓል ነበር፤ በዚያም ሌሊት እንደ ቀኑ ብርሃን ሆኖ ሙሉ ቤተ መቅደሱ እንዳለ አበራ፣ቀኖቹም ሁሉም የፋሲካው በአል ሰባት ቀናት ነበሩ።  የኢየሩሳሌም ሊቃውንት ሁሉ ይህ ክፉ ምልክት እንደሆነ ያውቁ ነበር፣ ነገር ግን የቀሩት አላዋቂዎች ይህ መልካም ምልክት ነው አሉ።

. . . ከዚህም በኋላ ሌሊቱን ሙሉ የአንድ ሰው የፊቱ ገጽታ በቅድስተ ቅዱሳን ላይ ከላይ ሆኖ ታየ፤ በውበቱም የሚመስለውም በምድር ሁሉ ላይ እንደ እርሱ ያለ ከቶ አልታየም፣ መልኩም እጅግ የሚያስፈራ ነበረ።

ከዚህም በላይ በዚያን ጊዜ የእሳት ሰረገሎችና ፈረሰኞች፥ ታላቅ ሠራዊትም ሆነው ወደ ሰማይ እየበረሩ እንደገናም ወደ ምድር ሲመጡ ኢየሩሳሌምንና የይሁዳን ምድር ሁሉ ሲከብቡ፥ ሁሉም የእሳት ፈረሶችና የእሳት ፈረሰኞች ሆነው ሲመጡ ታዩ።  በዚያም ወራት፣ የሻቩት በዓል በደረሰ ጊዜ ካህናቱ በሌሊት በቤተ መቅደሱ ውስጥ የሚያስተጋባ የሰዎችን ድምፅ የሚመስል ነገር ሰሙ፤ ሕዝቡም ወደ ቤተ መቅደሱ የሚገቡ የብዙ ሰዎችን ድምፅ የሚመስል ነገር ሰሙ፤ የሚያስፈራና ታላቅ ድምፅም እየተናገረ፡ “ኑ፣ እንሂድና ከዚህ ቤት እንውጣ" ሲል ተሰማ።

5ኛ/ Pseudo-Hegesippus፣ (በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የኖረ ማንነቱ ያልታወቀ አይሁዳዊ ክርስቲያን ጸሐፊ ሲሆን፣ ስራውም በጆሴፈስ የተጻፈውን የአይሁድ ጦርነት የተሰኘ ስራ ከልሶ በ70 አ.ም ላይ ሮማውያን በኢየሩሳሌም ላይ ያደረሱትን ጥፋት ይዘረዝራል) ምዕራፍ 44። (ይህ በዋድ ብሎከር ከላቲን የተተረጎመ ሲሆን በቪንሴንቴ ኡሳኒ ከላቲኑ ትርጉም ተቀንጭቦ የተጠቀሰ ነው)፡-

የአይሁድ መጻሕፍት እንደ ገለጹት ከሆነ ከብዙ ቀን በኋላ ብዙዎች ያዩት እጅግ ታላቅ ​​የሆነ ምስል እና ምልክት ታየ፤ ፀሐይም ገና ሳትጠልቅ ሠረገላዎችና የጦር ሠራዊቶች በደመና ውስጥ ይታዩ ነበር፤ በዚያም የይሁዳ ሁሉ ከተሞችና ግዛቶቿ ሁሉ ተወርረው ነበር።  በዓለ ሃምሳ የተባለው በዓል በሚከበርበት ወቅት ካህናቱ ወደ ቤተ መቅደሱ ውስጠኛ ክፍል በሌሊት ሲገቡና የተለመደውን የዘወትሩን መስዋዕት ሲያቀርቡ መጀመሪያ ላይ የተወሰነ እንቅስቃሴ እና ድምፅ እንደተሰማቸው ራሳቸው አረጋግጠው መስክረዋል።  ድምጹም በድንገት "ከዚህ ተሻግረን እንሄዳለን" ብሎ ይጮኽ ነበር።

ሌላ ተጨማሪ ላካፍላችሁ፦

6ኛ/ “ቤት ኮል” እና የቤተ መቅደሱ ጥፋት በ70 ዓ.ም።
[ቤት ኮል፣ ቃሉ  የዕብራይስጥ ቃል ሲሆን ትርጉሙም "የድምፅ ሴት ልጅ" ወይም "የመለኮት ድምፅ አስተጋባች" እንደ ማለት ነው። እሱም የሚያመለክተው በአይሁድ ምሥጢራዊ ልምምድ እና በትውፊታቸው ውስጥ የሚንጸባረቀውን የመንፈሳዊ ግንኙነት ዓይነት ነው። ይህም ከሰማይ የመጣ ድምጽ በግለሰቦች የሚሰማበት ልምምድ ነው።  ዳሩ ግን በተፈጥሮው ሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር በቀጥታ ከሚገናኙበት የጸሎትና የአገልግሎት ልምምድ የተለየ ነው። ነገር ግን እንደ መለኮታዊ ተመስጦ ሊቆጠር የሚችል መንፈሳዊ ልምምድ ነው።  ቤት ኮል በነቢያት የተሰማውን እና በዕብራይስጥ መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የተመዘገበውን ሰማያዊ ድምጽ ሊያመለክትም ይችላል። በአይሁድ ሮም ጦርነት ወቅት ከደብረ ዘይት ተራራ ላይ በቀጥታ ለኢየሩሳሌም ከተማ ነዋሪዎች ይሰማ የነበረ ድምጽ ነው።]

ከክርስቶስ ልደት በፊት በ6ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የይሁዳ ክህደት በነበረበት ወቅት፣ ነቢዩ ሕዝቅኤል የክብር ደመናው ከቤተ መቅደሱ ወጥቶ ወደ ምሥራቅ ወደ ደብረ ዘይት ሲሄድ አይቶ ነበር (ሕዝ. 10÷ 18-19፤ 11፥ 22-23)።  በኋላም፣ ስለ አዲሲቱ እየሩሳሌም ባየው በራዕዩ፣ የክብር-ደመናው ወደ አዲሱ ቤተ መቅደስ፣ ወደ ቤተክርስቲያን ተመልሶ ሲመጣ ደግሞ አይቷል (ሕዝ. 43፥ 1-5)።  ይህም ራእይ የተፈጸመው ክርስቶስ በሥጋ የተገለጠው የእግዚአብሔር ክብር ከደብረ ዘይት ወደ አባቱ በደመና ሲያርግ (ሉቃስ 24፥ 50-51) እና  በ30 ዓ.ም አካባቢ በበዓለ አምሳ ቀን- ቤተክርስቲያኑን እንዲሞላ መንፈሱን በላከ ጊዜ ነው።

በኋላም የዚህ የእግዚአብሔር ክብር ሽግግር አምሳል በአይሁድ ታሪካዊ ጽሑፎች ውስጥ ሰፍሮ ይገኛል። በ66 ዓ.ም በበዓለ አምሳ ዕለት፣ በቤተ መቅደሱ ውስጥ ያሉ ካህናት ገና ተግባራቸውን እየተወጡ ሳሉ፣ “ከዚህ እንሄዳለን!” እያለ የሚጮኽ ትላቅ ድምፅና “የሃይለኛ ግርግርና ሁካታ” ተሰማ።

ይህ በ66 ዓ.ም. በበዓለ አምሳ ዕለት መለኮት ከቤተ መቅደሱ የመውጣቱ ሁኔታ፣ ልክ በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ ሁለት ላይ ተመዝግቦ በሚገኘው በመጀመሪያው የክርስቲያን ጴንጤቆስጤ ላይ መንፈስ ቅዱስ ለመጀመሪያ ጊዜ ለሐዋርያት እና ለሌሎች በኃይል በይፋ ከተሰጠ ከ36 ዓመታት በኋላ፣ አሁንም እንደገና ልክ በጰንጠቆስጤ ቀን፣ እግዚአብሔር ራሱ የኢየሩሳሌምን ቤተመቅደስ ትቶ እንደሄደ የተሰጠ ምስክርነት ነው። ይህ ማለት እግዚአብሔር ከተለየው በኋላ ቤተ መቅደሱ አሁን የተቀደሰ መቅደስ አይደለም፣ ሕንጻውም ከማንኛውም ዓለማዊ ሕንጻ የበለጠ የተቀደሰና የተለየ አይደለም ማለት ነው። መለኮት በይፋ አድሮበት የነበረውን ቤት በይፋ ተወው።

በሚያስደንቅ ሁኔታ በዚህ ጊዜ [በ66 ዓ.ም.] የእግዚአብሔር ሼክናህ ክብር ቤተ መቅደሱን ለቆ ወጥቶ በደብረ ዘይት ላይ ለ3 ዓመታ ከመንፈቅ እንደቆየ አይሁዶች ያንን እንደተገነዘቡት የአይሁድ ጽሑፎች ይገልጻሉ። በዚህ ወቅት አይሁድ ከሥራቸው ንስሐ እንዲገቡ የሚለምናቸው ድምፅ ከደብረ ዘይት አካባቢ ተሰምቷል (ሚድራሽ - ሰቆ. 2፡11)። ይህም በክርስትና ታሪክ ላይ አስገራሚ ተጽእኖ አለው፣ ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ እንደተሰቀለ እና እንደተነሳ ስለምናውቅ ነው፣ -  የአይሁድ መዛግብት እንደሚናገሩት ከሆነ የእግዚአብሔር ሼክናህ ክብር በ66 አ.ም ላይ በጰንጠቆስጤ ዕለት ከቤተ መቅደሱ ከወጣ በኋላ፣ ለ3 ዓመት ከመንፈቅ እንደቆየ ትክክለኛውን የጊዜ ክልል ያመለክታሉ። አይሁድም ያላቸው የማመሳከሪያ ሰነድ እንደሚያመለክተው፣ ሮማውያን በ70 ዓ.ም. በኢየሩሳሌም ላይ ከፈጸሙት የመጨረሻ ወረራ አስቀድሞ ከሼክናህ ክብር የተሰጠውን ይህን ማስጠንቀቂያ ("ቤት ኮል" ብለው የሰየሙትን የእግዚአብሔር ድምፅ) እርሱም ምድርን ትቶ ወደ ሰማይ እንደተመለሰ  አይሁድ አልሰሙም ይላል።
 
ከክርስቲያኖች መካከል ማንም ቢሆን፣ በ66 ዓ.ም ከሆነው የጰንጠቆስጤ ዕለት ጀምሮ ከቤተ መቅደሱ ጋር የተያያዙትን እነዚህን ግልጽ ተአምራዊ ምልክቶች አክብሮ የሚመለከት ሰው፣ ህንጻው በያዘው ውቅር ከአሁን በኋላ የእግዚአብሔር ቅዱስ መቅደስ እንደማይሆን ማመን ይችላል። ጆሴፈስም ራሱ እንኳ "መለኮት ከቅዱሳት ስፍራ ሸሽቶ" (Wars, 5.412) ከመውጣቱ የተነሳ፣ እግዚአብሔር “ከመቅደሱ ርቋል” ብለው የሚያምኑትን የብዙ ሰዎች እምነት ጠቅለል አድርጎ አቅርቦታል (Wars 2.539)።

7ኛ/ ከሌላ ተጨማሪ ምንጮች፦
እነዚህ ክንውኖች ያኔ በአይሁድ አእምሮ ውስጥ ከፍተኛውን ስፍራ ይዘው በነበሩበት ወቅት፣ ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ ሲጽፍ፣ "ሰባቱም ኋለኛዎች መቅሠፍቶች የሞሉባቸውን ሰባቱን ጽዋዎች ከያዙት ከሰባቱ መላእክት አንዱ መጥቶ፦ ወደዚህ ና፥ የበጉንም ሚስት ሙሽራይቱን አሳይሃለሁ ብሎ ተናገረኝ። በመንፈስም ወደ ታላቅና ወደ ረጅም ተራራ ወሰደኝ፥ የእግዚአብሔርም ክብር ያለባትን ቅድስቲቱን ከተማ ኢየሩሳሌምን ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አሳየኝ፤ ብርሃንዋም እጅግ እንደ ከበረ ድንጋይ እንደ ኢያሰጲድ ድንጋይ ሆኖ እንደ ብርሌ የጠራ ነበረ፤" (ራእይ 21፥ 9-11) በማለት፣ ያ የእግዚአብሔር ክብር የሆነው ሼክናህ፣ በእውነተኛይቱ ቅዱስ ቤተ መቅደስ ማለትም የክርስቶስ ሙሽራ በሆነችው የፍጻሜው ገነት በከተማይቱ ላይ ያረፈ መሆኑን ገልጿል።
 
የያህዌህ “ሼክናህ” በመሲሑ የሕይወት ዘመንና በሞቱም ጊዜ ሁሉ እና ከቤተ መቅደሱ ወጥቶ በደብረ ዘይት ላይ ሲወርድ እስከታየበት ጊዜ፣ ማለትም እስከ 66 ዓ.ም. ድረስ በቤተ መቅደሱ ውስጥ ቆይቷል።

በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ይኖሩ የነበሩ የጥንት ክርስቲያኖች ስለ ደብረ ዘይቱ ተራራ ከፍተኛ ፍላጎት ያሳደረባቸው ሌላም ምክንያት አለ። ይኸውም በቤተ መቅደሱ ቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ ይኖራል ተብሎ ይታመን የነበረው ሼክናህ የሆነው የእግዚአብሔር ክብር ወደ ደብረ ዘይት ተራራ ሄዶ በዚያ ስፍራ ላይ ሰፍፎ ሲያንዣብብ የነበረው በ70 ዓ.ም በተጠናቀቀው የሮም/አይሁድ ጦርነት ወቅት ነው። ሼክናህ የሆነው የእግዚአብሔር ክብር ያንን አሮጌውን ቤተመቅደስ ትቶ ወደ ደብረ ዘይት ተራራ ከፍታ ላይ መውጣቱ [የቤተክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊና ምሁር ለነበረው፣ ከ260-340 ዓ.ም ለኖረው] ለኤውሳቢየስ በጣም አስፈላጊና ትልቅ ክስተት ነበር። (ኧርነስት ኤል. ማርቲን "የጎልጎታ ሚስጥሮች"፣ ሲል  በአልሃምብራ፡ ካሊፎርኒያ በ1988፡ ያሳተመውን መጽሐፍ   ገጽ 83 ላይ ይመልከቱ)

8ኛ/ ኤውሳቢየስ "Proof of the Gospel" በተሰኘው መጽሐፉ ውስጥ ይህንን ምንባብ እናገኛለን
በክርስቶስ ያመኑ ሁሉ ከዓለም ዳርቻ ይሰበሰባሉ፣ ይኸውም እንደ ቀድሞው ዘመን ስለ ኢየሩሳሌም ክብር ወይም በኢየሩሳሌም ከተማ በታነጸው በጥንቱ ቤተ መቅደስ ሊሰግዱ ሳይሆን ይልቁንም... የእግዚአብሔር ክብር [የያህዌ የሼኪናህ ክብር] ከቀደመችው ከተማ ወጥቶ ወደፈለሰበት ከከተማይቱ አንጻር በምትገኘው በደብረ ዘይት ተራራ ይሰግዱ ዘንድ ነው። (Book VI, Chapter 18 (288))

እንደ ኤውሳቢየስ አባባል “ሼክናህ” የሆነው ክብር ከቤተ መቅደሱ ወጥቶ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሰፍፎ ያንዣበበው “ኢየሩሳሌም ስትከበብ” (ከ66 እስከ 70 ዓ.ም.) ነው።  ሆኖም፣ “ሼክናህ” የሆነው ክብር መቅደሱ በጦርነቱ ማብቂያ ከመፍረሱ በፊት ቤተ መቅደሱን ለቆ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሰፍፎ እንዳንዣበበ የጠቀሰው ኤውሳቢየስ ብቻ አልነበረም።  የኢየሩሳሌም ጥፋት የዓይን ምስክር የነበረው ዮናታን የሚባል አይሁዳዊ መምህርም (ራባይ)  -- "ሼክናህ" ክብር ለሦስት ዓመታት ተኩል ቤተ መቅደሱን ለቅቆ ነበር ብሏል።

እስራኤል ንስሐ እንዲገቡ ተስፋ በማድረግ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ አደረ፣ እነርሱ ግን እምቢ አሉ፤
"እናንተ ከዳተኞች ልጆች ተመለሱ" [ኤር.  3፥ 14]፤  "ወደ እኔ ተመለሱ እኔም ወደ እናንተ እመለሳለሁ" (ሚል.  3፥ 7) እያለ፣ ቤት ኮል ሲሉ የሚጠሩት ያ ልዕለ ተፈጥሯዊ የሆነ ድምፅ] ከሰማይ መጣ፤ ያኔም "ንስሐም ባልገቡ ጊዜ፡— ወደ ስፍራዬ እመለሳለሁ" (ሆሴዕ 5፥ 15)፣ አለ። (Midrash Rabbah, Commentary on Lamentations 2:11). -- Secrets of Golgotha, by Ernest L. Martin. 84.

ከሮማውያን ጋር ጦርነቱ ከመጀመሩ አስቀድሞ በኢየሩሳሌም ከሚገኘው ቤተ መቅደሱ በመውጣት ተለይቶ የሄደውን “ሼክናህ” የተሰኘው የያህዌን ሃልዎት እውነታ የጻፈ ሌላም ጸሐፊ ነበር።  ጆሴፈስ በ66 ዓ.ም የጸደይ ወቅት በቤተመቅደስ ውስጥ አንዳንድ አስገራሚ ክስተቶች እንደተከሰቱ በዘገባው ጠቅሷል። ሲጽፍም ከያህዌህ “ሼክናህ” እና ከቤተ መቅደሱ ጋር የተያያዙ ሦስት ተአምራትን ዘግቧል -- በእያንዳንዱም  ዘገባው "ሼክናህ" ከቅድስተ ቅዱሳኑ ወጥቶ እየተለየ እንደነበር በግልፅ አሳይቷል።

War 6. 290 እንደሰፈረው፣ በ66 ዓ.ም. ከፋሲካ በዓል በፊት አንድ ሳምንት ቀደም ብሎ “ ከጠዋቱ 3 ሰዓት ጀምሮ ለሰላሳ ደቂቃ ያህል የቆየ ታላቅ ብርሃን በመሠዊያው ላይ አበራ፣ አስከትሎም ከዚያ ወጥቶ ሄደ። ሲናገርም፣ "የአይሁድ ቅዱሳን ጸሐፍት ይህንን ምልክት አስመልክቶ ሲናገሩ ለቤተ መቅደሱ መጻኢ እድል መጥፎ ምልክት አድርገው ተርጉመውታል" ብሏል። ልክ በምድረ በዳ ሳሉ የማደርያውን ድንኳኑን ነቅለው ወደ ሌላ ቦታ ሲያጓጉዙ እንደነበረው  ሼክናህ የሆነው ክብርም ከማደሪያው ርቆ ሲሄድ ነበር ።

ጆሴፈስ በመቀጠል እንዲህ ብሏል “ከጥቂት ቀናት በኋላ ደግሞ (በፋሲካ በአል ወቅት) ሃያ ሰዎች ሆነው በጉልበ የሚከፍቱትና የሚዘጉት ግዙፍ የኒካኖር የናስ በሮች ገና መንፈቀ ሌሊት ሳለ በራሳቸው ፈቃድ ተበርግደው ተከፈቱ። (War 6. 293-295)። ይህም ክስተት ደግሞ በቤተ መቅደሱ ላይ የሚመጣውን ጥፋት እንደሚያሳይ ተተርጉሟል። ከዚያም፣ ከሃምሳ ቀናት በኋላ ቆየት ብሎ፣ በበዓሉ አምሳ  ዕለት፣ ሌሎቹ ምልክቶች እንደሚያሳዩት የሼክናህ ክብር ቤተ መቅደሱን እየለቀቀ መሆኑን የሚያሳይ የመጨረሻው ምልክት ተሰጠ።

ከዚህም በላይ በዓለ ሃምሳ እየተባለ በሚጠራው በዓል ካህናት አገልግሎታቸውን ለመፈጸም እንደ ልማዳቸው ወደ ቤተ መቅደሱ ውስጠኛው አደባባይ ሲገቡ፣ ያኔ በመሸ ጊዜ፣ ግርግርና ጩኸት መኖሩን በመጀመሪያ እንዳወቁና ከዚያም በኋላ  "ኑ፣ ከዚህ እንሄዳለን" ሲል የብዙ ሕዝብ ድምፅ የሚመስል እንደሰሙ ዘግቧል (War 6. 299)።

የጆሴፈስን መረጃ ሌላው የዓይን ምስክር የነበረው ራባይ ዮናታን ነው፤ የዚህ ሰው ምስክርነት በጥንቷ እስራኤል ስለተፈጸሙ ክንውኖች የበለጠና የተሟላ ግንዛቤን ይሰጣል። የጆሴፈስን መረጃ ከዚህ ሰው ምስክርነት ጋር አጣምረን ስንመለከተው ከፀደይ ወራት 66 ዓ.ም እስከ ታኅሣሥ 69 ዓ.ም አካባቢ፣ ቤተ መቅደሱ በሮማውያን ከመፍረሱ ከስምንት ወራት በፊት ለሦስት አመት ተኩል "ሼክናህ" የሆነው ክብር በቀጥታ ወደ ደብረ ዘይት ሄዶ ከተራራው ጫፍ ላይ  - እንደቆየ፣ ከዚያም ወደ ሰማይ ተመልሶ እንደሄደና ይህ የራባይ ዮናታን ምክርነት እስከ ተጻፈበት ጊዜ ድረስም ወደ ምድር እንዳልተመለሰ እናያለን። 

¶ የዳግመኛ ምጽአቱ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ምስክሮች፦ 
የሰው ልጅ (ኢየሱስ) አስቀድሞ እርሱና ሐዋርያቱ እንደተነበዩት የሰጠውን የተስፋ ቃል ጠብቆ ከቅዱሳን መላእክቱ ጋር ያኔ በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ላይ በክብር መጥቷል፡- ማቴ  13፥ 41-43፤ 16፥ 27-28፤  24፥ 29-31፤  25፥ 31፤ ማርቆስ 8፥ 38፤ 9፥ 1፤ 13፥ 26-27፤ ሉቃስ 9፥ 26-27፤  1 ተሰ 4፥ 13-18፤ 2 ተሰ 1፥ 4-10፤ ይሁዳ 14-15

¶ እነዚህ ሁሉ ነገሮችም የሚጠበቁትና የሚፈጸሙት ደግሞ ራሱ ኢየሱስ በነበረበትና በሐዋርያቱ ትውልድ ውስጥ እንደነበር አዲስ ኪዳን በግልጽ ያስተምራል፦ ማቴ  11፥ 16፤ 12፥ 38፣ 41-45፤ 16፥ 4፤ 23፥ 36፤  24፥ 34፤  ማርቆስ 8፥ 38፤  9፥ 1፤ 13፥ 30፤ ሉቃስ 7፥ 31፤ 11፥ 29-32፣ 50-51፤ 17፥ 25፤ 21፥ 32፤ የሐዋርያት ሥራ 2፥ 40፤  ፊል  2፥ 15፤  ዕብ 3፥ 9-11።

ጥቂት መጻሕፍት ልጠቁማችሁ፦

- The New Complete Works Of Josephus, Translated by William Whiston.
_ Eusaebius, The History of the Church 
 - Mason, Steve. Josephus and the New Testament
- Stevens, Edward E. Final Decade Before the End. Jewish and Christian History Just Before the Jewish Revolt.
- Barrett, C.K. The New Testament Background: Selected Documents.
- Bruce, F.F. Israel and the Nation.
- Bruce, F.F. New Testament History.
- Gentry, Kenneth L., Jr. Before Jerusalem. Fell.



 

Friday, June 30, 2023

የብልጥግናና የጤንነት "ወንጌል"

የጥፋት ወንጌል

"ስለዚህም በመገለጥ ታላቅነት እንዳልታበይ የሥጋዬ መውጊያ፥ እርሱም የሚጎስመኝ የሰይጣን መልእክተኛ ተሰጠኝ፤ ይኸውም እንዳልታበይ ነው። ስለዚህ ነገር ከእኔ እንዲለይ ሦስት ጊዜ ጌታን ለመንሁ።  እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ። ስለዚህ ስለ ክርስቶስ በድካም በመንገላታትም በችግርም በስደትም በጭንቀትም ደስ ይለኛል፤ ስደክም ያን ጊዜ ኃይለኛ ነኝና።" 2 ቆሮ 12፥ 7-10

፩.

እንደ መነሻ የጠቀስኩትን ይህንን የንባብ ክፍል ኋላ ላይ እመለስበታለሁ። ልንሰማው በሚያስፈልገን የመዳን ወንጌል ጤናማ ቃልና እኛ ልንሰማው በምንፈልገው "ጥሩ ዜና" መካከል ልዩነት አለ። እንደሚታወቀው ሰዎች የሆንን ሁሉ ልንሰማው የሚያስፈልገን መልካሙ የምስራች አንድ ነው። ነገር ግን በዚህ አለም ብዙ አይነት ጥሩ ዜናዎች ሊኖሩ ይችላሉ። እስቲ ሰው ሁሉ ሊሰማው የምፈልገውን ጥሩ ዜና ላሰማችሁ።  ምናልባትም ይህ አንዳንዶቻችሁ ሰምታችሁት የማታውቁት፣ ብዙዎቻችሁ ግን አሁንም ድረስ እንደ እግዚአብሔር መልዕክት የምትቆጥሩት ስሜት ኮርኳሪ ምርጥ ዜና ሊሆንላችሁ ይችላል።  ልትሰሙት ዝግጁ ናችሁ?

 "እነሆ እግዚአብሔር ሁላችሁም ጤናማ እንድትሆኑ፣ በሽታም እንዳያገኛችሁ፣ ሀብታም እንድትሆኑ፣ ድህነትም እንዲርቃችሁ፣ ከሥቃይ ነፃ እንድትሆኑ እና በምትሠሩት ሁሉ እንድትበለጽጉና በብዙ እንድትከናወኑ ፈቃዱ ነው፤" የሚል ዜና ነው። ይህ ታዲያ ጥሩ ዜና ነው ወይስ መጥፎ? ይህ እኛ መስማት እጅጉን ደስ የሚለን ዜና ነው፣ አይደል? ይህ ታዲያ ምን ክፋት አለው?  እንዲህ ያለው ዜና የያዘውን መልእክት መስማት አትወዱምን? በርግጥም ትወድዳላችሁ እንጂ ለምን አትወዱም?  እግዚአብሔር ሁላችሁም ጤናማ እንድትሆኑ፣ ሀብታም እንድትሆኑ፣ ከሥቃይ ነፃ እንድትሆኑ እና በምትሠሩት ሁሉ እንድትበለጽጉ የሚፈልግ መሆኑ መልእክቱ አሪፍ ዜና ካልሆነ ታዲያ ምን ሊሆን ይችላል?

የዚህ መልእክት ብቸኛው ችግር ግን እውነት አለመሆኑ ነው። እውነት ደግሞ መስማት ደስ ከሚለንና ከምንፈልገው ነገር በላይ ዋና አስፈላጊ ነው። አዎን፣ በተለይም ይህ ስለ እግዚአብሔር እና ስለ መጽሐፍ ቅዱስ እውነቱን ስንናገር የሚሰራ ነው።

እስቲ ልጠይቃችሁ፣ ስለ ጤንነት/ብልጥግና ወንጌል ምን ይሰማችኋል?  እንዲህ ላለው ጉዳይ ግድ የለሾች ናችሁን?  እሱንስ ሳይጎረብጣችሁ ታግሶ ለመስማት አቅም አላችሁን? ሲሰሙት ለጆሮ የሚጥም ከመሰለ፣ ቃሉን እያጣመመ ከሚሰራ እንዲህ ካለ ትምህርት ጋር በጽኑ ካልተጣላችሁ፣ እንዲህ ያለው ትምህርት በንዴት ካላቃጠላችሁ፣ ከሁለት ነገሮች አንዱ በህይወታችሁ እውነት ነው ማለት ነው፦ 1ኛ. የብልጽግና ወንጌል የሚያስተምረው ግልሙትና ምን እንደሆነ አልገባችሁም ወይም ጨርሶ አታውቁትም ማለት ነው፤ አልያም 2ኛ. ወንጌል ራሱ ከመሰረቱ አልገባችሁም። ወንድሜ ሆይ፣ ወንጌልን በአግባቡ ተረድተኸው ከሆነ ያኔ ሕያው ሆነህ የጤንነት/ብልጥግና ወንጌል አስተማሪዎች የሚሰብኩትን አደጋ በንቃት ታውቃለህ፤ ራስህንም ሆነ በአጠግብህ ያለውን ክርስቲያን ከአደጋው ለመጠበቅም ትተጋለህ። ካልሆነ ግን ሞት በመሰለ ከባድ እንቅልፍ ተይዘሃል፣ ሳትቀበር በፊት ፈጥነህ መንቃት አለብህ። ዝም ብለን ተጎልተን አገሩን የሞላው የሀሰት ወንጌል ህዝባችንን እየጠራረገው ነው። "ሰይፍ ከዋጠው ሕዝብ ሁሉ ይልቅ ዱር ብዙ ዋጠ" (2ሳሙኤል 18፥ 8) እንደተባለ ኮምኒዝምና መከራው ካደረሰው ጥፋት በላይ የነጻነቱ ዘመን የትምህርት አሰስ ገሰስ ብዙዎችን ውጧል።

እኔ እንደማስበው ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን የተናገረው ቃል ዛሬ እኛን የሚመለከት ይመስለኛል፡-

"ይሁን እንጂ፥ መጥቼ ባያችሁ ወይም ብርቅ፥ በአንድ ልብ ስለ ወንጌል ሃይማኖት አብራችሁ እየተጋደላችሁ፥ በአንድ መንፈስ እንድትቆሙ ስለ ኑሮአችሁ እሰማ ዘንድ፥ ለክርስቶስ ወንጌል እንደሚገባ ኑሩ።" (ፊልጵስዩስ 1፥ 27)

ጳውሎስ ለእነዚህ አማኞች "ጸንታችሁ ቁሙ" የሚል ምክር ይሰጣቸዋል። ይህም ስቴኮ (Steko) ከሚለው የግሪክ ቃል የተተረጎመ ነው።  ይህ ቃል የሚልቴሪ ሳይንስ ሙያዊ ቃል ሲሆን፣ ትርጉሙም "በጦርነት ውስጥ ያለመናወጥ መቆም፣ መረጋጋት" ማለት ነው። የገጠመው ጦርነት የቱንም ያህል ቢከፋ ስፍራውን ለማይለቅና ከቦታው የማይነቃነቅ ወታደርን ለመግለጥ ጥቅም ላይ ይውላል።

ጳውሎስ በተሰጣቸው የወንጌል ባላደራነታቸው፣ ከስህተት ወይም ከኃጢአት ጋር ባላቸውም ተጋድሎ ጸንተው እንዲቆዩ፣ በትምህርታቸውም ሆነ በምግባራቸው ሳይነቃነቁ እንዲቆሙ እየነገራቸው ነው። ይህ ወታደራዊ የሆነ ያነጋገር ዘይቤ በከፍተኛ ጥቃት ውስጥ እያሉ ቢሆን እንኳ ገዢ ቦታን ሳይለቁ ገትሮ ከመያዝና ወጥሮ ከመዋጋት ጋር የተያያዘ ነው። “ጸንታችሁ ቁሙ” ሲልም በአእምሮው ውስጥ በአስተምህሮ እና በሥነ ምግባራዊ ጉዳዮች ላይ  የማመቻመች ፈተናን የመቃወም ነገር አለው። 

ጳውሎስ “ለወንጌል እምነት አብራችሁ ተጋደሉ” በማለት ይነግራቸዋል። “በአንድነት መጋደል” የሚለው የግሪክ ቃል "ሱናትሊዮ" (sunathleo) ከሚለው ሁለት ቃል የተገኘ ሲሆን፣ እሱም sun “በጋራ” እና athleo "ውድድርን ወይም ፉክክርን መሳተፍ" ማለት ነው። አትሌቲክስ የተሰኘው ስፓርታዊ ውድድርም ስያሜውን ያገኘውን ከዚሁ የግሪክ ቃል ነው።

ይህ ተጋድሎ በጦር ግንባር እና በጨዋታ ሜዳ ላይ እንደሚደረግ የሕይወትና የሞት ሽረት ትግል እንዳለበት የግላዲያተር ፍልሚያ ከውድድርና ከፉክክር ጋር የተያያዘ ነው።  ይህም አብሮ መጋደል በቡድን ተጣምሮ ለማሸነፍ ጥረትን ሁሉ የማሳየት  ጥሪ ነው። በወንጌል የመጋደልን ጥሪ እና አደራ ያላወቀ አማኝ የወንጌልን እውነት እያመቻመቸ ለአለም የሚመች ማህበረረባዊ ወንጌል (social gospel) አቀንቃኝ ይሆናል። እኛ የወንጌል አማኞች ግን፣ “በአንድ መንፈስ ጸንተን በአንድ ልብ ለወንጌል እምነት አብረን የምንጋደል” መሆን አለብን። በዛሬው ዘመን ክርስትና ግን የወንጌል መልእክት ምንነት ግልጽ አይደለም፣ ማንኛውም ሰው ወንጌል ምን እንደሆነ የብልጭታን ያህል ፍንጭ ቢኖረው በጤንነት/ብልጥግና ወንጌል ላይ አሰላለፉን ባስተካከለ ነበር።

ወንጌል እግዚአብሔር በልጁ ሞት በኩል ለኃጢአተኛው ሰው ቤዛ ሆኖ እንዳቀረበ የሚታወጅ የምስራች ነው።  ይህ ቤዛነት ለሚያምኑ ሁሉ በጸጋ ይታደላል።  በክርስቶስ ላይ የሚያርፈው እምነት በአእምሮው፣ በአካሉና በመንፈሱ የተበላሸውን ኃጢአተኛ ወስዶ ከኃጢአቱ ሁሉ ያነጻዋል፣ በእግዚአብሔርም ፊት ጻድቅ ያደርገዋል፣ የዘላለምንም ሕይወት ይሰጠዋል።  ያ ነው እንግዲህ መልካም ዜና ነው የምንለው።

፪.

ክርስቶስ የኃጢያት እዳዬን እንደከፈለልኝ አምናለሁ ከዚህ የተነሳ ኑሮዬና ደረጃዬ ፍጹም ተለውጦ ከችግር ሁሉ ተላቅቄ ሁሉ መልካም ይሆናል ብሎ ማሰብ ግን ፈጽሞ አይሰራም፤ እስቲ አሁን የምኞትና የቅዠት ጥግ ካልሆነ በቀር የኃጢአት ዕዳ ክፍያና የኑሮ ደረጃ ለውጥ ምን ያገናኛቸዋል? እንዲህ ያለው እብደት ፈጽሞ የክርስቶስ ወንጌል አይደለም። በክርስቶስ የሙስቀል ሞት የተገኘው የኃጢአት ዕዳ ክፍያ ከዘላለም ኩነኔ መዳኛ እንጂ ከችግር ነጻ ሆኖ የመኖር ዋስትና አይደለም። አሁንም የእለት ጉርስ ማጣት፣ የመኖሪያ ቤት እጦት፣ ያለቀ ጫማና የተቀደደ እራፊ፣ የተኛ የመኪና ጎማ፣ የተሰበረ አጥንት፣ የታመመ አካል ሊኖረኝ፣ የትዳር ጭቅጭቅ፣ የገንዘብ እጥረት ትግል ሊኖርብኝ ይችላል፤  እውነታው ደግሞ ይኸው ነው። የአገር ቀበኞች የደኃውን ገንዘብ ከመመዝበር እጆቻቸውን ካልሰበሰቡና በላብ  ሰርቶ በኢኮኖሚ ከመለወጥ ውጪ ህይወት እንደሁ ሁልጊዜ ትግል ናት! 

ነገር ግን የጤንነት/ብልጥግና ወንጌል አቀንቃኞች ደረጃው እየጨመረ በሚያድግ እምነት እግዚአብሔር በከፍተኛ ጤና እና ሀብት አትረፍርፎ እንደሚከፍል ደፍረው ያስተምራሉ።  ሲናገሩም እግዚአብሔር የዘላለም ሕይወትን ብቻ ሳይሆን ብራንድ ሀብታም እና ህመም የማያውቀው ፍጹም ጤናማ እንድትሆኑ፣ እንዲሁም ከየትኛውም ስቃይና መከራ ነፃ እንድትሆኑ፣ ከችግር ተላቃችሁም እንድትኖሩ ይፈልጋል ሲሉ በአዎንታዊ ማነቃቂያ እያባበሉ ያስተምራሉ። 

እንዲህ ያለ ከመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ያፈነገጠ ነገር "ወንጌል አማኝ" ነን በሚሉት ዘንድ እንዴት ሊታሰብ ቻለ?  እንዴትስ ስር ሰዶ በመሰራጨት "ወንጌላውያን አማኞችን" ከክርስቶስ ወንጌል ሊያርቃቸው ቻለ? በእውነቱ ይህ ጥሩ ጥያቄ ነው። ይህንን ለማስተዋል እንዲቻለን በአገራችን እንደ ጉድ የፉሉትን አነስተኛና ጥቃቅን እባብ የብልጥግና ሰባኪዎች ላይ ጊዜ ከምናጠፋ ዘንዶ እና አናኮንዳ የሆኑ አባቶቻቸውን፣ ትምህርቶቻቸውንና ልምምዶቻቸውን ነቅሰን እያወጣን ስለ ብልጽግና ወንጌል ታሪካዊ ዳራ ጥቂት ነገር ለማለት እንሞክራለን። ከምዕራባውያን የቴሌቪዥን ሰባኪዎች በተቀዳ ትምህርትና በተኮረጀ ስታይል የሚያቅራሩብንን የአገራችንን የብልጥግናና የስኬት እርኩስ ወንጌል ሰባክያንን ተውት አድርገን ምንጫቸውን እንመርምር።

እንደ ቅደም ተከተላቸው የመጀመሪያዎቹ የአዎንታዊ አስተሳሰብ አራማጆች፣ ፊኒያስ ፒ. ኩዊቢ እና ሜሪ ቤከር ኤዲ፣ የመሰሉ የአዲስ አስተሳሰብ እንቅስቃሴን እና የክርስቲያን ሳይንስ መንፈሳዊ አስተሳሰብ መስራቾች ቀደምት ፈጣሪዎች ነበሩ።  በ20ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መባቻ ላይ የቤቴል መጽሐፍ ቅዱስ ተቋም መሥራች እና መጋቢ ኤሴክ ዊልያም ኬንዮን ስለ ክርስቶስ የተጠናቀቀ ሥራ በሚሰብክበት ጊዜም ተመሳሳይ የሆኑ የአዎንታዊ ሐሳቦችን አካትቶ ያስተምር ነበር።  ኬንዮን ክርስቲያኖች ስሜታዊ እና አካላዊ የሆኑ ፍላጎቶቻቸውን ለማሟላት “አዎንታዊ ኑዛዜ” (positive confession) ሊያደርጉ እንደሚችሉ ጽፏል። ሲናገርም "እኔ የተናዘዝኩትን (ያልኩትን) ነኝ/አለኝም" ይል ነበር።

በ1930ዎቹ ኬኔት ሀገን የቃል-እምነት እንቅስቃሴን ሲጀምር የኬንዮንን ትምህርት እንዳለ በመቅዳት ከጴንጤቆስጤ እምነትና አስተምህሮ ጋር ቀይጦ ማስተማርን ጀመረ።  የእግዚአብሄር ማኅበረ ቅዱሳን የተባለ ቤ/ክ መጋቢ የነበረው ይህ ኬኔት ሀገን ክርስቲያኖች በቂ እምነት በማሰባሰብ ሀብታም መሆን እንደሚችሉ ሲያስተምር ይደመጣል።  "በእምነት በለው፣ አድርገው፣ ተቀበለው፣ አውራው" የሚሉ የቃል እምነት መርሆዎችን ፈብርኮ ክርስቲያኖችን በቅዠት አለም ያሰክራችው ነበር።  በእምነት የሚነገሩ ቃላቶች መሟላት እንዳለባቸው የሚገልጽ “ጥራው" እና "በይገባኛል ውረሰው” የሚሉ መፈክሮችን ያስከተለውን “የሬማ አስተምህሮ” አስፋፍቷል።  ይህን ተከትሎ በ1960ዎቹ የኦራል ሮበርትስ ወጣት ተባባሪ ኬኔት ኮፕላንድ እምነት “ኃይል” እንደሆነ ማስተማር ጀመረ፤ እሱም ጮክ ባለ ድምጸት በይሆናል አይነት ስሜት ሲናዘዝ (ሲመሰከር) የተጠበቀውን ቁሳዊ ውጤት ያመጣል፣ ይል ነበር። በሁለት አስርት አመታት ውስጥ፣ ይህ Word-Faith ልክ እንደ ካንሰር ሆኖ ወደ ትልቅ የካሪዝማቲክ እምነት ዘር አድጓል።

የእነዚህን ሰዎች አስተምህሮ እንደሚከተለው ማጠቃለል ይቻላል፡- እግዚአብሔር ሰውን የፈጠረው እንደ ሉዓላዊ ፍጡራን “የእግዚአብሔር ዓይነት እምነት”ን በመጠቀም ነገሮችን በመጥራት ወደ መኖር እንዲያመጣቸው፣ በብልጽግናና በስኬት የመኖር ችሎታ ያለው አድርጎ “በእግዚአብሔር ደረጃ” (ወይንም እንደ “ትናንሽ አማልክት”) እንዲሆን ነው። ነገር ግን በገነት ውስጥ በእግዚአብሔር ላይ በማመፅ እና የሰይጣንን ተፈጥሮ በመያዝ ይህንን እድል አጥተናል። ይህንን ሁኔታ ለማስተካከል፣ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆነና፣ በመንፈስ ሞተ (በዚያም የሰይጣንን ባሕርይ ለብሶ/ ሰይጥኖ)፣ ወደ ሲኦል ወረደ፣ “በሲኦልም ዳግመኛ ተወለደ”፣ እንደገናም በእግዚአብሔር ባሕርይ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፣ ከዚያም መንፈስ ቅዱስን ላከ።  በዚህም ትስጉዑቱን በአማኞች ውስጥ ሊያባዛ ይችላል፣ ከዚህም የተነሳ አማኞች እንደ እርሱ ትናንሽ አማልክት የመሆን ጥሪያቸውን ይፈጽማሉ። አሁን የተጠራነው እንደዚህ አይነት ህይወት እንድንለማመድ ስለሆነ በሁሉም የህይወታችን ዘርፍ ስኬታማ መሆን ይኖርብናል። እንግዲህ እነዚህ ሰዎች ብዙውን ጊዜ እንደሚያስተምሩት በዕዳ የመያዝ ሁኔታ ቢሆን፣ ወይም ጤና የማጣት ጉዳይ፣ ወይም ትዳርን የማጣትና የቤተሰብ መበተን ሁኔታ፣ እንዲሁም ማናቸውም እነዚህን የመሳሰሉ ችግሮችን በተመለከተ የእግዚአብሔርን ተስፋዎች "በማወጅ" መፍትሄን አለማግኘት ያው የእምነት ማነስን ያሳያል፣ ይላሉ። ከላይ ያለው አስተምህሮ አንዳንድ ገጽታዎች ከአስተማሪ ወደ አስተማሪ ሊለያዩ ቢችሉም ቅሉ፣ አጠቃላይ ዝርዝሩ ግን በእያንዳንዱ ጉዳይ ላይ ያው አንድ አይነት ነው።

የዚህ ዓይነቱ ሥነ-መለኮት ከምዕራቡ አለም እየናኘ ድንኳኖቹን በማስፋት ካስማዎቹንም በማርዘም ወደሩቅ ደርሷል። መላውን የሩቅ ምስራቅ ክርስትናና የአፍሪካን ምድር እያጥለቀለቀ በተለይ ከኮምኒዝም ስደት በኋላ በምድራችን በኢትዮጵያ ያለቅጥ ተሰራጭቷል። ይህ ትምህርት በእርግጥ ሰዎችን በጤናና በስኬት እያባበለ ይማርካል፣ ትምህርቱና ልምምዱ ከእምነት በስተቀር ምንም ስለማይፈልግ እርሱም ደግሞ በቂ እምነት ከሆነ፣ ከዚህ የተነሳ ሰዎች ባለጠጋና ጤናማ ሊሆኑ እንደሚችሉ ተስፋ ይሰጣል። እንዲህ ያለው መልዕክት "በህልሙ ቅቤ እንደሚጠጣ ደሀ"  ሰዎች ሊሰሙት የሚፈልጉት አይነት ስለሆነ በብዙዎች ዘንድ ተወዳጅ መልእክት ሆኖላቸዋል።

የዚህ ጠማማ ወንጌል አንዳንድ አስተማሪዎች የሚሉትን ስሙ፦ "እኔ ሙሉ በሙሉ እርግጠኛ ነኝ --እስከፍጻሜዬም እንደዚያም ነው ብዬ ማንም አማኝ በብሽታ እንዳይታመም በኢኮኖሚም እንዳይቸገር፣ እያንዳንዱም አማኝ በዚህ ምድር ላይ እድሜው ሳይቀጠፍ ሙሉ ህይወቱን ቆይቶ እንዲኖር፤ በታላቅ ፍቅሩ እና በታላቅ ምህረቱ የተገለጠ የአባታችን የእግዚአብሔር እቅድ ነው ብዬ በዚሁ እምነት እሞታለሁ፤ እያንዳንዱም አማኝ በመጨረሻ በኢየሱስ ሆኖ መተኛት አለበት" (ኬኔት ኢ ሃጊን፣ ስለ መለኮታዊ ፈውስ ማወቅ ያለብህ ሰባት ነገሮች፣ ገጽ 21)።

ኬኔት ኮፕላንድ "የብልጽግና ህጎች" በተሰኘው መጽሃፉ በገጽ 51 ላይ "እንዲያበለጽግህ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሆነ መገንዘብ አለብህ። ይህም ለአንተ ተዘጋጅቶ የሚጠብቅህ ነው፣ እውነቱን ለመናገር እስካሁንም ከሱ አለመካፈልህ ትልቅ ሞኝነት ነው" ይላል።

የብልጽግና ወንጌል ዋና ስህተት አንዱ ማዕከላዊ መርህ ፦ እግዚአብሔር ለእያንዳንዱ ክርስቲያን በገንዘብ ባለጸጋ እንዲሆን ፈቃዱ ነው፣ ስለዚህም አማኝ በድህነት መኖሩ እግዚአብሔር ካሰበለት ፈቃዱ ውጭ መኖር ነው የሚለው ነው። በተለምዶም ራሱን የሸሸገበት አንዳች ቦታ፦ እኛ የእግዚአብሔር ልጆች ስለሆንን ሁል ጊዜም ቢሆን የመጀመሪያውንና የታላቅነትን ደረጃ መያዝ አለብን፣ ራስ እንጂ ጅራት ስላልሆንን ከሁሉ ከፍ ያለውና መልካም የሆነው ሁሉ ሊኖረን ይገባል። ለእግዚአብሔር ክብር የሚያመጣውም ይህ ብቻ ነው! የሚለው ማረጋገጫው ነው። ሰሞኑን እንደውም አንዱ ያገራችን ጉድ ድህነት አርነት መውጣት የሚጠይቅ ሰይጣናዊ እስራትና እርግማን ነው እያለ ጣቃውን ሲቀደድ በሶሻል ሚዲያ ሰማሁት። እንዲህ ያለው ሰባኪ ነኝ ባይ በጥልቅ ድህነት ውስጥ ይኖሩ የነበሩትን የሜቄዶንያን ቅዱሳን ምን ሊላቸው ነው? ምነው ጳውሎስስ ቢሆን ከዚህ እስራት ሳይፈታቸው ቀረ?

እነዚህ የሐሰት ወንጌል አስተማሪዎች በአብዛኛው የእግዚአብሔርን ቃልና ተገቢነት ያለውን አተረጓጎም ችላ ቢሉም፣ ያንን እርኩስ ትምህርታቸውን ግን እዚህም እዚያም በተቆነጠረ የቅዱሳት መጻሕፍት ጥቅሶች ለማስደገፍ ይሞክራሉ። መቼም የቃል እምነት መልእክትን የሚያስተላልፉ ማናቸውም የሕትመት ሥራ ሆነ ወይም አስተማሪ ነኝ ባይ ከ3ኛ ዮሐንስ መልዕክት ቁጥር 2 መጥቀስ ቋሚ ልማዱ ነው፤ ጥቅሱም "ወዳጅ ሆይ፥ ነፍስህ እንደሚከናወን፥ በነገር ሁሉ እንዲከናወንልህና ጤና እንዲኖርህ እጸልያለሁ።" ይላል።

የብልጽግና ወንጌል አስተማሪዎች ይህን ጥቅስ ልክ የአዲስ ኪዳን ዶክትሪን የሆነ ያህል፣ ክርስቲያኖች ሁልጊዜ ከነፍሳቸው የመከናወን ሁኔታ ጋር ተመጣጣኝ በሆነ መጠን እንደሚበለጽጉ በእርግጠኝነት ያሳያል ሲሉ ይተረጉሙታል። በሌላ አነጋገር፣ በአካሄድህ ከእግዚአብሔር ጋር የምትራመድ ከሆነ፣ ማለትም ነፍስህ ከተከናዋወነ፣ በውጤቱ ኑሮ የተከናወነለት ባለጠጋና የማይታመም ጤነኛ ሰው ትሆናለህ።  በድህነት ውስጥ የምትኖር ከሆነ ግን ገና አሁንም በኃጢአትህ ውስጥ መሆን አለብህ፤ እንደ ማለት ነው፣ ይላሉ።

ይህ ጥቅስ ዮሐንስ ለወዳጁ ለጋይዮስ ያቀረበው ሰላምታና የጸሎት ዘገባ ብቻ ነው እንጂ ከእግዚአብሔር ዘንድ ለክርስቶስ አካል ሁሉ የተሰጠ የእምነት መግለጫ ወይም አቋም አይደለም፤ ዶክትሪን ሆኖ እንደ ተስፋ ቃል ወይም እንደ እምነት እንቀጽ መቆጠርም የለበትም። ሰላምታንና የጸሎት ርዕስን ሁሉ እየሰበሰቡ ዶክትሪን ለማድረግ መሞከር በእውነቱ አለመማር ብቻ ሳይሆን፤ ሁሉም የተጻፈው ለእኔ ነው የሚል ብልጣብልጥነትና ራስ ተኮርነትም ጭምር ነው። የብልጥግና ወንጌል ክፋቱ ሰዎችን ራስ ወዳድና ስግብግብ ማድረጉ ነው

ተመልከቱ፣ ይህ መልእክት የተቀረጸው በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን በነበረው የተለመደ የደብዳቤ አጻጻፍ ቅርጽ ነው። ዊልያም ባርክሌይ ይህንን በ3ኛ ዮሐንስ 2 ላይ ያለውን የተለመደ የደብዳቤ አጻጻፍ ቅርጽ እውነታ የሚመለከተው አንድ የመርከብ ካፒቴን ሸኝዎቹን ሲሰናበት ከሚጠቀምበት የስንብት ቃልና አብረውት የሚጓዙትን ሲያበረታታ ከሚጠቀምበት ማበረታቻ አረማዊ የመልካም ምኞት መግለጫ ጋር ተመሳሳይ የሆኑ ሐረጎችንና ቃላትን በመጥቀስ ነው። ሃዋርድ ማርሻልም፣ በኒው ኢንተርናሽናል የመጽሐፍ ቅዱስ ማብራሪያው ውስጥ፣ ሽማግሌው (ዮሐንስ) ለወዳጁ ለጋይዮስ መልካም ምኞቶችን በመግለጽ በጊዜው የነበረውን ባህላዊ ወግ እና እሴት እንደሚከተል በመግለጽ የባርክሌይን አስተያየት ያረጋግጣል። ይህ ልክ በሃገራችን ልማድ "ጤና ይስጥልኝ" ብሎ በመልካም ምኞት መግለጫ ሰላምታ የማቅረብ ሁኔታ እንጂ "የመከናወንና የጤንነት" ዶክትሪን ፈጽሞ አይደለም። ለሁሉም አማኞች ፈቃዱን በተመለከተ ከእግዚአብሔር የተሰጠ ሁለንተናዊ መግለጫም አዋጅም አይደለም። እንደዚያ ነው ብሎ መገመት ግን ከሥነ-ጽሑፋዊው እና ታሪካዊው አውድ ውጭ መሆን ነው። 

አስተውሉ፣ መጽሐፍ ቅዱስ ስለእኛ ተጽፎልናል እንጂ በቀጥታ ለእኛ አልተጻፈም። ጳውሎስ እስክንድሮስን በአይነ ቁራኛ እንዲጠብቅ ለጢሞቴዎስ የሰጠው ትዕዛዝ፣ እንዲሁም ከክረምት በፊት በርኖሱን ይዞለት እንዲያመጣ፣ ቲቶም በቀርጤስ እንዲኖር የተሰጠው መመሪያ፤ ወይም ጌታችን ኢየሱስ "ሽሽታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ" ያለው፣ ወይም "በአንዲቱ ከተማም መከራ ቢያሳዩአችሁ ወደ ሌላይቱ ሽሹ" ያለው፣ አልያም "በይሁዳ ያሉት ወደ ተራራዎች ይሽሹ" ያለው እና ይህን የመሰለ ነገር ሁሉ በእርግጥም የእግዚአብሔር ቃል አካል መሆኑ እሙን ነው፥ ዳሩ ግን እንዲህ ያለው ትዕዛዝ በቀጥታ ለእኛ የተጻፈ አይደለም። ብዙዎች ግን  ይህንን መለየት ተስኗቸዋል። የብልጽግና ወንጌል መምህራንም ይህን በተመለከተ በያዙት ግንዛቤ ግለሰብን ጠቅሶ በአድራሻው በተጻፈለት ሰላምታን በያዘ የመልካም ምኞት መግለጫና ለሁሉ በሚሆን ሉል አቀፍ ዶክትሪናል የተስፋ ቃል መካከል ያለውን ልዩነት አደባልቀዋል።

፫.

አሁን እንግዲህ ታዲያ ይህ ምንአለበት፣ በእኛ ላይስ ምን ጉዳት ሊያደርስ ይችላል? ተብሎ ይጠየቅ ይሆናል። በእርግጠኝነት ለመናገር የእግዚአብሔርን ቃል እየተማርን የምናድግ ማናችንም ብንሆን በዚህ የውሸት ወንጌል ልናምን የምንችልበት ምንም መሰረት እንደሌለን ይህንን አንድ ነገር እገነዘባለሁ፤ ይሁንና ግን ልታስተውሉት የሚገባችሁ ነገር እንዲህ ያለ የተሳሳተ ትምህርት በቤተ ክርስቲያን ላይ እየናኘ የብዙወችን ልብ እየወሰደ መሆኑን ነው። በኢንተርኔት በተደረገ ጥናት 61 በመቶ የሚሆኑት የአሜሪካ ጰንጤቆስጤ አማኞች እግዚአብሔር ሰዎች እንዲበለጽጉ እንደሚፈልግ ያሚያምኑ ናቸው። "የእርስዎ ምርጥ ህይወት አሁን"፣ በሚል ርዕስ መጽሐፍ አሳትሞ ከ4 ሚሊዮን በላይ ቅጂዎች የሸጠው የጆኤል ኦስቲን ድርሰት ይህንን ያሳያል። በግሌ መጽሐፍ ተራ ጎራ ብዬ አይኔን ሳማትር በየመደርደሪያው ላይ እዚህም እዚያ በርከት ብሎ አይኔን የሚያደናቅፈኝ እንደ ዚህ ሰውዬ ድርሳን ሌላ መጽሐፍ ብዙ አልገጠመኝም። 

ይህ እምነት የጰንጤቆስጤ መሰረቱን እያሰረገ ወደ ወንጌል አማኝ አብያተ ክርስትያናት ሁሉ ዘልቆ ግብቷል። በአገራችንም የወንጌል እምነት ታሪክ ውስጥም የቃል እምነት ህጸጹን አሹልኮ በማስገባት የአንበሳውን ድርሻ የሚወስደው ጰንጤቆስጤ ነው። እኔ በበኩሌ እንደ ጰንጤቆስጤ ከጤንነትና ከብልጽግና ወንጌል ጋር እርኩስ ጋብቻን የፈጸመ ሌላ እምነት አላየሁም፤ ይህም ግልሙትና እንደ ወረርሽኝ ወንጌላውያንና ካርዝማውያን ነን ሲሉ ራሳቸውን የሚጡሩትን እያዳረሰ በሁሉም ቤት እንደ ቀኖና የሚታመን እየሆነ ለመምጣት ጥቂት ስብከቶቻቸውንና መዝሙሮቻቸውን መታዘብ ብቻ ይበቃል።

እንደሰሜን አሜሪካ ባሉ አገሮች ውስጥ ትላልቆቹን ጉባኤያት ከሚመሩና ብዙሃኑ ካደነቃቸው ዝነኛ ሰባክያን ጋር በሥነ-መለኮታዊ ጉዳዮች አለመስማማት በተለይም በአሁኑ ጊዜ እንደ ሞኝነት እንደ እብደትም  ሊመስል ይችላል። ተመልከቱ ሠላሳ ሺህ የሚሆኑ ጎልማሶች በየእሁዱ የጆኤል ኦስቲንን ስብከት ለመስማት በቤተክርስቲያኑ ይገኛሉ። በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተጨማሪ ሰዎች ደግሞ በየቤታቸው ሆነው የእሱን ብሔራዊ እና የዓለም አቀፍ የቴሌቪዥን ስርጭቶችን በቻናሎቹ ይከታተላሉ። በእርግጠኝነት ይህ ለቁጥር የሚያታክት ተከታይ ያለው ሰው በትክክለኛው መንገድ ላይ የመሆኑ ምልክት ነው ብሎ ማንም ሰው መገመት ይችላል። እውነታው ግን ይህ አይደለም! ቢከፍቱት ተልባ የሆነ ይህ ሰው ኃሰተኛ የምኞት ወንጌል እየሰበከ ያለ የስህተት አስተማሪ ነው።

ጆኤል ኦስቲን ያተረፈው እንዲህ ያለ እውር ተወዳጅነት በእውነት በአሜሪካ ውስጥ ላለው አጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን ሁኔታ አይነተኛ ማረጋገጫ ነው። ይህ ሰው በሚያቀርበው ዲስኩር የሚደመጠው አነቃቂ ንግግሩ በእውነት ስለ ኃጢአታቸው የማይወቀሱና ሊወቀሱ የማይወዱ ሰዎችን ጆሮ ይማርካል። እነዚህም ንስሃ መግባት እና ኃጢአታቸውን መጥላት የማይፈልጉ ናቸው። ስለዚህም ጆኤል ኦስቲን፣ ሆነ ብሎ የእግዚአብሔርን እውነት ርዕሰ ጉዳዮች በሙሉ በስብከቱ ሜኑ ውስጥ አያካትታቸውም። በዚህም ምክንያት ከእግዚአብሔር  ክብር ወይም ክርስቶስ ለኃጢያታችን ከከፈለው የኃጢአት ዕዳ ክፍያ ጋር የማይገናኝ ሁለመናው ራስን ስለ ማሻሻል የሆነ፣ የተዛባና፣ ከረሜላ ከረሜላ የሚል "የምኞት ወንጌል" ያቀርባል። ይህ የምኞት ወንጌል ፈጽሞ ወንጌል አይደለም፤ እውነት እላችኋለሁ ግማሹንም ያህል እንኳ ወንጌል አይደለም። ለዚያም ነው በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የሚፈልጉትን የምኞት ወንጌል ለመመገብ ወደ ስፍራው የሚጎርፉት፣ እንዲሁም በሚሊዮን የሚቆጠሩ ሌሎች በቲቪ የሚመለከቱት። አስተውሎ ለተከታተለው ሰው፣ የዚህ ሰው ወንጌል ቅዱስና የተፈራ አምላክ የለውም፣ አስፈሪውን መለኮታዊ ፍርድም አያቀርብም፣ የስርየት አስፈላጊነትንም አያሳይም። ምናልባት በእርሱ ስብከት የሚነቃቃ ይኖር ይሆናል እንጂ ንስሃ የሚገባና ከክፉ ስራው ተጸጽቶ የሚመለስ አንድ ሰው የለም። በስብከቱም ራስን ስለመውደድ እንጂ ለራስ ወዳድነት ስለመሞት ፈጽሞ አይናገራትም፣ በእኔነት ላይ ያተኮረ፣ እኔ፣ እኔ የሚለው ስብከቱ ሲደመጥ እውነተኛውን ወንጌል በሚያውቁ ሰዎች ዘንድ እንጨት እንጨት ይላል።

የሰው ሃይማኖተኛ ዝንባሌ ሁል ጊዜ ለገዛ ራሱ ጥቅም ሲል የገዛ ፍላጎቱን የሚያሟላለትን  አማላክ ይፈበርካል። ወንጌል ካልገባህ የፈለግኸውን የሚሰጥህንና የአንተ አገልጋይ የሆነ አምላክ ለመፈልሰም አትቦዝንም። ይህ ሰዎችን በምኞት የሚያጠፋ የጤናና የብልጥግና ነገረ መለኮት ወንጌላዊውን ክርስትና ከደረጃው አውርዶ ዝቅተኛ ከሆነው የሰው ሀይማኖቶታዊ ዝንባሌ የማይለይ ተራ የከልት ስርዓት አድርጎታል። አምላክ በሰዎች ምርጫ እጁ የሚጠመዘዝ፣ ፈቃዱን ለመለወጥ የሚገደድ፣ በሰዎች አቀራረብ የሚታለል፣ በማባበያ የሚሸነገል፣ ሰዎች ሊቆጣጠሩትና ወደፍላጎታቸው ሊስቡት የሚችሉትና ክርስቲያኖች ለጥቅማቸው የሚበዘብዙት አይነት ከሆነ እንዲህ ያለው አምላክ የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አባትና አምላክ አይደለም። እንዲህ ያለውን የተፈበረከ አምላክ የተቀበለ ክርስትና ደግሞ አፍሪካዊ ተፈጥሮ ያለውን የቩዱ ሃይማኖት ዓይነት ጣዖታዊ መልክ አለው።

ጆኤል ኦስቲን ምን አይነት ወንጌል እንደሚያስተምር መረዳት እንድንችል 30,000 ለሚሆኑ አባል ቤተ ክርስቲያኑ ከላከላቸው መልእክቶች አንዱን ወስደን እንመልከት፡-

"እርሱ ከከፈለው ዋጋ የተነሳ በድል አድራጊነት የመኖር መብት አለን።  ጥሩ ቤተሰብ መመስረት፣ ጥሩ ጤንነት ማግኘት ወደቻልንበት ግማሽ ድል ውስጥ ገብተንም ሊሆን ይችላል፣ በገንዘብ አቅማችን ውስጥ ግን ያለማቋረጥ እየታገልን እንኖራለን፤ ይሄ ግን ፈጽሞ ሙሉ እና አጠቃላይ ድል አድራጊነት አይደለም።  እግዚአብሔር በአንዱ ዘርፍ መልካም ካደረገላችሁ በሌላው ዘርፍም መልካም ሊያደርግላችሁ ይወዳል።  እንዲህ ላለው ስኬት ግን ራዕይ ይኑራችሁ። በግሌ  ብዙ ገንዘብ ያላቸውን ሰዎች አውቃለሁ፣ ጥሩ ጤንነትም አላቸው፣ በቤተሰባዊ ግንኙነቶቻቸው ውስጥ ግን እርስ በርስ መግባባት አይችሉም።  በቤታቸው ውስጥ ሁል ጊዜ ጠብና ጭቅጭቅ አለ ፣ ይህ በእውነት ሙሉ በሙሉ ድል አይደለም።  ምናልባት ደግሞ እግዚአብሔር ባርኮህ ጥሩ ቤተሰብ እና ጥሩ ስራ ይኖርህ ይሆናል፣ ነገር ግን በሰውነትህ ላይ ለዓመታት እና ለዘመናት የሚታገልህ ህመም ያለብህ ልትሆንና፣  እርሱንም እየተቃወምህ ስትጸልይ ምናልባትም ከህመምህ ነፃ እንደምትወጣ ታምን ነበር።  አሁን ግን ይህ በህይወቴ ውስጥ ዕጣ ፈንታዬ ነው…ብለህ ተቀብለኸው መኖር ከወሰንክ በጣም ብዙ ጊዜ አልፎታል፣ አንድ ነገር ግን እወቅ ሙሉ በሙሉ ነፃ እንድንሆን ኢየሱስ ዋጋ ከፍሏል።  ይህ ማለት ከመጥፎ ልማዶች እና ከሱሶች ሁሉ፣ ከተስፋ መቁረጥ እና ከጭንቀት ሁሉ፣ ከድህነት እና ከእጦት ሁሉ፣ ነፃ እንድትሆን፣ ለራስህም ከፍ ያለ ዋጋ እንዳትሰጥ ከሚያደርግህ የዝቅተኛነት ስሜት ነፃ እንድትሆን ማለት ነው። እግዚአብሔር ፍጹም ነፃ እንድንሆን ይፈልጋል።  ቅዱሳት መጻሕፍት ክርስቶስ የሞተለትንና የተነሣበትን ሁሉ እንድንቀበል ይነግሩናል። እግዚአብሔር ጤናማ እና ሙሉ አድርጎሃል፣ የእኛ ቀዳሚ ስፍራም ሙሉ ነፃነት ነው... አማካኝ ቦታ ላይ እንድትሆን አለመፈጠርህን አረጋግጥልሃለሁ።  በጭንቅ ውስጥ እንድታልፍ እና ክፉንም ደጉንም ሁሉንም አይነት ነገሮች እንድትቀበል አልፈጠረህም።  ትክክለኛውን የህይወት ራዕይ ማግኘት አለብህ።  እግዚአብሔር የፈጠረህ ፍፁም ነፃ እንድትሆን፣ በአእምሮህ ሰላም እንዲኖርህ፣ በመለኮታዊ ጤንነት እንድትመላለስ፣ ጥሩ ቤተሰባዊ ግንኙነት እንዲኖርህ፣ የብድር ዕዳህን እንድትከፍልና ከብድር ህይወት ነጻ እንድትሆን፣ እንድትበዛና እንድትትረፈረፍ ነው። ይህ ሁሉ የሚገባህና ልዩ መብትህ ነው።  ከነዚህ መብቶችህ ውስጥ አንዱ አጠቃላይ ድል ነው።  ነፃ ሆኖ መኖር ያለ ጥርጥር ይገባናል፣ ይህም ማለት በአእምሯችን ነፃ ሆነን ከጭንቀት ሁሉ የጸዳን መሆን ማለት ነው። የባንክ ሂሳባችን ምንም አይነት ቢመስልም፣ ከድህነት እና ከእጦት የጸዳ መሆን ማለት ነው። አመለካከታችንም ተለውጦ እኔ እንደተባረኩ አውቃለሁ፣ የተረገምሁ ልሆንም ፈጽሞ አልችልም።  እኔ የነካሁት ሁሉ ይበለጥጋል ይሳካለታልም እንድንል ነው"።

ይህ እንግዲህ የጆኤል ኦስቲን ንግግር ነው። የእግዚአብሔርን ቃል በወጉ ላልተማሩ ሰዎች ይህ ንግግር ምንም ችግር የሌለበት ሆኖ ይሰማቸዋል። የክርስቶስን ወንጌል ተፈጥሮ ስታውቀው ግን ይህ ንግግር ወንጌልን የሚበርዝ በማር የተለወሰ መርዝ መሆኑን አስተውለህ ራስህንና የሚሰሙህን ከዚህ የጥፋት ወንጌል ለማዳን ትናጠቃለህ። ልብ አድርጉ፣ በዚህ ሰው ትርጓሜ መሰረት ከእግዚአብሔር ጋር በመንፈሳዊ ብስለት መሄድ ማለት ባለጠጋ መሆን ማለት ነው፣ ጤናማ፣ የማይታመም፣ ጥሩ ቤተሰባዊ ግንኙነት ያለህ፣ ሁልጊዜ ያለ ህመምና ያለ ጭንቀት በድል አድራጊነት እየኖርክ በሁሉ ቀዳሚና አንደኛ ሆነህ እንደ ባለ መብት መኖር አለብህ ማለት ነው።  የዚህ አመለካከት ችግሩ ግን ኢየሱስ የኖረውን ህይወትና መላው የአዲስ ኪዳንን ቤተ ክርስቲያን ያለፉበትን የህይወት ትግል ያገለለ መሆኑ ነው።

የዚህን ሰባኪ ንግግር ካደመጣችሁ በኋላ፣ ኢየሱስና በወንጌሉ የምናውቀው ኑሮው ከዚህ ሰው አሳብ ጋር  እንዴት ነው ሚስማሙት? ብላችሁ ጠይቁ። በውኑ ወንጌሉ የሚያስተዋውቀን ኢየሱስ ባለጠጋ ነበርን? ደልቶትስ ይኖር ነበርን?  ፈጽሞ እንደዚያ አልነበረም!  በሶስት ዓመት ተኩል አገልግሎቱ፣ የሚጠለልበት እንኳን ሳይኖረው በምድር ላይ እየተንከራተተ በድህነት ኖረ (ሉቃስ 9፥ 58)፤ የሚያርፍበት ቤት አልነበረውም፣ መሠረታዊ ፍላጎቶቹን ለማግኘት ሁልጊዜም ቢሆን የሌሎች ድጋፍ አስፈልጎት ነበር።  ብዙዎች የብልጥግና ወንጌል አጋፋሪዎች ግን ይህንን የእግዚአብሔር ልጅ ኑሮ "ድህነት" ነው ብሎ ለመጥራት ይፈተናሉ።

ኢየሱስ በማበራዊ ግንኙነቱ ላይ ችግር ነበረበትን? ተመልከቱ ሁሉም የሃይማኖት መሪዎች ይጠሉት ነበር፣ የገዛ ቤተሰቦቹ ንቀውት ነበር፣ ጴጥሮስ ክዶታል፣ ይሁዳ አሳልፎ ሰጥቶታል፣ ሕዝቡም ሁሉ "ስቀለው ስቀለው" እያሉ ጮኸዋል።  ጌታ ኢየሱስ በማህበራዊ ግንኙነቱ ውስጥ ጆኤል ኦስቲን በሚናገርለት አይነት በድል አድራጊነት እየኖረ እንዳልነበር  አስባለሁ። ብዙዎች ተወዳጅነትና ከበሬታን ነፍገውታል። ከከበሩትም ሰዎች መካከል የሚበዙት በቀንና በአደባባይ ከእርሱ ጋር መታየትም ሆነ ሊተባበሩት አይፈልጉም ነበር። ኢየሱስ  የህማም ሰው ነበር። ከባድ ሥቃይ ደርሶበታል።  ተገርፏል፣ ጉሰማና ድብደባ ደርሶበታል። አዋርደው ተፍተውበታል፣ እርሱ በመከራ እንጨት ላይ ተሰቅሎ እንዲገደል በእግዚአብሔርም በሰውም የተተወ የህማም ሰው ነው።  ስለዚህ ጆኤል ኦስቲን እየተናገረለት ያለው ይህ አይነቱ የድል ሕይወት በኢየሱስ አልተኖረም። መፅሃፍ ቅዱስም በግልጽ ሲያስተምረን እርሱን መስለን መኖር እንዳለብን ይናገራል። 

1ዮሐንስ 2፥ 6 "በእርሱ እኖራለሁ የሚል እርሱ እንደ ተመላለሰ ራሱ ደግሞ ሊመላለስ ይገባዋል።"

እንግዲህ ይህን ካደረግንና እንደ ኢየሱስ የምንኖር ከሆነ ኢየሱስ ያጋጠመውንና ያለፈበትን ዓይነት የህይወት ውጣ ውረድ እኛም ያጋጥመናል።  ክርስቶስ እንደኖረ ከኖርን ጆኤል ኦስቲን የሚሰጠውን ሃሰተኛ የድል ሕይወት ተስፋ አናይም። የኢየሱስ ነኝ የምትሉ ሁሉ ስሙኝ፣ በጤንነት ብልጥግና ወንጌል ኃሰተኛ ተስፋ ተታላችሁ ኢየሱስ በስጋው ወራት ያልኖረውን የቅምጥል ህይወት ለመኖር አታስቡ።

የጌታችን ደቀመዛሙርትስ እንዴት ነበር የኖሩት?  በአጠቃላይ የድል ኑሮ የሚኖሩ ህመም የማያውቃቸው ፍጹም ጤነኛ ነበሩን፣ ባለጠጎችስ የነበሩና በምድራዊ ፍላጎቶቻቸው ጉድለት ያላዩ ነበሩን?  በጭራሽ ቅምጥሎችም አልነበሩም ያንንም ተስፋ አድርገው አልተመኙም! ተመልከቱ  ከሐዋርያት መካከል አንዳቸውም ባለጠጋ አልነበሩም።  ሁሉም ሊታመን የማይችል ፈተናና መከራ ነበረባቸው፣ ቢያንስ የጳውሎስን ጉዳይ እንኳ ብናነሳ መሰረታዊ የቁሳዊ ጉዳዮች እጦት እና ከባድ የጤና ችግሮች ለህይወቱም አስጊ የነበሩ ተስፋ አስቆራጭ ከፍተኛ ፈተናዎች ደርሰውበታል።

ሐዋርያው ​​ጳውሎስን ከእግዚአብሔር ጋር በመልካም ኅብረት የተራመደ፣ ነፍሱ የተከናወነለት የእግዚአብሔር ሰው ነበርን?  አዎ በሚገባ ነበር። እግዚአብሔር ራሱ በጳውሎስ እጅ የሚያስገርም ተአምራት እያደረገ፣ ለድውዮችም ከአካሉ ላይ ጨርእቅ ወይም ልብስ ይወስዱ እንደነበር እናውቃለን። አብዛኛውን አዲስ ኪዳንን እንዲጽፍ እግዚአብሔር ጳውሎስን በብዙ ተጠቅሞበታል።  ጳውሎስ ግን በማህበራዊ በግንኙነት ላይ ችግር አጋጥሞት ያውቃልን? አዎ። በእርግጥም እንዲህ ያለው ታላቅ የእግዚአብሔር ሰው በሰዎች መተውና መረሳት ደርሶበት ያውልቃ፤ አመዛኙን ህይወቱን ያሳለፈውም  ወህኒ ቤት ውስጥ እንደነበር እናውቃለን፦

2ጢሞቴዎስ 4፥ 16 "በፊተኛው ሙግቴ አንድ ስንኳ አልደረሰልኝም፥ ሁሉም ተዉኝ እንጂ፤ ይህንም አይቍጠርባቸው፤"

አካላዊ ሕመምን በተመለከተስ? ፣ ጳውሎስ የአካላዊ ጤና ችግር ነበረበትን?

2ቆሮንቶስ 12፥ 7 "ስለዚህም በመገለጥ ታላቅነት እንዳልታበይ የሥጋዬ መውጊያ፥ እርሱም የሚጎስመኝ የሰይጣን መልእክተኛ ተሰጠኝ፤ ይኸውም እንዳልታበይ ነው።"

እዚህ ላይ ጳውሎስ አካላዊ የጤንነት ዕክል የነበረበት መሆኑን እናያለን።  ይህን ችግር ያጋጠመው ለምን እንደሆነም የእግዚአብሔር ቃል ይነግረናል።  በጠቅላላ ህይወቱ በድል ስላልተራመደ ወይም መንፈሳዊ የሕይወት ድካም ስለነበረበት ሳይሆን ይልቁንም ትህትናውን ጠብቆ ለማቆየት እግዚአብሔር የተጠቀመበት መንገድ ነበር።  "እግዚአብሔር ለትሑታን ጸጋን ይሰጣልና" ያ ደግሞ መልካም ነገር ነው።

2ቆሮንቶስ 12፥8 "ስለዚህ ነገር ከእኔ እንዲለይ ሦስት ጊዜ ጌታን ለመንሁ።"

ይህንን ችግር እግዚአብሔር እንዲወስድለት ጳውሎስ በጸሎት ጠየቆ ነበር።  እግዚአብሔር ግን የሰጠውን መልስ ልብ በሉ፦

2ቆሮንቶስ 12፥ 9 "እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ።"

ጳውሎስ በድህነቱና በሥቃዩ ላይ ስለተቀዳጀው አጠቃላይ ድል ይመካ ነበርን? ደስታውስ ይህ የጤናና የኢኮኖሚ ችግር ከእርሱ ስለተለየ ነበርን?  ፈጽሞ ደስታውም ትምክህቱም በዚያ አልነበረም! ይልቁንም በነዚያ  ድክመቶቹ ሲመካ ይታያል።  ይህ ለምን እንደሆነ ልብ አድርጉ፦

2ቆሮንቶስ 12፥ 10 "ስለዚህ ስለ ክርስቶስ በድካም በመንገላታትም በችግርም በስደትም በጭንቀትም ደስ ይለኛል፤ ስደክም ያን ጊዜ ኃይለኛ ነኝና።"

ልብ አድርጉ፣ ይህ የጤና/ብልጥግና ወንጌል የተባለ የትምህርት አረም ይህንን እውነት ሙሉ በሙሉ ስቶታል።  ጳውሎስ፣ “ስደክም፣ ማለትም በዚህ አካላዊ ሕመሜ፣ በማልፍበት እጦትና ድህነት፣ በሚገጥመኝ የማህበራዊ ተቀባይነት እጦት፣ በመከዳቴ እና በሰዎች በመረሳቴ እመካለሁ፣ ደስ ይለኛል” ሲል ተናግሯል።  አያችሁ፣ በሕይወታችን ውስጥ ችግሮች ሲያጋጥሙን ያኔ ነው እንደ ጳውሎስ ወደ ክርስቶስ የምንዞረው እና በኃይሉ የምንታመነው።

የጳውሎስን የግል የህይወት ምስክርነት ተመልከቱ እና ምን ያህል ከጆኤል ኦስቲንን አጠቃላይ የድል ኑሮ ሃሳብ እና አስተምህሮ ጋር መስማማት አለመስማማቱን መዝናችሁ እዩ፦

2ቆሮንቶስ 11፥ 23-27 "እንደ እብድ ሰው እላለሁ፤ እኔ እበልጣለሁ፤ በድካም አብዝቼ፥ በመገረፍ አብዝቼ፥ በመታሰር አትርፌ፥ በመሞት ብዙ ጊዜ ሆንሁ። አይሁድ አንድ ሲጎድል አርባ ግርፋት አምስት ጊዜ ገረፉኝ። ሦስት ጊዜ በበትር ተመታሁ፤ አንድ ጊዜ በድንጋይ ተወገርሁ፤ መርከቤ ሦስት ጊዜ ተሰበረ፤ ሌሊትና ቀን በባሕር ውስጥ ኖርሁ። ብዙ ጊዜ በመንገድ ሄድሁ፤ በወንዝ ፍርሃት፥ በወንበዴዎች ፍርሃት፥ በወገኔ በኩል ፍርሃት፥ በአሕዛብ በኩል ፍርሃት፥ በከተማ ፍርሃት፥ በምድረ በዳ ፍርሃት፥ በባሕር ፍርሃት፥ በውሸተኞች ወንድሞች በኩል ፍርሃት ነበረብኝ፤ በድካምና በጥረት ብዙ ጊዜም እንቅልፍ በማጣት፥ በራብና በጥም ብዙ ጊዜም በመጦም፥ በብርድና በራቁትነት ነበርሁ።"

ጆኤል ኦስቲን ይህን ምስክርነት አንብቦ ያውቃልን? እንጃ። ለክርስቶስ መኖር እና እግዚአብሔርን በመታዘዝ መመላለስ ለጳውሎስ ይህን ይመስል ነበር።  ምን ያህሎቻችሁ ለእንደዚህ አይነት የህይወት ስርአት መፈረም ትሻላችሁ?  ጆኤል ኦስቲን ይህንን ህይወት የእግዚአብሔር ፈቃድ ነው ብሎ ለአማኞች ሰብኮ ቢሆን ኖሮ እንዲህ ያለ ትልቅ የሕንፃ ካቴድራል ባልኖረውም ነበር።

፬.

ያለህባት ቤተ ክርስቲያን እግዚአብሔር ሀብት ሰጥቶ ባለጠጋ ሊያደርግህ እንደሚፈልግ የምታምን ከሆነ፣ ፓስተርህም ይህንንው እየደጋገመ ሲሰብክ፣ አንተ ግን "በእምነትህ ማነስ " ምክንያት ከዚህ እንደጎደልህ ማወጅና ማስተማር ሲጀምር፣ እንዲህ ያለው ይህ የትምህርት እብደት በተለይ በድህነት ውስጥ ለሚኖሩ በሚሊዮን ለሚቆጠሩ እግዚአብሔርን ለሚፈሩ ሰዎች ምን ማለት ይሆን?

ተመልከቱ በገጠራማዋ የኢትዮጵያ መንደሮች በየእሁዱ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ለማምለክ  3 በ 5 ስፋት ባላት አነስተኛ "የጸሎት ቤት" ውስጥ ወይም በዛፍ ጥላ ስር ይሰበሰባሉ። ያቺ ቤተመቅደስ በሰዎች አይን የምታምር አይደለችም፣ ነገር ግን በምድር ላይ ካሉት በጣም ድሆች ከሆኑ አማኞች ጥቂቶቹን በአባልነት ያቀፈች ቤተክርስቲያን ናት።  ነገር ግን የእነዚህ ሰዎች ኢኮኖሚያዊ ዝቅተኛነት ያለባቸውን መንፈሳዊ የበታችነት አያመለክትም። እርግጥ ነው እነዚህ ሰዎች እንደብዙዎቹ ምዕራባውያን የጤና እንክብካቤ ዋስትና የላቸውም፣ ነገር ግን በህመማቸው ጊዜ ጌታ እንዲፈውሳቸው በጸሎት ይጠይቃሉ። ምናልባትም ከብዙዎቻችን በተለየ በእግዚአብሔር ሉዓላዊነት ላይ የመተማመን እጅግ የላቀ ደረጃ ያላቸው ናቸው።  እነዚህ ሰዎች "የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን" ብለው ሲጸልዩ - በእርግጥ ለማለት ያህል በልማድ ሳይሆን የምራቸውን መለመናቸው ነው።  በጣም መሠረታዊ የሆኑ ፍላጎቶቻቸውን ሊሰጣቸው እንደሚችልም በእግዚአብሔር እየታመኑ ውሱን በሆኑ ግብአቶቻቸው በገዛ እጃቸው ለሥራ ይተጋሉ እንጂ አይለግሙም።

የሚቀጥለው ምግብ እንዴትና ከየት እንደሚመጣ የማያውቁ ነገር ግን መንፈሳዊ ኃያላን የሞሉባት እንዲህ ያሉ ታናናሽ መንጋ ያሏቸውን ታናናሽ የቅዱሳን ማህበራት ኢትዮጵያን ከመሰሉ የአፍሪካ ገጠራማ መንደሮች ማግኘት የተለመደ ነው።  ሆኖም በድህነታቸውና በሥቃያቸው መካከል እግዚአብሔርን በደስታ ውዳሴ ሲያመልኩት ነፍስ አይቀርላቸውም። እኔ ከወንጌል እንደምረዳው ጆኤል ኦስቲን ከሚደሰኩረው ኃሰተኛ የድልና የስኬት ህይወት ይልቅ ፍጹም ድል ይህ ነው።

ምእመናን አጥብቀን ልንረዳው የሚገባን እውነት እዚህ አለ፤ ክርስቲያኖች በዚህ ዓለም ውስጥ መኖር እንደሚገባው ያህል በጽድቅ ሕይወት በሚኖሩበት ጊዜ ሁሉ ወንጌልን በኃይል ለማስፋፋት እና ሰዎችን ደቀ መዛሙርት ለማድረግ እየተጋደሉ ለጽድቅ ሲቆሙ የዚህ ተፈጥሮዋዊ ውጤት መከራ መቀበል ይሆናል።  ኢየሱስ ደቀ መዛሙርቱ ይህንን እንዲረዱ ይፈልጋል፣ መከራንም እንዲጠብቁ ያስተምራል። ጳውሎስም እንዲሁ ሲያመለክተን፡-

2ጢሞቴዎስ 3፥ 12 "በእውነትም በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ።" ይላል።

ይህ ጥቅስ ክርስቲያኖች ሁሉ በጅምላ ስደትን መጠባበቅ ይችላሉ አይልም። ይልቁን ምን ይላል?  "በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ።" ነው የሚለው። መከራንና ስደትን ወዳለንበት ስቦ የሚያመጣው እግዚአብሔርን የመምሰል ሕይወት ነው።  ማለትም ከእግዚአብሔር ጋር ስትቆም፣ ኃጢአትን ስትቃወም፣ ውርጃን፣ ግብረ ሰዶማዊነትን፣ ተመሳሳይ ጾታዊ ጋብቻን ስትነቅፍ እና የስነምግባር ዝቅጠትን ተቃውመህ ስትናገር፣ ያኔ በዚህ ምክንያት ስደት ሊደርስብህና መከራን ልትቀበል እንደምትችል ጠብቅ!

ጳውሎስ በብዙ መልዕክቶቹ የንባብ ክፍሎች ላይ መከራና ስቃይ የሐዋርያዊ አገልግሎት አስፈላጊ አካል እንደሆ በማሰብ ጽፏል።  በሌሎች ክፍሎች ግን ጳውሎስ መከራን እና ስቃይን በሐዋርያት አገልግሎት ላይ ብቻ አልወሰናቸውም።  ይልቁንም አለፍ ብሎ የደቀመዝሙርነት ኑሮ አስፈላጊ አካል እንደሆነም ያመለክታል።  ይህም ትምህርት በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ወጥነትና ቀዋሚነት ያለው አጽንዖት ነው። ችግሮችና ፈተናዎች፣ ተግዳሮቶችና ግጭቶች ህመምም ከደቀመዝሙርነት ኑሮ ጋር የማይነጣጠሉ ሆነው የተቆራኙ ናቸው።

ምእመናን፣ ልንረዳው የሚገባን አንድ ጉዳይ ህመምና ስቃይ ድኅነትም የዚህ ሕይወት ሥርአትና አካል ናቸው፤ ክርስቲያን መሆናችንም ሆነ የድል ኑሮ መኖር ደግሞ ሁሉም ከህይወታችን እንዲወገዱ አያደርጋቸውም።  ጥበበኛ፣ ቅዱስ እና አፍቃሪ የሆነው አምላካችን በህመማችን እና በመከራችን ውስጥ የማይመረመር አላማ አለው።  ጳውሎስ ለቆሮንቶስ ሰዎች የሚነገራቸውን ልብ አድርጉ፦

2ቆሮንቶስ 1፥ 8 "በእስያ ስለ ደረሰብን መከራችን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ታውቁ ዘንድ እንወዳለንና፤ ስለ ሕይወታችን እንኳ ተስፋ እስክንቆርጥ ድረስ ከዓቅማችን በላይ ያለ ልክ ከብዶብን ነበር፤"

ይህ ጆኤል ኦስቲን የሚናገርለትን አጠቃላይ የድል ኑሮ ፈጽሞ አይመስልም።  ጳውሎስ ግን እርሱና ባልደረቦቹ መከራ ለምን እንደደረሰባቸው በግልጽ ነግሮናል፣ ተመልከቱ፦

2ቆሮንቶስ 1፥ 9  "አዎን፥ ሙታንን በሚያነሣ በእግዚአብሔር እንጂ በራሳችን እንዳንታመን፥ እኛ ራሳችን የሞትን ፍርድ በውስጣችን ሰምተን ነበር።"

ወገኖች ሆይ፣ መከራን መቀበል በራስ የመደገፍ ኃጢያትን ከላያችን ያራግፍልናል።  ብዙ ወንዶች እና ሴቶች የእግዚአብሔር ልጆች እግዚአብሔር ይህን ትምህርት በህይወታቸው እንዳስተማራቸው፣ በእርሱም ላይ ጥገኛ እንዳደረጋቸው፣ በስህተት የተመኩባቸውን ነገሮቻቸውን ሁሉ ከውስጣቸው ነቅሶ በማውጣት የእርሱ ተደጋፊ እንዳደረጋቸው መስክረዋል።  በአብዛኛው የሚያጋጥመን ሥቃይና መከራ አላማው በእግዚአብሔር ጸጋ እና ኃይል ላይ ብቻ የማይቋረጥ ጥገኛነትን ማምጣት ነው።  መከራችን ፍጥረቱ የተነደፈውና የተሰራው በእኛ በራሳችን እንድንደገፍ ሳይሆን በእግዚአብሔር ችሎታ፣ ኃይል እና ዝግጅት እንድንመላለስ ነው። እርሱ ብቻ በገዛ ራሳችን አለን ከምንለው ሀብታችን እያላቀቀ ወደ ባለጠግነቱ ዘወር እንድንል ያደርገናል።

ምእመናን ይህን ስሙ፣ ሌሊቱ ሲነጋ፣ ፀሀይ ስትወጣላችሁ ሰማዩ ጥርት ያለ ሲሆን፣ የተነቃቃ ታላቅ ስሜት ሲሰማችሁ፣ ብዙ ገንዘብ ያላችሁና "ሀብታም ነኝና ባለጠጋ ሆኜአለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም" ለማለት ስትፈተኑ፣ ሁሉም ሰው ሲወዳችሁና ሁሉንም ሰው ስትወዱ፣ ተቀባይነታችሁና ተፈላጊነታችሁ ሲጨምር፣ ያኔ በእርግጠኝነት እግዚአብሔርን ችላ የማለት ዝንባሌ መኖሩ አይቀርም። እንዲህ ባለው ስኬት በሚመስል ውድቀት ውስጥ  በራሳችን የመታመን እና እግዚአብሔርን ሙሉ በሙሉ የመርሳት ዝንባሌ በእርግጥ አለ።  እግዚአብሔር እስራኤላውያንን ስለ ብልጽግና አስጠንቅቋቸው የነበረው ለዚህ ነው።

ዘዳግም 8፥ 11 "ዛሬ እኔ አንተን የማዝዘውን ትእዛዙንና ፍርዱን ሥርዓቱንም ባለመጠበቅ አምላክህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ ተጠንቀቅ፤"

እግዚአብሔር እዚህ ላይ እስራኤላውያንን የሚያስጠነቀቃቸው፣ ስለ ድህነት አደጋ ሳይሆን ስለ ሀብት አደጋ ነው እያስጠነቀቃቸው ያለው።

ዘዳግም 8፥ 12-16 "ከበላህና ከጠገብህ በኋላ፥ መልካምም ቤት ሠርተህ ከተቀመጥህበት በኋላ፥ የላምና የበግ መንጋ ከበዛልህ በኋላ፥ ብርህና ወርቅህም ያለህም ሁሉ ከበዛልህ በኋላ፥ ልብህ እንዳይጓደድ፤ ከግብፅም ምድር ከባርነት ቤት ያወጣህን፥ እባብና ጊንጥ ጥማትም ባለባት፥ ውኃም በሌለባት፥ በታላቂቱና በምታስፈራው ምድረ በዳ የመራህን፥ ከጭንጫ ድንጋይም ውኃን ያወጣልህን፥ በመጨረሻም ዘመን መልካም ያደርግልህ ዘንድ ሊፈትንህ ሊያዋርድህም አባቶችህ ያላወቁትን መና በምድረ በዳ ያበላህን አምላክህን እግዚአብሔርን እንዳትረሳ፤"

ልባቸው እንዲጓደድ፣ በትዕቢት እንዲኮሩና ጌታን እንዲረሱ የሚያደረጋቸው ድህነታቸው ሳይሆን የሚያከማቹት ሀብት መሆኑን ልብ በሉ።

ይህንኑ ሃሳብ በምሳሌ መጽሐፍ ውስጥ እናያለን።

ምሳሌ 30፥ 8-9 "ከንቱነትንና ሐሰተኛነትን ከእኔ አርቃቸው፤ ድህነትንና ባለጠግነትን አትስጠኝ፤ ነገር ግን የሚያስፈልገኝን እንጀራ ስጠኝ፥ እንዳልጠግብ እንዳልክድህም፦ እግዚአብሔርስ ማን ነው? እንዳልል፤ ድሀም እንዳልሆን እንዳልሰርቅም፥ በአምላኬም ስም በሐሰት እንዳልምል።"

ስንጠግብ፣ ሁሉም ነገር ሲስተካከል ጌታን የመካድ አደጋም አብሮት አለ።

ቅዱሳን ስሙኝ፣ በእውነቱ ለአንድ አማኝ የዚህ ምድር ህይወቱ በጣም ከባድ ሊሆንበት የሚችል መሆኑ ነው፤  እግዚአብሔርም በእርሱ ስንታመን ጤናንና  ሀብትን ሊሰጠን የገባው ቃል የለም። እግዚአብሔርን በመምሰል የምንኖር ከሆነ ግን ስደት እንደሚደርስብን ቃል ገብቷል።  የወንጌል መልእክትም እነ ጆኤል ኦስቲንና መሰሎቻቸው አጣመው እንደሚያስተምሩት በድህነት እና በበሽታ ላይ፣ በማህበራዊ ግንኙነቶችም ተቀባይነት ማጣት ላይ በድል አድራጊነት ፈጽሞ ስለመኖር አይደለም። ወንጌል በብቸኝነት የሚናገረው እግዚአብሔር በእርሱ ለሚታመኑት ሁሉ የኃጢአትን ዕዳ ለመክፈል የሚወደውን አንድያ ልጁን መስዋዕት አድርጎ ስለማቅረቡ ነው።  እግዚአብሔር የዘላለም ሕይወትን ሊሰጠን እንጂ የሀብትና የመጽናናት ሕይወት እንድንኖር ቃል አልገባልንም።

እግዚአብሔር በእርሱ እንድንታመንና፣ በእርሱ ላይ በመታመን ብቻ እንድንኖር ይፈልጋል፣ ያንንም ለማድረግ የሚረዱን የህይወት ፈተናዎቻችን ናቸው።

ስለዚህ ጆኤል ኦስቲን "አጠቃላይ የድል ህይወት" እያለ በሚሰብከው የቅዠት አለም ውስጥ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፈጽሞ እንዳልኖረበት ወንጌሉ ነግሮናል፤ ሐዋርያትም ሆኑ የየዘመኑ ቅዱሳን ሁሉ ባለፉት ዘመናት እንዲህ ባለ ቅዠት አልኖሩም።  ወደ ቅዱሳት መጻሕፍት ስትጠጉ ይህ የጤና/ብልጥግና ወንጌል ፈጽሞ መጽሐፍ ቅዱሳዊ እንዳልሆነ ታያላችሁ።  ታዲያ ብዙዎች ይህንን የውሸት መልእክት በውድ ዋጋ እየገዙ ወደዚህ ትምህርት የሚሳቡት፣ የነዚህ ኃሰተኞችስ ግባኤ በብዙ ቁጥር እያደገ የመጣው ለምንድነው? በመጀመሪያ ስለ እድገታቸው መገረምና መደነቅ የለብንም ምክንያቱም ካንሰርም ያድጋል። እኔ እንደማስበው ግን የዚህ እድገት ዋናው ምክንያት የትምህርቱ ድምጸት በጣም ጥሩ ስለሚመስል ነው።  መቼም ቢሆን ጤናማ ለመሆን፣ ሀብት ለማግኘት፣ ከችግርም ነጻ የሆነ ኑሮ መኖር የማይፈልግ ማን ሰው አለ?  ስለዚህ የስብከቱ ድምጸት ጥሩ ስለሚመስል ብዙ ሰው ይከተለዋል። ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ በጣም ጥቂት ሰዎች ብቻ መጽሐፍ ቅዱሳቸውን በቅጡ ስለሚያውቁ፣ አብዛኛው ግን ቃሉን መማርና ማወቅ እምቢ ስላለ፣ ወይም ንጹሁን ወንጌል የሚያስተምረው ስላጣ ይህ የጤና/ብልጥግና ወንጌል እግዚአብሔር ለእነርሱ እንዲሰሙትና እንዲከተሉት የሚፈልገው ነው ብለው ስለሚያስቡ ነው።  አማኞች በዚህ ኢ-መጽሐፍ ቅዱሳዊ በሆነ አጉል ትምህርት ውስጥ ሲጠመዱ ስናይ በቅዱሳን መካከል ይህንን የሚመዝን መለኪያ ድምጽ በመሆን ኃሰትን ለመጋፈጥ የእግዚአብሔርን ቃል እውነት አውቀን ልንቆም ይገባናል።

በአገራችንም እንደ አሸን የፈሉት የጥፋት ወንጌል ሰባኪዎች ቢከፍቱት ተልባ የሆነው ዲስኩራቸው ምንጩና መሰረቱ ይኸው ከላይ በስፋት የተቸነው መስቀል አልባ የትምህርት ቅዠት ነው። ስራ ጠል የሆኑ ቁጭ ይበሉዎች በኃሰተኛ ትንቢታቸው እያዋዙ ሕዝብ በሚያደነቁሩበት የትባረካላችሁ ስብከት መንጋው እየከሳ ዘርፈው የጠገቡ እነርሱው ብቻ ናቸው። "ማን መጥቶ ባሳሳተን" በሚል ክፉ ምኞት ተይዘው ላይ ላዩን የሚጋልቡና አጥብቀው የማጠይቁ ሰነፍ የቤተስኪያን ደንበኞችም ይጠፉ ዘንድ ለዚህ የተመደቡ ናቸው፤ ቃሉንም ከመማር ርቀው በዝነኞቻቸው የትምህርት ንፋስ ተጠርገዋል። ብዙ ዘመን በውሃ ውስጥ የኖረ ጥቁር ድንጋይ ውሃው ወደውስጡ እንደማይገባ ሁሉ እነዚህም ደጋግመን በወንጌል ያስጠነቀቅናቸው ሆነው ሳሉ ትምህርታችንና የምክር ቃላችን አልገባቸውም።

እንግዲህ በብዙ ዝርዝር ልናየው የሞከርነውና ይህ “የጥፋት ወንጌል” ስል የሰየምኩት የጤና/ብልጥግና ወንጌል አደገኛነቱ ሊሰማን ይገባል።  የዚህ ወንጌል አራማጆች እንደሚደሰኩሩት እግዚአብሔር አማኞች ሁሉ ጤናማና ባለጸጋ እንዲሆኑ፣ ከየትኛውም አካላዊ ስቃይና መከራ ነጻ እንዲሆኑ፣ በሚያደርጉት በማናቸውም ነገር እንዲበለጽጉና እንዲከናወንላቸው ይፈልጋል ብለው ያስተምራሉ።  በመግቢያዬ ላይ እንዳመለከትኩት ይህ ጥሩ ዜና ይመስላል።  ብቸኛው ችግሩ ግን እውነት አለመሆኑ ነው። ይህም መጽሐፍ ቅዱስ የሚያስተምረው ወንጌል ሳይሆን ሰዎች ሊሰሙት የሚፈልጉት "ማጽናኛ" (ማዝናኛ ቢባል ይቀላል) እና ስሜትን የሚኮረኩር ማነቃቂያ ብቻ ነው።

የዚህ የጤና/ብልጥግና ወንጌል ሰባኪዎች የሚያደርጉት አንድ ክፉ ስራ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሀብት የሚናገረውን ዋና መልዕክት ገልብጠው ስሜታችን ሊሰማው የሚፈልገውን እየደሰኮሩ ባህላችን ስለ ሀብት/ብልጽግና በሚናገረው ለመተካት የሚያደርጉት እውር ጥረት ነው።  እርግጥ ነው፣ “እግዚአብሔር ባለጠጋ ሊያደርግህ ይፈልጋል” የሚለውን መልእክት ስትሰብክ፣ ትርጉሙ አጠቃላዩ የወንጌል መልእክት ስለ እኛና ስለ ፍላጎቶቻችን ነው የሚል ብቻ ሳይሆን፣ ወንጌሉ እግዚአብሔር ፍላጎቶቻችንን እንዲያሟላልን የምናደርግበት መንገድ፣ በራሳችንም ላይ ብቻ እያተኮርን ራስ ተኮር በሆነ ህልማችን የምንወሰድበትም ጭምር ይሆናል። ያኔ የእኛ ትክክለኛ የህልውናችን ማእከልም የፍላጎቶቻችን መሟላት እንጂ ራሱ እግዚአብሔር አይሆንም።  ከእግዚአብሔር ጋር የምንገናኘው ከእግዚአብሔር ልናገኘው በምንችለው ነገር ብቻ ነው ማለት ነው። ትክክለኛው የህልውና ማእከላችንም "እግዚአብሔር ስኬታማ የአኗኗር ደረጃዬን ይባርክልኝ" በሚል ምኞት የሚነዳ በራሳችን ላይ ያተኮረ የብልጽግና እና የስኬታማ የህይወት ዘይቤአችን መሆኑ ነው። 

(gkr)

Friday, June 2, 2023

ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያው

ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፩

“የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ” የሚለው ይህ በማርቆስ 14፥ 61-62 ያለው ቃል እና በዮሐንስ 21፥ 22-23፣ ያለው ቃል፣ ሊቀ ካህናቱ ቀያፋ እና ሐዋርያው ​​ዮሐንስ የጌታን ዳግም ምጽአት በአይናቸው ለማየት በህይወት እንደሚኖሩ ኢየሱስ የተናገረው የታመነ ቃል ነው።

በማርቆስ 14፥ 61-62፣ ኢየሱስን እንዲገደል ለሮማውያን አሳልፎ የሰጠውን ሊቀ ካህናቱን ቀያፋን በተመለከተ የሰው ልጅ በሰማይ ደመና ሆኖ ሲመጣ እንደሚያየው በግልጽ ነግሮታል። እንደገናም በዮሐንስ 21፥ 22-23፣ እንደተጻፈው ሐዋርያው ​​ዮሐንስ ኢየሱስ ተመልሶ እስኪመጣ ድረስ በሕይወት ኖሮ እንደሚቆይ ተነግሮታል። ኢየሱስም በማቴዎስ 16፥ 27-28፣ በማቴዎስ 24 እና ማርቆስ 8፥ 38-9፥ 1 ባለው ክፍል ላይ በዚያው ትውልድ እንደሚመለስ ቃል ገብቷል። ኢየሱስ ስለዳግመኛ ምጽአቱ ደጋግሞ ከተናገራቸው እንደነዚህ ካሉት ንግግሮቹ የተነሳ ደቀ መዛሙርቱም ሆኑ የጥንት ቤተክርስቲያን ምዕመናን በሙሉ ኢየሱስ በህይወት ዘመናቸው ተመልሶ እንደሚመጣ በብዙ ያምኑና ይጠባበቁ እንደነበር መላው የአዲስ ኪዳን መልዕክቶች ያሳያሉ። ይህንን በበቂ ሊያስተባብልና ሊቃወም የቻለ ሥነመለኮት ፈጽሞ የሌለ በመሆኑ ፓሮውዥያው ከፍ ሲል በተጠቀሱት አይነተኛ ሰዎችና በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ቅዱሳን ትውልድ ውስጥ ተፈጽሟል ብሎ በዚህ እምነት ለመቆም ፕሪቴሪዝም ከተረትና ከልማድ ርቆ የእግዚአብሔርን ቃል ብቻ መሰረት አድርጓል።

ፕሪቴሪዝም ይለመልማል።

አልጨረስኩም 

(GKR)


ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፪

ስለ ፓሮሺያ ቅድመ ፕሪተርስት እይታ–

“የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ”፡- 

"ታያላችሁ" የተባሉት እና ይህ ሲሆን ያዩ ዘንድ የተገባቸው እነማን እንደሆኑ ካላወቅን፣ "ታያላችሁ" የተባሉት ሊያዩ የተገባቸውን ካላዩ፣ ጌታም በኃይል ቀኝ መቀመጡንና በሰማይ ደመና መምጣቱን እስካሁን ካላሳያቸውና፣ ታያላችሁ የተባሉት ሊያዩ የተገባቸውን ሳያዩ ካለፉ፣ እኛን ጨምሮ ከዚያስ በኋላ ባለው ትውልድ የኖረና ገና ወደፊት የሚመጣ ሌላ ትውልድ ይህንን ሊያይ እንዴት ይችላል?  ጌታስ እንዴት ታማኝ ይሆናል? እኛ እናይ ይሆናል የምትሉ ሁሉ እውነት እላችኋለሁ፣ ታያላችሁ ከተባሉት በቀር ማንም ቢሆን ይህ ሲሆን የሚያይ ከዚህ በኋላ እንደማይኖር ታውቁ ዘንድ እወዳለሁ።

ተመልከቱ፣ ዳግም ምጽአት በራእይ 19፥ 11-14 እንዴት እንደተገለጠ ተዘግቧል።  በዚያም የራእዩ ክፍል ኢየሱስ የመላእክትን ሠራዊት በሰማይ ላይ ሲመራ ይታያል። እንዲህ ሲል፦

"ሰማይም ተከፍቶ አየሁ፥ እነሆም አምባላይ ፈረስ፥ የተቀመጠበትም የታመነና እውነተኛ ይባላል፥ በጽድቅም ይፈርዳል ይዋጋልም። ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ናቸው፥ በራሱ ላይም ብዙ ዘውዶች አሉ፥ ከእርሱም በቀር አንድ እንኳ የማያውቀው የተጻፈ ስም አለው፤ በደምም የተረጨ ልብስ ተጐናጽፎአል፥ ስሙም የእግዚአብሔር ቃል ተብሎአል። በሰማይም ያሉት ጭፍራዎች ነጭና ጥሩ ቀጭን የተልባ እግር ልብስ ለብሰው በአምባላዮች ፈረሶች ተቀምጠው ይከተሉት ነበር።" 

ፕሪቴሪዝም ይህ ቃል በጊዜው ለዚያውም በገሃድ እንደተፈጸመ ያምናል። የዚህ ትንቢታዊ ራእይ ታሪካዊ ፍጻሜ ደግሞ የሰው ልጅ የሆነው ጌታ ኢየሱስ፣ በ66 ዓ.ም በአይሁድ ሮም ጦርነት መጀመሪያ ላይ በደመና ውስጥ በገሃድ መታየቱ ነው። ይህንን ታሪካዊ ክስተት እና ዘገባውን ከዚህ ቀደም በግርድፉ አካፍያችሁ እንደነበር ይታወሳል። በቀጣዩ ጽሁፌ ሰፋ አድርጌ በማስረጃዎቹ ላይ እመለሳለሁ። ይሁንና ግን ይህ ታሪካዊ ማስረጃ ባይኖረን እንኳ፣ ክርስቶስ በዚያ ከተማይቱና መቅደስዋ ፈጽመው በሚፈራርሱበት የአይሁድ ሮም ጦርነት ወቅት ተመልሶ ለመምጣት የሰጠውን ተስፋ እንደፈጸመ ያለጥርጥር ማመን ይቻለናል። ምክንያቱም እንደዚያ እንድናምን በእግዚአብሔር ቃል ብቻ ተይዘናልና። 

ተመልከቱ፣ ዳግመኛ ምጽአቱ በራዕይ 19፥ 11-14 በዝርዝር እንደተገለጸዉ ጌታ ኢየሱስ በነጭ ፈረስ ላይ ተቀምጦ የመላእክትን ሠራዊት እየመራ በደመና ላይ የታየበት ነው። ይህ ቃል እንዴት እንደተፈጸመና የዳግም ምጽአቱ ገሃዳዊ መታየት ምን እንደሚመስል፣ ታሪክም እንዴት ዘግቦ እንዳስቀመጠው በሚቀጥለው ክፍል እናያለን። 

ከዝባዝንኬ ተረትና የቆየ ልማድ ርቃችሁ የእግዚአብሔርን ቃል ብቻ ማመንና መታዘዝ ይበዛላችሁ ዘንድ እጸልያለሁ። ጌታም በነገር ሁሉ ማስተዋልን ይስጠን። 

(GKR)


ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፫) 

የዳግም ምጽአቱ ቀዳሚ ፍጻሜ ታሪካዊ ምስክርነት—

“የሰው ልጅም .  .  .  በሰማይ ደመና ይመጣል”፡- 

አሁን የምታነቡትን ነገር ምናልባት ከዚህ ቀደም ያልሰማችሁት ታሪክ ሊሆን ይችላል። ዳሩ ግን ይህን ታሪካዊ ዘገባ ለሚያስተውለው ሰው ከዘሙኑ ፍጻሜና ከጌታ ዳግም ምጽአት ምንነት አንጻር አእምሮን ሊይዝ የሚችል ብርቱ ምስክርነትእንደሚሆንቡት አልጠራጠርም። የዳግም ምጽአቱ ኹነት በአይሁድ ሮም የጦርነት ታሪክ ተዘግቦ ትውልድ እንዲያነበው ተቀምጧልና። አሁንም ደግሜ እላለሁ፣ ይህ ታሪካዊ ማስረጃ ፈጽሞ ባይኖረን እንኳ፣ ክርስቶስ በዚያ ከተማይቱና መቅደስዋ ፈጽመው በሚፈራርሱበት የአይሁድ ሮም ጦርነት ወቅት ተመልሶ ለመምጣት የሰጠውን ተስፋ እንደፈጸመ ያለጥርጥር ማመን ግን ይቻለናል። ምክንያቱም እንደዚያ እንድናምን በእግዚአብሔር ቃል ብቻ ተይዘናልና። ሆኖም የክርስቶስን ቃል ለሚጠራጠሩ ላልተማሩና ለሚስቱ ወገኖች ስንል ታሪካዊ ዘገባዎችን አንስተን እንይ፦

….ከዚያ ከበዓሉ ጥቂት ቀናት በኋላ፣’… በ21ኛው በአርጤምስየስ [ጂያር] ቀን… “አንድ አስደናቂ እና ሁሉንም ያስገረመ ክስተት ታየ። ይህ ክስተት ሲፈጸም ታሪኩን በገዛ አይናቸው ባዩት በነዚያ ሰዎች ህይወትና የእለት ተለት ኑሮ ውስጥ ምንም ተጽዕኖ ባይኖረውና፣ ከዚያም በኋላ ተከትለው የተፈጸሙ ድርጊቶች እንደነዚህ ያሉ ምልክቶች የሚገባቸው አይነት ትላልቅ ተፈጥሮ ያላቸው ክስተቶች ባይሆኑ ኖሮ፣ እኔ ራሴ ታሪኩ ተረት ይመስላል ብዬ ባሰብሁና ትኩረት ሰጥቼ ሳልዘግበው በተውኩት ነበር፤ የታየውና የሆነው ግን ይሄ ነው፣ ፀሐይ ከመጥለቋ በፊት ሠረገሎችና በላያቸው ላይ ተቀምጠው የሚጋልቡ የታጠቁ የሰራዊት ጭፍሮች በደመናው መካከል ወዲህና ወዲያ እየተሯሯጡ ከተማይቱን ሲከብቧት ታዩአቸው። ከዚህም በላይ በዓለሃምሳ ብለን በምንጠራው በዚያ የበዓል ቀን ካህናቱ በሌሊት እንደ ልማዳቸው ወደ ውስጠኛው የቤተ መቅደሱ ክፍል ገብተው የዘወትሩን አገልግሎታቸውን እይፈጸሙ ሳለ፣ በመጀመሪያ ለራሳቸው ብቻ የሚታወቅ መሸበርና ፍርሃት ይሰማቸው እንደነበሩ ሲገልጡ፣ በታላቅ ድንጋጤም ውስጥ ሆነው እየተንቀጠቀጡ የሰሙት ታላቅ ድምፅ "ኑ ከዚህ በኋላ ይህንን ስፍራ ለቅቀን እንሂድ” የሚል እንደ ብዙ ሕዝብ ያለ ድምፅ ነበር። (Wars, 6-5-3, አንቀጽ 297-299)



በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ይኖር የነበረው አይሁዳዊ የታሪክ ጸሐፊ ጆሴፈስ በራእይ 19፥ 11-14 ላይ ኢየሱስ ይመራው እንደነበረው ያለ ሠራዊት በደመና ውስጥ የተመመውን ሰማያዊ ሠራዊት በትረካው ገልጿል። ይህ ክስተት በሌሎች የታሪክ ተመራማሪዎችም ተዘግቧል። በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ይኖር የነበረው ሌላው አረማዊ የታሪክ ጸሐፊ ታሲተስም ይህን ክስተት ጠቅሶ "በሰማይ ውስጥ የሰራዊት ግጭትና የሚያብረቀርቅ የጦር ራእይ ታየ" ሲል ጽፏል [Tacitus The Histories 5.13.]። ፕስዩዶ ሄጌሲፐስም በዚያን ጊዜ ከኃያላን መላእክቱ ጋር የክርስቶስን በደመና ላይ መምጣቱን ሲገልጽ እንዲህ ሲል ጽፏል፦"“የአይሁድ መጻሕፍት እንደ ገለጹት ብዙዎች ያዩት እጅግ ታላቅ ​​የሆነ ምስል በሰማዩ ላይ ታየ፤ ፀሐይም ሳትጠልቅ በደመና ውስጥ ሰረገሎችና የታጠቁ የጦር ሠራዊቶች በደመናት ላይ ሆነው ሲርዋርዋጡ ታዩ፤  የይሁዳ ከተሞችንና ግዛቶቿንም ሁሉ ወረሩ።" [Pseudo-Hegesippus 44.] የመካከለኛው ዘመን አይሁዳዊ የታሪክ ምሁር ሴፈር ዮሲፖንም በ66 ዓ.ም ሰማይ ላይ ስለነበረው የመላእክት ሠራዊት እንዲህ ሲል ገልጾታል፦ “በዚያም ወራት የእሳት ሰረገሎችና ፈረሰኞች፣ ታላቅ ሠራዊትም ሆነው በሰማዩ ላይ እየበረሩ ወደ ምድር በቀረቡ ጊዜ በኢየሩሳሌምና በይሁዳ ምድር ሁሉ ላሉ ሰዎች የእሳት ፈረሶችና የእሳት ፈረሰኞች ሲመጡ ታዩአቸው" [Sepher Yosippon A Mediaeval History of Ancient Israel በተሰኘውና Steven B. Bowman ከዕብራይስጥ ቋንቋ የተረጎመው ሲሆን በምዕራፍ 87 “Burning of the Temple” ከተሰኘው ክፍል ላይ የተጠቀሰ ነው] በተጨማሪም፦


http://fulfilledtheology.ning.com/forum/topics/historical-records-with-some (9/16/2014) በተሰኘው ድረ ገጽ ላይም  ተጠቅሶ ይገኛል። 

እንግዲህ ልብ ብለን ካየነው በእነዚህ ሦስት ዘገባዎች እና በራእይ 19 መካከል ያለው ተመሳሳይነት በእጅጉ አስደናቂ ነው። በመሆኑም፣ በዮሲፖን ዘገባ እንደሰፈረው 2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 ላይ ያለውና "ጌታ ኢየሱስ ከሥልጣኑ መላእክት ጋር ከሰማይ በእሳት ነበልባል ይገለጣል" የሚለው ቃል በ66 ዓ.ም ላይ በነበረው የአይሁድ ሮም ጦርነት መባቻ ላይ እንዴት ግልፅ እና ተዳሳሽ በሆነ መልኩ እንደተፈጸመ ማየት እንችላለን። ያ የመጅመርያው ክፍለ ዘመን የአይሁድ ሮም ጦርነት በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ ከተካሄዱ ጦርነቶች ሁሉ ይልቅ የከፋው ብቻ ተብሎ የሚወሰድ አይደለም። በሁለት ህዝቦች መካከል የተደረገ ግጭት ብቻም ሳይሆን፤ መለኮት ያስከተተው፣ የሰው ልጆችን ታሪክና መጻኢ እድል ሊቀይር ሰማይ ራሱ የዘመተበት፣ በአይሁድ ቅዱሳት መጻህፍት በብዙ የተነገረለት የፍጻሜው አርማጌዶን ነበር። ያ የጦርነት ታሪክ ግንዛቤ ውስጥ ሳይገባ የሚደረግ የአዲስ ኪዳን ትንቢት ትርጓሜ ሁሉ ቤተክርስቲያንንና ትምህርቷን ወደማይረባ የተረት ዝባዝንኬ ውስጥ እየዶለ እምነቷንና ተስፋዋን የአለም መሳቂያና መሰደቢያ እያደረገ፣ ሰዎችንም ከእምነት ይልቅ ለክህደት የሚጋብዝ ሆኖ መቀጠሉ አይቀርም።

በሚቀጥለው ጥሁፍ ይህ ታሪካዊ ሰማያዊ ክስተት የትንቢት ፍጻሜ ሆኖ ለመወሰድ እንዴት የመለኮታዊ መገለጥን መስፈርት እንደሚያሟላ በመጽሐፍ ቅዱሳዊ  በማስረጃ እንመለከታለን። 



ቸር ሰንብቱ

(GKR)


ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፬) 

የዳግም ምጽአቱ ፕሪቴሪስታዊ እይታ— በቀደመው ጽሁፌ የዳሰስሁት ታሪክ ዘግቦ ያቆየልን ሰማያዊ ክስተት የትንቢት ፍጻሜ ሆኖ ለመውሰድ እንዴት የመለኮታዊ መገለጥ መስፈርትን እንደሚያሟላና፣ ያ በእስራኤል ሰማይ ላይ የታየው ትንግርት የጌታ መምጣት መሆኑን፣ እርሱም በቀደመው ኪዳን የአምላክ አመጣጥ ሁናቴ የተብራራ እንደሆነ ጨምረን እንመለከታለን፦

“የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ”

ዮሲፖን በ66 ዓ.ም የሰማይ ላይ የእሳት ሠራዊት በሰማይ ላይ መታየቱን አስመልክቶ የሰጠው ታሪካዊ ዘገባ በብሉይ ኪዳን ቀደም ሲል በኢሳይያስ 66፥ 15፤ በመዝሙረ ዳዊት 68፥ 17 እና በዕንባቆም 3፥ 1-8 የተገለጠውን የጌታን መምጣት መግለጫና መስፈርት በሚገርም የቃል በቃል ንግግር የሚያሟላ ነው።  ያህዌ በጥንቱ ዘመን ወደህዝቦችና መንግስታት በፍርድ እና በምርት ይመጣ የነበረበትን መንገድ በሚመስልና በሚስተካከል አኳኋን የ66ቱ ዓ.ም ክስተትም እንዲሁ ነው።

በ66 ዓ.ም በፈረሶችና በሰረገሎች እየጋለቡ በእስራኤል ሰማይ ላይ ለታዩ እሳትማ መላእክቶች ፊት አውራሪ ሆኖ ክርስቶስ መምጣቱ  በ2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 ላይ "ጌታ ኢየሱስ ከሥልጣኑ መላእክት ጋር ከሰማይ በእሳት ነበልባል ይገለጣል"" ሲል የተተነበየውን ቃል በቃል ፍጻሜ ይሰጠዋል። ይህም በኢሳይያስ 66፥ 15 ላይ "እነሆ፥ እግዚአብሔር መዓቱን በቍጣ፥ ዘለፋውንም በእሳት ነበልባል ይመልስ ዘንድ ከእሳት ጋር ይመጣል፥ ሰረገሎቹም እንደ ዐውሎ ነፋስ ይሆናሉ።" ሲል የተነገረውን የጌታን አመጣጥ በሚያስገርም ሁኔታና ቀጥተኛ በሆነ መንገድ ያንጸባርቃል። በመዝሙር 68፥ 17 እና ዕንባቆም 3፥ 1-8 ላይ የተገለጠው በፍርድ የሆነው የጌታ አመጣጥ ገለጻዎችም በተመሳሳይ መልኩ የሚታዩ ናቸው። የሚገርመው፣ በ66 ዓ.ም በእስራኤል ሰማይ ላይ ታይቶ የነበረው እሳትማ የመላእክት ፈረሰኞችና ሠረገላዎች በጥንታዊ የእስራኤል ታሪክ ውስጥ የተለመደ በመሆኑ እንደዚህ ያለ ትዕይንት ሲዘገብ ይህ የመጀመሪያው አልነበረም።

ይህ በዮሲፖን የተዘገበውና  በ66 ዓ.ም በሰማይ ላይ የታየው የመላእክት የእሳት ሠራዊት መግለጫ በ2ኛ ነገሥት 6፥ 17 ላይ ከብዙ ዘመን በፊት የተገለፀውን የእሳት መላእክት ሠራዊት በትክክል ያንጸባርቃል።

በዳግም ምጽአቱ ኢየሱስን አጅበው ከእርሱ ጋር ወደ ክብሩ ለመግባት ሲጠበቁ እንደነበሩት ቅዱሳን ሁሉ በ2ኛ ነገሥት 6፥ 17 ላይ ኤልሳዕም በመላእክት ሠራዊት ይጠበቅ እንደነበር እናያለን። ይህ እሳትማ የመላእክት ሠራዊት በዮሲፖን እንደተዘገበው የፈረሰኞች፣ የፈረሶች እና የእሳት ሰረገሎች ሠራዊት ተብሎ በትክክል ተገልጿል። 2ኛ ነገ 6፥ 17 "ኤልሳዕም፦ አቤቱ፥ ያይ ዘንድ ዓይኖቹን፥ እባክህ፥ ግለጥ ብሎ ጸለየ። እግዚአብሔርም የብላቴናውን ዓይኖች ገለጠ፥ አየም እነሆም፥ በኤልሳዕ ዙሪያ ያሉት የእሳት ፈረሶችና ሰረገሎች ተራራውን ሞልተውት ነበር።" እንግዲህ በሁለቱም ሁኔታዎች ውስጥ የመላእክት ፈረሰኞች ሠራዊት እንደ ፈረሰኞችና የእሳት ሠረገላዎች መከሰታቸውን ልብ በሉ።

በሐዋርያት ሥራ 9፥ 3-6 ሳውል በአሳዳጅነት መንገዱ ላይ ተገልጦ ያየው ኢየሱስና እና በራዕይ 1፥ 13-16 በፍጥሞ ለዮሐንስ ተገለጦ በታየው መሰረት፣ ኢየሱስ በትንሳኤው ያለው አካል ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ የበለጠ የከበረ አካል እንደሆነ፣ ይህም እንደ ነበልባል እሳት የሚያበራ መሆኑን እናያለን። ይህ ዕፁብ ድንቅ ብርሃን የሳውልን አይኖች አሳውሮ በምድር ላይ ጥሎታል፤ በተለይ ለዮሐንስ ደግሞ በደረቱ ላይ ተጠግቶ ምስጢርን ከእርሱ ይሰማ እንደነበረበት ጊዜ ሳይሆን፣ ትእይንቱ በእግሩ ስር እንደሞተ ሰው አድርጎ የሚደፋው ነበር። 

"ራሱና የራሱ ጠጕርም እንደ ነጭ የበግ ጠጕር እንደ በረዶም ነጭ ነበሩ፥ ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ነበሩ፤ እግሮቹም በእቶን የነጠረ የጋለ ናስ ይመስሉ ነበር፥ ድምፁም እንደ ብዙ ውኃዎች ድምፅ ነበረ። በቀኝ እጁም ሰባት ከዋክብት ነበሩት፥ ከአፉም በሁለት ወገን የተሳለ ስለታም ሰይፍ ወጣ፤ ፊቱም በኃይል እንደሚበራ እንደ ፀሐይ ነበረ።"

ማንም ሊቀርበው በማይችል ብርሃን የሚኖር እርሱ ሲገለጥ ብረቱንና ናሱን የሚያቀልጥ ሁሉን የሚበላ እሳት ይሆናል። ከሙታን ተነስቶ ወደክብሩ የገባው ይህ ኢየሱስ እንደ አባቱ ሁሉ የሚያስፈራ፣ በማንነቱ ("በተፈጥሮው") የሚባላና ማንም ሊቀርበው የማይችል የእቶን እሳት ነው። ስለዚህ ይህ የኢየሱስ አካል በ2ኛ ነገሥት 6፥ 17፣ በ2 ቆሮንቶስ 11፥ 14 እና በማቴዎስ 28፥ 2-3 ባለው መሠረት የሰማይ መላእክትን ዓይነት መልክ የያዘ ነበር።

በ2ኛ ነገሥት 6፥ 17 ላይ ያሉት መላእክት እና በ66 ዓ.ም በዮሲፖን ዘገባ የተገለጹት የእሳት ፍጡራን ተመሳስለው ለምን ተገለጡ? በ2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ ​7 ላይስ ጌታ ኢየሱስ በዳግም ምጽአቱ ወቅት የሚነድ እሳትን የመሰለ መልክ እንደሚይዝ የሚናገረው ለምንድን ነው? ምንም እንኳን የኢየሱስ የትንሳኤ አካል ከእርገቱ አስቀድሞ ገና በምድር ሳለ ከሥጋዊ አካሉ ጋር ቢመሳሰልም፣ ነገር ግን በሐዋርያት ሥራ 1 ላይ ኢየሱስ ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ ይህ የተለወጠ ይመስላል (የሐዋርያት ሥራ 9፥ 3-6፣ ራዕይ 1፥ 13-16)። ወደ ሰማይ ካረገ በኋላ፣ በቀረው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ውስጥ የተገለጸው የኢየሱስ አካል በሰማይ ካለው አባቱና ስለ ሌሎች ሰማያዊ አካላት ከተሰጠው መጽሐፍ ቅዱሳዊ መግለጫዎች ጋር በቅርበት ይመሳሰላል። ለምሳሌም፣ ነብዩ ሕዝቅኤል በትንቢቱ ምዕራፍ 1፥ 26-28 ባለው ክፍል የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ መልክን በራእይ አይቶ፣ "የእግዚአብሔር ክብር እንደ እሳት ምስያ ያበራል" ብሎ ሲናገር፣ በሐዋርያት ሥራ 9፥ 3-6 እና በራዕይ 1፥ 13-16 ላይ ኢየሱስን አስመልክቶ ከተሰጡት መግለጫዎች ጋር ተመሳሳይ በሆነ ሁኔታ ተነግሯል፦ "በራሳቸውም በላይ ካለው ጠፈር በላይ የሰንፔር ድንጋይ የሚመስል የዙፋን አምሳያ ነበረ፤ በዙፋኑም አምሳያ ላይ እንደ ሰው መልክ አምሳያ ነበረ። ከወገቡም አምሳያ ወደ ላይ የሚብለጨለጭ የወርቅ ምስያ አየሁ፤ ከወገቡም አምሳያ ወደ ታች እንደ እሳት ምስያ አየሁ፤ በዙሪያውም ፀዳል ነበረ። በዝናብ ቀን በደመና ውስጥ እንደ ቀስተ ደመና አምሳያ፥ እንዲሁ በዙሪያው ያለ ፀዳል አምሳያ ነበረ። የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ መልክ ይህ ነበረ። ባየሁም ጊዜ በግምባሬ ተደፋሁ፥ የሚናገርንም ድምፅ ሰማሁ።" 


ተመልከቱ፣ ከዕርገቱ በኋላ ያለው የክርስቶስ ትንሳኤ አካል ብሩህነትና ግርማው እንደ ጸሐይ ብሩህነ የሚያበራ መሆኑ በሐዋርያት ሥራ 9፥ 3-6 ውስጥም ተጠቅሷል፤ ጌታ ካረገ በኋላ የነበረውንና ጳውሎስን ለጊዜው በእውርነት የመታውንና የጣለውን ታላቅ ብርሃን ክፍሉ ያመለክታል። ዮሲፖን በትረካው በሰማይ ላይ የታዩት እነዚያ ትንግርታዊ ፈረሶች ምን አይነት እንደነበሩ ሲገልጥ የእሳት ፈረሶች እንደነበሩ ይናገራል፤ በራእይ 19፥ 14 ላይ ግን መላእክቱ ነጭ ፈረሶችን ይጋልቡ እንደነበር ይናገራል፣ ይህ ታዲያ ተቃርኖ ነው ወይ? በጭራሽ አይቃረንም። ወደ ሞት የቀረቡና የዚያ ራእይ ልምምድ ያላቸው በርካታ ሰዎች ከነቁ በኋላ ስላለፉበት የሞት ጽልመት ሲናገሩ በሰማያዊው ግዛት ውስጥ ያሉ ፍጥረታት በከፍተኛ ሁኔታ የሚያብረቀርቅ ነጭ ብርሃን እንደሚፈነጥቁ ሲገልጹ በተደጋጋሚ ይደመጣሉ። ስለዚህ በዮሲፖን ትረካ የተገለጹት ፈረሶችና ፈረሰኞች በሰማይ እንዳሉት ሌሎች ፍጥረታት ሁሉ በሚያንጸባርቅ ነጭ ብርሃን ውስጥ ሆነው ሳይታዩ እንዳልቀረ ይመስላል ማለት ነው።

በዚያን ጊዜ ጌታ ኢየሱስ የዚህ ሠራዊት ፊት አውራሪና ራስ ሆኖ ተገኝቶ መሆን እንዳለበት ከታሪካዊው ዘገባ እናስተውላለን፤ ይህም ግምታችን ብቻ አይደለም። ምንም እንኳን ኢየሱስ በደመና ውስጥ ባለው በዚህ የመላእክት ሠራዊት ራስ ላይ በውል ተለይቶ ባይታወቅም፣ በዚያ ተአምራዊ ትዕይንት ውስጥ ግን ያንን ሰማያዊ ጭፍራ ድል ለመንሳት አስከትቶ በግርማው የመጣው እርሱ ራሱ መሆን እንዳለበት ግልጽ ነው ብዬ አምናለሁ። በአገልግሎቱ ዘመን ሁሉ ሲናገር እንደነበረው ጌታ ኢየሱስ በአገልግሎቱ ወቅት በነበሩት አድማጭ ተመልካቾቹ ሰዎች የህይወት ዘመን በትውልዳቸው ውስጥ የሰማይ ሰራዊትን እየመራ በደመና ላይ ሆኖ እንደሚመጣ ይተንብይ ነበርና። ኢየሱስ በዚያ ሁኔታ ተመልሶ እንደሚመጣ ተንብዮ ከነበረ፣ እኛ በትንሽዋ አእምሮአችን ታሪክንና ክስተትን አነጻጽረን ከምንደርስበት ድምዳሜ በላይ የትንቢት ቃል የጸና እውነት መሆኑን እናውቃለን። በእስራኤል ሰማይ ላይ የታየው ይህ ልዕለ ተፈጥሯዊ የሆነ ክስተት ከሆነ፣ በእርግጥም የዮሐንስ ራእይ 19፥ 14 እና ሌሎች ስለ ዳግም ምጽአቱ የተነገሩ የመጽሐፍ ቅዱስ ገለጻዎችን ሁሉ አሟልቶ የሚፈጽመውም ከሆነ፣ እንግዲያውስ ኢየሱስ በደመና ላይ ባለው በዚህ ሠራዊት ራስ ላይ ፊት አውራሪው ሆኖ ተገኝቶ መሆን አለበት ማለት ነው። እሱ ባይሆን ኖሮ ግን ይህ ተአምራዊ ክስተት በጣም የአጋጣሚ ጉዳይ ብቻ ሊሆን ይችል ነበር ብለን ከትንቢት ፍጻሜ ደረጃ ማውረድ በቀለለን ነበር፤ ያንን እንዳናዱርግ ግን በትንቢቱ ቃል ተይዘኔል። ጌታ ኢየሱስ በስጋው ወራት ባገለገለው ማህበረሰብ እና በትውልዱ ውስጥ በሰማይ ደመናና በክብር ተመልሶ ለመምጣት ከሰጠው ጽኑና ተደጋጋሚ ተስፋው አንጻር ሲታይ ይህ ታሪክ ከትቦ ያስቀመጠው ተአምራዊ ክስተት የአጋጣሚ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን፤ ይልቁንም ይህ ክስተት የሰጠውን ተስፋ የሚሞላ በትክክልም የፓሮውዥያው ትንቢት ፍጻሜ ነበር። በተጨማሪም ኢየሱስ በዚህ የሰማይ ሠራዊት መሪነቱ ተለይቶ የታወቀ ከሆነ በጥቅሉ ይህ በደመና ውስጥ የታየው የሰራዊቱ ታሪካዊ ዘገባ ትንቢት መፈጸሙን ለማስረዳትና በክርስቲያናዊ መስተጋብር ውስጥ እምነታችንን ከጥቃት ለመከላከል በእጅጉ የሚረዳ ጠንካራ ማስረጃችን ተደርጎ ሊወሰድም ይችላል። ተመልከቱ፣ ክርስቲያን ያልሆኑ የታሪክ ሰዎች ስለ ክርስቲያናዊ የነገረ ፍጻሜ ጥናት ዝርዝሮች በጥልቀት ሊያውቁ የማይችሉ እንደመሆናቸው መጠን፣ እነዚያ ክርስቲያን ያልነበሩ ታሲተስ እና ጆሴፈስ የተባሉ የታሪክ ዘጋቢዎች በዘገባቸው እንዲህ ዓይነት ግልጽ መለያን ያደርጋሉ ተብሎ አይጠበቅም። በአንጻሩ ግን የታሪክ ዘገባቸው የዮሐንስ ራእይ መጽሐፍና የማቴዎ 24 ፍካሬ ማብራሪያ እስኪመስል ድረስ ታሪክ ባይነት ባይነቱ ተቀናብሮ መገኘቱን ስናይ፣ ትንቢት ለመፈጸሙ ማስረጃ የሚሆን ውጫዊ ሰነድ እግዚአብሔር በኪነ ጥበቡ እንዳሰናዳልን እናስተውላለን። ይህ ውጫዊ የታሪክ ሰነድ ደግሞ በባህርይው ውስጣዊ ለሆነው ጽኑ የትንቢት ቃል ሲገዛ እንደ ማየት ለቃሉ አማኝና ለቃሉ ተማሪ ምን የሚያስደስት ነገር ይኖር ይሆን! ታሪክ ለእግዚአብሔር ቃል ይሰግዳል። የዚህን ክስተት ታሪካዊ አስተማማኝነትና ማስረጃዎችን የበለጠ በዝርዝር ማብራሪያ ለማቅረብ የተሞከረበትን ጥናት ጊዜ ከተሰጠን ኋላ ላይ ቆየት እያልን እንመለስበታለን።

ለአሁኑ እዚህ ላይ ላብቃ፤ ቸር ሰንብቱ

(GKR)

ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያ (፭)

“የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ”

እንደ ታሲተስ ታሪካዊ ዘገባ ከሆነ፣ ያኔ በአይሁድ አመጽ መጀመርያ ላይ መብረቅ በርቆ መቅደሱን መትቶት ነበር፤ ይህም

የማቴዎስ 24፥ 27 ትንቢትን ፍጻሜ በሚሰጥበት መልኩ በዳግመኛ ምጽአቱ ወቅት የሚጠበቅ ክስተት መሆኑን እናውቃለን።

ማቴዎስ 24፥ 27 እንዲህ ይላል፡- “መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ፥ የሰው ልጅ መምጣት እንዲሁ ይሆናልና፤" 

ይህ ጥቅስ የሰው ልጅ በደመና ላይ ሲመጣ እንደ መብረቅ ሆኖ እንደሚመጣ የሚያመለክት ይመስላል። የመብረቅ መኖር ፓሮውዥያውን የሚያጅበው ክስተት መሆኑ በቃሉ እንደተገለጠ ሁሉ ከምጽአቱ ጋር ባለው ግንኙነት አብሮ ሊሆን እንደሚችል የሚያሳዩ የታሪክ ማስረጃዎች በ66 ዓ.ም የአይሁድ ዓመፅ መጀመሪያ ላይ በሮማውያን ታሪክ ጸሐፊ ታሲተስ ተመዝግቧል፦ "የጭፍሮች ግጭትና የሚያብረቀርቅ የጦር ትጥቅ፣ የፈረሶች ኮቴና የሰረገላ ድምጽ ራእይ ከፍ ብሎ በከተማይቱ ሰማይ ላይ ይታይ ነበር።  ድንገትም ከደመናው መሃል በኃይል የሚያበራ የመብረቅ ብልጭታ፣ የገሞራ እሳትም በመቅደሱ ላይ አበራ። ብራቅም ሆነ፤  የቅዱሱ ቦታ በሮችም በድንገት ተበርግደው ተከፈቱ፣ አማልክት እንደሚለቁት ያለና ሰው ሊያወጣው ከሚችለው በላይ የሆነ ድምፅም ተሰማ፣ እናም በዚያው ቅጽበት በችኮላ ስፍራውን ለቅቀው መሄዳቸውን የሚያመለክት የመለከት ድምጽ ሆነ።" [Tacitus The Histories 5.13]



በማቴዎስ 28፥ 2-3 ላይ እንደተገለጸው ሰማያዊ አካላት እንደ ጸሐይ የሚያንጸባርቅ መልክ እንዳላቸው ተነግሯል፤ ስለዚህም በማቴዎስ 24፥ 27 ክርስቶስ መብረቅ በሚመስል ብሩህ፣ አንጸባራቂ መልክ እንደሚገለጥ ሲነገር በፓሮዥያውም እንዲሁ ይፈጸማል። እንደ እውነቱ ከሆነ፣ ዳግመኛ ምጽአቱ ከምስራቅ ወጥቶ በስተምዕራብ ከሚታየው መብረቅ ጋር መነጻጸሩን ስናስተውል ያ የክርስቶስ መብረቃዊ ብርሃነ መለኮት ከዕርገቱ በኋላ በፓሮዥያው ላይ ያለውን ክብር የሚገልጽ መሆኑን እናያለን። ከኢየሱስ ትንሣኤ በኋላ የታየው የጌታ መልአክም በማቴዎስ 28፥ 2-3 በተነገረው መሠረት መብረቅ በሚመስል መልክ መገለጡን አስታውሱ፡-"እነሆም፥ የጌታ መልአክ ከሰማይ ስለ ወረደ ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ፤ ቀርቦም ድንጋዩን አንከባሎ በላዩ ተቀመጠ። መልኩም እንደ መብረቅ ልብሱም እንደ በረዶ ነጭ ነበረ።" በቀደመው የዚህ ጽሁፍ ክፍል እንደተገለጸው፣ ኢየሱስ ከዕርገቱ በኋላ በሥጋው እንደሚታወቅ አይደለም፤ ይልቁን ግን በግርማው የማይቀረብና የሚያስፈራ ሆኖ ተመሳሳይ አንጸባራቂ መልክን ይዟል፣ እርሱም ደግሞ እንደ መብረቅ ብራቅ ይመስላል። 

እንግዲህ በ66 ዓ.ም በሰማዩ ላይ ታይቶ የነበረው ያ የመላእክት ሠራዊትና የተሰማው የፈረሶች ኮቴና የሰረገላ ድምጽ ስለ ዳግመኛ ምጽዓቱ የተነገሩትንና የተገለጡትን ሁሉንም የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች በበቂ ያሟላል እያልሁ ደጋግሜ አጽንዖት የሰጠሁበትን ሃሳብ ልብ አድርጉ። ይህም ማለት ከላይ በታሪክ ጸሓፍያኑ ተዘግቦ ያየነው ያ ሰማያዊ ሰራዊት ስለ ዳግመኛ ምጽአቱ በዝርዝር የተነገሩትን ሁሉንም መጽሐፍ ቅዱሳዊ መግለጫዎች ፍጻሜ ይሰጣቸዋል ማለት ነው። ከዚህ ቀጥሎ በምንመለከታቸው ስምንት ነጥቦች ወደ ማጠቃለያዬ አልፋለሁ። እነዚህን ነጥቦችና የጠቀስኳቸውን የቅዱሳት መጻህት ምንባባት ከተከፈተ መጽሐፍ ቅዱስ ጋር ልትመለከቷቸው ካልወደዳችሁ ግን ኮስታራ የቃሉ ተማሪዎች ስላልሆናችሁ እዚህ ሩም ውስጥ ለናንተ የሚሆን ምንም መነባነብ አይኖርም። ነጥቦቹን እነሆ፦

  1. በማቴዎስ 24፣ ማቴዎስ 16፥ 28፣ ማቴዎስ 10፥ 23፣ ማርቆስ 8፥ 38-9፥ 1፣ ማርቆስ 14፥ 61-62፣ ዮሐንስ 21፥ 22 እና ራእይ 1፥ 7 የተተነበየው ይህ ክስተት የተፈፀመው በራሱ ኢየሱስ ትውልድ እና ዘመን፣ በሐዋርያቱና በጥንት ቤተክርስቲያን ዘመንና ትውልድ ውስጥ መሆኑ የታመነ ነው። ይህን አለማመን የእግዚአብሔርን ቃል አለማመን ብቻ ሳይሆን ራሱን ጌታችንን ውሸተኛ ማድረግ ነው፤ ውሸተኛ ጌታ ደግሞ እውነተኛ አዳኝ ሊሆነን አይችልም። እውነተኛ አዳኝ ከሌለን ደግሞ ክርስትና የለም። ስለዚህ አስተውሉ፣ ይህ የምጽአቱ ትንቢት የመጀመርያውን ክፍለ ዘመን ከሚሽፍነው ከዚህ የጊዜ ወሰን ውጭ በሌላ በየትኛውም ሌላ መጻኢ ዘመን ውስጥ የሚፈጸም ለመሆኑም ሆነ የፍጻሜውን ጊዜ አራዝመን ወደፊት ለመጠባበቅ ምንም አይነት የቃሉ ድጋፍ የለንም። ይህም የትንቢት ፍጻሜ ዘመን በቤተ ክርስቲያን ትውፊት ሲነገር በኖረው መሠረት እስከ ትራጃን ዘመነ መንግሥት ድረስ በህይወት እንደኖረ በሚገመተው በሐዋርያው ​​ዮሐንስ የሕይወት ዘመን ውስጥ፣ ማለትም በአንደኛው መቶ ክፍለ ዘመን የመጨረሻዎቹ አስርት ዓመታት አልያም በሁለተኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ ማለት ነው። [Eusebius The History of the Church 3.23.]

  1. በማቴዎስ 24፥ 30፤ ራእይ 1፥ 7 እና ማርቆስ 14፥ ​62 ትንቢት መሠረት ይህ ክስተት በደመና ላይ የሚፈጸም እንደሆነ ተዘግቧል።

  1. ይህ ልዕለ ተፈጥሯዊ የሆነና ብዙ መላእክትን እየመራ የመጣው የሰው ልጅ የሆነው ኢየሱስን የሚመስለው ሰማያዊ ትዕይንት ታሪካዊ ዘገባ በማቴዎስ 16፥ 27፣ በማርቆስ 8፥ 38፣ በ2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 እና በይሁዳ 14-15 የተጻፈውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ የትንቢት ቃል መሰረት ያደረገ መሆኑን ያሳያል። የትንቢቱ ቃል እና የታሪክ ጸሐፍያኑ ዘገባ እርስ በርሳቸው የተስማሙ ናቸው።

  1. ይህ በማቴዎስ 16፥ 27-28፣ በማቴዎስ 24፥ 27፣ በማቴዎስ 24፥ 30፣ በማርቆስ 14፥ 62፣ በራእይ 1፥ 7 እና በሐዋርያት ሥራ 1፥ 9-11 ያለውና  በታሪክ ውስጥ በገሃድ ፍጻሜውን ያገኘው ክስተትና መገለጡ የታወቀው (ቢያንስ በራእይ መልክ) ነበር።

  1. ይህ ክስተት የመብረቅ መኖርን  በሚያሟላ ይዘቱ  ታጅቦ በማቴዎስ ወንጌል 24፥ 27 ላይ የተጻፈውን ፍጻሜ ይሰጠዋል።

  1. ኢየሱስ በማቴዎስ 24፥ 27 እና በ2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 7 የተነገረውን ፍጻሜ በሚስጥ መልኩ በገሞራ እሳትና የመብረቅ ብልጭታን በሚመስል ደማቅ ብርሃን በሚበርቅና በሚያንጸባርቅ ሰማያዊ ሠራዊት ላይ ሆኖ ተገለጧል።

  1. ፓሮውዥያው የተጀመረው በራዕይ 8፥ 5 እና በራዕይ 14፥ 14 ላይ እንደተገለጸው የአይሁድ ሮም ጦርነት ሲጀመር ነው። ፓሮውዥያ የሆነው በ66 ዓ.ም ነበር ወይንስ በ70 ዓ.ም? የሚለው ጥያቄ ብዙዎችን ሊያወዛግብ ይችል ይሆናል፤ ፓሮውዥያ የግሪክ ቃል ሲሆን ቀላል ትርጉሙ መገኘት ወይም መምጣት ማለት ነው። በጥቅሉ ግን ለረጅም ጊዜ ቆይታ መምጣት ማለት ደግሞ ነው።  ፓሮውዥያ አጭርና፣ የአንድ ጊዜ ብቻ የክርስቶስ መገለጥ የሚመስላቸው በርካቶች ናቸው፤ ይህ ግን የቃሉን መሰረታዊ አጠቃቀም ካለመረዳት የዳበረ ተለምዷዊ አመለካከት ነው። ብዙውን ጊዜ ሰዎች ስለ ፓሮውዥያ ሲያስቡ፣ የክርስቶስን በደመና ላይ ለአንድ ጊዜ አጭር መገለጥ መምጣቱን ያስባሉ፣ ይህ ግን ልክ አይደለም። ፓሮውዥያ አጭርና፣ የአንድ ጊዜ ብቻ የክርስቶስ መገለጥ  ከሆነ፣ እንግዲያውስ ፓሮውዥያ የተሰኘው ቃል ይህን ክስተት ለመግለፅ የሚጠቀምበት እንግዳ የሆነ፣ ወይም ትክክለኛና ተገቢ ያልሆነ፣ ወይም ክስተቱን የማይመጥን ቃል ይሆናል።  ፓሮውዥያ አንድ ድል አድራጊ ጄኔራል፣ ወይም ንጉሠ ነገሥት ወይም ከፍተኛ ባለሥልጣን ወደ አንዲት ከተማ መምጣቱን ለማመልከት የሚያገለግል ቃል ሲሆን፣ የመንግስቱ መቀመጫ ወደሆነችው  ዋና ከተማው ከመመለሱ በፊት ለብዙ ጊዜ፣ ለብዙ ወራት ወይም  ረዘም ላለ ዓመታትና ጊዜ የጉብኝት ቆይታ ማድረጉን የሚያሳይ ቃል ነው። ለምሳሌ፣ የኔሮ ቄሳር ፓሮውዥያ በግሪክ ግዛቱ ውስጥ ለብዙ አመታት ተራዝሞ ቆይቷል።  ኔሮ በ66 ዓ.ም ላይ ግሪክ ደርሶ ወደ መንግስቱ መቀመጫ ወደ ታላቂቱ ሮም እስኪመለስ ድረስ ማለትም እስከ 67 ዓ.ም መጨረሻ ወይም በ68 ዓ.ም መጀመሪያ ድረስ ቆይታ አድርጓል። ስለዚህ ቃሉ በመሰረታዊ ትርጉሙና ጠቀሜታው ብዙ ጊዜ ሊመጣ ያለው ተመልሶ ከመሄዱ በፊት ያለውን እና የተራዘመ መገኘቱን ወይም ቆይታውን ያሳያል። የሆነ ሆኖ፣ ፓሮውዥያ በፊልጵስዩስ 2፥ 12 ላይ ጥቅም ላይ በዋለበት መንገድ እንደሚታየው፣ ይህ ቃል ከተለመደው የብዙዎች እሳቤ በተለየ ሁኔታ በአጠቃላይ መምጣትን እና ረጅም ቆይታን ወይም መገኘትን ያመለክታል።  ስለዚህ የኢየሱስ ዳግመኛ ምጽአት ወይም ፓሮውዥያም እንዲሁ ረጅም የጉብኝት ቆይታ ወይም መገኘት ያለው መምጣት እንደሆነ ይመስላል። ስለዚህም ፓሮውዥያ ከያዘው መስረታዊ ትርጉም ተነስተን በ66 ዓ.ም እንደጀመረ እና በ70 ዓ.ም እስከሆነው የእየሩሳሌም ውድቀት ድረስ እንደተራዘመ ልናምን እንችላለን።

  1. ለ1ኛ ተሰሎንቄ 4:፥ 16 ፍጻሜ በሚሰጥ መልኩ ይህ ሰማያዊ ሠራዊት በ66 ዓ.ም በሰማዩ ላይ ታይቷል፣ በዚያው ዓመትም የሙታን ትንሣኤ መጀመሪያ በሚመስል ሁኔታ ብዙ መንፈሳዊ አካላት ከምድር ሲነሱ ታይተዋል። 

[በ66 ዓ.ም የአይሁድ ዓመፅ ሲጀምርና ሠራዊቱ በደመና ውስጥ ከታዩ ጥቂት ቀናት ወይም ሳምንታት በኋላ፣ ብዙ መንፈሳዊ አካላት ከምድር ወጥተው እንደነበር  ካሲየስ ዲዮ እንዲህ ሲል ጽፏል፡- “የመጀመሪያዎቹ ሠራተኞች ምድሪቱን በነኩ ጊዜ ያኔ ደም ከእርስዋ ወጣ፣ ከባድ ጩኸት እና እሪታም ተሰማ፣ ብዙ መናፍስታዊ ምስሎችም ታዩ።  ኔሮ ራሱ ምንጣፉን በመያዝ ከአፈሩ የተወሰነውን እየበተነና እየነሰነሰ የተቀሩት ሁሉ እርሱን እንዲመስሉ አስገደዳቸው።  ሱኢቶኒየስ ይህንን ክስተት ሲዘግብ ኔሮ መሬቱን ሲሰብር ያኔ የመለከት ድምፅ ተሰምቷል።  የሙታን መናፍስት በተነሱበት ወቅት መለከት መሰማቱ ደግሞ በ1 ቆሮንቶስ 15፥ 52 ላይ ላለው ቃል ግልጽ ፍጻሜ ይሰጠዋል:- “መለከት ይነፋልና፣ ሙታንም የማይበሰብሱ ሆነው ይነሣሉ፤….” በማለት ተናግሯልና።  በራእይ 15፥ 8 ላይ እንደተገለጸው፣ እነዚህ የሙታን መንፈሶች ግን ሰባቱ መቅሰፍቶች እስኪፈጸሙ ድረስ ገና ህያዋን ሆነው ወደ ሰማይ አልገቡም ነበር። ይልቁን በአይሁድ ጦርነት መጀመሪያ ላይ የተነሡት እነዚህ መንፈሶች ግን ሰይጣን ሊደርስበት ወደማይችልበት ሥፍራ ለ1260 ቀናት ተወስደዋል፤ ይህም በ66 ዓ.ም በቲሽሪ ወር (መስከረም - ጥቅምት) ሮማውያን ለወረራ በመጡበት፣ የኔሮም ፓሮውዥያ በግሪክ በጀመረበትና ጀነራል ቲቶ በመጨረሻው መለከት በኢየሩሳሌም ላይ ጥቃት እስከጀመረበት እስከ 70 ዓ.ም ፋሲካ ድረስ ባለው ጊዜ መካከል ካለው የጊዜ ክፍተት ጋር ይዛመዳል ብዬ አምናለሁ።] 

ይህንን የሱኢቶኒየስ ዘገባ ከሰማእታቱ ፊተኛ ትንሳኤ ፍጻሜ ጋር ባለው ተዛምዶ የምንመለከትበት ሌላ ጥናት እድሜ ከሰጠን በሌላ ጊዜ ይዤ እቀርባለሁ። ለአሁኑ ፕሪቴሪዝምና ፓሮውዥያን ከታሪክ መዛግብት አንጻር በመጠኑ ለማሳየት የሞከርሁበትን ጥናት በዚሁ አበቃሁ

ቸር ሁኑ።
ግዛቸው /ቄስ/
♥♦♣♠♣♦♥♦♣♠♣♦♥♦♣♠

 

Saturday, May 27, 2023

ፕሪቴሪዝምና ተስፋችን


ፕሪቴሪዝምና ተስፋችን 

ተስፋችን ምንድን ነው? ምንስ ተስፋ አለን?

2ቆሮ 5፥ 1 "ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ፥ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘላለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንጻ እንዳለን እናውቃለንና።"

መግቢያ:-

ከበርካታ አመታት በፊት፣ የመካነ የሱስ ሴሚናሪ የስነመለኮት ትምህርት አጠናቅቄ እንደወጣሁና ገና በአፍላ የቅስና አገልግሎት ላይ እንዳለሁ ነው  በሙሉ ኃላፋውያን የነገረ ፍጻሜ ትምህርት መሳብና መገረም የጀመርኩት። ለማንበብና በወጉ ለማሰብ፣ እምነቴንም ለመመየቅ፣ ከማምነውና ከምወደው መጽሐፍ ቅዱሴም መልስ ለማግኘት ቀድሞ በብዙ ያልነበረኝ ትጋት የወቅቱ የለት ተለት ጥሞናዬም እንደነበር አስታውሳለሁ። ለበርካታ አመታት በውስጤ ሲያወዛግቡኝ የነበሩ ስነመለኮታዊ የነገረ ፍጻሜ ጥያቄዎቼም ቀስ በቀስ እየተመለሱ፣ የተፈጸመውን ወንጌል በደስታ ለመቀበልና ትንቢት ሁሉ ተፈጽሟል ብሎ ለማመን ብዙ ጊዜ አልፈጀኝም። ምናልባትም ያኔ ጥቂት አጠገቤ ለነበሩ ለሚሰሙኝና ለምሰማቸው ካልሆነ በቀር የነገረ ፍጻሜ አቋሜንና እይታዬን ማስተዋል የተቻላቸው ግን እምብዛም አልነበሩም። ይሁንና ከጊዜ ወደጊዜ ባንጽባርቅሁአቸው እይታዎቼ፣ ይልቁንም አብዛኛውን የብቸኝነት ወራት ባሳለፍሁበት የአራት አመት የቱርክ ምድር ቆይታዬ በሰፊው ለማንበብና ለማሰላሰል እድሉን በማግኘቴ ይህ የተፈጸመ የነገረ ፍጻሜ ምልከታ በእጅጉ እየማረከኝና እየወረሰኝ እንደመጣ ግን አስተውያለሁ። እኔም እሸሽገው እና እይዘው ዘንድ የማይቻለኝ የቃሉ ትምህርት መሆኑን ባወቅሁ መጠን፣ ምነም ያህል የሰላ ትችት ባያጋጥመኝም ተቃውሞውንና ነቀፋውን ለመሸከምና ቃሉን ይወዳሉ ብዬ ላሰብሁዋችው ሁሉ የገባኝን እውነት በፍቅር ለማካፈል እተጋለሁ። እንደሚታወቀው ሙሉ ኃላፋዊነት (ፕሪተርሪዝም) በ70 ዓ.ም በሆነው የኢየሩሳሌም ጥፋት ትንቢቶች ሁሉ በሙላት ተፈጽመዋል ሲል የሚያምንና የሚያስተምር የነገረ ፍጻሜ አመለካከት ነው። እንግዲህ መጽሐፍ ቅዱሴን ተጠግቼ ባጠናሁት ቁጥር፣ ፕሪቴሪዝም የለየለት እውነት መሆኑን ይበልጥ እርግጠኛ እየሆንኩ መጥቻለሁ። እኔ እንደማስበው ፕሪቴሪዝም የተስፋና የድል ህይወት ፍጻሜ ነው እንጂ፣ አንዳንዶች እንደሚመስላቸውና ሊተቹት እንአሚዳዳቸው ተስፋ ገዳይ እምነት አይደለም። ነገር ግን ይህንን የፕሪቴሪዝም አመለካከት ለሌሎች ለማካፈል ገና እፌን ስከፍት በርካቶች የሚያነሱትና የሚጠይቁኝ ጥያቄ፣ “ጌታ አስቀድሞ ተመልሶ መጥቶ ከሆነ፣ ታዲያ ምን ተስፋ አለኝ?” የሚለው ነው። በዚህች አጭር ምልከታ ይህንን ጥያቄ ለመመለስ እጥራለሁ።

ስለ ፕሪቴሪዝም አመለካከት ለሌሎች ለመናገር ደፈር ብለህ እምነትህን ስታካፍል ፈጥኖ ከሚቀርብልህ ጥያቄዎች መካከል አንዱና ዋነኛው “ታዲያ ምን ተስፋ አለኝ?" የሚለው የሰዎች ጥያቄ ነው። የቤተክርስቲያን ተስፋ ምን እንደሆነ ለመረዳት በዛሬው ዘመን ክርስቲያን ማህበረሰብ ዘንድ ትልቅ ግራ መጋባት ያለ ይመስላል። እስቲ እንጠያየቅ፣ እንደ አማኝ ያለን ተስፋ በአካል ከምድር ገጽ ወደ ላይ መነጠቅ ነውን? በውኑ ተስፋችን ከመሞታችን በፊት ገና በዚሁ ሥጋ እያለን ወይም እርሱን አውልቀን ከምድር ላይ ሽቅብ እንደ ሮኬት መተኮስ ነውን? አብዛኞቹ ክርስቲያኖች ፍርጥም ብለው “አዎ!” እሱ ነው የሚሉ ይመስለኛል። ስለዚህ፣ ቃሉን ብቻ መሰረት አድርገህ ዳግም ምጽአቱ አስቀድሞ የተፈጸመና ያለፈ ክስተት መሆኑን ስትነግራቸውና ንጥቀትም ልበወለድ ተረት እንደሆነ ስታረዳቸውው፣ ልክ ጡጦውን እንደነጠቁት ህጻን ያለቻቸውን አንዲት ተስፋ የተነጠቁና ያጡ የሆኑ ያህል ይሰማቸዋል። በተስፋ ገዳይነትም ሊከሱህ ይጀምራሉ።

ፕሪቴሪዝም የሰዎችን ተስፋ ይገድላልን?

ፈጽሞ እንደዚያ አያደርግም፣ ፕሪቴሪዝም ተስፋችንን የበለጠ ያጠናክራል እንጂ ተስፋችንን አይገድልም። ይህ ደግሞ በጣም አስፈላጊ ነጥብ ነው፣ ምክንያቱም "ተስፋ" ለሰው ልጆች በጣም አስፈላጊ ጉዳይ ነው። ፕሪቴሪዝም የቤተ ክርስቲያንን ተስፋ ያጠፋል ብሎ መፈረጅ ደግሞ ከባድ የሆነ ውንጀላና ተቃውሞ ነው ምክንያቱም፡-  ሰዎች ኃይማኖተኝነትን ጨምሮ በየትኛውም የህይወት እርምጃ ውስጥ ተስፋ ያስፈልጋቸዋል!

እንበልና፣   "ይህ የ20 ዓመት ልጃችሁ ከደረሰበት አደጋ የተነሳ ቀሪ ህይወቱን ከአንገቱ በታች ሽባ ሆኖ ይኖራል፣  ምንም ማድረግ የምንችልም አይመስለንም" ተብሎ በሀኪሞች ለወላጆቹ ሲነገራቸው፣  ወላጆቹ የሚያደርጉትን በማጣት የሚያነሱት ጥያቄ "ታዲያ ምን ተስፋ አለ ትላላችሁ?" የሚል ነው" 

ተጋብተው ለሚኖሩ ባልና ሚስትስ ማባሪያ በሌለው የትዳር ጭቅጭቅ ውስጥ ሁልጊዜ እየተጣሉ ወደመለያየት ሲደርሱ አይተን ይህ እንዳይሆን ለሚፈልጉ ልጆቻቸውና ወዳጅ ዘመዶቻቸው ምን ተስፋ ይኖር ይሆን?

ወይም በአልኮል መጠጥ እየሰከረ ወይም ወሲብ ቀስቃሽ በሆኑ የብልግና ሥዕሎች የተጠመደ፣ ወይም በቁማር ጨዋታ ፍቅር የተለከፈ፣  ወይም በበርካታ ሱስ የሚያስይዙ ድርጊቶች ሰለባ የሆነ ሰው፣ እንዲህ ባለ አዘቅት ውስጥ ወድቆ ሳለ መቼም ከዚህ ጉድጓድ መውጫ መንገድ እንዳላገኝ ፈራሁ? ሲል  እንዲህ ላለው ሰው ምን ተስፋ ይኖረው ይሆን?

ነፍሰ ጡር ሆና የልጅ እናት ለመሆን የተዘጋጀች ሴት የጽንስ ክትትል የምታደርግበት የማህፀን ሐኪሟ ዘንድ ሄዳ ሳለ "እናዝናለን የጽንሱን የልብ ምት መስማት አልቻልንም?" ስትባል ያኔ ሊነገራትና ልትሰማው የምትችለው፤ ወይም ብቸኛ እናት ሆና በየቀኑ የሙሉ ጊዜ ሥራ እየሰራች፣ ሌሊቱንም  እንደ እናት እና አባት ሆና ልጆችዋን የምታሳድግና  የምታገለግል ሴት፣ "እንዲህ ሆኜ እስከ መቼ ልቀጥል እችላለሁ?" ብትል፤ ወይስ ድባቴንና ጭንቀትን እየታገለ ለሚኖር ሰው? ወይስ ሚስቱ ከሞት ጋር እየታገለች በምታጣጥርበት አልጋዋ አጠገብ ለቆመ አፍቃሪ ባል፣ ሊነገር የሚችል ምን ተስፋ ይኖር ይሆን?

በአደንዛዥ እፅ ቀንበር ስር ለወደቀ፣ በልቅ የወሲብ ልምምድ ሰበብ በሚተላለፉ በሽታዎች ለተበከለ ወጣት ትውልድ እና በፈረሰ ቤተሰብ ህመም ለሚሰቃይ ትውልድ  አንዳች ተስፋ የሚሆን ነገር ከወዴት አለ?

እኛ አማኞች የሆንን፣ ለእነዚህ ሁሉ ሰዎች፣ “አዎ፣ በኢየሱስ ክርስቶስ ተስፋ አለ" ብለን ልንመሰክር መድፈር አለብን። ወገኖች ሆይ፣ ተስፋ ለሌላቸው ሰዎች ሁሉ እንደ ክርስቲያኖች ተስፋ መስጠት እንችላለን።

አንድ ጸሃፊ እንዲህ ሲል ገልጾታል, "ተስፋ የህይወት አስፈላጊ ዋና ነገር ነው፣ ሰው በተስፋ ይሠራል፣ በተስፋ ያድናል፣ በተስፋ ይሞታል፣ እያንዳንዱ ታላቅ ሃይማኖት፣ እያንዳንዱ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ለሰዎች ተስፋን ይሰጣል."  ሌላው ጸሃፊ ደግሞ "ሰው 40 ቀን ያለ ምግብ፣ 4 ቀን ያለ ውሃ፣ 4 ደቂቃ ያለ አየር፣ ይኖራል ያለ ተስፋ ግን ሊኖር የሚችለው 4 ሰከንድ ብቻ ነው" ሲል ጽፏል።  ተስፋ በጣም አስቸጋሪ በሆነው የህይወት ዘመን ውጣ ውረድ ውስጥ ወደፊት እንድንራመድ የሚያደርገን ኃይል ነው።  ተስፋ እንቅፋቶችን ወስዶ ወደ እድሎች ይለውጣቸዋል።  ተስፋ ከሕይወታችን ምርጡን ለመጠቀም የሚያስፈልገንን ብርታት እና ድፍረት ይሰጠናል።

የተስፋን አስፈላጊነት እንደምትረዱት እርግጠኛ ነኝ።  ተስፋ ሊኖረን ይገባል፣ ነገር ግን ተስፋችን የተሳሳተ ተስፋ መሆን የለበትም።

የምታስታውሱ ከሆነ ከበርካታ አመታት በፊት 39 "የገነት በር" በመባል የሚታወቁት የከልት እንቅስቃሴ አባላት በኮሜት ሃሌ-ቦፕ መነቃቃት እየተካሄደ ነበር፣  በዚህ ንቅናቄ ተሳታፊ የነበሩ በርካታ ሰዎችም ከዩፎዎች ጋር ለመገናኘትና ይህንን ፕላኔት ትቶ ለመሄድ በማሰብ መተኪያ የሌለውን ህይወታቸውን አጥፍተዋል። ይህ የተሳሳተ ተስፋ ምሳሌ ነው። ሰዎቹም ከሞቱ በኋላ፣ የአካባቢው ባለሥልጣናት ባደረጉት ምርመራና ፍተሻ የአምልኮ ሥርዓቱ መሪ የአስትራል ትራቭል በማድረግ ስላለው ተስፋ ማብራሪያ የሰጠበትን የቪዲዮ ካሴት አግኝተው ተመልክተውታል። በቪዲዮውም ላይ አባላቱም ይህንን አለም ለመጨረሻ ጊዜ ለመሰናበት ሁለት ሁለት ሆነው አንድ ላይ በካሜራው ፊት ለፊት በመቅረብ ስንብት ያደርጉ እንደነበር ይታያል። በፊልሙ ላይ አንዲት ሴት፦ "ምናልባት እኔ እስከማውቀው ድረስ እነዚህ ሁሉ ሰዎች አእምሯቸውን የጣሉና ያበዱ ሊሆን ይችላል ነገር ግን በግሌ በዚህች ፕላኔት ላይ ለ 31 ዓመታት ኖሬ እዚህ ለእኔ የሚሆን ምንም ነገር ስለሌለ ወደዚያ ከመሄድ የተሻለ ሌላ ምንም ምርጫ የለኝም." ስትል ትደመጣለች። ያን አባባል ከሪፖርቱ ላይ ሳነብ በጣም አድርጌ አዘንሁ፣ ገረመኝም፡- ስለ ህይወት አንዳች ተስፋ የምትፈልግ ሴት ናት፣ ዳሩ ግን ምንም ተስፋ ለማይሆን ጉዳይ ክቡር ህይወቷን በከንቱ ሰጠች። የቅርቡ የኬንያው ጉድ የምስራች አለምአቀፍ ቤ/ክርስቲያን ፓስተር ፖል ማኬንዜ ህጻናት፣ ሴቶችና ወላጆቻቸውን ጨምሮ ከስድስት መቶ በላይ የሚቆጠሩ ተላላ አባላቱ ራሳቸውን አስርበው በጅምላ እንዲያልቁ ያደረገው በስብከቱ የአለም ፍጻሜ ደርሷል፣ ገነት ትገባላችሁ ተብለው ተሰብከው ነው፤ የፓስተራቸውን ሓሰተኛ የሆነ ገነት የመግባት ተስፋ አምነው ሁሉም ራሳቸውን በማስራብ ክቡር ህይወታቸውን አጡ። ከዩጋንዳ ሸሽተው ወደ ኢትዮጵያ የገቡ ስደተኞችን የአለም ፍጻሜ ቀርቧል ብለው ስላመኑ የምጽአትን ቀን በኢትዮጵያ ሆነው ለመቀበል መዘጋጀታቸው ነው። እንዲህ ያለ በተሳሳተ ተስፋ ላይ የተመሰረተ የበዛ ቅዠት በየስፍራው መስማት የተለመደ ነው።

የተወዳጁ አለንን በማስተዋል የተሰጠ ትንታኔ አዳምጡማ፣ "በታሪክ ውስጥ ከየትኛውም ጊዜ በላይ የሰው ልጅ በህይወቱ ለምርጫ አስቸጋሪ የሆነ መስቀለኛ መንገድ ያጋጥመዋል። አንደኛው መንገድ ወደ ተስፋ ቢስነት እና ፍፁም ወደሆነ ተስፋ መቁረጥ የሚመራው ሲሆን፤ ሌላኛው ደግሞ ሙሉ በሙሉ ወደ መጥፋት። እንግዲህ ምንን በትክክል የመምረጥ ጥበብ እንዲኖረን አጥብቀን መጸለይ ይኖርብናል"።  ይህ ግን እንዴት ያለ አስከፊና አስጨናቂ  ምርጫ ነው! እኔ በግሌ የትኛውንም መንገድ አልመርጥም። ይህ የአለን ትንታኔ ግን  ዛሬ የብዙዎችን አስተሳሰብ ያንጸባርቃል።

ከጥቂት ጊዜ በፊት ስለተደረገ አንድ አስገራሚ ሳይንሳዊ ሙከራ አንብቤያለሁ። እነዚህ የሰው ልጆችን ባህርይ የሚያጠኑ ሳይንቲስቶች አንዳንድ አይጦችን ይዘው በውኃ ማጠራቀሚያ ገንዳ ውስጥ አስቀመጧቸውና ከመስጠማቸው በፊት ምን ያህል ጊዜ በህይወት መቆየት እንደሚችሉ ተመለከቷቸው።  በአማካይ በህይወት የቆዩበት ጊዜ 17 ደቂቃዎችን ነበር።  ከዚያም ሙከራውን እንደገና ደገሙት፣ ነገር ግን በዚህ ጊዜ አይጦቹ ለመስጠም ገና ጥቂት ሲቀራቸው "አዳኑአቸውና"፣ ውሃውን ካደረቁላቸው በኋላ ወደ ሳጥኖቻቸው በመመለስ ምግብ እንዲበሉ እና ለጥቂት ቀናት እንዲጫወቱ ፈቀዱላቸው። ከዚያም እንደገና ያንን የመስጠም ሙከራውን ደገሙት። በዚህ ጊዜ፣ የእነዚህ አይጦች በአማካይ በህይወት የመትረፍ ጊዜ ከ17 ደቂቃ ወደ 36 ሰአታት አድጓል።  ሳይንቲስቶቹም ለሁለተኛ ጊዜ ባደረጉት ሙከራ አይጦቹ በህይወት ለመቆየት የሚያስችል ተስፋ እንደነበራቸው በመግለጽ ክስተቱን አብራርተዋል።  አይጦቹ ከዚህ ቀደም በተመሳሳይ ልምምድ ውስጥ አልፈው ስለነበር በድጋሚ ይህንንም አልፈው በሕይወት መትረፍ እንደሚችሉ ያምኑ ነበር። 

ስለዚህ ተስፋ በጣም አስፈላጊ እንደሆነ እናያለን። ተስፋ ሊኖረን ይገባል።

ተስፋ ምንድን ነው?

በዛሬው ዘመን ተርጓሚ ዘንድ “ተስፋ” የተሰኘው ቃል አስቀድሞ በአዲስ ኪዳን ከነበረው ትርጓሜ የተለየ ባዕድ ትርጉም እየያዘ ስለመጣ አስቀድሜ መጽሐፍ ቅዱሳዊውን የተስፋ ፍቺ ልሰጣችሁ እወዳለሁ። ዛሬ ዛሬ መደዴው የቃሉ አጥቃቀም ድንገተኛ ነገርን እንደመጠባበቅ ሆኖ ያመለክታል፤ የሆነ ነገር በድንገት እንደሚሆን መጠበቅ ማለት ነው። ነገር ግን በእርግጥ የሚከሰት መሆን አለመሆኑ ላይ አንዳንድ የሚነሳ ብዥታና ጥያቄ ግን አያጣውም። ለምሳሌ፣ ስለወደፊቱ አንዳንድ ጥርጣሬዎችን ወይም እርግጠኛ አለመሆንን በሚያሳይ መልኩ “ዛሬ አይዘንብም ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ” ወይም “ወደሚቀጥለው የደመወዝ ቀን እንደምደርስ ተስፋ አደርጋለሁ” ልንል እንችላለን። ይህ ግን ተስፋ ለተሰኘው ለዚህ አይነተኛ ቃል የአዲስ ኪዳን እኩያ አጠቃቀም አይደለም።  በአዲስ ኪዳን ውስጥ ባለው አጠቃቀም ተስፋ ስለ ወደፊቱ ጊዜ ፍጹም እርግጠኝነትን፣ ጓጉቶ የመጠባበቅ ዝንባሌን፣ በእግዚአብሔር የመታመንን እና የገባውን ቃል የመፈጸም ችሎታውን ያመለክታል። የእብራይስጡ batach ወይም bittachown (baw-takh / bit-taw-khone) የተሰኘው ቃል ትርጉሙ፦ መሸሸጊያ ቦታን፣ መታመንን፣ መተማመንን ወይም እርግጠኛ መሆንን፣ እና ደፋር መሆንን ያመለክታል፤ ይህም የደህንነትን ወይም ደህና የመሆንን እውነታ እና ስሜት, የያዘ እምነት ወይም ዋስትና ነው። የግሪኩም elpizo ወይም elpis የተሰኘው ቃል ርትጉሙ እንደ እብራይስጡ ሁሉ ጓግቶ መጠበቅን ወይም ናፍቆትን መግለጽ፣ ተስፋ እና  እምነት፣ ወይም መተማመንን ያሳያል። ተስፋ፣ "ይህንን ዓለምና በውስጡ ያለውን ተግዳሮት ሁሉ ፊት ለፊት ለመገናኘት በኢየሱስ ክርስቶስ ውስጥ ተዝቆ የማያልቅ መዝገብ ሁሉ  አለኝ" የሚለው እርግጠኝነት ነው።

በርካታ ክርስቲያኖች ስለ ዳግመኛ ምጽአት አልፏል የሚለውን የፕሪቴሪዝም ትምሕርት በሚሰሙበት ጊዜ “ታዲያ ተስፋዬ ወዴት ነው” ብለው በርግገው ይጠይቃሉ፣ ምክንያቱም እንደ ክርስቲያን ተስፋችን ከክርስቶስ ዳግም ምጽዓት ጋር የተጋመደ መሆኑን እንዲያምኑ ተደርገው እየተማሩ ስላደጉ ነው። ለምሳሌ፦

ጆን ፓይፐር። ሲጽፉ “አማኝ ለሆኑ ሁሉ የተባረከው ተስፋቸው የታላቁ አምላካችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መገለጥ ነው” ብለዋል።

ጄሪ ፋልዌልም፣ “አብዛኞቹ ዳግመኛ የተወለዱ ክርስቲያኖች ክርስቶስ ከሺህ አመት መንግስት አስቀድሞ፣ ከመከራው በፊት ለቤተክርስቲያኑ ሁሉ እንደሚመጣ  ያምናሉ፣ ይህም የተባረከ የቤተ ክርስቲያን ተስፋ ነው።  የክርስቶስን መምጣት በቅርቡ መጠበቅና ሙሽራውን ለመቀበል መዘጋጀት የክርስቶስ ተከታዮች የሆኑትን ሁሉ  በዚህች ፕላኔት ከሚኖሩ ከሌሎች ነዋሪዎች የሚለያቸው አንዱ ምክንያት ነው" ሲሉ ጽፈዋል።

ይህ የመጻኢነትን ነገረ ፍጻሜ የዘመን መዳቢነት ትርጉምን የሚከተሉ አማኞች ድምዳሜ ነው። ባነሳኋቸው ምሳሌዎች እንደተጠቀሱት እውቅ ሰባኪያን ሁሉ ይህ የመጻኢነት እምነት የአማኝን የተባረከ "ተስፋ" በቅርቡ ይሆናል ብሎ በሚጠባበቀው የጌታ ዳግም ምጽዓት ላይ ትኩረት አድርጎ የሚያስተምር የነገረ ፍጻሜ ዘውግ ነው። እነዚህ ሰዎች በየዘመናቱ ምንም እርማት ሳያደርጉ ክርስቶስ በቅርቡ ይመጣል ብለው ያስተምራሉ። እንደ እነርሱ እምነት ከሆነ ይህ ተስፋ ላለፉት ሁለት ሺህ ዓመታት ሲጠበቅ ያልተፈጸመ፣ እስካሁንም ዘግይቶ እየተጠበቀ ያለና አሁንም በሚበዙት ዘንድ ወደፊት አንድ ቀን ይፈጸማል ተብሎ እየተጠበቀ ብዙ የሚሰብኩለት፣ የሚዘምሩለትና አልፎም የሚጽፉለት ዋና ትምህርታቸው ነው።  በሚሊዮን የሚቆጠሩ ክርስቲያኖችም በአለም ዙሪያ በየዘመናቱ ለዚሁ እየጸለዩ የዚህ ተስፋ ፍጻሜ በሕይወት ዘመናቸው ውስጥ እንደሚሆን ጠብቀው ሳያዩት ሞተዋል።  መጻኢነት ግን አሁንም ለስህተቱ እርማት ሳያደርግ የምጽአቱን ተስፋ ፍጻሜ እየጠበቀ አለ።  በዚህም ምክንያት የክርስቶስ ጠላቶች የሆኑ ከሃዲያን በስፋት የሚያውቁት የመጻኢነት አቋምና ትምህርት የክርስትናው አለም ብቸኛ እምነት የሆነ ይመስል እርሱኑ እንደ በቀቀን እየጮሁ የቅዱሳት መጻህፍትን ታማኝነት ጥያቄ ውስጥ የጣሉ እየመሰላቸው እምነታችን ላይ ይሳለቃሉ የክርስትናን አስተምህሮም ውሸት ነው ሲሉ በጽኑ ይቃወማሉ።  መጻኢነት የብዙ ሰዎችን እምነት እያቀጨጨ ወደ ክህደት እንዲሳቡ የሚያደርግ፣ በምዕመናንና በሚወዷቸው ሰዎች ላይም በሚያሳዝን ሁኔታ ብስጭትና ተስፋ ማጣትን ያስከተለ ትምህርት ብቻ ሳይሆን፤ ከሃዲያንና የመስቀሉ ጠላቶች በክርስቶስ ላይ የሚያቀርቡትን ውንጀላ አመቻችቶ የሚያቀብል አደገኛ ስነ መለኮት ነው።

መጽሐፍ ቅዱስ በእርግጠኝነት የክርስቶስ መምጣት የተባረከው ተስፋ እንደሆነ ያስተምራል። የፕሪቴሪዝም እምነትም ይኸው ነው። ፕሪተርዝም ለአማኙ የተፈጸመ ተስፋን እና የዘላለምን ሕይወት እምነት በሙላት ያቀርባል። ይህ የተፈጸመ ወንጌል ለአማኙ ፍጻሜውን ያገኘ መሻት እና የሕይወት ዛፍ ይሆንለታል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰጠው ተስፋ መሰረት እርሱ በቀጠረው የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን እንደተመለሰ ማወቃቸው ኃላፋዊያን ለሆኑ አማኞች የማይናወጥ ሰላምና ታላቅ መጽናናትን ይሰጣቸዋል። ፕሪቴሪዝም ጌታ ኢየሱስ እና ሐዋርያቱ እነዚያን የመጀመርያው ክፍለ ዘመን ቅዱሳንን በትውልዳቸው በቅርቡ እንደሚመጣ የሐሰት ትንቢት እየነገሩ እንዳላሳቷቸው በጽኑ ያረጋግጣል። መጥቶም የሰጠውን የተስፋ ቃል በመፈጸሙ እና ለመዳናችን ሙላት በመስጠቱ  ፕሪቴሪዝም በዚህ ሙሉ ደስታን  ያጣጥማል። እርግጥ ነው የክብር መገለጡ ለአማኞች የተባረከ ተስፋ ነው፣ ግን ለየትኞቹ አማኞች?

ቲቶ 2፥ 13 ".... የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥…." 

ችግሩ፣ የክርስቶስ ዳግመኛ  ምጽአት በተስፋነቱ በዚህ ክፍል "እኛ" ለተባሉት ወይም በቀጣዩ ጥቅስ "እናንተ" ለተባሉት የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳን የተሰጠ ተስፋ መሆኑን አለማወቅ ነው።

ያዕ 5፥ 8 "እናንተ ደግሞ ታገሡ፥ ልባችሁንም አጽኑ፤ የጌታ መምጣት ቀርቦአልና።"
 
ተስፋውም ያኔ ለእነርሱ የተፈጸመ ተስፋ ነው ብለን ለማመን በቅዱስ ቃሉ ትምህርት እንገደዳለን። ዛሬ እኛ ግን የምንኖረውና እየኖርን ያለነው በምን አይነት ዘመን ነው? ብለን መጠየቅ አለብን፤ እኛ የምንኖረውና እየኖርን ያለነው እነዚያን የአዲስ ኪዳን ደብዳቤዎች ከተቀበሉና የምጽአቱ ተስፋ ተሰጥቷቸው የነበሩ የመጀመሪያዎቹ ተቀባዮች ከኖሩበት ዘመን በተለየ ዘመን ላይ ነው። በመላው አዲስ ኪዳን በስፋት ሲነገርለት የምናየውም ሁለት አይነት ዘመናትን ነው፣ እነርሱም፡-  "ይህ ዓለም" እና "የሚመጣው ዓለም" ወይም በተለዋጭ "ይህ ዘመን” እና “የሚመጣው ዘመን በመባል ይታወቃሉ።

ማቴዎስ 12፥ 32 "በሰው ልጅ ላይ ቃል የሚናገር ሁሉ ይሰረይለታል፤ በመንፈስ ቅዱስ ላይ ግን የሚናገር ሁሉ በዚህ ዓለም ቢሆን ወይም በሚመጣው አይሰረይለትም።" 

በጥቅሱ መጨረሻ ላይ በሚመጣው የተባለው (በእንግሊዝኛው the world to come) "ሊመጣ ያለው" የሚለው ሀረግ በግሪኩ "ሜሎው" ነው፤ ሲተረጎምም፦ ከጊዜው ቅርበት አንጻር "(እነሆ) ሊሆን ነው" ወይም "ሊሆን ቀርቧል"፣ ማለት ነው። እርሱም ለእነርሱ “ሊመጣ የቀረበ ዘመን ነው”። ለማን ነው "ሊመጣ ያለው"?  የሚመጣው በመጀመሪያው መቶ ዘመን ለነበሩት ለመጀመሪያዎቹ በኩረ ተደራስያን ነው፤ አለቀ፣ ይህንን መለጠጥም ሆነ፣ ዘመን አሻግሮ ማስፈንጠር አይቻልም።

ኤፌ 1፥ 21 "ክርስቶስንም ከሙታን ሲያስነሣው ከአለቅነትና ከሥልጣንም ከኃይልም ከጌትነትም ሁሉ በላይና በዚህ ዓለም ብቻ ሳይሆን ነገር ግን ሊመጣ ባለው ዓለም ደግሞ ከሚጠራው ስም ሁሉ በላይ በሰማያዊ ስፍራ በቀኙ ሲያስቀምጠው በክርስቶስ ባደረገው ሥራ የብርታቱ ጉልበት ይታያል፤"

እዚህም ላይ እንደገና ስለ ሁለቱ ዓለማት ወይም ዘመናት እናያለን። አዲስ ኪዳን ስለ ሁለት ዘመናት ሲያስተምር፣ “ይህ ዘመን” እና “የሚመጣው ዘመን” በማለት ይናገራል። እነዚህ ሁለት ዘመናት ምን አይነት ዘመናት እንደሆኑ እና አንዱ በሌላው የተተካበትንና ዘመናቱ የተለወጡበትን ጊዜ በወጉ መረዳት መጽሐፍ ቅዱስን በአግባቡ ለመተርጎም እና የዛሬ ተስፋችን ምን እንደሆነ ለመረዳት መሰረታዊ ነገር ነው። ይህንን ያስተማርሁበትን ጽሁፍ ማንበብ ለምትወዱ በብሎገሬ ላይ የከተብኩትን እንድትመለከት እጋብዛችኋለሁ፣ አሆ ሊንኩ፦

 https://gizachewkr.blogspot.com/2022/04/blog-post.html?m=1

የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች የኖሩበት ዘመን  “ይህ ዘመን” ብለው ሲጠሩት በነበረ ዘመን ነው፣ እርሱም ለእነርሱ እያለቀና እየተዘጋ የነበረ የመጨረሻው ዘመን ነበር።  ለአዲስ ኪዳን ጸሓፊዎች፣ "የሚመጣው ዘመን" ብለው የሚጠሩት ወደፊት ይጠብቁት የነበረ ዘመን ተስፋቸው ነው። ነገር ግን "ይህ ዘመን" ሲሉ የጠሩትና የኖሩበት ዘመን ሊያበቃ ወደ ፍጻሜው ቀርቦ ስለነበር የሚጠባበቁትና "የሚመጣው ዘመን" ተስፋቸው ሊመጣ ለእነርሱ እጅግ ቀርቦ ነበር።

1ቆሮንቶስ 10፥ 11 "ይህም ሁሉ እንደ ምሳሌ ሆነባቸው፥ እኛንም የዘመናት መጨረሻ የደረሰብንን ሊገሥጸን ተጻፈ።"

የዘመናት ፍጻሜ በእነርሱ ላይ እንደደረሰ ጳውሎስ ለመጀመርያው ክፍለ ዘመን ቅዱሳን በግልጽ ይነግራቸዋል። ምክንያቱም እየኖሩበት የነበረውና  "ይህ ዘመን" እየተባለ የሚጠራው የእነርሱ ዘመን ሊያበቃ ተቃርቦ ነበርና።

መጽሐፍ ቅዱሳዊው “ይህ ዘመን” የአሮጌው ኪዳን ዘመን፣ እርሱም የአይሁድ ዘመን ነው።  ያ ዘመን ደግሞ ያበቃውና የተደመደመው በ70 ዓ.ም ቤተ መቅደሱ ሲፈርስ ነው። የአዲስ ኪዳን ጸሐፊዎች የኖሩት መጽሐፍ ቅዱስ “ይህ ዘመን” ብሎ ይጠራው በነበረው ዘመን መጨረሻ ላይ ነው። እኛ ግን  እየኖርን ያለነው መጽሐፍ ቅዱስ "የሚመጣው ዘመን" እያለ በሚጠራው ዘመን ውስጥ ነው። "ይህ ዘመን" እየተባለ የተጠራው ያ የአሮጌው ኪዳን ዘመን የሚደመደመውና ሙሉ በሙሉ የሚያበቃው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን በ70 ዓ.ም ላይ የአይሁድ ቤተ መቅደስ ሲፈራርስ ነው። መጽሐፍ ቅዱሳዊው "ይህ ዘመን" አሁን ጥንታዊ ታሪክ ሆኗል።

ይህንን በአይምሮአችን ይዘን “ተስፋ” የሚለውን ቃል በአዲስ ኪዳን ስናስስ  መጽሐፍ ቅዱስ “ይህ ዘመን” ብሎ በሚጠራው ዘመን ውስጥ ይኖሩ ለነበሩ የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን  ተስፋ የሆኑ በርካታ ነገሮችን እናገኛለን። የፕሪቴሪዝም አስተምህሮም እነዚህን ተስፋዎች ያጠፋቸው እንደሆነም እመልከት።

ተመልከቱ በአዲስ ኪዳን ውስጥ፣ ተስፋ ሆነው የተገለጡ  በርካታ ነገሮችን እናገኛለን፡-

1.ዳግመኛ ምጽአቱ፦

ቲቶ 2፥ 13 "ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤"

1ጴጥ 1፥ 13 "ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና በመጠን ኖራችሁ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ።"

1ዮሐ 3፥ 2-3 "ወዳጆች ሆይ፥ አሁን የእግዚአብሔር ልጆች ነን፥ ምንም እንደምንሆን ገና አልተገለጠም። ዳሩ ግን ቢገለጥ እርሱ እንዳለ እናየዋለንና እርሱን እንድንመስል እናውቃለን። በእርሱም ይህን ተስፋ የሚያደርግ ሁሉ እርሱ ንጹሕ እንደ ሆነ ራሱን ያነጻል።"

ስለዚህ፣ ዳግመኛ ምጽአቱ “ይህ የአሁኑ ዘመን” እየተባለው በተጠራ የዘመን ምዕራፍ ውስጥ ለኖሩ ሰዎች የተሰጠ ተስፋ እንጂ "የሚመጣው ዘመን" ተብሎ በሚጠራው ዘመን ውስጥ እየኖርን ላለን ቅዱሳን የተሰጠ ተስፋ  እንዳልሆነ በግልጽ እናያለን።

2. የሙታን ትንሣኤ፦ 

 ጳውሎስ ትንሳኤ ሙታን የእስራኤል እና የአዲስ ኪዳን ቅዱሳን ተስፋ እንደሆነ በግልፅ አስተምሯል፡-

ሐዋ 23፥ 6፦ "ጳውሎስ ግን እኵሌቶቹ ሰዱቃውያን እኵሌቶቹም ፈሪሳውያን መሆናቸውን አይቶ፦ ወንድሞች ሆይ፥ እኔ ፈሪሳዊ የፈሪሳዊም ልጅ ነኝ፤ ስለ ተስፋና ስለ ሙታን መነሣት ይፈርዱብኛል ብሎ በሸንጎው ጮኸ።"

ሐዋ 24፥ 15፦ "እነዚህም ራሳቸው ደግሞ የሚጠብቁት፥ ጻድቃንም ዓመፀኞችም ከሙታን ይነሡ ዘንድ እንዳላቸው ተስፋ በእግዚአብሔር ዘንድ አለኝ።"

ሐዋ 28፥ 20፦ "ስለዚህም ምክንያት አያችሁና እነግራችሁ ዘንድ ጠራኋችሁ፤ ስለ እስራኤል ተስፋ ይህን ሰንሰለት ለብሻለሁና።"

ሐዋ 26፥ 6-8፦ "አሁንም ከእግዚአብሔር ዘንድ ለአባቶቻችን ስለ ተሰጠው ስለ ተስፋ ቃል አለኝታ ልፋረድ ቆሜአለሁ። ወደዚህም ወደ ተስፋ ቃል አሥራ ሁለቱ ወገኖቻችን ሌሊትና ቀን በትጋት እያመለኩ ይደርሱ ዘንድ አለኝታ አላቸው፤ ስለዚህም አለኝታ፥ ንጉሥ አግሪጳ ሆይ፥ ከአይሁድ እከሰሳለሁ። እግዚአብሔር ሙታንን የሚያስነሣ እንደ ሆነ ስለ ምን በእናንተ ዘንድ የማይታመን ነገር ሆኖ ይቈጠራል?"

ጳውሎስ እንደሚሰብከው ከሆነ ይህ የሙታንን ትንሣኤ ተስፋ የሚመለከተው “እግዚአብሔር ለአባቶቻችን የገባውን የተስፋ ቃል የሚፈጽም" እንደሆነ በተለይ ከዚህ የመጨረሻው ጥቅስ መረዳት ይቻላል።

3. ጽድቅ የአዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን ተስፋ ነበር፡-

ገላ 5፥ 5፦ "እኛ በመንፈስ ከእምነት የጽድቅን ተስፋ እንጠባበቃለንና።"

4. ድነት የአዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን ተስፋ ነበር፡-

1ተሰ 5፥ 8፦ "እኛ ግን ከቀን ስለ ሆንን፥ የእምነትንና የፍቅርን ጥሩር የመዳንንም ተስፋ እንደ ራስ ቁር እየለበስን በመጠን እንኑር፤"

5. የዘላለም ሕይወት የአዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን ተስፋ ነበር፡-

ቲቶ 1፥ 2፦ "በእግዚአብሔር ለተመረጡት እምነት እንዲሆንላቸው በዘላለምም ሕይወት ተስፋ እንደ አምልኮት ያለውን እውነት እንዲያውቁ የተላከ፤ ስለዚህም ሕይወት የማይዋሽ እግዚአብሔር ከዘላለም ዘመናት በፊት ተስፋ ሰጠ፥"

ቲቶ 3፥ 6-7፦ "ያን መንፈስም፥ በጸጋው ጸድቀን በዘላለም ሕይወት ተስፋ ወራሾች እንድንሆን፥ በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ላይ አትርፎ አፈሰሰው።"

ለሰዎች አሁን የዘላለም ሕይወትን፣ መዳንን እና ጽድቅን ተቀብላችኋል፣ እነዚህ ነገሮች አሁን አሏችሁ፣ ብለን ብንነግራቸው፣ “ተስፋዬ ምንድን ነው፣ ወዴትስ አለ?” ብለው ይጠይቁን ነበርን?  በጭራሽ አይጠይቁንም፣ ምክንያቱም እነዚህ ነገሮች አሁን እንዳሏቸው ያምናሉና። ነገር ግን የዘላለም ሕይወት፣ ድነት እና ጽድቅ ሁሉም እነዚህ ነገሮች "ይህ ዘመን" እየተባለ ይጠራ በነበረ ዘመን ውስጥ ይኖሩ ለነበሩ ሰዎች ያኔ ተስፋቸው ነበሩ። የዘላለም ሕይወት፣ ድነት፣ እና ጽድቅ ሁሉ በብሉይ ኪዳን ዘመን መጨረሻ ላይ በሆነው በዳግም ምጽአቱ ጊዜ የቤተ ክርስቲያን ሙሉ ርስትና ውርስ ሆነዋል። እስከዚያ ድረስ ግን ተስፋ ነበር።

ኤፌ 1፥ 13-14 ፦ "እናንተም ደግሞ የእውነትን ቃል፥ ይኸውም የመዳናችሁን ወንጌል፥ ሰምታችሁ ደግሞም በክርስቶስ አምናችሁ፥ በተስፋው መንፈስ በመንፈስ ቅዱስ ታተማችሁ፤ እርሱም የርስታችን መያዣ ነው፥ ለእግዚአብሔር ያለውን ሁሉ እስኪዋጅ ድረስ፥ ይህም ለክብሩ ምስጋና ይሆናል።"

የርስት ጉዳይ ሲነሳ በመጻኢያንና በኃላፋውያን መካከል ያለው ልዩነት ጉልህ ነው። መጻኢያን በትምህርታቸው …..በክርስቶስ ያመኑ ሁሉ በሰማይ የዘላለም ህይወት፣ ርስትና ሽልማትን እንደሚያገኙ ያስተምራሉ። ይህም ርስት መያዣው አሁን በመንፈስ ቅዱስ የታተመ ቢሆንም እንኳ በሙላት ይገለጥ ዘንድ ክርስቶስ በመጨረሻው ፍርዱ ዳግም እስኪመለስ ድረስ ገና ወደፊት ይጠበቃል እንጂ እስከ አሁን ድረስ ተጠናቆ አልተፈጸመም ይላሉ።

ፕሪተርዝም የሚያስተምረው ክርስቶስ አስቀድሞ በ70 ዓ.ም ተመልሶ ፍርድን ሁሉ በማጠናቀቁ፣ በክርስቶስ ያመኑ ሁሉ የተጠናቀቀውን የዘላለም ህይወት ርስት በሙላት ተቀብለዋል። ከ70ው ዓ.ም ዳግመኛ ምጽአቱ አንስቶ መንፈሳዊ በሆነው የአዲሱ ኪዳን የወንጌል መንግሥት ውስጥ ላለ ለእያንዳንዱ ዳግመኛ ለተወለደ ክርስቲያንም የቤዛነት ስራው ያስጀመረውን መንፈሳዊውን ርስት ዳግም ምጽአቱ ለዘላለም አስገኝቶቷል ማለት ነው።

በዚህ ጉዳይ ላይ ፕሪቴሪዝም ቀድሞውኑ የተጠናቀቀውን ርስት በሙላት ሲያቀርብልን አንዳች የሚቀረውና የሚጎድለው ነገር የለውም።  መጻኢነት ግን ይህንን ርስት በሙላት ለማግኘት የክርስቶስን ዳግመኛ መምጣት ወደፊት መጠበቅ አለበት። 

በዚህ ጉዳይ ማጠቃለያ የሚሆን አሳብ አንስቼ ወደሚቀጥለው ጉድይ ልሻገር፡- በክርስቶስ የመጀመሪያ በሥጋ መምጣት እና ሁለተኛው የፍርድ ምጽአት መካከል ባለው የአርባ አመታት የሽግግር ወቅት ለነበሩት ለነዚህ የመጀመርያው መቶ ክፍለ ዘመን የጳውሎስ ተደራስያን በትምህርቱ ገና ተጠናቅቆ ስላልተፈጸመ ርስት ይነግራቸዋል። 

በአጠቃላይ መጻኢያን ለመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ቅዱሳን የተጻፉ ጽሑፎችን በአለም ዙርያ በየትኛውም ታሪክ ውስጥ ለነበሩ እና ላሉ ክርስቲያኖች ሁሉ የተጻፉ ናቸው ብለው ስለሚያምኑ፣ ተጠናቅቆ በሙላት የተሰጠውን ርስት አይገነዘቡትም። በመሆኑም እስከአሁን ድረስ የጌታ ዳግም ምጽአት አንድ ቀን ወደፊት ይሆናል ብለው ስለሚያምኑ ርስታቸውን በሙላት የሚቀበሉበትን ቀን እየተጠባበቁ ናቸው።

ፕሪቴርሪዝም ግን ጳውሎስ በቀጥታ ለመጀመሪያው ክፍለ ዘመን አማኞች እየጻፈ መሆኑን እና የርስታቸው ሙላት  ወደፊት በቅርቡ ለእነርሱ የሚፈጸም እንደሚሆን እያስተማራቸው መሆኑን በሚገባ ተረድቷል።

በዚያ የሽግግር ወቅት ለነበሩ ቅዱሳን ሊቀበሉት ያለው ርስት ቃል የተገባላቸውና የተጠበቀላቸው ስጦታ፣ ተስፋቸው ነበር። የጳውሎስ ትምህርትም እንደሚያመለክተው ርስት እነርሱ በነበሩበት አሁናቸው ላይ በሙላት የተገኘና የተጨበጠ ሳይሆ ለእነርሱ ገና ወደፊት በምጽአቱ (ፓሮውዥያው) ላይ ሊሆን ያለና የሚጠባበቁት መሆኑን ያሳያል። ለምሳሌ ቀጥሎ ያሉትን የንባብ ክፍሎች በጥንቃቄ ስሙ:-

ሐዋ 20፥ 32 "አሁንም ለእግዚአብሔርና ያንጻችሁ ዘንድ በቅዱሳንም ሁሉ መካከል ርስትን ይሰጣችሁ ዘንድ ለሚችል ለጸጋው ቃል አደራ ሰጥቻችኋለሁ።"

ኤፌ 1፥ 15-18 "ስለዚህ እኔ ደግሞ በእናንተ ዘንድ ስለሚሆን በጌታ በኢየሱስ ስለ ማመንና ለቅዱሳን ሁሉ ስለሚሆን መውደድ ሰምቼ፥ ስለ እናንተ እያመሰገንሁ ስጸልይ ስለ እናንተ ማሳሰብን አልተውም፤ የክብር አባት የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ እርሱን በማወቅ የጥበብንና የመገለጥን መንፈስ እንዲሰጣችሁ እለምናለሁ።  ይህም የልባችሁ ዓይኖች ሲበሩ የመጥራቱ ተስፋ ምን እንዲሆን በቅዱሳንም ዘንድ ያለው የርስት ክብር ባለ ጠግነት ምን እንዲሆን ለምናምን ከሁሉ የሚበልጥ የኃይሉ ታላቅነት ምን እንዲሆን ታውቁ ዘንድ ነው፤"

ቆላ 3፥ 23-24 "ለሰው ሳይሆን ለጌታ እንደምታደርጉ፥ የምታደርጉትን ሁሉ በትጋት አድርጉት፥  ከጌታ የርስትን ብድራት እንድትቀበሉ ታውቃላችሁና፤ የምታገለግሉት ጌታ ክርስቶስ ነውና።"

ዕብራ 9፥ 11-15 "ነገር ግን ክርስቶስ ይመጣ ዘንድ ላለው መልካም ነገር ሊቀ ካህናት ሆኖ፥ በምትበልጠውና በምትሻለው በእጆችም ባልተሠራች ማለት ለዚህ ፍጥረት ባልሆነች ድንኳን፥ የዘላለምን ቤዛነት አግኝቶ አንድ ጊዜ ፈጽሞ ወደ ቅድስት በገዛ ደሙ ገባ እንጂ በፍየሎችና በጥጆች ደም አይደለም። የኮርማዎችና የፍየሎች ደም በረከሱትም ላይ የተረጨ የጊደር አመድ ሥጋን ለማንጻት የሚቀድሱ ከሆኑ፥ ነውር የሌለው ሆኖ በዘላለም መንፈስ ራሱን ለእግዚአብሔር ያቀረበ የክርስቶስ ደም እንዴት ይልቅ ሕያውን እግዚአብሔርን ልታመልኩ ከሞተ ሥራ ሕሊናችሁን ያነጻ ይሆን? ስለዚህም የፊተኛው ኪዳን ሲጸና ሕግን የተላለፉትን የሚቤዥ ሞት ስለ ሆነ፥ የተጠሩት የዘላለምን ርስት የተስፋ ቃል እንዲቀበሉ እርሱ የአዲስ ኪዳን መካከለኛ ነው።"


ጴጥሮስም እነዚያ የሚጽፍላቸው የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ቅዱሳን ለእነርሱ በሆነ መጻኢ ጊዜ በሰማይ ስለሚጠብቃቸው የርስት ተስፋ ተናግሯል፣ ይህም ርስት ክርስቶስ በዳግመኛ ምጽአቱ ተመልሶ ሲመጣ በሙላት ስለሚቀበሉት ነው።

1ጴጥ 1፥ 3-5 " ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ለሕያው ተስፋና ለማይጠፋ፥ እድፈትም ለሌለበት፥ ለማያልፍም ርስት እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ፤ ይህም ርስት በመጨረሻው ዘመን ይገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀ መዳን በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ ለእናንተ በሰማይ ቀርቶላችኋል።"

በብሉይ ኪዳን ዘመን መጨረሻ ማለትም በ70 ዓ.ም ላይ (ይኸውም የብሉይ ኪዳን የመጨረሻ ቀን ነው)፣ ያኔ ብዙ ነገሮች ተከስተዋል፡-
1. ክርስቶስ ተመልሷል፡-

2ጢሞ 4፥ 1፦ "በእግዚአብሔር ፊት በሕያዋንና በሙታንም ሊፈርድ ባለው በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ፊት፥ በመገለጡና በመንግሥቱም እመክርሃለሁ፤"

ዕብ 10፥ 37፦ "ገና በጣም ጥቂት ጊዜ ነው፥ ሊመጣ ያለውም ይመጣል አይዘገይምም፤"

2. የሙታን ትንሣኤ ሆኗል፦

ዮሐ 11፥ 24፦ "ማርታም፦ በመጨረሻው ቀን በትንሣኤ እንዲነሣ አውቃለሁ አለችው።"

ይህ መጨረሻ “ይህ ዘመን" በመባል የሚታወቀው የአሮጌው ዘመን የመጨረሻ ቀን” ማለት ነበር፣ “የሚመጣው ዘመን” በመባል የሚታወቀው ዘመን ግን ዘላለማዊ ነው እንጂ የመጨረሻ ቀናት የሉትም፤  ስለዚህ፣ የሙታን ትንሳኤ የሚሆነው በአሮጌው ኪዳን ዘመን መጨረሻ ላይ ጌታ በተመለሰ ጊዜ ነው።

3. ፍርድ ተከናውኗል፡-

ማቴ 13፥ 40፦ "እንግዲህ እንክርዳድ ተለቅሞ በእሳት እንደሚቃጠል፥ በዓለም መጨረሻ እንዲሁ ይሆናል።"

መጽሐፍ ቅዱስ “ይህ ዘመን” ሲል የሚያውቀው የአሮጌው ኪዳን ዘመን ያኔ በመጀመርያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በ70 ዓ.ም የቤተ መቅደሱ ውድመት ጊዜ በተከናወነው የጌታ ተመልሶ መምጣት ስላበቃ እኛ ዛሬ የምንኖረው መጽሐፉ “የሚመጣው ዘመን” ብሎ በሚያወቀው አዲሱ ዘመን ውስጥ መሆን አለበት።  እኛም አሁን እየኖርን ያለነው "የሚመጣው ዘመን" ተብሎ በሚጠራው አዲስ ዘመን ውስጥ ከሆነ እንግዲያውስ ክርስቶስ እንደ ተስፋ ቃሉ አስቀድሞ ተመልሷል፣ ትንሣኤም ከአሁን በፊት ሆኗል፣ የአሕዛብ ፍርድም ተፈጽሟል ማለት ነው።

አማኞች በሚመጣው ዘመን ምን እንደሚቀበሉ ኢየሱስ የተናገረውን አስተውሉ፡-

ማር 10፥ 29-30፦ "ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለ፦ እውነት እላችኋለሁ፥ ስለ እኔና ስለ ወንጌል ቤትን ወይም ወንድሞችን ወይም እኅቶችን ወይም አባትን ወይም እናትን ወይም ሚስትን ወይም ልጆችን ወይም እርሻን የተወ፥ አሁን በዚህ ዘመን ከስደት ጋር ቤቶችን ወንድሞችንና እኅቶችንም እናቶችንም ልጆችንም እርሻንም መቶ እጥፍ፥ በሚመጣውም ዓለም የዘላለም ሕይወት የማይቀበል ማንም የለም።"

ከፍ ሲል እንዳየነው የዘላለም ሕይወት “ይህ ዘመን” በመባል ይጠራ በነበረው ጊዜ ውስጥ ይኖሩ ለነበሩት የተሰጠ “ተስፋቸው” ነበር ነገር ግን አሁን ባለውና እኛ እየኖርንበት ባለው በዚህ  “የሚመጣው ዘመን” በተባለው ማለትም የአዲሱ ኪዳን ዘመን የአማኞች ሁሉ ርስት ነው።

እንግዲህ ዳግመኛ  ምጽአቱን  ጨምሮ የሙታን ትንሣኤ፣ ፍርድ፣ የዘላለም ሕይወት፣ መዳንና ጽድቅ ሁሉም ቀደም ሲል ተፈጽመዋል ተከናውነዋልም፤ ታዲያ ለምን ተስፋችን ይሆናሉ?  ያለህንና ያገኘኸውን ነገር ተስፋ አታደርግም፦

ሮሜ 8፥ 24-25፦ "በተስፋ ድነናልና፤ ነገር ግን ተስፋ የሚደረግበቱ ነገር ቢታይ ተስፋ አይደለም፤ የሚያየውንማ ማን ተስፋ ያደርገዋል?  የማናየውን ግን ተስፋ ብናደርገው በትዕግሥት እንጠባበቃለን።"

ፕሪተርስቶች የሆንን እኛ ተስፋን ተፈጽሟል ብለን እናፅናናለን እንጂ ወዲያ አሽቀንጥረን አንጥለውም። የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ተስፋ ስታደርገው የነበረውን ሁሉ አሁን እኛ ወርሰነዋል፣ አሁን ለእኛ ይዞታችን ነው።

ታዲያ ዛሬ ተስፋችን ምንድን ነው?

በኢየሱስ ክርስቶስ ለማያምኑ ሰዎች ምንም ተስፋ የላቸውም።

ኤፌ 2፥ 12፦ "በዚያ ዘመን ከእስራኤል መንግሥት ርቃችሁ ለተስፋውም ቃል ኪዳን እንግዶች ሆናችሁ በዚህም ዓለም ተስፋን አጥታችሁ ከእግዚአብሔርም ተለይታችሁ ያለ ክርስቶስ ነበራችሁ።"

እምነታችንን በኢየሱስ ክርስቶስ ላይ ላደረግን ሁሉ ግን ሰማይ ተስፋችን ነው። ቀደም ሲል ያልነውን አትርሱ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊው ተስፋ የመልካም ምኞት መግለጫ ንግግር አይደለም፤ ይልቁንም ወደፊት ስለሚመጣ እርግጠኛ መልካም ነገር ፍጹም የሆነ መተማመን ነው።

2ቆሮ 5፥ 1 ፦ "ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ፥ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘላለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንጻ እንዳለን እናውቃለንና።"

ጳውሎስ እዚህ ላይ “ድንኳን” የሚለውን ቃል ሥጋዊውን ተዳሳሽ  አካል በሚወክልበት መንገድ እየተጠቀመበት ነው።  ጴጥሮስም፦
 
በ2ኛ ጴጥሮስ 1፥ 13-14 ባለው ክፍል "ሁልጊዜም በዚህ ማደሪያ ሳለሁ በማሳሰቤ ላነቃችሁ የሚገባኝ ይመስለኛል። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳመለከተኝ ከዚህ ማደሪያዬ መለየቴ ፈጥኖ እንዲሆን አውቃለሁና።" ሲል የተጠቀመበት ማደሪያ የተሰኘው ልቃ ተመሳሳይ አጠቃቀም አለው።

ምእመናን፣ ሁላችንም አንድ ቀን በአካል እንሞታለን፣ ይህም የማይለወጥ ተፈጥሯዊ ህግ ነው። "ለሰዎች አንድ ጊዜ መሞት ከዚያም በኋላ ፍርድ ተመድቦላቸዋል" ተብሏልና፤ ይህ በሚሆንበት ጊዜ ግን ወደ ሰማይ እንሄዳለን እንጂ እልም ብለን እንጠፋለን ማለት አይደለም፣ ወደ እሳት ባህርም እንጣላለን ማለት አይደለም፤ እንሞታለን ግን በተስፋ እንሞታለን። ተስፋ ያለው ሞት የአማኞች ሞት ነው፤ አማኝ ሲሞት "ከሞት ወደ ህይወት የተሻገረ" ሟች እንጂ "ወደ ፍርድ አይሄድም" ።

2ቆሮ 5፥ 6-8 "እንግዲህ ሁልጊዜ ታምነን፥ በእምነት እንጂ በማየት አንመላለስምና በሥጋ ስናድር ከጌታ ተለይተን በስደት እንዳለን የምናውቅ ከሆንን፥ ታምነናል ይልቁንም ከሥጋ ተለይተን በስደት መኖር በጌታም ዘንድ ማደር ደስ ይለናል።"

እንግዲህ ተስፋችን (ተስፋ ትርጉሙ፡- “ስለ ወደፊቱ ያለን ፍጹም እርግጠኝነት ነው)” ይኸውም በሞታችን ጊዜ ይህን አካል ትተን ስንሄድ በሰማያት ከጌታ ጋር ለዘላለም አብረን እንደምንሆን ያለን አለኝታ ነው።

የብሉይ ኪዳንን መጻሕፍት ጠንቅቀው የሚያውቁ ሁሉ የሳባ ንግሥት የነበረችው ሰሎሞንን ለመጎብኘት ያደረገችውን የጉዞ ታሪክ ያስታውላሉ ብዬ አስባለሁ።  የሳባ ንግሥት የሰሎሞንን ታላቅነት፣ የክብሩንና የጥበቡን ዝና ሁሉ ሰምታ ነበር።  አገልጋዮቿም ስለሚያውቁት የዚህን ሰው ታላቅ ዝና ምን እንደሚመስል ሀሳብ ሊሰጧት ሞክረው ነበር።  እነርሱም የሰለሞንን ክብር በግልፅ እና በብርቱ ቃል ነገሯት።  እሷ ግን የሰማችውን ሁሉ በቀላሉ  ማመን አልቻለችም።  ይልቁንም ራሷ ሄዳ የሰማችውን በአይኗ ለማየት እንደወሰነች በ1ኛ ነገሥት 10 ላይ ከተጻፈው ታሪክ እናነባለን።  በመጣችም ጊዜ የሰሎሞንን ጥበብ በጆሮዋ ሰማች እርሱም በልቧ ያለውን ሁሉ ነገራት።  እሷም ብዙ የተለያዩ ጥያቄዎችን ጠየቀችው፣ ክብሩን፣ ልብሰ መንግስቱን እና በመንግስቱ ላይ ያሉትን የከበሩ ነገሮች ሁሉ አየች።  የንጉሥ ሰሎሞንንም ክብር ሁሉ እያየች፣ ንጉሡንም አለችው፦

1ነገስት 10፥ 6-7 " ስለ ነገርህና ስለ ጥበብህ በአገሬ ሳለሁ የሰማሁት ዝና እውነት ነው። እኔም መጥቼ በዓይኔ እስካይ ድረስ የነገሩኝን አላመንሁም ነበር፤ እነሆም፥ እኩሌታውን አልነገሩኝም ነበር፤ ጥበብህና ሥራህ ከሰማሁት ዝና ይበልጣል።"

"እኩሌታውን አልነገሩኝም ነበር፤" ወደ ሰማይ የሚሄዱ ሰዎችም የሚያጋጥማቸው እንዲህ ያለው ነገር ይሆናል።  ሰማይ ምን እንደሚመስልና ምን እንደሆነ ከፊሉ እንኳ ገና ሊነገርህ አልተቻለም። ሞተህ እዚያው ስትሄድ አንተው ራስህ ታየዋለህ።

ሰማይ ግን የት ነው?

ለዚህ ጥያቄ መልስ እንዲሆነን መጽሐፍ ቅዱስ ሰማይ መንፈሳዊ እንደሆነ ይነግረናል።  ሰማይ እውን ነው፤ ሰማይ ከምድር በተለየ ግዛት ውስጥ ብቻ ያለ ነው።  በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ስለ ሰማያዊው ዓለም እና ስለ ምድራዊው ዓለም በግልጽ እናነባለን።  ምድራዊው ዓለም የሥጋ፣ የቁሳቁስና፣ ለዓይናችን የሚታየው ነገር ሁሉ ነው። ልናየው፣ ልንዳስሰው፣ ልናሸትተው፣ ልንሰማው፣  እና ልንቀምሰው የምንችለው ተዳሳሹ ግዛት ነው።

በሌላ በኩል ሰማይ መንፈሳዊ ነው። ሰማይ ተፈጥሮው ሰማያዊ (ቀለሙን እንዳይመስላችሁ) ነው።  በነዚህ አይኖቻችን ልናየው አንችልም።  በነዚህ ጆሮቻችን ልንሰማው አንችልም።  በእነዚህ እጆቻችን ልንዳስሰውና ሊሰማን አንችልም።  በምላሳችን ልንቀምሰውም ሆነ በአፍንጫችን ልናሸትተው  አንችልም።  ሰማይ ከምድር በሆነ ምንም ነገር አልተሰራምና ምድራዊ በሆነ የትኛውም እሳቤ አይተረክም። ጳውሎስ ለግሪክ ፈላስፋዎች ሲናገር ፦

ሐዋ17፥ 24 "ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ ነውና እጅ በሠራው መቅደስ አይኖርም፤" ይላል።

ጳውሎስ ይህንን በግሪክ ፈላስፎች ፊት የተናገረው የማርስ ኮረብታ እያሉ በሚጠሩት አርዮስፋጎስ ላይ ቆሞ ነበር።  ግሪኮች ለአማልክቶቻቸው የድንጋይ ቤቶችን ይሰሩ ነበር። ለአማልክቶቻቸውም ልዩ ልዩ ስጦታዎችን ይሰጡ ነበር፤ እንዲበሉላቸውም ፍራፍሬና ሥጋ ያቀርቡላቸው ነበር።  ምናልባትም የጥንት ጣዖት አምላኪዎች ለጣዖቶቻቸው ሰይፍና ታንኳ፣ እንዲሁም ከሞት በኋላ ያለውን ሕይወት የሚያገለግሉ ሁሉንም ዓይነት መሣሪያዎች ያቀርቡ ይሆናል።  ከዚህ ምድራዊ አለምን የህይወት ቅርጽ ጽንሰ አሳብ ተነስተው የአማልክቶቻቸውን ተፈጥሮና ግዛታቸውን ፅንሰዋል።  ጳውሎስም ሲናገር ይህ  ሞኝነት ነው አለ።  ሰማይ መንፈሳዊ ነው።  ሰማይ ዘላለማዊ እና ሕያው የሆነ አምላክ የፈጠረው ቦታ ነው።  መላእክት የሚኖሩበት ቦታ ነው።  በዕብራውያን ውስጥ እንደምናነበውም የጻድቃን መንፈሶች አሁን ፍጹማን ሆነው የተከማቹበት የክብር ስፍራ ነው።  ሰማይ ቅድስተ ቅዱሳን ናት፤ የከበረች ናት፤ ከፍ ያለች ናት፤ ፍትሐዊም ናት።

በሰማያዊውና በምድራዊው መካከል ያለውን ልዩነት መፅሃፍ ቅዱስ የሚነግረን ከክብር አንፃር ነው።  ሰማይ ከፍ ከፍ ያለ ነው። ሰማይ ከፍ ያለውና በከፍታው የሚኖረው - በአካላዊና በተፈጥሯዊ ሁኔታ አይደለም። ሊለካና ሊሰፈር በሚችል ከፍታም ከፍ ያለ አይደለም። ነገር ግን ሰማይ ከፍ ያለው፣ በግርማው የከበረ፣ በእግዚአብሔር ክብር ከፍ ከፍ ያለ፣ በእግዚአብሔር ቅድስና ከፍ ያለ ሰማያዊ ከፍታ በመሆኑ ነው። በመዝሙር 113 ላይ እንዲህ ይላል፦

 መዝ 113፥ 4-5፦ "እግዚአብሔር በአሕዛብ ሁሉ ላይ ከፍተኛ ነው፥ ክብሩም ከሰማያት በላይ ነው። እንደ አምላካችን እንደ እግዚአብሔር ማን ነው? በላይ የሚኖር፤"

በግርማው ከፍ ያለ! እንደገናም እንዲህ የሚል እናነባለን፦

ኢሳ 57፥ 15፦ "ለዘላለም የሚኖር ስሙም ቅዱስ የሆነ፥ ከፍ ያለው ልዑል እንዲህ ይላል፦ የተዋረዱትን ሰዎች መንፈስ ሕያው አደርግ ዘንድ፥ የተቀጠቀጠውንም ልብ ሕያው አደርግ ዘንድ፥ የተቀጠቀጠና የተዋረደ መንፈስ ካለው ጋር በከፍታና በተቀደሰ ስፍራ እቀመጣለሁ።"

እንደገናም በኢሳይያስ 63 ላይ እንዲህ ይላል፦

ኢሳ 63፥ 15፦ "ከሰማይ ተመልከት፥ ከቅዱስነትህና ከክብርህም ማደሪያ ጐብኝ፤ ቅንዓትህና ኃይልህስ ወዴት ነው? ለእኔም የሆነው የልብህ ናፍቆትና ርኅራኄህ ተከለከለ።"

ሰማይ የእግዚአብሔር የቅድስናውና እና የክብሩ ቦታ ነው።  ሰማያት ንጹሕ፣ ቅዱስ ፣ የከበረም ነው።  ሰማይን ከማየትህ በፊት እግዚአብሔር አዲስ መንፈሳዊ ዓይኖችን ሊሰጥህ ይገባል።

ሰማይ ምንድን ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ በሁሉም ስፍራ፡- ሰማይ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነው ሲል መልስ ይሰጣል። ከሕያው እና ከእውነተኛው አምላክ ጋር ፍጹም የሆነ ኅብረት የሚኖረንበት ቦታ ነው።  ያ እውነት በሁሉም ቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ እንደ ሸማኔ መውርውሪያ ወዲና ወዲህ እያለ የሚፈስ የወርቅ ክር ነው።  ሰማይ ይህ ነው፡ የእግዚአብሔር ማደሪያ እንደሆነም በተደጋጋሚ ተነግሮናል።  ፍጡር የተባረከውን የሕያው እግዚአብሔር ኅብረት ሊደሰት በሚችልበት መጠን የእግዚአብሔር ኃልዎት በሙላት የሚገለጥበት እና የእግዚአብሔርን ፍጹም መገኘት ሙሉ በሙሉ የሚደሰትበት ስፍራ ነው።

መጽሐፍ ቅዱስ ሰማይን ለመግለጽ እነዚህን ቃላት ይጠቀማል፡- ቅዱስ ማደሪያ፣ መኖርያው፣ የተቀደሰው ማደሪያው፣ ከፍ ያለው የመቅደሱ ከፍታ።  መጽሐፍ ቅዱስ በሰማያት ስለሚኖረው ስለ እግዚአብሔር ይናገራል። ሰማይ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነው፣ እግዚአብሔርን በቅርብ የምናውቅበት ሕይወት እና ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ሕይወት የምንደሰትበት ስፍራ ነው። ታውቃላችሁ፣ "መኖርያ" የሚለው ቃል በጣም ሀብታም ቃል ነው፤ ቃሉ  በቀላሉ ከመኖር የበለጠ ማለት ነው።  እኔ የምኖርበት ቦታ ነው ስትል፣ ያለህበትን ቦታ እያልክ አይደለም።  ነገር ግን "መኖርያ" የሚለው ቃል የህብረትን ሀሳብ የተሸከመ ቃል ነው። የምትኖርበት ቦታ ማንነትህን የምትገልጥበት ነው።  በዚያ አንተ የተከፈትህ ነህ።  ፍቅርህን በዚያ ታሳያለህ፣ ቅርብ የሆኑ የህይወትህን ክፍሎች ታጋራለህ። ስለዚህ ሰማይ የእግዚአብሔር ማደሪያ፣ መገኛውና ኅብረቱ፣ የእግዚአብሔር ፍቅርና ጸጋ የሚታወቅበት ቦታ ነው።  ሰማይን ሰማይ የሚያደርገው ያ ነው። የሰማይ ክብሩም ይኸው ነው፣ እርሱም ከመታወቅ የሚያልፍ እኛ መገመት የማንችለው ነገር ነው። ጳውሎስ ስለ ሰማይ ያለውን ነገር ልብ ብላችሁ አስተውሉ፡-

2ቆሮ 12፥ 1-4 "ትምክህት የሚያስፈልግ ነው፤ አይጠቅምም ነገር ግን ከጌታ ወዳለው ራእይና መገለጥ እመጣለሁ። ሰውን በክርስቶስ አውቃለሁ፥ በሥጋ እንደ ሆነ አላውቅም ወይም ከሥጋ ውጭ እንደ ሆነ አላውቅም፥ እግዚአብሔር ያውቃል፤ እንዲህ ያለው ሰው ከአሥራ አራት ዓመት በፊት እስከ ሦስተኛው ሰማይ ድረስ ተነጠቀ። እንዲህ ያለውንም ሰው አውቃለሁ፥ በሥጋ እንደ ሆነ ወይም ያለ ሥጋ እንደ ሆነ አላውቅም፥ እግዚአብሔር ያውቃል፤ ወደ ገነት ተነጠቀ፥ ሰውም ሊናገር የማይገባውን የማይነገረውን ቃል ሰማ።"

መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ሰማይ ብዙና ዝርዝር ነገር አይነግረንም፤ ይህም ጉዳዩ አሁን ከመረዳት አቅማችን በላይ ስለሆነና፣ "ሰውም ሊናገር የማይገባው የማይነገረው ቃል" በመሆኑ ብቻ አይደለም። ነገር ግን ሰማይ በመሰረቱ ምጡቅ የእግዚአብሔር ማደሪያ መሆኑንም ጭምር በጥልቀት እንድንረዳና እንድንናፍቀው እግዚአብሔር ስለሚፈልግ ነው።  ሰማይን እጅግ የተባረከ፣ ግርማ ሞገስ ያለው፣ በግርማውም እጅግ አስፈሪ ስፍራ የሚያደርገው አንድ ማዕከላዊ ነገር አለው። ይህም  አንድ ነገር፤ በዚያ እግዚአብሔርን በዘላለማዊ ህያውነቱ የምናየው መሆኑን ነው።

ምእመን ልብ ብላችሁ ስሙ፣ ተስፋችን ያ ነው - እርሱም ሰማይ። በ1ኛ ተሰሎንቄ ትምህርት መሠረት፣ በሞታችን ቀን ጌታን በአየር ላይ ለመቀበል እንወሰዳለን፣ እናም ከጌታ ጋር ለዘላለም እንሆናለን።  ይህ ታዲያ እንዴት ያለ በጽኑ የሚናፈቅ ታላቅ ተስፋ ነው።

1ተሰ 4፥ 17 "ከዚያም በኋላ እኛ ሕያዋን ሆነን የምንቀረው፥ ጌታን በአየር ለመቀበል ከእነርሱ ጋር በደመና እንነጠቃለን፤ እንዲሁም ሁልጊዜ ከጌታ ጋር እንሆናለን።"

"እንነጠቃለን" የሚለው ቃል በግሪኩ harpazo ይሰኛል፣ ትርጉሙም፡- “መወሰድ” ማለት ነው።  “መነጠቅ” የሚለው ቃልም የመጣው ከዚህ ነው። ነገር ግን በእርግጠኝነት “መወሰድ” ማለት ቁስ የሆነውን ሥጋዊ አካልን ከምድር ላይ ወደ ሰማይ ከባቢ አየር (ጠፈር) ከማስወጣት ተግባር የተለየ ነገር ነው።  ሃርጳዞ የሚለው ቃል የሚያመለክተው ክርስቲያን ያለ ቁሳዊ አካሉ "መወሰዱን" ነው።

የተነጠቀው ተዳሳሹ ሥጋዊው አካል አይደለም።  በሥጋዊው ሞት ጊዜ ሥጋውን ትቶ ወደ መንፈሳዊው ዓለም ሲሸጋገር የተነጠቀው ራሱ ክርስቲያኑ ነው። ክርስቶስ በተመለሰ ጊዜ ያኔ አስቀድመው ሞተው የነበሩ አማኞች ተነስተዋል፣ ክርስቲያኖች ሁሉ ደግሞ በሥጋዊ ሞታቸው ጊዜ በደመና ይነጠቃሉ። 

(በዚህ ርዕሰ ጉዳይ "ንጥቀትና ትምህርቱ"፣ እንዲሁም "የተዋሩደው ስጋችን ልውጠት" በሚል ርዕስ በጽሁፍ ያስተማርሁበትን ማየት ለምትወዱ እነሆ ሊንኩ)፦

https://gizachewkr.blogspot.com/2018/01/blog-post.html?m=1

https://gizachewkr.blogspot.com/2021/08/blog-post.html?m=1


ወገኖች ሆይ፣ ከክርስቶስ ጋር ለዘላለም ለመኖር ወደ ሰማይ ከመወሰድ የበለጠ ምን ተስፋ አለን?  ይህም ቤተክርስቲያን አሁን በምድር ያለችበትና የምትጋደልለት ተስፋዋ ነው፣ ፕሪተሪዝምም ይህንን ተስፋ አጥብቆ ያረጋግጣል እንጂ ፈጽሞ አይክደውም።

ምዕመናን ስሙኝ፣  ፍርድን እንጂ ሥጋዊውን ሞት ልናመልጥ የምንችልበት ምንም አይነት መንገድ የለም - ሁሉም ሰው ይሞታል።

 እብራ 9፥ 27፦ "ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ እንደ ተመደበባቸው" ይላልና።

በአካል ስንሞት ግን ከጌታ ጋር ለዘላለም ወደምንኖርበት ሰማያዊው ዓለም በክብር እንሄዳለን! ይህ እንዴት ያለ መጽናናት የሞላበት የተባረከ ተስፋ ነው! ምዕመናን በሃሰተኛ ተስፋ አትታመኑ። ሞታችሁ በብጹዕ መሰናበት ከጌታ ጋር ለመሆን በቅጽበት አይን ትወሰዳላችሁ እንጂ በሞት መንገድ ሳትሄዱ የሰው ልብ ወልድ ቅዥት የሆነውን አካላዊ መነጠቅን ፈጽሞ አታዩም። በእምነትና በንስሃ ለሞታችሁ ቀን ተዘጋጁ እንጂ በማይፈጸም የንጥቀት ተስፋ ልባችሁን አታዝሉ።

ግዛቸው (ቄስ)