Thursday, February 28, 2019

ከዚህ ሕይወት በኋላ (ለሚያምኑ እና ለማያምኑ)

ከዚህ ሕይወት በኋላ
(ለሚያምኑ እና ለማያምኑ)

“ከሕይወት በኋላ” የተሰኘውን ሃረግ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ጨርሶ ማግኘት አይቻልም፤ ሆኖም ሰዎች በምድር ላይ ያላቸውን የሕይወት ዘመን ቆይታቸውን ጨርሰው ከሞቱ በኋላ ምን አይነት ሕይወት እንደሚኖራቸውና፣ ዘላለማዊ እድላቸውን በተመለከተ ያለውን ሁኔታ ሊያሳይ እንዲችል ሆኖ ጥቅም ላይ የዋለ ቃል መሆኑ በሁሉ ዘንድ ይታወቃል ። አማኞች ለሆኑ ከልዩ ልዩ ዘርና ወገን ለተመረጡትና ለተዋጁት ኃጢአተኞች፣ ከዚህ ሕይወት በኋላ ያለው ሕይወት ማለት ሊታይ በማይችለው ሰማያዊ መንግስትና ግዛት፣ በማይታየው የክርስቶስ ሀልዎት ፊት ሊኖሩ የሚቀበሉት ዘላለማዊ በረከት ነው።

የመጨረሻው ፍርድ ከተሰጠና ከተጠናቀቀ ከ70 ዓም በኋላ ወዲህ ያለን እግዚአብሔር ለሕይወት የመረጠን ቅዱስን ሁሉ በምንሞትበት ቅጽበት፣ ክርስቶስ ከቅዱሳኑ ሁሉ ጋር በክብር በሚገዛበት መንፈሳዊ ግዛት (spiritual realm)፣ ይኸውም  በአዲሲቱ ከተማ በኢየሩሳሌም ከ70 ዓም በፊት አስቀድመው ከሞቱ ቅዱሳን ጋር በሕይወት እንገናኛለን። ክርስቶስ በክብር በደመና ተመልሶ ከመጣበት ከ70 ዓም በኋላ ያሉ አማኞች ሁሉ እያንዳንዳቸው፣ የአዲሱ ኪዳን ወንጌል የሚያውጀው መንግስት አካል ሲሆኑ፣ “እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ፥ የብዙዎችን ኃጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ፥ ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታይላቸዋል።” (ዕብራውያን 9፥ 28) ተብሎ እንደተጻፈ፣ በዳግመኛ ምጽአቱ በክርስቶስ ሙሉ በሙሉ የተጠናቀቀውን ድነት አግኝተዋል።

አማኞች ሲሞቱ ወዲያውኑ በሰማያት የተዘጋጀላቸውንና የሚጠብቃቸውን፣ የማይሞተውን፣ የማይበሰብሰውን፣ የከበረውን፣ መንፈሳዊውን፣ የማይታየውን ሰማያዊውን አካል ይለብሳሉ። “ይህ የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሊለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሊለብስ ይገባዋልና። ዳሩ ግን ይህ የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሲለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሲለብስ፥ በዚያን ጊዜ፦ ሞት ድል በመነሣት ተዋጠ ተብሎ የተጻፈው ቃል ይፈጸማል” (1ቆሮንቶስ 15፥ 53-54)። ስለዚህ ያ ከስጋና ከደም የተሰራው አሮጌው አካላቸው ተመልሶ እንደገና ላይታሰብና ላይታይ ወደ ምድር አፈር ገብቶ ብስባሽ ይሆናል። በሚሞቱበት ጊዜ የተሻለውንና የሚበልጠውን ሰማያዊ አካል ይለብሳሉ እንጂ ራቁታቸውን ሆነው አይገኙም። ሟች የሆነው የአሮጌው ሥጋዊ አካል ሞት በአዲሱ የማይሞት መንፈሳዊ አካል ሕይወት ይዋጣል፣ እንጂ የሥጋ ትንሳኤ የሚባል ተረት አይኖርም።

“ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ፥ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘላለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንጻ እንዳለን እናውቃለንና። በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፥ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና  ለብሰን ራቁታችንን አንገኝም። በእውነትም የሚሞተው በሕይወት ይዋጥ ዘንድ ልንለብስ እንጂ ልንገፈፍ የማንወድ ስለ ሆነ፥ በድንኳኑ ያለን እኛ ከብዶን እንቃትታለን።” (2ቆሮንቶስ 5፥ 1-4)።

እግዚአብሔር በጸጋው ለመረጠን ለእኛ ለአማኞች ከዚህ ሕይወት በኋላ ያለው ዘላለማችን በአዲሲቱ ኢየሩሳሌም በክርስቶስ ሀልዎት ፊት በደስታ የምንቆምበት ነው።

“ቅድስቲቱም ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም፥ ለባልዋ እንደ ተሸለመች ሙሽራ ተዘጋጅታ፥ ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ። ታላቅም ድምፅ ከሰማይ፦ እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው ከእነርሱም ጋር ያድራል፥ እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤ እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና ብሎ ሲናገር ሰማሁ።” (ራእይ 21፥ 2-4)

የማያምኑ ግን ከዚህ ሕይወት በኋላ የሚጠብቃቸው እድል የማይታየው አለም አካል በሆነውና “ሲኦል” ወይም “የእሳት ባህር” ተብሎ በሚታወቅ ስፍራ ለዘላለም መሆን ነው። ቤዛነቱን የገፉ፣ እምነትን እምቢ ያሉ፣ መዳንንም ያልተቀበሉ የማያምኑ ኃጢአተኞች ሁሉ ከየትኛውም ዘር ቢሆኑ ዘላለማዊ ኩነኔ ይቀበላሉ። መጽሐፍ ቅዱስ የኃጢአተኞችን ዘላለማዊ እድል አስመልክቶ ሲናገር፦ “ለሰዎችም አንድ ጊዜ መሞት ከእርሱ በኋላም ፍርድ” ተመድቦባቸዋል፥ (እብራውያን 9፥ 27)፣ ሲል ይደነግጋል። ይህም ማለት በዘላለማቸው ውስጥ ትክክለኛውንና ጽድቅ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቁጣ በነፍሳቸው ለዘላለም ይቀበላሉ፣ ማለት ነው። (ሮሜ 2፥ 5፤ 9፥ 22፤ ኤፌሶን 5፥ 6፤ ቆላስይስ 3፥ 6፤ተሰሎንአግኝተዋል።እይእይእይ 14፥ 10-11)። ይህም ለሰዎችን ሁሉ የምናስጠነቅቅበት የእግዚአብሔር እውነት፣ በኢየሱስ ክርስቶስም አለማመን የተሰኘውን ዋና ኃጢአት የሚመጥን ጽኑ ፍርድ ነው እንጂ፣ ማንንም የምናስፈራራበት የፈጠራ ሽብር አይደለም።

“በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።” (ዮሐንስ 3፥ 36)

የዘላለምን ሕይወት ያገኙ በመሆንና ሕይወትን የማያዩ ሆኖ በእግዚአብሔር ቁጣ ስር የወደቁ በመሆን መካከል ያለው ወሳኝ  መስመር በልጁ ማመን ወይም አለማመን ብቻ ነው። የማያምኑ ሰዎችም ሕይወትን ሳያዩ በእርግጠኝነት ዘላለማቸውን የሚያሳልፉት ስጋንና ደምን ባላካተተ አካላዊነት መሆኑ እሙን ነው። ከተዳሳሹ አካላቸው ተነጥለው ነገር ግን መጽሐፍ ቅዱስ በሙላት ያልገለጠልን አንዳች አይነት የተለየ “አካል” ኖሯቸው፣ “እያወቁ”፣ “እየተሰማቸው”፣ “እያለቀሱ”፣ “እየጮኹ”፣ በነፍሳቸው ጸጸት እየተንገበገቡና ጥርሳቸውን እያፋጩ የእግዚአብሔርን ቁጣ ይቀበላሉ። ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ሲናገር ያልዳኑ ሰዎች በሚሞቱበት ጊዜ ወደ ሲኦል ይሄዳሉ ብሏቸዋል። ወደ ሲኦል የሚሄዱ ሰዎችን በተመለከተ እንዴት እንደሆነ ባይገባንም፣ ቢያንስ ግን መጽሐፍ ቅዱስ “እጆች”፣ “እግሮች” እና “አይኖች” እንደሚኖራቸው፣ “ትላቸውም እንደማይሞት” “እሳቱም እንደማይጠፋ” ይጠቅሳል

“እጅህ ብታሰናክልህ ቍረጣት፤ ሁለት እጅ ኖሮህ ትላቸው ወደማይሞትበት እሳቱም ወደማይጠፋበት ወደ ገሃነም ወደማይጠፋ እሳት ከመሄድ ጕንድሽ ሆነህ ወደ ሕይወት መግባት ይሻላል። እግርህ ብታሰናክልህ ቍረጣት፤ ሁለት እግር ኖሮህ ትላቸው ወደማይሞትበት እሳቱም ወደማይጠፋበት ወደ ገሃነም ወደማይጠፋ እሳት ከመጣል አንካሳ ሆነህ ወደ ሕይወት መግባት ይሻልሃል። ዓይንህ ብታሰናክልህ አውጣት፤ ሁለት ዓይን ኖሮህ ትላቸው ወደማይሞትበት እሳቱም ወደማይጠፋበት ወደ ገሃነመ እሳት ከመጣል አንዲት ዓይን ኖራህ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት ይሻልሃል። (ማርቆስ 9፥ 43-48)፤ በተጨማሪም ኢሳይያስ 66፥ 24 ላይ “ወጥተውም በእኔ ያመፁብኝን ሰዎች ሬሳቸውን ያያሉ፤ ትላቸው አይሞትምና፥ እሳታቸውም አይጠፋምና፤ ለሥጋ ለባሽም ሁሉ አስጸያፊ ነገር ይሆናሉ” ይላል።

ክርስቶስ በትምህርቱ፣ በሲኦል በስቃይ ያለ አንድ ባለጠጋ ሰው “አይኖች” እና “ምላስ” እንደነበሩት፣ መናገርና ማሰብ እንደተቻለው፣ ስሜትም እንደነበረው ጠቁሞናል። ነገር ግን በጉዳዩ ላይ ከዚያ ያለፈ ምንም ገለጻ አልተሰጠም (ሉቃስ 16፥ 22-24)፣ እኛም ከተጻፈው አልፈን ምንም ለማለት አንደፍርም። ክርስቶስ እንዳይነግስባቸው ለእምነት በማይታዘዙት ላይ የሚኖረው ዘላለማዊው የእግዚአብሔር ቁጣ ግን እርግጥ ነው፣ ምንም ጥርጥር የለውም። ያልዳኑ ሰዎች፣ አዳኛቸው እንዳይሆን ክርስቶስን እምቢ ያሉ እስከሆነ ድረስ፣ ወዮ ለእነርሱ!! ከዚህ ሕይወት በኋላ ፈጽሞ ሕይወትን አያዩም፣ የእግዚአብሔርንም ጸጋ አያውቁም አይለማመዱትምም። ስማቸውም በሕይወት መጽሐፍ የለም፣ አልተጻፈምም፤ ዘላለማዊ እድላቸውም ለእያንዳንዳቸው በእሳት ባህር ውስጥ መጣል ብቻ ነው
“በሕይወትም መጽሐፍ ተጽፎ ያልተገኘው ማንኛውም በእሳት ባሕር ውስጥ ተጣለ።” (ራእይ 20፥ 15)።

Sunday, February 24, 2019

ልጅነታችን

ልጅነታችን
ልጆች የተደረግንበት መንገድ፣ ይኸውም በእግዚአብሔር የተመረጡትን አማኞች ሁሉ እውነተኛና ትክክለኛ የእግዚአብሔር ልጆች ያደረጋቸው መለኮታዊ አሰራር መጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ ነው። እግዚአብሔር ባዳነን ጊዜ ያዳነን፣ በኃጢአታችን ምክንያት ከሚገባን እና ልንቀበለው ካለን ዘላለማዊ ቅጣት ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን በገዛ ራሱ ሰማያዊና መለኮታዊ ቤተሰብ ውስጥ ከእግዚአብሔር ልጅ ጋር ልጆቹ አድርጎ ደግሞ ተቀብሎናል። በውድ ልጁም ምክንያት ብቻ ወራሾቹ ልንሆን ልጆቹ አድርጎናል።

በፈጸመው ገደብ ያጣ ወንጀል ጽኑ ፍርድ ለሚገባው ወንጀለኛ፣ በፍርድ ዙፋኑ ላይ ተቀምጦ ያለው ዳኛ ህጉን ጠቅሶና ለዚያ ጥፋት ተገቢ የሆነው ዋጋ መከፈሉን አውጆ፣ ያንን ወንጀለኛ ምህረት ቢያደርግለት ያ አንድ ነገር ነው፤ ነገር ግን ዳኛው ከዚህ በላይ አልፎ በፍርድ ችሎት ላይ እንዳለ ያንን ምህረት የተደረገለትን ወንጀለኛ ሰው በርህራሄ አይን አይኑን እያየ፣ “ከዛሬ ጀምሮ ከልጆቼ እንደ አንዱ ትቆጠርና የቤተሰቤ አባል እንድትሆን እንደ ልጅ ተቀብዬሃለሁ፣ እነሆ ልጄ ሆነሃል!” ቢለውና አቅፎ ቢስመው፣ ወደ ቤተሰቡም ወስዶ ቢቀላቅለው፣ ከተወላጅ ልጆቹም እንደ አንዱ ሆኖ በገበታው ከእርሱ ጋር እንዲቀመጥ ርስቱንም እንዲካፈል እኩል መብት ቢሰጠው ይህ ደግሞ ከምህረትና ከይቅርታ ያለፈ ሌላ ነገር ነው። ምናልባት ልጆቹ የተደረግንበትን የጸጋ አሰራር የሚያሳይ ከዚህ የተለየና የተሻለ ምሳሌ ይኖር እንደሆነ አላውቅም። ለእግዚአብሔር ልጆቹ ይሆንነው ግን እርሱ ከውድ ልጁ የተነሳ እንደ ልጆች ተቀብሎን ነው። ልጆች የሆንነው ልክ እንደ ጉዲፈቻ (adopted) ተደርገን ነው። ይህ የትኛውንም ኃይማኖታዊ የሆነ ባዶ የስጋ ኩራትና ትምክህትን ያስወግዳል ብዬም አምናለሁ። ልጅነታችን የተሰራበት ይህ የጉዲፈቻ (adoption) መንገድ ከጠፋብን ከጸጋው ተለይተን የኃይማኖትና የማንነት ኩራትና ትምክህት ፈተና ውስጥ እንወድቃለን

ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታችንና መድሃኒታችን፣ ንጉሳችንና ሊቀ ካህናታችን ነው፣ እኛም በእርሱ (ውስጥ) ነን። ሁሉም ነገራችን ያለው ኢየሱስ ጋር ነው፣ ከእኛ በእኛ የሆነ ምንም የለም። እርሱ ከአባቱ ጋር ሊያስታርቀን፣ ፍጹም የሆን የመታዘዝን ሕይወት ኖሮ ፍጹም የሆነ መስዋዕታዊ ሞትን ሞተ፤ ሕጉ የሚጠይቀውንና መከፈል የነበረበትንም የኅጢአት እዳ በመስቀሉ ደም ከፍሎ ሥርየትን ሰጠን፤ የዘላለምንም ሕይወት በትንሳአኤው አምጥቶ በጸጋው አደለን፤ ባለመታዘዝ የጠፋነውንና በበደላችን ምክንያት የሞትነውንም ለአዲስ ሕይወት አስነስቶ ወንድሞቹና እህቶቹ በምንሆንበት ማዕረግ የእግዚአብሔር ልጆች አደረገን። ይህም የጸጋው ክብር ይመሰገን ዘንድ፣ እኛም ለክብሩ ምስጋና እንሆን ዘንድ ያደረገው ነው።

ሁሉም ነገር የእርሱ የኢየሱስ ነው፣ አብ ልጁን ይወዳል፣ ማጽደቅንም መኮነንንም ሰጥቶታል፤ የእግዚአብሔር የተስፋ ቃላትና በረከቱ ሁሉ የእርሱ ነው። የእርሱ ያልሆነ ምንም የለም። በጸጋው የእግዚአብሔር ልጆች የተደረጉ ሁሉ፣ የእርሱ ለእርሱ እና በእርሱ ናቸው። እግዚአብሔር ህጋዊና አግባብ በሆነ መንገድ፣ ይኸውም በራሱ ሉዓላዊ የጸጋ አሰራር በእርሱ ፊት እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ መብትና ስልጣንን አጎናጽፎ የእርሱ የክርስቶስ ስላደረገን፣ የእርሱ የሆንን ሁላችን ከእርሱ ጋር አብረን የምንወርስ ሆነናል። እኛ ክርስቲያኖች ከክርስቶስ የተነሳ ያለፍርሃትና ያለጭንቀት፣ ሙሉ በሆነ መተማመን፣ ግርማን ወደ ተሞላው ወደ እግዚአብሔር የጸጋ ዙፋን መቅረብ እና መምጣት እንችላለን፤ “አባ አባት” ብለን ልንጠራውም እንችላለን። ፍጻሜ በሌለው መንግስቱም ከዘላለም የተዘጋጀውን የመዳንን ተስፋም ወርሰናል።

“ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤ እንደ ልጆች እንሆን ዘንድ፥ ከሕግ በታች ያሉትን ይዋጅ ዘንድ። ልጆችም ስለ ሆናችሁ እግዚአብሔር አባ አባት ብሎ የሚጮኽ የልጁን መንፈስ በልባችሁ ውስጥ ላከ። ስለዚህ ከእንግዲህ ወዲህ ልጅ ነህ እንጂ ባሪያ አይደለህም፤ ልጅም ከሆንህ ደግሞ በክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሽ ነህ።” (ገላትያ 4፥ 4-7)

ይህ አባ የተሰኘውን አጠራር ጌታ ኢየሱስ በጌትሰማኒ በስቅላቱ ዋዜማ ትጨንቆ ሲጸልይ በምን ሁኔታ እንደተጠቀመው በማርቆስ ወንጌል ላይ ተመልከቱ፦

“አባ አባት ሆይ፥ ሁሉ ይቻልሃል፤ ይህችን ጽዋ ከእኔ ውሰድ፤ ነገር ግን አንተ የምትወደው እንጂ እኔ የምወደው አይሁን አለ” (ማርቆስ 14፥ 36)

ጌታችን አባቱን የሚጣራበትን ቅርበትና ዝምድና አስተውሉ “አባ አባት ሆይ፥” በዚያ በጭንቀቱ ሰዓት እንዲህ ብሎ መጣራቱ የሚይሳየው በልጁና በአባቱ መካከል ያለውን ታላቅ ግንኙነት፣ ኢየሱስስም ለአባቱ በእቅፉ ያለ የባህርይ ልጅ እንደመሆኑ በአብ ላይ ያለውን አስገራሚ መደገፍ ነው። የመከራውን ጽዋ ለመጨለጥ አቅምና ጉልበት የሆነው የአባቱ ልጅ መሆኑን ከማወቁ ነው። ለእኛም በእርሱ ላይ ያለን መደገፍ የሚቀዳው “በሰማይና በምድር ያለ አባትነት ሁሉ ከሚሰየምበት ከአብ ፊት” ነው። እንደ እግዚአብሔር ልጆች ለመኖር በጸጋው በታደልነው በዚህ ሕይወት የምናልፍበትን የትኛውንም ተግዳሮት ፊት ለፊት ተጋጥመን አቸንፈን የምንወጣውም በአባትነቱ ፍቅርና በመንፈስ ቅዱስ መሰጠት በተረጋገጠው የልጅነታችን ማዕረግ ነው፦

“በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና። አባ አባት ብለን የምንጮኽበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና።” (ሮሜ 8፥ 14-15)
(gKR)

Monday, February 18, 2019

የአብርሃም እቅፍ

የአብርሃም እቅፍ
“ቀይ ልብስና ቀጭን የተልባ እግር የለበሰ አንድ ባለ ጠጋ ሰው ነበረ፥ ዕለት ዕለትም እየተመቸው በደስታ ይኖር ነበር። አልዓዛርም የሚባል አንድ ድሀ በቍስል ተወርሶ በደጁ ተኝቶ ነበር፥ ከባለ ጠጋውም ማዕድ ከሚወድቀው ፍርፋሪ ሊጠግብ ይመኝ ነበር፤ ውሾች እንኳ መጥተው ቍስሎቹን ይልሱ ነበር። ድሀውም ሞተ፥ መላእክትም ወደ አብርሃም እቅፍ ወሰዱት፤ ባለ ጠጋው ደግሞ ሞተና ተቀበረ። በሲኦልም በሥቃይ ሳለ አሻቅቦ አብርሃምን በሩቅ አየ አልዓዛርንም በእቅፉ። እርሱም እየጮኸ፦ አብርሃም አባት ሆይ፥ ማረኝ፥ በዚህ ነበልባል እሣቀያለሁና የጣቱን ጫፍ በውኃ ነክሮ መላሴን እንዲያበርድልኝ አልዓዛርን ስደድልኝ አለ። አብርሃም ግን፦ ልጄ ሆይ፥ አንተ በሕይወትህ ሳለህ መልካም እንደ ተቀበልህ አስብ  አልዓዛርም እንዲሁ ክፉ፤ አሁን ግን እርሱ በዚህ ይጽናናል አንተም ትሣቀያለህ። ከዚህም ሁሉ ጋር ከዚህ ወደ እናንተ ሊያልፉ የሚፈልጉ እንዳይችሉ፥ ወዲያ ያሉ ደግሞ ወደ እኛ እንዳይሻገሩ በእኛና በእናንተ መካከል ታላቅ ገደል ተደርጎአል አለ” (ሉቃስ 16፥ 19-26)።

“የአብርሃም እቅፍ” የተሰኘው ሃረግ ገነትን ለማመልከት ጥቅም ላይ የዋለ ጽንሰ ሃሳብ ነው። ገነት በግሪኩ paradeisos በስትሮንግስ የግሪክ ቃላት መፈለጊያ #3857 አትክልት ለሞላበት አረንጓዴ ፓርክ ወይም የመናፈሻና የመዝናኛ ስፍራ የሚል ትርጉምን የሚሰጥ ምስራቃዊ ቃል ነው፣ እርሱም ኤደን ይባላል፣ ይኸውም እጅግ ደስ የሚልና ደስታ የሞላበት ስፍራ ነው፤ ሲል ያብራራዋል። ኢየሱስ በመስቀል ላይ ከጎኑ ተሰቅለው ከነበሩ ወንበዴዎች ንስሃ ለገባው ለአንዱ “እውነት እልሃለሁ፥ ዛሬ ከእኔ ጋር በገነት ትሆናለህ” (ሉቃስ 23፥ 43) ሲል እንደ ነገረው እናውቃለን።

ገነት የሆነው “የአብርሃም እቅፍ” ማለት ሃደስ (ሲኦል) በተሰኘው ስፍራ የሚገኝና የሞቱ ጻድቃን መንፈሶች ትንሳኤን የሚቀበሉበትን የቤዛነታቸውን ቀን እየተጠባቡቁ የሚቆዩበት ቦታ ነው። በመላው መጽሐፍ ቅዱስም ይህ “የአብርሃም እቅፍ” የተሰኘ ሃረግ የተጠቀሰው  በሉቃስ 16፥ 22-23 ባለው ክፍል አድ ጊዜ ብቻ ነው። ክርስቶስ ይህንን የተናገረውም ፈሪሳውያን ከደቀመዛሙርቱ ጋር ሊሰሙት በተገኙበት ነው። ሲኦል በእብራይስጥ ሼኦል በመጀመርያውም ኪዳን ከአጠቃላይ ትንሣኤ አስቀድሞ ሙታን የሚከማቹበት ቦታ ነው። በአይሁድ እምነት በኪዳኑ የታመኑ እስራኤላውያን በሞታቸው ጊዜ "ወደ አባቶቻቸው ተከማቹ" እስከ ተባለላችው ድረስ፣ ያ የሚከማቹበት ስፍራ ወይም ሲኦል “የአብርሃም እቅፍ” ተብሎም ይታወቃል። ስለዚህ ሲኦል ሁልጊዜ እና የግድ የስቃይና የቅጣት ቦታ ብቻ ላይሆንም ይችላል ማለት ነው። ለምሳሌ፣ ከአባቶች መካከልእንደ ያእቆብ ያሉ ታማኝ የያሕዌ ባሪያዎችም ከሞትን በኋላ እንሄድበታለን ብለው የሚጠብቁት ስፍራ እንደሆነ እናያለን፦

"ወንዶች ልጆቹና ሴቶች ልጆቹም ሁሉ ሊያጽናኑት ተነሡ፤ መጽናናትን እንቢ አለ፥ እንዲህም አለ፦ ወደ ልጄ ወደ ሙታን ስፍራ እያዘንሁ እወርዳለሁ። አባቱም ስለ እርሱ አለቀሰ።" (ዘፍጥረት 37፥ 35)

"እርሱም አለ፦ ልጄ ከእናንተ ጋር አይወርድም፤ ወንድሙ ሞቶ እርሱ ብቻ ቀርቶአልና፤ በምትሄዱበት መንገድ ምናልባት ክፉ ነገር ቢያገኘው ሽምግልናዬን በኅዘን ወደ መቃብር ታወርዱታላችሁ።" (ዘፍጥረት 42፥ 38)

" ይህንም ከእኔ ለይታችሁ ደግሞ ብትወስዱት ክፋም ቢያገኘው፥ ሽበቴን በኅዘን ወደ መቃብር ታወርዱታላችሁ። ....  ባሪያዎችህም የባሪያህን የአባታችንን ሽበት በኅዘን ወደ መቃብር ያወርዳሉ።" (ዘፍጥረት 44፥ 29፣ 31)

በእነዚህና መሰል በርካታ የብሉይ ኪዳን ምንባባት፣ አባቶች በሞታቸው ጊዜ እንወርድበታለን የሚሉት የ”ሙታን ስፍራ” እርሱም “መቃብር” ሲኦልን የሚያመለክት እንደሆነ፣ በዚያም አንቀላፍተው ከአባቶቻቸው ጋር የሚከማቹበት “የአብርሃም እቅፍ” መሆኑን እናስተውላለን።

በዚህ የክርስቶስ ምሳሌ ገለጻ ውስጥ “ሲኦል” የተባለውን ሃደስን፣ እርሱም ሙታን ከአጸደ ሥጋ ተለይተው በአጸደ ነፍስ የሚሄዱበትን ሥፍራ፣ ከአንዱ ወደ ሌላው ማንም አቋርጦ ማለፍ እንዳይችል  በመካከሉ በጥልቅ ጉድጓድ፣ በገደል፣ ወይም በታላቅ መለያየት በተከፈለ ሁለት ምድብ ገጽታው ያቀርበዋል። ስፍራውም የሲኦል የእረፍት ቦታን እና የሲኦል የስቃይ ቦታን በሁለት ከፍሎ የያዘ ነው። ምሳሌው የሚያመልክተን አንዱ እውነታ ኃጢአተኞችም ሆኑ ጻድቅን ሁለቱም ወገኖች ስጋና ደም ከሆነ ተዳሳሽ አካል ተለይተው በአጸደ ነፍስ ሆነው ያሉበት ሃደስ ውስጥ ንቁ እና የሚያውቁ መሆናቸውን ነው። በተጨማሪም ለነዚያ በስቃይ ሃደስ ውስጥ ላሉ ሙታን ሁለተኛ የይግባኝ እድልም ሆነ ወይም አጠቃላይ (universal) እርቅ የሌለ መሆኑን ይህ ምሳሌ ያረጋግጥልናል።

ክርስቶስ ሲናገር “አልዓዛር” የሚባል አንድ ደሃ ለማኝ ሰው በሞተ ጊዜ “መላእክት ወደ አብርሃም እቅፍ ወሰዱት” ይለናል። አንድ ባለጠጋ ሰው ደግሞ ሲሞት ተቀበረና በስቃይ ስፍራ ሆነ ይለናል። ይህንን የስቃይ ስፍራ በግሪኩ “bsanos” ይለዋል፣ ስትሮንግስ የተሰኘው የግሪክ ቃላት መፈለጊያ #931 ሲተረጉመው፣ እጅግ የከፋ ስቃይን የቀላቀለ  በቀል ባለበት ሁኔታ፣ በምስያው ጥቋቁር ድንጋዮች እየተሰቃዩ እንደሚፈተኑባቸው፣ ብረቶችም እንደሚቀልጡባቸው ያለ ጥልቀት ውስጥ መውረድ ይለዋል። ይህ እንግዲህ አማኝ ያልነበሩ የአሮጌው ኪዳን ኃጢአተኞች፣ ከሞቱ በኋላ በ70 ዓ.ም የሚሆነውን ይግባኝ የሌለውን የመጨረሻ ፍርድ እየተጠባበቁ የሚቆዩበት በሃደስ ውስጥ የተዘጋጀላቸው የስቃይ ስፍራ ያለበት ምድብ ነው። ያ ሟች ባለጠጋ ሰው ከሲዖል የስቃይ ስፍራ ሆኖ አሻቅቦ ሲያይ አብርሃምንና አልዓዛርን ተመለከተ።

ባለጠጋው ሰው በእሳት ነበልባል እየተሰቃየ ስለነበር፣ ለአብርሃም ያቀረበው ጥያቄ አልዓዛር በጣቱ ጥቂት ውሃ ይዞ ምላሱን እንዲያረጥብለት ነበር። አብርሃም ግን ለባለጠጋው ሲመልስለት ይህ አይቻልም! ምክንያቱም አንተ በምድር ሳለህ እጅግ ተመችቶህ መልካሙን እየተቀበልህ በመጽናናት ስትኖር አልዓዛር ደግሞ በከፋ ስቃይ ውስጥ መከራን እየተቀበለ ነበር። አሁን ግን ሁለቱም ከሞቱ በኋላ በአጸደ ነፍስ ሆነው አልዓዛር መጽናናትን ባለጠጋው ደግሞ ስቃይን እየተቀበሉ መሆናቸውን ያመለክታል። ጨምሮም አብርሃም ሲናገር መጽናናት ባለበት የሃደስ ምድብ (ይኸውም የአብርሃም እቅፍ ነው) እና ስቃይ ባለበት የሃደስ ምድብ መካከል ማንም ከአንዱ ስፍራ ወደ ሌላው ማለፍ እንዳይችል በመካከል የሚከፍል፣ ጥልቅ የሆነ ታላቅ ገደል ተደርጎአል የሚል ነው። ይህ “የአብርሃም እቅፍ” የተባለ ስፍራ ገነትም ይሁን ወይም ሲኦል፣ በምንም ስም ቢጠራ ከክርስቶስ ትንሳአኤና ከእርገቱ በፊት በነበረው አሮጌ ኪዳን ውስጥ ለኖሩ ቅዱሳን ግን ሰማይ እንዳልሆነ ግልጽ ነው።

ይህ “የአብርሃም እቅፍ” የተባለው ስፍራ ማለትም ገነት ክርስቶስ ሞትንና ሲኦልን ድል ነስቶ በትንሳኤው ግርማ ወደ ሰማይ ባረገ ጊዜ ሃደስ ከሚባለው ስፍራ ተለይቶ ወደ ሶስተኛው ሰማይ እንደ ተወሰደ ማመን እንችላለን። ይህም የሆነው ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ከተነሳ ከ40 ቀን በኋላ ነው ( ሐዋ 1፥ 3፣ 9)። የሆነውም “ወደ ላይ በወጣ ጊዜ ምርኮን ማረከ ለሰዎችም ስጦታን ሰጠ ይላል። ወደ ምድር ታችኛ ክፍል ደግሞ ወረደ ማለት ካልሆነ፥ ይህ ወጣ ማለትስ ምን ማለት ነው? ይህ የወረደው ሁሉን ይሞላ ዘንድ ከሰማያት ሁሉ በላይ የወጣው ደግሞ ያው ነው።” (ኤፌ 4፥ 8-10) ሲል ጳውሎስ እንደሚጽፈው ክርስቶስ ምርኮኞችን በማረከ ጊዜ ነው።

ሐዋርያው ጳውሎስ ጨምሮም ስለ ገዛ ራሱ መንፈሳዊ ልምምድ ሲናገር፣ እርሱ ራሱ ደግሞ ገነት ወዳለበት ወደ “ሦስተኛው ሰማይ” ተወስዶ ቃላት ሊገልጡት የማይችሉትን ድምጽ እንደሰማ በ57 ዓ.ም ላይ “ሰውን በክርስቶስ አውቃለሁ፥ በሥጋ እንደ ሆነ አላውቅም ወይም ከሥጋ ውጭ እንደ ሆነ አላውቅም፥ እግዚአብሔር ያውቃል፤ እንዲህ ያለው ሰው ከአሥራ አራት ዓመት በፊት እስከ ሦስተኛው ሰማይ ድረስ ተነጠቀ። እንዲህ ያለውንም ሰው አውቃለሁ፥ በሥጋ እንደ ሆነ ወይም ያለ ሥጋ እንደ ሆነ አላውቅም፥ እግዚአብሔር ያውቃል፤ ወደ ገነት ተነጠቀ፥ ሰውም ሊናገር የማይገባውን የማይነገረውን ቃል ሰማ።” (ቆሮ 12፥ 2-4) ሲል ይጽፋል። ጳውሎስ ይህንን በሚጽፍበት ጊዜ ይህ ገነት የተባለው ስፍራ የመገኛው ቦታ በ”ሦስተኛው ሰማይ” እንደሆነ እናስተውላለን።

እነዚያ ሟች የነበሩ ያንቀላፉት የአሮጌው ኪዳን ምርጦች እና ከዳግመኛ ምጽአቱ በፊት የሞቱ ቅዱሳን፣ ከሙታን እስኪነሱ እና ክርስቶስ በ70 ዓ.ም በዳግመኛ ምጽአቱ ከዚያ እስኪፈታቸው ድረስ በዚያ ምርኮኛ ሆነው የቤዛነታቸውን ቀን እየተጠባበቁ ነበር። አሁን ግን “ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፤ ሕያው የሆነም የሚያምንብኝም ሁሉ ለዘላለም አይሞትም፤” (ዮሐንስ 11፥ 25-26) ተብሎ እንደተጻፈ፣ በአሮጌው ኪዳን ስር አስቀድመው ሞተው በዳግመኛ ምጽአቱ ትንሳኤን የተቀበሉ አባቶች፣ “ትንሳኤ” ከሆነው ከክርስቶስ የተነሳ በዚያ በሃደስ እንደሌሉ ሁሉ፤ በክርስቶስ ሆነን በብጽእና የምንሞት ሁላችን “ህይወት” ከሆነው ከክርስቶስ የተነሳ “ሁልጊዜ ከጌታ ጋር እንሆናለን” እንጂ ስንሞት ወደዚያ አንሄድም። ጌታ ኢየሱስ ለማርታ ይህንን ከተናገረ በኋላ የጠየቃት ቀላል ጥያቄ “ይህንን ታምኛለሽን?” የሚል ነበር፣ የሚያስፈልገው የክርስቶስን ቃል ማመን ብቻ ነው።

ይህንን ደግሞ ስሙ፦

“ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ተስፋ እንደሌላቸው እንደ ሌሎች ደግሞ እንዳታዝኑ፥ አንቀላፍተው ስላሉቱ ታውቁ ዘንድ እንወዳለን። ኢየሱስ እንደ ሞተና እንደ ተነሣ ካመንን፥ እንዲሁም በኢየሱስ ያንቀላፉቱን እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ያመጣቸዋልና። በጌታ ቃል የምንላችሁ ይህ ነውና፤ እኛ ሕያዋን ሆነን ጌታ እስኪመጣ ድረስ የምንቀር ያንቀላፉቱን አንቀድምም፤ ጌታ ራሱ በትእዛዝ በመላእክትም አለቃ ድምፅ በእግዚአብሔርም መለከት ከሰማይ ይወርዳልና፥ በክርስቶስም የሞቱ አስቀድመው ይነሣሉ፤ ከዚያም በኋላ እኛ ሕያዋን ሆነን የምንቀረው፥ ጌታን በአየር ለመቀበል ከእነርሱ ጋር በደመና እንነጠቃለን፤ እንዲሁም ሁልጊዜ ከጌታ ጋር እንሆናለን።” (1ተሰሎንቄ 4፥ 13-17)። “ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም!” የተባለለት ጌታ፣ “እነሆ በቶሎ ብዬ እመጣለሁ ባለው ቃሉ መሰረት፣ ቃሉን ጠብቆ “ጌታ ራሱ በትእዛዝ በመላእክትም አለቃ ድምፅ በእግዚአብሔርም መለከት ከሰማይ” ወርዷል፤ ትንሳኤም ንጥቀትም ሆኖአል። እግረ መንገዴን ልንገራችሁ ብዬ ነው፣ ይህ መፈጸሙን አለማመን ብዙ የፎረሸ ትምህርት ውስጥ ያስገባል። አሁን ስለ ገነት የጀመርነውን እንቋጭ...

ገነት የአዲሲቱ ኢየሩሳሌም አካል ለመሆን ወይም ራስዋን ከተማይቱን ለመሆን በክርስቶስ ትንሣኤ እና በእርገቱ ከፍ ከፍ ካለችበት ከ”ሦስተኛው ሰማይ” በላይ፣ “ከሰማያትም ሁሉ በላይ” በዳግመኛ ምጽአቱ ከፍ እንዳለችም ጭምር ማየት እንችላለን። ይህም ሰማይ የእግዚአብሔርና የልጁ ሰማይ፣ ድል ነሺው ንጉሰ ነገስት ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅዱሳኑ ሁሉ ጋር ለዘላለም የሚገዛበት፣ ቅድስቲቱ ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ለባልዋ እንደተሸለመች ሙሽራ ሆና የተመሰረተችበት መንፈስዊው ሰማይ ነው። ይህም የሆነው ክርስቶስ በ70 ዓ.ም ዳግመኛ ሲመጣ በ”ፓሮዥያው” ነው። ዮሐንስ በራእዩ ሲጽፍ “መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ። ድል ለነሣው በእግዚአብሔር ገነት ካለው ከሕይወት ዛፍ እንዲበላ እሰጠዋለሁ” (ራእይ 2፥ 7)፣ ሲል ክርስቶስ ማወጁን ይነግረናል።

በንባብ ክፍላችን እንደምንመለከተው አብርሃም ጨምሮ የሚናገረው፣ እነዚያ በሲኦል የስቃይ ስፍራ ያሉ ነፍሳት ገና በህይወት እያሉ ሙሴና ነብያት ስለ መሲሁ የሚሉትን ሊሰሙ ያልፈለጉ ናቸው፤ ስለዚህም ከሙታን አንድ ቢነሳላቸው እንኳ የሚሰሙም የሚያምኑም አይሆኑም። ይህ ባለጠጋ ሰው ሙሴና ነብያት ስለመሲሁ የተናገሩትን ከማመን ልባቸውንና አንገታቸውን ያደነደኑትን የእስራኤልን ቤት ይወክላል። አልዓዛር ደግሞ በህጉና በነብያት የተነገረውን አምኖ የሚጠባበቅን ጻድቅ እስራኤላዊ ይወክላል። ክርስቶስ ከመስቀሉ ሞት በኋላ ከመቃብር ተነስቷል፣ ብዙዎች ሟች የሆኑ ቅዱሳንንም በኢየሩሳሌም እንዲመሰክሩ  ከሃደስ አስነስቶአል (ማቴዎስ 27፥ 52-53፤ ሉቃስ 23፥ 27-31)። ምንም እንኳ ከትንሳኤው በኋላ ሕያው ሆኖ ክርስቶስ ቢታይም፣ ከሙታን የተነሱትን ቅዱሳን ምስክርነት ለመስማትም ቢታደሉ፣ ከዚህም በላይ የትንሳኤው የአይን ምስክር በሆኑ ሐዋርያት ለ40 ዓመታት ቢሰበኩም፣ የሚበዙት አይሁድ ግን እንደ ሟቹ ባለጠጋና በአባቱ ቤት እንዳሉ የማያምኑ አምስት ወንድሞቹ ለእምነት ሳይታዘዙ ቀርተው በ70 ዓም በሚያጠፋው ጠፉ። ይህንን የአልዓዛርንና የባለጠጋውን ሰው ምሳሌ ኢየሱስ ለአይሁድ የተናገረው ገና በስጋው ወራት እያለ መሆኑንም ልብ አድርጉ።
(gkr)

Friday, February 15, 2019

የጥፋት ርኩሰት

የጥፋት ርኩሰት
“ከእርሱም ጋር ሠራዊቶች ይቆማሉ፥ መቅደሱንም ግንቡንም ያረክሳሉ፥ የዘወትሩንም መሥዋዕት ያስቀራሉ፥ የጥፋትንም ርኵሰት ያቆማሉ።” (ዳንኤል 11፥ 31)

“ነገር ግን በነቢዩ በዳንኤል የተባለውን የጥፋት ርኵሰት በማይገባው ስፍራ ቆሞ ብታዩ፥ አንባቢው ያስተውል፥ በዚያን ጊዜ በይሁዳ ያሉ ወደ ተራሮች ይሽሹ፥” (ማርቆስ 13፥ 14)

ኢየሱስ ይህንን “የጥፋት ርኩሰት” የተሰኘ ርእሰ ጉዳይ በንግግሩ ያነሳው ደቀመዛሙርቱ (ጴጥሮስ፣ ያዕቆብ፣ ዮሐንስና እንድርያስ) በግል ቀርበው እየሩሳሌም እና መቅደስዋ መቼ እንደሚደመሰሱ፤ የዳግመኛ ምጻቱና፣ የአይሁድ ዘመን ማብቂያ ምልክቱም ምን እንደሆነ፣ በጠየቁት ጊዜ ነው። የጥያቄዎቻቸውን ይዘት አለመረዳት ግን የተለያዩ ተርጓሚዎችን በየዘመናቱ የትርጉም ቀዋሚነት ለጎደላቸው መላምቶች ሲያጋልጣቸው ይስተዋላል። ጥያቄዎቹን ከምስስለ ወንጌላት አቀራረብ ለመረዳት እነሆ ጥቅሶቹ፦

(ማርቆስ13፥ 2-4፤ ማቴዎስ 24፥ 1-3፤ ሉቃስ 21፥ 5-7)።

ጌታ ኢየሱስ በመልሱ በዚያን ጊዜ ሊሆኑ ስላሉ ምልክቶች እና ሁነቶች በርካታ ነገር ለጠያቂዎቹ ነግሮአቸዋል። እነዚህም ሁነቶች “ይህ” የተባለው የዚያ አንድ ትውልድ ሁነቶች ናቸው፡፡ ለእነርሱም ከነገራቸው ነገሮች መካከል በትውልዳቸው ውስጥ ሲሆን የሚያዩት አንዱ በነብዩ በዳንኤል የተነገረው “የጥፋት ርኩሰት” ጉዳይ ፍጻሜ ነው። እርሱም በሰጣቸው መመርያ መሰረት በዚያን ጊዜ በይሁዳ የሚኖሩ እነዚህ የተመረጡ ምእመናን ይህንን “የጥፋት ርኩሰት” የተሰኘ ምልክት ሲያዩ የኢየሩሳሌም ጥፋት የቀረበ መሆኑን ስለሚያስረዳቸው ያኔውኑ ፈጥነው በአቅራቢያቸው ወደሚገኙ ተራሮች ወደ አንዱ ሸሽተው ማምለጥ ይኖርባቸዋል። ይህም ማለት በተሰጣቸው መመርያ መሰረት የጥፋትን እርኩሰት ባዩ ጊዜ፣ ከይሁዳ ሁሉ ወደ ተራሮች ሸሽተው ማምለጥ አለባቸው ማለት ነው፤ (ማቴ 24፥ 15-16፤ ሉቃ 21፥ 20-22)።

የጥፋት ርኩሰት እርሱም ጥፋትን የሚያመጣ ርኩሰት፣ ምናልባትም ራሳቸውን ቀነናውያን ወይም ነጻ አውጪዎች ሲሉ የሰየሙና፣ እርስ በርሳቸው እየተዋጉ ሕዝቡን ለአሙጽ ያነሳሱ የነቡሩ የአይሁድ ሽፍቶች በቤተመቅደሱ ያለውን ቅድስተ ቅዱሳን ሙሉ በሙሉ በተቆጣጠሩበትና የእግዚአብሔርን ሕግ በመተላለፍ እጅግ የከፋ የአመጽና የኃጢአት ተግባር በሚፈጽሙበት ጊዜ የነበረውን ሁኔታ ያሳይ ይሆናል። ይህም አመጽ ለሮም መንግስት የሚቀርበውን የሰላም መስዋዕት ጨምሮ የዘወትሩን መስዋእት በማስቀረትም የታጀበ ነበር።

እነዚህ የአይሁድ ቀነናውያን ቅዱሱን መሰውያ አረከሱት፣ በውስጡም ገብተው መላውን ቤተመቅደሱን አቆሸሹት፣ ሌሎች የተከለከሉ ርኩሰቶችንም ሁሉ ፈጸሙ። በቅርቡም እየሩሳሌምንና መቅደስዋን ፈጽሞ በሚደመስስበት ሁኔታ የእግዚአብሔር ቁጣ ይፈስባቸው ዘንድ እጅግ እየከፉ ሄዱ። ድንጋይ በድንጋይ ላይ እስኪፈርስም ድረስ ከመቅደሱ አንድ ድንጋይ እስከማይቀር ድረስ ይወድቁ ዘንድ የተመደቡ ናቸው (ማቴ 24፥ 2)።

ሉቃስ ግን፣ የጥፋት ርኩሰት የሚታይበትን እና ደቀ መዛሙርትም ሸሽተው የሚያመልጡበትን አይነተኛ ጊዜ ለይቶ ሲያመለክት፣ ከተማይቱ በጦር ኃይል መከበብዋን ሲያዩ እንደሆነ ግልጽ አድርጎአል። ይህ ማለት ግን ከላይ እንደተገለጸው የአይሁድ ቀነናውያን የአመጽ ጦር በኢየሩሳሌም ከተማ ውስጥ እና ውጭ ሲሰበሰብ ማለት ብቻ አይደለም፣ ይልቁን ግን በጌሲዩስ ፍሎሩስ የሚመራውና ይሁዳን የሚሰባብረው የሮማውያን ጦር ሰራዊት የከተማይቱን በሮች ዘግቶ ከበባ ሲያደርግ ማለትም ነው (ከ64-66 ad)።

ይህንን በጌታ የተነገረ የሽሽት መመርያ በሰአቱ ለመተግበር በንቃት ሲጠባበቁ የቆዩ በይሁዳ ይኖሩ የነቡሩ ክርስቲያን አማኞች የፍሎሩስ ወታደሮች የላይኛውን የቤተ መቅደሱን የገበያ ስፍራ ማጥቃት ከመጀመራቸው ጥቂት ጊዜ ቀድመው ኢየሩሳሌምን የሚያጠቃ ጦር ከተማይቱን እንደከበባት ሲያዩ የያኔውኑ ሳይዘገዩ ከተማይቱን ሙሉ በሙሉ ለቀው ወጡ። ጊዜውም ያራ በተባለው ወር (በግሪኩ አርጤምስዮስ) (በሚያዝያና በግንቦት ወር)16ኛ ቀን ላይ ነው። በዚያን ጊዜው ጥቃት ብቻ ከ3600 አይሁድ በላይ ተገድለዋል። ያኔ የአይሁድ አማጽያን የመከላከልና የመልሶ ማጥቃት ተጋድሎ በማድረጋቸው ፍሎሩስ አፈግፍጎ ወረራውን በማቋረጥ ቂሳርያ ወደሚገኘው የማዘዣ ጣቢያው ተመልሶ ነበር። ይህ የሆነው እንግዲህ በቨስፓስያንና በልጁ በጀነራል ቲቶ የሚመራው ዋነኛው የሮም መንግስት የጦር ኃይል ከጥቂት ወራት በኋላ በሙሉ ኃይላቸው ወደ ጦርነቱ ከመግባታቸው ቀደም ብሎ ነበር።

ጆሳፈስ  እንደ ጻፈው "ቤተመቅደሱ በተደመሰሰ ጊዜ  የቲቶ ሰራዊት የሮማዊያን ግርማ ምልክት የሆነውን SPQR የተጻፈበትንና የሮምን የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት እና የሕዝብ ኃይልና ብዛት የሚወክል የንስር ምልክት ይዘው  ወደ ቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ ዘልቀው በመግባት በዚያ አስቀመጡት፤ በዚያም በቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ በግንባራቸው ወድቀው ቄሳርን አመለኩ" ሲል ይዘግባል /Wars, መጽሐፍ 6፣ ምዕራፍ 6 አንቀጽ 1/፡፡ ይህ እንግዲህ ቤተ መቅደሱን ያረከሰና በቅድስት ከተማ ላይ ጥፋትን ያደረገው ርኩሰት የመጨረሻ ተግባር ነው፤ የቁጥር 15 የጥፋት ርኩሰት በሉቃስ ወንጌል ውስጥ ግልጽ በሆነ ቃል ቀርቦልናል፡፡ ይህ የጥፋት ርኩሰት  የጀመረው በሉቃስ 21÷ 20 እንደተዘገበው ገና ኢየሩሳሌም በሮማውያን ጦር ተከባ በነበረበት ጊዜ ነው፡፡

ወንጌላዊው ሉቃስ ይህንን የጥፋት ርኩሰት እንዴት እንደሚታወቅ ተርጉሞ እንዲህ ሲል አቅርቦልናል፦

“ኢየሩሳሌም ግን በጭፍራ ተከባ ስታዩ በዚያን ጊዜ ጥፋትዋ እንደ ቀረበ እወቁ። የዚያን ጊዜ በይሁዳ ያሉ ወደ ተራራዎች ይሽሹ፥ በመካከልዋም ያሉ ከእርስዋ ፈቀቅ ይበሉ፥ በገጠር ያሉም ወደ እርስዋ አይግቡ፤ የተጻፈው ሁሉ እንዲፈጸም ይህ የበቀል ጊዜ ነውና።” (ሉቃስ 21፥ 20-22)

ኢየሱስ ሐዋርያቱን ነቅተው እንዲመለከቱ ከነገራቸው ብዙ ነገር መካከል፣ ኢየሩሳሌምን የሚከባት ሠራዊት ዋነኛው ምልክት ነው፡፡ ያ መሆን ሲጀምር ያ እርሱ በትንቢት የተናገረለት ጥፋት እና ፍርድ እንደቀረበና ጊዜው እንደሆነ ያውቃሉ፡፡ ሊመጣም ባለው እልቂት ከቅዱሳኑ መካከል ማንም እንዳይካፈል ፈጥነው በችኮላ ከኢየሩሳሌምና ከይሁዳ አምልጠው በሽሽት መውጣት አለባቸው፡፡ የጥፋት ርኩሰቱ ገና ሲጀምር በይሁዳ ያሉ ፈጥነው ከዚያ  እንዲወጡ የሚያሰጠነቅቅ ቃል በማቴዎስ 24÷ 16 ላይ እናገኛለን፡፡

"በዚያን  ጊዜ በይሁዳ ያሉት ወደ  ተራራዎች ይሽሹ፥" (ማቴ  24÷ 16)

ይሄ በተለይ ለደቀ መዛሙርቱና በይሁዳ ለሚገኙ ለዚያን ዘመን ሰዎች የተሰጠ ማስጠንቀቂያና መመርያ ነበር።

በ68 ዓ.ም  በጦርነቱ መሃል  ኔሮ በቤተ መንግስቱ ውስጥ  ራሱን ካጠፋ በኋላ፣ ኢየሩሳሌምን ለመሰባበር ዘምቶ የነበረው የሮማውያን ጦር ዋና አዛዥ ጀነራል ቨስፓሲያን ወደ ሮም በመመለስ አዲሱ ተተኪ ንጉሰ ነገስት ለመሆን ውጊያ አደረገ፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ በኢየሩሳሌምና በይሁዳ አካባቢ የነበሩ ክርስቲያኖች በማቴዎስ 24÷ 16 ያለውን ማስጠንቀቂያ ስላስተዋሉ በተከፈተላቸው በር ኢየሩሳሌምን ለቀው ወጡ፤ አይሁድ ግን በተቃራኒው ፍሎሩስ አፈግፍጎ ወረራውን በማቋረጡና ወደ ማዘዝ ጣቢያው በመመለሱ፣ ቨስፓሲያንም ጦሩን ይዞወደ ሮም በመመለሱ ይህ ሁኔታ ከእግዚአብሔር ዘንድ    የሆነላቸው የድል    መንሳት    ምልክት    አድርገው ስለ ወሰዱት በኢየሩሳሌም ከቀድሞው ይልቅ በብዙ ቁጥር በመሰባሰብ የተጀመረውን አመጽ በማጋጋል ቀጠሉበት፡፡ በፍጻሜው ግን ሮማውያን ተመልሰው በመምጣት ከተማይቱን ፈጽመው አወደሟት፡፡

የሚቀጥለው ታሪካዊ ትንታቴ ዊኪፒዲያ ድህረ ገፅ ላይ ስናነብ፦ በ70 አመተ ምህረት ከተለያየ የአለም ክፋሎች ተጉዘው የፍሲካን በአል ለማክበር ወደ እየሩሳሌም የመጡ ዳያስፖራ አይሁዶች ከጥቃቱ ማምለጥ ስላልቻሉ በሮማዊያን ወራሪ ጦር እንዳለቁ ይጠቁመናል ፦

"According to Josephus, 1.1 million non-combatants died in Jerusalem, mainly as a result of the violence and famine. Many of the casualties were observant Jews from across the world such as Babylon and Egypt who had travelled to Jerusalem wanting to celebrate the yearly Passover but instead got trapped in the chaotic siege." [ትርጉም፦ ጆሴፈስ እንደዘገበው ከሆነ፣ 1,1 ሚልዮን የሚገመቱ በጦርነቱ መሃል የተጨፈጨፉ ያልታጠቁ ሰላማዊ ሰዎች በኢየሩሳሌም ተገድለዋል። አብዛኞቹ የጦርነቱ ሰለባዎች እንደ ባቢሎን እና ግብጽ ካሉ ሩቅ ሃገር ተጉዘው ታዋቂ የሆነውን አይሁዳውያንን ዓመታዊውን የፋሲካ በዓል ለማክበር ወደ ኢየሩሳሌም የመጡ ዲያስፖራዎች ናቸው። ከከተማይቱ ሊወጡ እንዳይችሉ ሆነው የተታለሉና የተጠመዱ ነበሩ።]

በ60ዎቹ ዓ.ም አጋማሽ ላይ ሮማውያን ይሁዳን እና ኢየሩሳሌምን በጦርነት አጥቅተው በ70 ዓ.ም መላውን አገሪቱንና ቤተ መቅደሱን ጭምር እንዳወደሙ ታሪክ ይነግረናል፡፡ ከ 1,000,000 በላይ የሚሆኑ አይሁድ በጦርነቱ ተገድለዋል፣ የተረፉትንም ሮማውያኑ ማርከው በመውሰድ የሚበዙትን በየክብረ በዓላቱ ለጣኦቶቻቸውና ለነገስታቶቻቸው ክብር መስዋዕት አድርገዋቸዋል፤ የቀሩትንም ባሪያዎችና ግዞተኞች አድርገው ሸጠዋቸዋል፡፡ ቅድስት ከተማቸው፣ ቤታቸውና ምድራቸው፣ የተቀደሰው መቅደሳቸው፣ እንዲሁም እንደ አይሁድ የነበራቸው የአኗኗር ዘይቤአቸው ሁሉ የተፈታ ሆኖ ሊቀር እንደገናም ላይሰራ ሙሉ በሙሉ ፈጽሞ ተደምስሶ ጠፍቶአል፡፡ የኢየሱስ ትንቢትም ሳይፈጸም የቀረ የለም፣ ሁሉ ተፈጽሞአል።

በዘመናት ውስጥ ቤተክርስቲያን በወጉ ልብ ካላለቻቸው ታሪካዊ ሁነቶች መካከል በ70 ዓ•ም በኢየሩሳሌም ከተማና በመቅደስዋ ላይ የደረሰው ይህ ውድመት፣ በህዝቡም ላይ የተከናዉነው ፍርድና እልቂት ዋናው ነው። ይህ ግን በመጽሐፍ ቅዱሳዊ ትንቢቶች አስቀድሞ የተነገረባቸው ብሔራዊ ውድመት ነበር እንጂ ዝም ብሎ አጋጣሚ አይደለም። በእግዚአብሔር ልጅ ላይ ለፈጸሙት ወንጀል እና በሕጻንዋ ቤተክርስቲያኑ ላይ ለፈጸሙት ግፍ የሚመጥናቸውን ቅጣት እንዲቀበሉ በእግዚአብሔር በቀል ስር ወድቀው ነበር። ይህ ታሪካዊ ክስተት መጽሐፍ ቅዱሳዊ የትንቢት ንግሮችን ለመተርጎም በምናደርገው ጥረት ውስጥ ከፍ ያለ ቦታ ያለው እንደሆነም ማስተዋል ያስፈልጋል። ይህ ታሪካዊ ማስረጃ ከእምነታችን ቀጥሎ የቃሉን ታማኝነት፣ ኢየሱስም እግዚአብሔር በወንድሞቹ መካከል ቀብቶ ያስነሳው እውነተኛ መሲህና ነብይ መሆኑን ይመሰክራል። የኢየሱስን ቃሎች እንዳንጠራጠር ተጨማሪ ማስረጃችን እንደቃሉ የተፈጸሙ እነዚህ ታሪካዊ ሁነቶች ናቸው። ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ “በተቀደሰችው ስፍራ ቆሞ” ታዩታላችሁ ሲል የነገራቸው የጥፋት ርኩሰት ያኔ ድሮ ተፈጽሞ አልፎአል። እርሱ ለእኛ ታላቅ መጽናናትን የሚሰጠን፣ የእግዚአብሔርንም የፍርዱን ጽናትና ጭከና እያስተማረን የምንመከርበት ያለፈ ታሪክ ነው።