Sunday, August 14, 2022

ኢየሱስና የአዲስ ኪዳን ጸሐፍያን ተሳስተው ነበር ወይ?

ኢየሱስ እና የአዲስ ኪዳን ጸሐፍያን ተሳስተው ነበር ወይ?

የፕሪቴሪዝም  አመለካከት ሊብራሎችና ተጠራጣሪ ከሃድያን በኢየሱስ እና በአዲስ ኪዳን ታማኝነት ላይ የሚሰነዝሩትን ትችት እና ተቃውሞ በመመከት ዋና የሆነውን የሙግታቸውን ውቅር ፈጽሞ ውድቅ ያደርጋል። ለምሳሌ ታዋቂው ሊበራል የነገረ መለኮት ምሁር የሆነው አልበርት ሽዌይዘር ፣ The Quest For The Historical Jesus በተሰኘው መጽሐፉ ክርስቶስ በባልንጀሮቹና በእርሱ ዘመን በነበሩ አብሮ አደጎቹ የህይወት ዘመን ውስጥ (ማለትም፣ “በዚህ ትውልድ”፣ "በዚያ ከእርሱ ጋር ከቆሙት መካከል አንዳንዶቹ ሳይሞቱ" በፊት) ተመልሶ እንደሚመጣ የተነበየ መሆኑን ለማሳየት በርካታ ቃላቱንና ንግግሮቹን ይጠቅሳል። ሽዌይዘር በደረሰበት ድምዳሜ ኢየሱስ ቃል በገባው መሰረት እመለሳለሁ ባለበት  ጊዜ መመለስ አልቻለም፣ ስለዚህ በትንቢቶቹ ተሳስቶ ነበር ብሎ ጉዳዩን ዘግቶታል። የዚህን ምሁር መስመር ተከትለው ቲኦሎጂ እናስተምራለን የሚሉ ሊብራሎች በመካከላችን እንዳሉ ስንቶቻችሁ ታውቃላችሁ? ቤተ ክርስቲያንስ ቲኦሎጂ እናስተምርልሻለን ከሚሉ እንዲህ ካሉ ሊብራሎቿ በጌታዋና በአዳኝዋ ታማኝነት ላይ የሚሰነዘረውን እንዲህ ያለ ትችትና ነቀፋ ለመመከት ምን ያህል በቃሉ ትምህርት ታጥቃ ተዘጋጅታለች? 

በርትራንድ ራስል የተባለ ከሃዲ ደግሞ፣ Why I am not a Christian በሚለው መጽሐፉ፣ ያንን ክርስቶስ ዳግመኛ ለመመለስ የሰጠውን ተስፋ ባለመፈጸሙ ከታማኝነቱ የወደቀ መሆኑን ለማሳየት፣ የራሱን የክርስቶስን ቃል ተጠቅሞ ጌታችንን ለማጣጣልና ክርስትናን ለመቃወም ሲያውለው ይታያል። ብዙ እንደዚህ ያሉ ተቺዎችና ተቃዋሚዎች (ሊበራሎች፣ ተጠራጣሪዎች፣ አምላክ የለሾች፣ አይሁዶች እና እስላሞች) ወደነዚያው የአዲስ ኪዳን ጽሑፎች ዝርዝር እያመለከቱ ጌታችን ኢየሱስን ሐሰተኛ ነቢይ እንደሆነ እንዲሁም መላው የአዲስ ኪዳን ጸሐፍያን በጽሁፎቻቸው ተሳስተው እንደነበሩ እንጂ ምንም አይነት ትክክለኛነት እንዳልነበራቸው፣ በመንፈስም ተመርተው እንዳልተናገሩ አረጋግጠናል ብለዋል።

በበርካታ ክርስቲያኖች የሃያኛው ክፍለ ዘመን ዕቅበተ እምነት ምሁር ተደርጎ የሚቆጠረው ሲ.ኤስ.ሉዊስም እጅግ ተነባቢ ከሆኑ ሥራዎቹ በአንዱ፦The World's Last Night: And Other Essay,፣ በተሰኘው መጽሐፉ፦ "የፈለጋችሁትን ማለት ትችላላችሁ፣ ጥንታውያን የሆኑቱ የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ግን ያምኑት የነበረው አቡቀለምሲሳዊ እምነት ሃሰት መሆኑ ተረጋግጧል። ምክንያቱም፣ ዳግመኛ ምጽአቱ እንዲፈጸም ይጠባበቁ የነበሩት በገዛ ራሳቸው የምድር ላይ የህይወት ዘመን መሆኑን ከጠቅላላው የአዲስ ኪዳን ገጾች በግልጽ ማየት ይቻለናልና። እጅግ የከፋው ደግሞ ለዚህ መጠባበቅ አሳፋሪ የሆነ ምክንያት የነበራቸው መሆኑ ነው፤ መምህራቸውና ጌታቸው ስለ ዳግመኛ ምጽአቱ የነገራቸው እንደዚያ እንዲጠባበቁ ነበርና። ያንን ቅዠት ያካፈላቸውና የፈጠረባቸውም እርሱው ነበር።  በብዙ ሌላ ቃልም "ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም" ሲል ነገሯቸው ነበር፤ ዳሩ ግን ይህን ሲል ተሳስቶ ነበር። እንደውም እርሱ ከማንም በተሻለ ስለአለም መጨረሻ የሚያውቀው ነገር እንደሌለ ግልጽ ነው፤ ይህም ጥቅስ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ካሉት ሁሉ እጅግ አሳፋሪው ጥቅስ ነው" ሲል ይጽፋል። (ገጽ 97-98.)

መጻኢያን በነገረ ፍጻሜ አስተምህሯቸው ይህንን ትችት ለመመከት የሚያቀርቡት፣ ኢየሱስ እስካሁን እንዳልመጣ ወይም ገና ወደፊት አልያም በቅርቡ እንደሚመጣ አዲስ ኪዳንን ጠቅሰው የሚሰነዝሩት መከላከያ መሰል ውዥንብር ሙከራ ለሊብራሎችና ለከሃዲያን ምሁራን በእጃቸው ዱላ እንደማቀበል ይቆጠራልንና የሚሉትን ካላወቁ ዝም ቢሉ ይመከራል። በታናሽዋ የንባብ ልምምዴ ከፍ ሲል የጠቀስኩትን ይህንን አሳፋሪ የሆነ የሊብራሎችና የከሃዲያን አስተያየትና ትችት በመመከት በጌታችን ፊት ላይ የተተፋውን "ምሁራዊ" ቅርሻት ለመጥረግ አቅም ያለው አስተምህሮ ግን ፕሪቴሪዝም ብቻ ሆኖ አግኝቸዋለሁ።

ከዚህ በታች ያሉት የቅዱሳት መጻሕፍት ምንባባት ዝርዝር እነዚህ ተቺዎችና ነቃፊዎች የክርስቶስንና የአዲስ ኪዳንን ተአማኒነት ለማጥቃት ሲሉ ጠቅሰው የሚጠቀሙባቸው ናቸው። የጠላትህን ትጥቅ አይነቱንና ብዛቱን ሳታውቅ እንዲሁ በሜዳ "ኢየሱስ ይመጣል" የሚል መፈክር እያሰማህ ጦርነቱን አታሸንፍም። ተመልከቱ በነዚህ ምንባባት አብዛኛዎቹ የአዲስ ኪዳን ጸሓፍያን በዝርዝር ተወክለዋል። ቃሉን እናምናለን፣ ለህይወትና እግዚአብሔርን ለመምሰል የሚጠቅመው ምክር ሁሉ አለበት፣ በቤተክርስቲያንም ውስጥ አስተምህሮንና ልምምድን ሁሉ የሚገዛ ብቸኛ ሥልጣን ነው ብለን የምንሰብክና የምናስተምር ሁሉ ይህንን የእነርሱን የትችት ክብደት በቀላሉ ለመረዳት እንዲቻለን እነዚህን ጥቅሶች ስናነብ ከተከፈተ መጽሐፍ ቅዱስ ጋር ሆነን በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ታሪካዊ አውድ ውስጥ እየተመለከትን እንድናጠናቸው አሳስባለሁ፡-

ሀ. የዳግመኛ ምጽአቱ ጊዜ ለመጀመርያው ክፍለ ዘመን ቅርብ እንደነበር የሚያሳዩ የአዲስ ኪዳን ምንባባት

♦ ማቴዎስ 10፥ 23 (ከመመለሱ በፊት ሐዋርያት እስራኤልን ዞረው አይጨርሱም።)

♦ ማቴዎስ 16፥ 27-28 (ከእርሱ ጋር ከነበሩት መካከል አንዳንዶች አስቀድመው ሳይሞቱ በሕይወት ኖረው ሲመጣ ያዩታል)

♦ ማቴዎስ 24፥ 33-34 (ትንቢቱ ፍጻሜውን የሚያገኘው፣ ጌታም የሚመጣው ትውልዱ ከማለቁ በፊት)

♦ ማቴዎስ 26፥ 64 (ያኔ የአይሁድ ገዢዎች የነበሩቱ እርሱ በደመና ሲመጣ እንዲያዩት በሕይወት መቆየት አለባቸው)

♦ ሮሜ 13፥ 11-12 (የሮሜ መልዕክት እየተጻፈ "አሁን" በተባለበት በዚያን ጊዜ ሰአቱ ደርሶና ቀርቦ ነበር)

♦ ሮሜ 16፥ 20 (ያኔ የሮሜ ክርስቲያኖች ገና እያሉ ሰይጣን ከእግራቸው በታች ፈጥኖ እንደሚቀጠቀጥ ይጠበቅ ነበር)

♦ 1ቆሮንቶስ 7፥ 26-31 (ያኔ 1ኛ ቆሮንቶስ እየተጻፈ ሳለ ጊዜው እያጠረ፣ አለሙም እያለፈ ነው ተብሎ ይታሰብ ነበር)

♦ 1ቆሮንቶስ 10፥ 11 ("እኛ" በተባሉት በጳውሎስና በቆሮንቶስ ምዕመናን ላይ የዘመናት መጨረሻ ደርሶ ነበር)

♦ 2ተሰሎንቄ 2፥ 7 (የአመጽ ሚስጥር "አሁን" በተባለው ጊዜ ያኔ በስራ ላይ ነበር)

♦ ዕብራውያን 1፥ 2 ("በዚህ" ሲል የጠቀሰው ያ ጊዜ የመጨረሻው ዘመን ነበር)

♦ ዕብራውያን 9፥ 26 ( እነርሱ የኖሩት ጌታ ኃጢአትን ሊሽር በተገለጠበት የአለም / የዘመን ፍጻሜ ላይ ነበሩ)

♦ ዕብራውያን 10፥ 25 (ለጸሐፊውና ለዕብራውያን ክርስቲያኖች ያኔ ቀኑ እጅግ እየቀረበ ነበር)

♦ ዕብራውያን 10፥ 37 ("ሊመጣ ያለው" እርሱ ሳይዘገይ ሊመጣ የቀረው "ጥቂት ጊዜ" ነበር)

♦ ያዕቆብ 5፥ 7-9 (ያኔ ያዕቆብ እየጻፈ የጌታ መምጫው ቀርቦ ሊፈርድ በደጅ ነበር) ፊልጵስዩስ 4፥ 5ን አስተያይ

♦ 1ጴጥሮስ 1፥ 20 (ያኔ ጴጥሮስ መልዕክቱን እየጻፈ ሳለ ጊዜው የመጨረሻው ዘመን ነበር)

♦ 1ጴጥሮስ 4፥ 7 (ያኔ ጴጥሮስ መልዕክቱን እየጻፈ ሳለ የነገር ሁሉ መጨረሻ ቀርቦ ነበር)

♦ 1ጴጥሮስ 4፥ 17 (ፍርድ የሚጀምርበት ጊዜ ጴጥሮስ መልዕክቱን እየጻፈ ሳለ ያኔ ደርሶ ነበር) ራዕይ 3፥ 10ን አስተያይ

♦ 1ዮሐንስ 2፥ 8፣ 17፣ 18 (ሐዋርያው ዮሐንስ ያኔ "አሁን" እያለ በጠቀሰው ጊዜ  ሰአቱ የመጨረሻ እንደሆነ ያውቅ ነበር)

♦ ይሁዳ 18፣19 (ይሁዳ መልዕክቱን እየጻፈ ሳለ ያኔ የመጨረሻው ዘመን ዘባቾች ነበሩ)

♦ ራዕይ 1፥1-3፤ 22፥ 6፣10 (ራእዩ እይተጻፈ ሳለ በራእዩ የተነገረው ነገር ሁሉ "ቶሎ" እና ፈጥኖ ሊሆን "በቅርብ" ነበር)

♦ ራዕይ 22፥ 7፣ 12፣ 20 (ዮሐንስና ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ክርስቶስ ቶሎ ይመጣል ሲሉ ተንብየዋል፣ ጠብቀዋልም) ራዕይ 2፥ 16 እና 3፥ 11ን አስተያይ

ለ. ስለ ዘመኑ መጨረሻና ስለ ዳግመኛ ምጽአቱ በምሳሌ የቀረቡ ትምህርቶች፦

♦ ማቴዎስ 13፥ 24-43 የእንክርዳዱና የመከሩ ምሳሌ

♦ ማቴዎስ 13፥ 47-50 ወደ ባህር ተጥላ ከሁሉ አይነት የሰበሰበች መረብ ምሳሌ

♦ ማቴዎስ 21 33 ጀምሮ (ማርቆስ 12፥ 1 ጀምሮ፤ ሉቃስ 20፥ 9 ጀምሮ) የወይኑ አትክልት ምሳሌ

♦ማቴዎስ 22፥ 1ጀምሮ (ሉቃስ 14፥ 16 ጀምሮ) የሰርጉ ድግስ ምሳሌ

♦ ሉቃስ 19፥ 11-17 መንግስትን ይዞ ሊመለስ ወደሩቅ አገር የሄደ መኮንን ምሳሌ

♦ ማቴዎስ 25 የአስሩ ቆነጃጅትና የመክሊቱ ምሳሌ

♦ ሉቃስ 13፥ 6-9 የፍሬ ቢሷ በለስ ምሳሌ

ሐ. ሊመጣ ስላለ ጥፋትና ስለ ምጽአቱ የሚያመለክቱ ሌሎች ንግግሮች

♦ ማቴዎስ 3፥ 7-12 (ሉቃስ 3፥ 7-17፤ ሉቃስ 12፥ 49)

♦ ማቴዎስ 10፥ 17-34 (ሉቃስ 10፥ 3-21፤ ሉቃስ 12፥ 11-56)

♦ ማቴዎስ 23፥ 29-24፥ 44 (ሉቃስ 13፤ ሉቃስ 17፥ 20-37፤ ሉቃስ 21)

♦ ሉቃስ 11፥ 42-52፤ 12፥49፤ 13፥ 33-35፤ 19፥ 41-44፤ 23፥ 27-31

በመጨረሻም፣ ቤተክርስቲያንን የራሷን የእምነት መጽሐፍ ተጠቅመው በጥርጣሬና በክህደት በትር ለሚመቷት፣ ጌታዋንና መድሐኒቷን እያዋረዱ ለሚያጠለሹ፣ የምትመራበትንም የህይወት ቃል ተአማኒነት ውድቅ ለማድረግ በምሁራዊ ለዘብተኛነት ማብራርያ ለሚሰጡና የብዙዎችን እምነት ለሚገለብጡ ከሃዲያን፣ ሞልቶ ከፈሰሰው የመጻኢያን ጎራ ምሁራን ምን ምካቴ ይኖር ይሆን? ወዮ! አዝናለሁ፣ ምንም የለም። ይልቁኑ መጻኢነት የሚያቀርበው መከላከያ ራሱን መጻኢነትን ጎርፍ ሆኖ ጠርጎ የሚወስደውን ውሃ ይተፋል። የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ሆይ በዚህ የኪሳራ ነገረ ፍጻሜ ምንም ተስፋና ተገን የለሽም። እንዲህ ያለውን ተረትና ቡትቶ የሆነ ትምህርት እምቢ ማለትን እንዲሰጥሽ እጸልያለሁ። 

Gkr ታናሽ ባሪያው ነኝ። 

ፕሪቴሪዝም ይለመልማል!!


 


 

 


Sunday, August 7, 2022

ታሪካዊው የኢየሩሳሌም ቤ/መ ውድመት

የኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ውድመት

"እርሱ ግን መልሶ፦ ይህን ሁሉ ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ፥ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም አላቸው።….እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም።"(ማቴዎስ 24፥ 2፣ 34)

በእኔ አስተሳሰብ ይህን ከላይ የጠቀስኩት የመፅሐፍ ቅዱስ ቃል ፍቺው እና ታሪካዊ ፍጻሜው በአማኙ መንፈሳዊ ሕይወትና መረዳት ውስጥ ቦታ ሊያገኝ የሚገባውን ያህል ትኩረት የተነፈገው ቃል ነው። ነገር ግን ዓይንን በብዙ ሊከፍቱ ከሚቻላቸው ትንቢቶች መካከል አንዱና ዋናው ደግሞ ነው። ይህንን ጥቅስ በአግባቡ መረዳት ከቻልን ግን ስለ ቅዱሳት መጻሕፍት ጠለቅ ያለ የመረዳትን መንገድ የሚከፍትልን ከመሆኑም በላይ፣ እግዚአብሔርን በማወቅ ከቃሉ ጋር ያለንን ግንኙነት ይወስናል። በታሪክ ውስጥ ፍጻሜው የተረጋገጠውን የዚህን ቤተመቅደስ ውድመት በአዲስ ኪዳን ትንቢቶች ትርጓሜ ውስጥ ያለውን ፋይዳ አለማወቅና ቸል ማለትን የመሰለ ድንቁርና /ignorance/ ያለ አይመስለኝም። 

ኢየሱስ ከላይ የተጠቀሰውን ይህንን ቃል በተናገረበት ጊዜ  ደቀ መዛሙርቱ በአድናቆት ይመለከቱትና ያሳዩት የነበረው ያ በኢየሩሳሌም ከተማ ቆሞ የነበረው ቤተ መቅደስ በዚያን ዘመን በዓለም ላይ ከነበሩ ታላላቅና ድንቃ ድንቅ ቅርሶች አንዱና ዋናው ነበር። ኢየሱስ በደቀ መዛሙርቱ “ትውልድ” ወቅት “ይወድቃሉ” ሲል የተናገራቸው ቤተመቅደሱ የታነጹባቸው ድንጋዮች በእጅጉ አስገራሚና እና በይዘታቸው ግዙፍ ነበሩ። የፍርስራሹ የአይን ምስክር የሆነው ታሪክ ጸሐፊው ጆሴፈስ እንደዘገበው፣ የአንዱ ድንጋይ ወርዱና ስፋቱ አርባ ስድስት ጫማ በአሥራ አምስት ጫማ በሃያ ሁለት ጫማ የሚለካ ሲሆን ክብደታቸውም እያንዳንዳቸው አራት መቶ አሥራ አምስት ቶን የሚመዝኑ ነበሩ። (ጆሴፈስ፣ 'የአይሁድ ጥንታዊ ነገሮች'፣ሲል በጻፈው መጽሐፍ 15፣ ምዕራፍ 11፣ አንቀጽ 3፣ መስመር ቁጥር 392 ላይ ይህንን ዘግቦታል) ይህ በእርግጥ በኢየሱስ የተነገረ ታላቅ የትንቢት ቃል ሲሆን፣ ደቀ መዛሙርቱም ሲሰሙት ለመረዳት አስቸጋሪ የሆነባቸው ከባድ ቃል መሆኑን እናስተውላለን። ስለሆነም፣ “ይህ መቼ ይሆናል…” (ማቴዎስ 24፥ 3) ብለው ኢየሱስን ከመጠየቅ መከልከል አልቻሉም። ይህ ቤተ መቅደስ እንዴት እና መቼ ነው ወደ ፍርስራሽና ባድማነት የተቀየረው?

የናዝሬቱ ኢየሱስ ምድራዊ አገልግሎቱን በፈጸመበት ጊዜ (ማለትም 30ዎቹ ዓ.ም መጀመሪያ አካባቢ)፣ ያኔ ሮም የዓለም ልዕለ ኃያል መንግሥት ነበረች። ይሁዳ፣ በዚህ ጊዜ የምትመራው በሮማውያን ቅኝ ገዢዎች ነበር፤ ከገዢዎቿም የሚበዙት ስለ አይሁድ ሃይማኖት የነበራቸው እውቀት እምብዛም ሲሆን ወይም ከነጭራሹ ምንም አያውቁም ነበር፤ ይህም ሁኔታ  በአይሁዶች ላይ የማያቋርጥ ብስጭት እና ቁጭት አስከትሏል። በኢየሩሳሌም ከተማ ውስጥም ቀነናውያን በመባል የሚታወቀው ቡድን የሮማውያንን አገዛዝ ለማብቃት በዚህ ጊዜ ንቁ ተሳትፎ ያደርግ ነበር። ቀነናውያንም የቤተ መቅደሱን ካህናት ለንጉሠ ነገሥቱ እና ለመንግሥቱ በየጊዜው የሚገባውን ግብር እና ቀረጥ እንዲያቆሙ አግባብተዋቸውና አሳምነዋቸው ነበር፤ ይህም በመሠረቱ በሮም አገዛዝ  ላይ የተደረገ አመጽ ነበር።

ሮም በኢየሩሳሌም የተቀሰቀሰውን አመፅ በሰማች ጊዜ ዓመፁን ለማጥፋት በሴስቲየስ ጋሉስ ትእዛዝ የሚመራውን የሮማን ጦር በ66 ዓም ላከች። ኢየሩሳሌምን ዙሪያዋን ከከበቧት በኋላ የከተማይቱን በሮች መዝጋት ጀመሩ፣ ነገር ግን ከጥቂት ጊዜ ከበባ በኋላ፣ ያለ ምንም አሳማኝ ምክንያት ጀነራል ሴስቲየስ ወታደሮቹን በኃይል ከያዙት ይዞታ አስወጥቶ አፈግፍጎ ሄደ። ያኔም አይሁዶች ሮማውያንን አሳደዱ፣ ብዙዎችንም ገድለው በየጦሩ ግንባርና በከተማይቱ ቅጥር ዙሪያ የተተዉ የጦር መሣሪያዎቻቸውን ማረኩ። ይህ ሮማውያንን ያዋረደ ክስተት አይሁዶች ስለራሳቸው የማይሸነፉ የሆኑ ያህል የተሳሳተ አመለካከት እንዲኖራቸው አድርጎ በአመጻቸው እንዲቀጥሉ የልብ ልብ እንዲሰጣቸው አድርጓል። በተጨማሪም ይህ ክስተት፣ ያኔ በቅርቡ ድንገት በእነርሱ ላይ ከሚመጣው የጌታ ቀን ጥፋት በፊት “… ሰላምና ደኅንነት…” አገኘን፣ የሚሉበትን ድባብ ለመፍጠር ረድቷል (በተጨማሪ 1 ተሰሎንቄ 5፥ 3ን ተመልከት።)

ሮም በአይሁዳውያን መሸነፏን የሚገልጸው ዜና ወደ ንጉሠ ነገሥቱ በደረሰ ጊዜ ሴስቲየስ ባደረገው ደካማ አፈጻጸም ኔሮ ተበሳጨ። በምላሹ የአይሁድን አመጽ ለመደምሰስ እና የሮምን ውርደት ለመበቀል እንዲሁም በአገዛዝ ክብሯ ላይ የደረሰውን የሞራል ጉዳት ለመበቀል እንደገና በ67 ዓ.ም ላይ ኔሮ አንጋፋውን ጄኔራል ቬስፓሲያንን ወደ ኢየሩሳሌም ላከው። ቬስፓሲያንም ወራሪውን ጦር እየመራ ይዞታውን በማስፋት ከኢየሩሳሌም በስተሰሜን ወደምትገኘው ወደ ገሊላ ገሰገሰ። የእስራኤልን ታላላቅ ከተሞቿንም በውጊያ አሸንፎ ምድሪቱን አንበረከከ። በሰሜን በኩል ካለው የገሊላ ዘመቻ በኋላ ወደ ደቡብ ዘምቶ በኢየሩሳሌም ዙሪያ ሰፈረ፣ ነገር ግን በዘመቻው ላይ ሆኖ ለሌላ ማጥቃት እየተዘጋጀ ሳለ ስለ ኔሮ ሞት ወሬ በሰማ ጊዜ ጀነራል ቬስፓሲያን ኢየሩሳሌምን ለመያዝ የነበረውን እቅድ ትቶና ወታደሮቹን አስወጥቶ ወደ አገሩ ወደ ሮም በመመለስ ተተኪው ንጉሠ ነገሥት ሆነ። አሁንም አይሁድ በጦርነቱ ያሸነፉና ድል የቀናቸው መስሎ ታያቸው።

ከዚያም በኋላ ብዙም ሳይቆይ በሚያዝያ ወር 70 ዓ.ም. ከፋሲካ በአል በፊት የቬስፓሲያን ልጅ የሆነው ጀነራል ቲቶ በሰሜናዊ ዳርቻ ካሉት ጭፍሮቹ ጋር ጣምራ ጦር በመሆን የአይሁድን አመጽ ለመጨረሻ ጊዜ ለማስቆም እና አመፁን ለመደምሰስ ገስግሶ ኢየሩሳሌም ደረሰ። ጦሩም በገሊላ በኩል አድርጎ ወደ ደቡብ በመዝመት ከተማዋን በቅርብ ርቀት ለማየትና ለመቆጣጠር በሚያስችሉት ሦስት የጦር ካምፖች ላይ ሰፈረ። መጀመሪያ ላይ አይሁዳውያን እጃቸውን በሰላም እንዲሰጡ ለማሳመንና ከተማይቱን ከመፍረስ ጠብቀው እንዲቆዩ ለማድረግ የማግባባት ጥረት ተደረገ፤ ይህ ግን አይሁድ አስቀድሞ በነበራቸው የተሳሳተ የአሸናፊነት ስሜት የተነሳ አሁንም እንደቀድሞው ድል የሚቀናቸው ስለ መሰላቸው በቀረበላቸው የሰላም ጥሪ ላይ እየተሳለቁ ጥረቱ ሳይሳካ ቀረ።

ቲቶ ግን አይሁዳውያን እርዳታ እንዳይቀርብላቸው አድርጎ የከተማዋን ደጆች ዘግቶ በማስጨነቅ የመጨረሻውን ከበባ ጀመረ። በዚህ ጊዜ ውስጥ ማናቸውም ሰው ቢሆን ከከተማይቱ ሸሽቶ ለመውጣት ሙከራ እንዳያደረግ ተከልክሏል፣ የሞከሩትም በከተማው ውስጥ ባሉ የአይሁድ አንጃዎች ተገድለዋል። አልያም ከከተማ ሲወጡ በሮማውያን ተይዘው ሁሉም ለመቀጣጫ እንዲያያቸው በከተማይቱ  ቅጥር ላይ  ተሰቅለው ተሰቃይተው እንዲምቱ ተደርጓል። ኢየሱስ በሉቃስ 19፥ 43፣ 44 ላይ "ወራት ይመጣብሻልና፥ ጠላቶችሽም ቅጥር ይቀጥሩብሻል ይከቡሻልም በየበኵሉም ያስጨንቁሻል፤ አንቺንም በአንቺም ውስጥ የሚኖሩትን ልጆችሽን ወደ ታች ይጥላሉ፥ በአንቺ ውስጥም ድንጋይ በድንጋይ ላይ አይተዉም፥ የመጐብኘትሽን ዘመን አላወቅሽምና።" ሲል እንደተናገረው የሮም ጦር ለከበባው እንዲመቸው በከተማይቱ ዙርያ የሚቆም ቅጥር ወይም ግንብ አደረጉ።

የቲቶ ወታደሮች በግንቦት 25 የኢየሩሳሌምን ሦስተኛውን (ውጨኛውን) ቅጥር ጥሰው በመግባት አዲሱን የከተማውን ክፍል ያዙ። በሰኔ ወር ከበባው ወደ ሁለተኛው ቅጥር አካባቢ ተስፋፍቶ አይሁድ ከተማዋን ከጠበቀው የመጨረሻው ግድግዳ ጀርባ አፈግፍገው ሸሹ። የአንቶኒያ ምሽግም ሐምሌ 22 ቀን በቲቶ ተወሰደ፤ ከዚያም ሮማውያን የቤተ መቅደሱን በሮች በእሳት አቃጠሉ። ከቲቶ ፍላጎት በተቃራኒው በጥቃቱ ወቅት አንድ ወታደር በመስኮቱ አሳልፎ ወደ አንዱ የቤተ መቅደሱ ክፍል ውስጥ የእሳት ፍንጣቂ ወርውሮ አስገባ፣ በመቀጠልም ሁለተኛው የእሳት ቃጠሎ ወደ ቅዱሱ ስፍራ ተወረወረ፣ ይህም የመቅደሱን ውስጠኛ ክፍል በእሳት እንዲያያዝ አደረገ።

ፍላቪዬስ ጆሴፈስ ስለ አይሁድ ጦርነቶች በሚተርከው መጽሐፉ ይህን ጉዳይ ሲያብራራ፣ ሮማዊው ጀነራል ቲቶ ቤተ መቅደሱ ከጥፋት እንዲተርፍ ውሳኔ አስተላልፎ እንደነበር ይተርካል፡፡ ቲቶ ቤተ መቅደሱ እጅግ የሚያምር ሕንጻ ከመሆኑ የተነሳ እንዳይፈርስ ፍላጎት ነበረው፡፡ ለሮም መንግስት ክብር እንደ ሮማውያን የስኬት መገለጫ አድርጎ ሊጠብቀውም ተመኝቶት ነበር፡፡ ቤተ መቅደሱን በተመለከተ የእርሱ ትዕዛዝ አንዳች ጉዳት እንዳይደርስበትም ነበር፡፡ የሆነ ሆኖ ከፍ ሲል እንደጠቀስኩት ከቲቶ ወታደሮች አንዱ ከቤተ መቅደሱ መስኮቶች በአንዱ ወርውሮ ያስገባው የእሳት ድንጋይ የዚያን ቅዱስ ሥፍራ መሠረት በእሳት አያያዘው፡፡ ቲቶ ነገሩን በሰማ ጊዜ በታላቅ ድንጋጤ ተነስቶ … ወደ ቅዱሱ ቤት ሮጦ በመሄድ የተነሳውን የእሳት ቃጠሎ ለማስቆም ሞክሮ ነበር፡፡ በከፍተኛ ድምጽ፣ እየጮኸ፣ ለወታደሮቹም በቀኝ እጁ ምልክት እየሰጠ እሳቱን እንዲያጠፉ ወታደራዊ የአለቃ ትዕዛዝ ሲያስተላልፍም ነበር፡፡ የሰማው ግን አልነበረም፡፡ እነዚያ የአለቃቸውን ትዕዛዝ ለመፈጸም በአግባቡ የሰለጠኑና ሥነ- ሥርዓት የተማሩ የሮማውያን ወታደሮች ልክ አውሬ የሆኑ ያህል እንደ እብድ ሰው ተለውጠው የቄሳርን ትዕዛዝ እንዳልሰሙ ያህል በመሆን አሁንም አሁንም እየጨመረ ከሚሄድ ታላቅ የበቀል መነሳሳት ጋር እሳቱን እየጨመሩ ያቀጣጥሉት ያዙ፡፡ 

ይሄ ታሪክ ባስብኩት ጊዜ ሁሉ ሲያስገርመኝ ይኖራል! ታላቁ ሮማዊ የጦር ጀኔራል እና በአሥር ሺህዎች የሚቆጠሩ ሠራዊቱ ቤተ መቅደሱን ሊያድኑት ከቶ አልቻሉም፡፡ ለምን ይህ ሆነ ቢባል ምክንያቱም ከቲቶ የሚበልጠው፣ ከቄሳርም የሚበልጠው የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ይህ ከመሆኑ ከዓርባ ዓመታት በፊት ቀደም ብሎ “ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም” (ማቴ 24÷ 3) ሲል ተናግሮአልና ነው፡፡ እግዚአብሔር ተናግሮአል፣ ጀነራል ቲቶም ትዕዛዙን ይከተላል እንጂ ምንም ሊያደርግ ስለማይችል ያ ቤተ መቅደስ ተቃጥሏል፡፡ ይህ እንግዲህ ድል ለመንሳት የተመመው የሮም ሠራዊት ኃይልና ጀግንነት ሳይሆን፣ በሕዝቡ ላይ የሚፈርደው የእግዚአብሔር ኃይል ነበር፡፡ በጆሳቨስ የታሪክ ዘገባ የሚከተለውን እናነባለን፡- “ቲቶ ወደ ከተማይቱ በገባ ጊዜ (መስከረም 26 ቀን 70 ዓ.ም ማለት ነው) የከተማይቱን ጥንካሬ በተለይ ከፍ ብለው የተሰሩትን ቅጠሮቿን እየተመለከተ ይገረም ነበር፡፡ እነዚያ ግንቦች ምን ያህል ረጃጅሞችና ጠንካሮች መሆናቸውን በተመለከተ ጊዜ፣ የእያንዳንዱንም ግንብ ውፍረት እያየ ´´በእርግጥ አይሁድን ከነዚህ ጠንካራ ምሽጎች አውጥቶ ያዋረዳቸው እግዚአብሔር በጦርነቱ ከእኛ ጋር ነበር እንጂ፣ ምን ዓይነት እጅ ወይስ ማሽን ይህንን ግንብ ሊያፈርሰው ይችል ነበር? “ እያለ ይደነቅ ነበር” ይለናል፡፡ በተጨማሪም ወደ 6,000 የሚጠጉ በዚያ ጠለላ ፈልገው  የነበሩ ሰዎች ያኔ በቃጠሎው ነደው አልቀዋል። በመስከረም 26፣ 70 ዓ.ም በከተማው ውስጥ የተቀጣጠለው የአይሁድ ተቃውሞ ሁሉ በኃይል ተቋረጠ። እንደዚህ አይነት ዝርዝር ጉዳዮችን ማንበብ ለሚፈልጉ፣ "የጆሴፈስ ስራዎች፣ የአይሁድ ጦርነት የተሰኘው ጥራዝ፣ መጽሐፍ 6 አስገራሚ ትረካን ያቀርባል።

እንደ ጆሴፈስ ገለጻ ከሆነ በከተማይቱ ላይ በተፈፀመው ጥቃት አንድ ነጥብ አንድ ሚሊዮን አይሁድ ሲገደሉ 97,000 ሰዎች ተማርከው ለባርነት በግዞት ተወስደዋል። ከእነርሱም መካከል አያሌዎቹ በአረማውያን የጣዖት ክብረ በአል ላይ፣ እንዲሁ ለነገስታቱና ለጦር አዛዦች ክብር በአሰቃቂ አገዳደል መስዋዕት ሆነው ታርደዋል። አይሁድ በገዛ አገራቹውና ተበትነው በነበሩበት የአህዛብ ምድር፣ በደረሱበት ሁሉ ተጨፍጭፈዋል። የቀሩትንም ባሪያዎችና ግዞተኞች አድርገው ሸጠዋቸዋል፡፡ ቅድስት ከተማቸው፣ ቤታቸውና ምድራቸው፣ የተቀደሰው መቅደሳቸው፣ እንዲሁም እንደ አይሁድ የነበራቸው የአኗኗር ዘይቤአቸው ሁሉ ሙሉ በሙሉ ፈጽሞ ተደምስሶ ጠፍቶአል፡፡ 

ከጦርነቱ መጠናቀቅ በኋላ በሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት ውስጥ የቤተ መቅደሱ ድንጋዮች ፈራርሰው መሬት ላይ ተከምረው ነበር፤ ልክ ጆሴፈስ በዘገባው እንደገለጸውም "እስከመሠረቱ ድረስ በቈፈሩት መሬት ላይ የድንጋይ ቁልል ተከማችቶ ነበር፤ ስለዚህም በዚያ በኩል የሚያልፉ ሰዎች ከዚያ ቀደም በቦታው ላይ ሰው ይኖር እንደነበር እንኳ ማሰብ እስከማይችሉ ድረስ በስፍራው ምንም ነገር አልነበረም።" ቄሳርም ዛሬ በአይናችን ማየት ከምንችለው በስተቀር ሁሉም ነገር ድምድምና ድልድል እንዲሆን ትእዛዝ ሰጥቶ ነበር። የሮማውያን ጀግኖች ያወደሟት ምን አይነት ከተማ እንደነበረች ለዓለም ሁሉ ለመቀጣጫ ለማሳየት፣ ለወታደሮቹና ለሌሎች የጦር ክፍሎችም ካምፕ ለማዘጋጀት በሚል ከቅጥሩ የተወሰነው ክፍል ብቻ ቆሞ እንዲቀር ተደርጓል።.(የአይሁድ ጦርነት፣ መጽሐፍ 7፣ ምዕራፍ 1ን ተመልከት፤) የህ ታሪካዊ ዘገባ በራእይ 18 ቁጥር 15-18 “እነዚህን የነገዱ በእርስዋም ባለ ጠጋዎች የሆኑት እያለቀሱና እያዘኑ፦ በቀጭን ተልባ እግርና በቀይ ሐምራዊም ልብስ ለተጐናጸፈች በወርቅና በከበረ ድንጋይም በዕንቁም ለተሸለመች ለታላቂቱ ከተማ ወዮላት፥ ወዮላት፥ ይህን የሚያህል ታላቅ ባለ ጠግነት በአንድ ሰዓት ጠፍቶአልና እያሉ ስቃይዋን ከመፍራት የተነሣ በሩቅ ይቆማሉ። የመርከብም መሪ ሁሉ በመርከብም ወደ ማናቸውም ስፍራ የሚሄድ ሁሉ መርከበኞችም ከባሕርም የሚጠቀሙ ሁሉ በሩቅ ቆሙ፥ የመቃጠልዋንም ጢስ ባዩ ጊዜ፦ ታላቂቱን ከተማ የምትመስላት ምን ከተማ ነበረች? እያሉ ጮኹ።” ሲል ከተነገረው ትንቢታዊ የፍርድ ቃል ጋር ይስማማል።

የዚህን ታሪካዊ ክስተት አንድምታ ሙሉ ለሙሉ ለመግለጽ ከዚህ አጭር ጽሁፍ ሃሳብ በእጅጉ የላቀ ጥናትና ምርምር ይጠይቃል። በክርስቲያኑ አእምሮ ውስጥ “ብዙ ለማሰብ አቅም የሚሰጥ ምግብ” መሆን የሚችሉ ጥቂት ነገሮችን ብቻ በግርድፉ መዘርዘር ግን አስፈላጊ መስሎ ይሰማኛል።

  1. ጆሴፈስ ኢየሩሳሌምንና ቤተ መቅደሱ ማንም ሊያድናቸው እስከማይቻለው ድረስ ፈጽመው እንዲወድሙ የወሰነውና እንዲህ ላለ የከፋ ጥፋት አሳልፎ የሰጣቸው እግዚአብሔር ራሱ መሆኑን በታሪካዊ ዘግባው ከትቦታል፡- "....ከተማይቱም ሆነ መላው ቤተ መቅደስ አሁን በአገሩ ሰዎች የሙታን በድን የተሞሉ አይደሉምን? ከተማዋንና ቤተ መቅደሱን በሮማውያን እጅ ያነጻ ዘንድ ይህን እሳት የሚያቀጣጥለው እግዚአብሔር ራሱ ነው፤ በብክለታችሁ የሞላችኊትን ይህችን ከተማ ሊነቅላት ነው።" (የአይሁድ ጦርነቶች፣ መጽሐፍ 6፣ ምዕራፍ 2፣ መስመር 110።)

  2. ከላይ ያለው ታሪካዊ ክስተት በማቴዎስ 24፥ 2 እና 34 በኢየሱስ የተሰጠው የትንቢቱ ፍጻሜ ነው። "አንድ ትውልድ" በመጽሐፍ ቅዱሳዊው  ቀመር ግምቱ አርባ ዓመታት ያህል ጊዜን የሚያጠቃልል እንደሆነ በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ይታወቃል። ያም “ትውልድ” ከ30 ዓ.ም እስከ 70 ዓ.ም ያለውን ጊዜ የሚሸፍን መሆኑ ግልጽ ነው። ይህም በትንቢቱ እና በፍጻሜው መካከል ያለ እንደ የተወሰነ የጊዜ ክፍተት ሆኖ የሚታይ ነው።

  3. የ1ኛ ጴጥሮስ መልዕክት የተጻፈበትን ጊዜ በ 60 ዎቹ መጀመሪያ ላይ ነው ብለን መስማማት ከቻልን፣ እንግዲያውስ ያ የመጀመሪያው የሮማውያን የከበባ ሙከራ ከመድረሱ በፊት ጴጥሮስ "ፍርድ ከእግዚአብሔር ቤት ተነስቶ ሊጀምር" መሆኑን በማስታወቁ ጉዳዩ ከአጋጣሚ በላይ መሆኑን ማየት እንችላለን (1ጴጥሮስ 4፥ 17)።

  4. ሐዋርያው ዮሐንስ በ1ኛ መልዕክቱ ምዕራፍ 2፥ 18 ላይ ሲጽፍ ሁለት ጊዜ እየደጋገመ "መጨረሻው ሰዓት ነው" ይላል። በርካቶች የኖሩበትን ጊዜ "የመጨረሻው ዘመን" ሲሉ የገለጹትን ዮሐንስ ግን መልዕክቱን እየጻፈ የነበረበትን ጊዜ "የመጨረሻው ሰዓት" በማለቱ መጨረሻው ምን ያህል እያጠረ እንደመጣ ያስገነዝባል።

  5. ያኔ ገና በ27 ዓ.ም ላይ መጥምቁ ዮሐንስም እንኳ በሉቃስ 3፥ 7 ላይ በገዛ ዘመኑ የኖሩትን የትውልዱን ሰዎች "ከሚመጣው ቍጣ እንድትሸሹ ማን አመለከታችሁ?" ሲል ይጠይቃቸዋል።

  6. በዳንኤል አሥራ አንድ እና በሕዝቅኤል ሠላሳ ስምንት እና ሠላሳ - ዘጠኝ የተነገረለት ንጉሥ ወይም ከሰሜን ይነሳል የተባለው ወራሪ ኃይል ብዙዎች እንደሚመስላቸው ከሰሜን የሚመጣ የዘመናችን የሩሲያ ኃይል ወይም የኢራቅ ጦር አይደለም። ይልቁን ግን  በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ላይ ከሰሜን ተነስቶ በሶስቱም ግንባር ወደ ደቡብ ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ ለወረራ የተመመው የሮማውያን ሠራዊት ነበር።

እነዚህ የቅዱሳት መጻሕፍት የንባብ ክፍሎች በ70 ዓ.ም በኢየሩሳሌምና በቤተ መቅደሱ ላይ ከተፈጸሙት ነገሮች አንጻር ሲታዩ በጣም ግልጽ ስለሆኑ አጠቃላዩን የአዲስ ኪዳን ትንቢት በወጉ ተርጉሞ ከመረዳት አኳያ ቸል ሊባሉም ሆነ፣ ወደ ጎን ሊገፉ አይገባም፤ ትንቢቱንም ከዚህ ፍጻሜው ነጥሎ ለማብራራት መሞከር አያስፈልግም የሚለው እንደ ፕሪቴሪስት መጽሐፍ ቅዱሳዊ አቋማችን ነው! ሊሰሙን ለሚወዱ ሁሉ የምናስረዳውም የ70ውን ዓ.ም ታሪካዊ ፍጻሜ ጠቅሰን ነው።

(gkr)

 


 

 

 

 

 



Tuesday, August 2, 2022

ፖሮውዥያው ተፈጽሟል

ፓሮውዥያው ተፈጽሟል!

"ቶሎ" ማለት ምንም መቀባባት አያሻውም፣ ያው "ቶሎ" ማለት ነው።

መግቢያ፦

MELLO የተሰኘውን የግሪክ ቃል "ሊሆኑ ያሉ ነገሮች" በሚል መተርጎሙንና ይኸውም "እርግጠኛው አይቀሬ" እንደሆነ፣ በነገረ ፍጻሜ መረዳታችን ውስጥም ያለውን ከፍተኛ ጠቀሜታ የዳሰስኩበትን ሰፋ ያለ ጽሁፍ ከዚህ ቀደም ማስነበቤን አስታውሳለሁ፤ ጽሁፉም በመጠኑ ከተወሰኑ ሰዎች ጋር አነጋግሮን ነበር። ምናልባት ጽሁፉን የማየት አጋጣሚ ያላገኛችሁ በብሎገሬ ላይ ይገኛል፣ እነሆ ሊንኩ፦ 

http://gizachewkr.blogspot.com/2021/09/blog-post_26.html

አሁን ደግሞ እንደቀድሞው ሰፊ ባይሆንም፣ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ሳነሳውና ስጥለው የቆየሁትን 'en tachei' የተሰኘውን የግሪክ ቃል "ቶሎ" በሚል እንደተተረጎመና በነገረ ፍጻሜ ምልከታችን ላይ ያለውን ጠቀሜታ በአጭሩ እንድንመለከት እወዳለሁ

"ቶሎ ይሆን ዘንድ የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ ያሳይ ዘንድ እግዚአብሔር ለኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠው በእርሱም የተገለጠው ይህ ነው፥ ኢየሱስም በመልአኩ ልኮ ለባሪያው ለዮሐንስ አመለከተ፥" ራእይ 1፥ 1

"እርሱም፦ እነዚህ ቃሎች የታመኑና እውነተኛዎች ናቸው፥ የነቢያትም መናፍስት ጌታ አምላክ በቶሎ ሊሆን የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ እንዲያሳይ መልአኩን ሰደደ።" ራእይ 22፥ 6

የእግዚአብሔርን ቃል ስናነብ፣ እግዚአብሔር ለሰው ልጆች የተናገረው ለሰዎች ትርጉም ባለው ቃል እንደነበር ማስታወስ ጠቃሚ ነው። ጊዜ ጠቋሚ ምንባባቱም ቢሆኑ ሆነ ተብሎ እኛን ለማታለል እና ለማደናገር አልተጻፉም። እግዚአብሔር አምላክ ወደፊት ስለሚፈጸሙት ክንውኖች ለአማኞች እንዲነግራቸው መልአኩን ልኮ እንደ ነበር የዮሐንስ ራእይ መጽሐፍ ለዚህ ማሳያ ነው። የራዕይ መጽሐፍ ማለት እንቆቅልሽ ወይም ድብቅ ሚስጥር ወይም ድፍን ቅል አይደለም፣ ይልቁንም  ሰዎች ሊከሰቱ ስላሉ ሁከቶች እና ብጥብጦች ያውቁ እና ይረዱ ዘንድ እንዲቻላቸው የተሰወሩ ነገሮችን የሚገልጥ 'መገለጥ' ነው። መጽሐፉን አክብሩት፣ ታዘዙትና ተጽናኑበት እንጂ ስታነቡት አትሸበሩ፤ እርሱን እንተረጉማለን እያሉ በምዕመናን ላይ ሽብርን ከሚነዙ መጻኢያን መምህራንና ሀሰተኛ ነብያት ራቁ፣ በማህበራቸውም አትደመሩ። የዮሐንስ ራእይ መጽሐፍ ማስፈራርያና ያልተገባ ትርፍ መሰብሰቢያ ከሆነላቸው የቀበሮ ባህታውያን ጋር ምን ትሰራላችሁ?

የመጽሐፉ አውዳዊ ቅኝት የመጀመርያው ክፍለ ዘመን ጥንታዊው የሮም ዓለም ነው። መጽሐፉ በመሰረታዊነት ደግሞ ደብዳቤ ነው፣ ደብዳቤውም የተላከላቸው በኩረ ተደራሲያን ያኔ በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ላይ በትንሿ እስያ (በዛሬዋ ቱርክ) ውስጥ በ62 ዓ.ም አካባቢ ለነበሩ ሰባት እውነተኛ፣ ታሪካዊና በስም ተለይተው ለሚታወቁ አብያተ ክርስቲያናት ነው እንጂ  ከ2000 ዓመታት በኋላ ግልጽ ባልሆነ አሻሚ ጊዜ ውስጥ ለሚኖሩ ለማይታወቁና ሚስጥር ለሆኑ ሰዎች የተነገረ ትንቢት ወይም ንግርት አይደለም። ይሄ መጽሐፉን ልንተረጉም ስንነሳ የሚገዛን አውዳዊ መርህ ነው።

የዮሐንስ ራዕይ መጽሐፍ “በቅርቡ ሊፈጸሙ የሚገባቸውን ነገሮች በመግለጥ በእምነታቸው ለማጽናትና ለማበረታታት ለእነዚያ እውነተኛና ታሪካዊ አማኞች፣ ከኢየሱስ የተላከ መልእክት ነው። በግሪኩ: 'en tachei' ማለት በፍጥነት (quickly) ማለት ነው፤ ቃሉ ጥቅም ላይ በዋለበት የአዲስ ኪዳን ክፍሎች ሁሉ ከጊዜ አንጻር ቶሎ ሊፈጸሙ ያሉ ነገሮችን እና ፈጥነው በጥድፊያ እንዲከናወኑ የተመደቡ አስቸኳይ ጉዳዮችን "ጊዜ የለም" በሚል ስሜት በችኮላ መደረግ ስላለባቸው ነገሮች ያመለክታል [the things which must soon take place and come to pass in quickness ] (ራእይ 1፥ 1፤  22፥ 6) 

በመጽሐፉ የመግቢያ ምዕራፍ እና በመዝጊያው ምዕራፍ ላይ የሚገኙት እነዚህ ሁለቱ ጥቅሶች (ራዕ 1፡1፣ 22፡6)፣ ራእዩ ያካተታቸውና በትንቢቱ መጽሐፍ የተነገሩት ክንውኖች ሁሉ በዚያው አንድ ትውልድ ውስጥ ማለትም በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በቅርቡ እንደሚፈጸሙ የሚናገረውን መልእክት በአንድነት አዋቅረው እንደያዙ እንደ ሁለቱ የመጽሐፉ ቅንፍ መሆናቸውን አስተውሉ።

ኢየሱስም በትንቢቱ የእነዚህ ሁሉ ትንቢታዊ ክንውኖች መቃረቡን ለማጉላት " ዘመኑ ቀርቦአል….." [በግሪኩ: 'ho gar kairos engys' ማለትም ጊዜው ቅርብ ነው ማለት ነው] (ራእይ 1፥ 3) ሲል ተናግሯል።

ከዚህም በተጨማሪ ኢየሱስ "ፓሮውዥያውን" (ዳግመኛ ምጽአቱን እንደማለት ነው) የሚያዩ አንዳንድ የተወሰኑ ሰዎችን "እነሆ፥ ከደመና ጋር ይመጣል፤ ዓይንም ሁሉ የወጉትም ያዩታል፥ የምድርም ወገኖች ሁሉ ስለ እርሱ ዋይ ዋይ ይላሉ። አዎን፥ አሜን።" (ራእይ 1፥ 7) ሲል ግልጽ አድርጓል።

“የወጉት” የሚለው ሐረግ የሚያመለክተው የአሮጌው ኪዳን እስራኤልን ሲሆን፣ ያም የመጨረሻው ዘመን ክፉ ትውልድ ነው፣ እነርሱም መሲሐቸውን የገደሉት ሰዎች ናቸው። በኃይልና በክብር ተመልሶ ሲመጣ ያዩት ዘንድ ያኔ እነርሱ በሕይወት መኖር አለባቸው።

ከዚያም ኢየሱስ፣ በመጽሐፉ የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ፣ እነዚህ ሁሉ በመጽሐፉ ተካተው ያሉ ክንውኖች በቅርቡ እንደሚሆኑ የሚናገረውን ማስጠንቀቂያ ሦስት (3) ጊዜ ደጋግሞ "እነሆ በቶሎ እመጣለሁ" [በግሪኩ: 'tachy' ማለትም: quickly] (ራእይ 22፥ 7፣ 12፣ 20) ሲል ተናግሯል።

ሲጠቃለል፦
በግልጽ ለማየት እንደሚቻለው የዮሐንስ ራእይ መጽሐፍ የሚያወራው “በቅርቡ” ቶሎ/ፈጥኖ፣ ስለሚሆኑ ነገሮች ነው፣ ይኸውም ማለት መጽሐፉ በመጀመሪያ የተጻፈላቸው ደቀ መዛሙርት በሕይወት በነበሩበት ጊዜ ስለ ሚመጣው የፓሮውዥያ ምጽዓት ትንቢት ተናግሯል ማለት ነው፤ እንዲሁም እነዚያ የመጀመሪያው ከፍለዘመን የመሲሁ ገዳዮች እንኳን እርሱ በፍርድ ሲመለስ በሕይወት ሆነው ቁጣውን እንደሚያዩና እንደሚቀበሉ ይጠቁማል። እስካሁን ከመጽሐፍ ቅዱሴ ጋር ባለኝ ትውውቅ ይህንን ያፈጠጠ እውነታ ከሚክዱ በቀር እውነታውን በበቂ ሊያስተባብል የተቻለው ስነመለኮታዊ ምሁርም ሆነ ጥሁፍ አላየሁም።

መጽሐፍ ቅዱስ ስህተት የሌለበት እውነተኛ የእግዚአብሔር ቃል ነው ብላችሁ የምታምኑ ወንድሞችን ልጠይቅ፣ እስቲ መልሱልኝ፤ ኢየሱስ አሁንም እንኳ እንደተናገረው ገና ያልተመለሰ ከሆነ “የወጉትም እንኳ” ከደመና ጋር ሲመጣ ያዩታል ሲል የሚናገረው  ታዲያ  ለምንድን ነው? መከራና ግፍ ለሚቀበሉ ለነዚያ ለድሆቹ የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን አማኞች እና የዮሐንስ ራእይ መጽሐፍ ተጽፎላቸው ለነበሩ በኩረ ተደራስያንስ ቢሆን እንዲህ ያለ የውሸት ተስፋ መስጠት እና 'ቶሎ' ይመጣል የሚሉ ባዶ መግለጫዎችን ማስተጋባትስ ምን የሚሉት ግራ ማጋባት ነው? እውነታውን ሳይክድ ይህንን ጥያቄዬን ሊመልስልኝ የሚቻለው ካለ በልብ ስፋትና በትህትና ላዳምጠው ዝግጁ ነኝ። የእግዚአብሔር ቃል ትምህርት ቤት ሁልጊዜ የተማሪ ቤት እንጂ የበቁ ምሩቃን የሉበትምና።

የሚሆነው ከሁለት አንዱ ነው፣ ይኸውም ወይ እነዚያ ቃላት ለዋናዎቹ በኩረ ተደራስያን ግልጽ የሆኑና የማያሻማ ትርጉም ያላቸው ናቸው (ማለትም "ቶሎ" ማለት ያው "በቶሎ" እንዲሁም " በቅርቡ" ማለት ያው "በቅርቡ"፣ "በፍጥነት" ማለትም ያው "በፍጥነት" ማለት ነው እንጂ ምንም ሰምና ወርቅ የላቸውም)፤ አልያም እነዚህ ቃላት ባዶና ምንም ትክክለኛ ትርጉም የሌላቸው ናቸው ከተባለ፣ እንግዲያውስ የትኞቹም ሰዎች ቢሆኑ ምንም ትርጉም ከማይሰጡ የመጽሐፍ ቅዱሳዊ መልእክቶች ምንም መማር አይችሉም ማለት ነው። መጽሐፍ ቅዱስን እያረማችሁና፣ "አይ 'ቶሎ' ሲል እኛ የሰው ልጆች ጊዜን በምንረዳበት አኳኋን ቶሎ ማለቱ ሳይሆን ሌላ ነገር ማለቱ ነው" እያላችሁ የምትደናበሩና የምታደናብሩ መምህራን ልምከራችሁ፤ በመጀመርያ ቁጭ በሉና ቃሉን እንደተጻፈው ማመንና ማጥናት ጀምሩ፣ ከዚያ በኋላ ታስተምሩናላችሁ። 

ተመልከቱ፣ የእግዚአብሔር ቁጣ ልክ ኢየሱስ የሰው ልጅ ተመልሶ በፍርድ እንደሚመጣ እንደተነበየው ሁሉ በመጨረሻው ክፉ የአሮጌው ኪዳን የእስራኤል ትውልድ ላይ፣ ያኔ በ70 ዓ.ም ላይ እንደወረደባቸው ታሪክ ዘግቦታል።

ፍላቪየስ ጆሴፈስ የተባለው የመጀመሪያው ክፍለ ዘመን አይሁዳዊ የታሪክ ምሁር፣ በኢየሩሳሌም እና በሌሎች የይሁዳ ከተሞች ያሉ ሰዎች ያኔ በ70 ዓ.ም. ሮማውያን ኢየሩሳሌምን በከበቧት ወቅት የመላእክትን ሠራዊት “በደመና ላይ ሆነው ሲመጡ” ያዩበትን አስደናቂ ራእይ እንዲህ ዘግቦታል፦

….ከዚያ ከበዓሉ ጥቂት ቀናት በኋላ፣’… በ21ኛው በአርጤምስየስ [ጂያር] ቀን… “አንድ አስደናቂ እና ሁሉንም ያስገረመ ክስተት ታየ። ይህ ክስተት ታሪኩን ባዩት በነዚያ ሰዎች ህይወትና የእለት ተለት ኑሮ ውስጥ ምንም ተጽዕኖ ባይኖረውና፣ ከዚያም በኋላ ተከትለው የተፈጸሙ ድርጊቶች እንደነዚህ ያሉ ምልክቶች የሚገባቸው አይነት ትላልቅ ተፈጥሮ ያላቸው ክስተቶች ባይሆኑ ኖሮ፣ እኔ ራሴ ታሪኩ ተረት ይመስላል ብዬ ባሰብሁና በተውኩት ነበር፤ የታየውና የሆነው ግን ይሄ ነው፣ ፀሐይ ከመጥለቋ በፊት ሠረገሎችና በላያቸው ላይ ተቀምጠው የሚጋልቡ የታጠቁ የሰራዊት ጭፍሮች በደመና መካከል ወዲህና ወዲያ እየተሯሯጡ ከተማይቱን ሲከብቧት ታዩአቸው። ከዚህም በላይ በዓለሃምሳ ብለን በምንጠራው በዚያ የበዓል ቀን ካህናቱ በሌሊት እንደ ልማዳቸው ወደ ውስጠኛው የቤተ መቅደሱ ክፍል ገብተው የዘወትሩን አገልግሎታቸውን እይፈጸሙ ሳለ፣ በመጀመሪያ ለራሳቸው የሚታወቅ መሸበርና ፍርሃት ይሰማቸው እንደነበሩ ሲገልጡ፣ በታላቅ ድንጋጤም ውስጥ ሆነው እየተንቀጠቀጡ የሰሙት ታላቅ ድምፅ "ኑ ከዚህ በኋላ ለቅቀን ከዚህ እንሂድ” የሚል እንደ ብዙ ሕዝብ ያለ ድምፅ ሰምተዋል። (Wars, 6-5-3, አንቀጽ 297-299)

ሮማዊው የታሪክ ጸሐፊ ቆርኔሌዎስ ታሲተስም ጭምር፣ እነዚህን አስገራሚ ድርጊቶች በኢየሩሳሌም መከሰታቸውን መዝግቧል (Histories, መጽሐፍ 5, ቁጥር. 13)።

መልዕክቴ፦ 

ምንም ዝንፍ ሳይል፣ ልክ ኢየሱስ እንደተነበየው፣ እነዚያ መሲሓቸውን “የወጉት" እንኳ ሳይቀሩ፣ ያኔ በ70 ዓ.ም ላይ በኃይል እና በታላቅ ክብር ሲመጣ የተገለጠውን የእርሱን ፓሮውዥያዊ ትዕይንት በሕይወት ቆይተው ተመልክተዋል። ንስሃ ግቡ፣ ይህንን እውነታ ተቀበሉ። በስነመለኮታዊ መተጣጠፍ ይህንን እውነታ ለማስተባበል መሞከር ግን በእግዚአብሔር ቃል ታማኝነት ላይ የሚፈጸም የክፍለ ዘመኑ ታላቅ ክህደትና ግልሙትና ይሆናል።

ለተጨማሪ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ማብራርያ ፈላጊዎች በብሎገሬ፣ በፌስ ቡክ ገጼ እና በphilologus66 የፌስ ቡክ ገጽ ያጋራሁዋቸውን ጥሁፎቼን ጉብኙ።
gkr

Saturday, May 28, 2022

ጴጥሮስን በጴጥሮስ (የመጻኢነት መከላከያ ሲደረመስ)

                                                                   ጴጥሮስን በጴጥሮስ

(የመጻኢነት መከላከያ ሲደረመስ)

 "እናንተ ግን ወዳጆች ሆይ በጌታ ዘንድ አንድ ቀን እንደ ሺህ አመት ሺህ አመትም እንደ አንድ ቀን እንደ ሆነ ይህን አንድ ነገር አትርሱ" (2ጴጥሮስ 3፥ 8)

ይህች ምንባብ ለበርካታ ጊዜያት የነገረ ፍጻሜ ርዕሰ ጉዳይ ተነስቶ ከአንዳንድ ወገኖች ጋር ስለጌታ ዳግም ምጽአት ውይይት (አንዳንድ ጊዜም ክርክር ይመስላል) ሲጀመር፣ ብዙዎቹ እንደመጨረሻ ጥይት የሚጠቀሙባት ጥቅሳቸው ናት። እነዚህም የመጻኢነት አቋም ያላቸው ወንድሞቼ፣ በአዲስ ኪዳን የሚገኙና የዳግመኛ ምጽዓቱ አመልካች የሆኑ የትንቢት ምንባባት ሁሉ በመጀመሪያይቱ ቤተክርስቲያን ትውልድ ወቅት የሚፈጸሙ እንዳልሆኑ፣ ይልቁንም ገና ያልተፈጸሙ መሆናቸውን  ወይም ገና ወደ ፊት የሚፈጸሙ መሆናቸውን ለማስረዳት፣  ብዙ ርቀት ሄደው የሚያቀርቡት መከላከያና መከራከርያ እንዳላቸው እየመሰላቸው የሚያነሱት ጥቅስ ነው።

ይህ ጥቅስ ለመጻኢነት አቋም ድጋፍ ነው ተብሎ የሚታስብ እንደሆነ በስፋት ይታወቃል። እኔም እግዚአብሔር ምሕረት ያድርግልኝና ይህንን ጥቅስ እስከ ቅርብ አመታት ድረስ መጻኢያን ወገኖቼ በሚጠቀሙበት መንገድ ጴጥሮስን አጉል እየጠቀስኩ ያለቦታው ስሰነቅረው ኖሬአለሁ። እንዲህ የሚተረጉሙት በርካታ ወዳጆችም አሁንም ድረስ አሉኝ።

 ጴጥሮስ በዚህ ጥቅስ ሊነግረን የሚፈልገው "ዳግምኛ ምጽዓቱ በሺህዎች  ለሚቆጠር አመታት ክፍለ ጊዜ ይዘገያል ማለቱ አይደለም" ብዬ ለያዝኩት አቋም መከላከያ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ድጋፍ አለኝ ወይ? አዎን አለኝ ስል እውነትን እናገራለሁ፣ ራሱን ቅዱስ ጴጥሮስን ዋቢ አድርጌም እመሰክራለሁ። ስለመጨረሻው ቀን የጴጥሮስ ምስክርነትና የራሱ የጴጥሮስ እምነት ስለ ዘመኑ ግልጽ አድርጎ የሚናገረው እውነት በኖረውና እድሜ ጠገብ በሆነው ልማዳዊ አመለካከቴ ላይ እርማት የሰጠኝ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መገለጥ ነው።  

ቅዱስ ጴጥሮስ በበዓለ አምሳ ቀን ባቀረበው ስብከቱ፣ "እግዚአብሔር እንዲህ ይላል በመጨረሻው ቀን እንዲህ ይሆናል ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ….ደግሞም በዚያች ወራት በወንዶችና በሴቶች ባሪያዎቼ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ…." (ሐዋ 2፥ 17-18) ሲል ነብዩ ኢዩኤልን ጠቅሶ መንፈስ ቅዱስ የፈሰሰበትን ያንን ጊዜ የመጨረሻው ቀን ነው ሲል መስክሯል። መልዕክቱንም ለመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ምዕመናን አንባቢዎቹ ሲጽፍላቸው"ዳሩ ግን የነገር ሁሉ መጨረሻ ቀርቦአል። እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ" (1ጴጥሮስ 4፥ 7)፣ ሲል መክሯል።

እነዚህ የጴጥሮስ ንግግሮች ግልጽ ያደረጉልኝ አንድ ነገር፣ ሐዋርያው ራሱም ሆነ፣ ወይም የመልዕክቱ አድማጮችና አንባቢዎች ራሳቸውም ቢሆኑ፣ በመጨረሻዎቹ ቀኖች ላይ መሆናቸውንና የነገር ሁሉ መጨረሻም ቀርቦ እንደነበር ያምኑ የነበረ መሆናቸውን ነው። እነርሱ ከሚያምኑት የተለየውን ማመን ምንፍቅና ይሆናል። እነርሱ ያኔ ከሁለት ሺህ አመታት በፊት በመጨረሻው ቅኖች ውስጥ እንደነበሩ በእውነት ያምኑ ነበር፣ እኛም ዛሬ ከሁለት ሺህ አመታት በኋላ አሁንም በመጨረሻወቹ ቀኖች ውስጥ ነን ያለነው ብለን በስህተት ብናምን ሐዋርያቱ ያላመኑትን አምነን እንስታለን።

ቀጣይ የሆኑት የዚህ የ1ኛ ጴጥሮስ መልእክት ምንባብ በርካታ ቁጥሮች በዚሁ ፍሰት ያንኑ ሃሳብ የሚያመለክቱ መሆናቸውንም አስተውያለሁ፦

"ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም፣ ነገር ግን ሁሉ ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለ እናንተ ይታገሳል። የጌታው ቀን ግን እንደ ሌባ ሆኖ ይመጣል፤ በዚያም ቀን ሰማያት በታላቅ ድምጽ ያልፋሉ፣ የሰማይም ፍጥረት በትልቅ ትኲሳት ይቀልጣል፣ ምድርም በእርስዋም ላይ የተደረገው ሁሉ ይቃጠላል። ይህ ሁሉ እንዲህ የሚቀጥል ከሆነ የእግዚአብሔርን ቀን መምጣት እየጠበቃችሁና እያስቸኮላችሁ በቅዱስ ኑሮ እግዚአብሔርንም በመምሰል እንደ ምን ልትሆኑ ይገባችኋል? ስለዚያ ቀን ሰማያት ተቃጥለው ይቀልጣሉ የሰማያትም ፍጥረት በትልቅ ትኩሳት ይፈታል፣ ነገር ግን ጽድቅ የሚኖርበትን አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር እንደ ተስፋ ቃሉ እንጠብቃለን። ስለዚህ ወዳጆች ሆይ ይህን እየጠበቃችሁ ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ ሆናችሁ በሰላም በእርሱ እንድትገኙ ትጉ፣ የጌታችንም ትዕግስት መዳናችሁ እንደሆነ ቁጠሩ። እንዲሁም የተወደደው ወንድማችን ጳውሎስ እንደ ተሰጠው ጥበብ መጠን ጻፈላችሁ፥ በመልእክቱም ሁሉ ደግሞ እንደ ነገረ ስለዚህ ነገር ተናገረ" (2ጴጥሮስ 3፥ 9-15) 

እንግዲህ ጴጥሮስ ዳግመኛ ምጽዓቱ ከሺህዎች አመታት በኋላ ይፈጸማል ብሎ  የሚያምንም የሚያስተምርም እንዳልነበረ ግልጽ ነው። ከዚያ ይልቅ ግን ጥቅሱ እግዚአብሔር ጊዜን አስመልክቶ ሰው ከሚያይበት አተያይ በተለየ እንደሚያየው ሐዋርያው ጴጥሮስ ያስተማረበት ሃሳብ ነው። የሆነው ሆኖ ግን ለእግዚአብሔር እንደ ቅጽበት አይን ጊዜ የነበረ ቢሆንም እንኳ፣ ለጴጥሮስ ትውልድ ሰዎች ግን "ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ አይዘገይም" የተባለለትን የዳግመኛ ምጽዓቱን ተስፋ ፍጻሜ፣ ረጅም ለሚመስል ጊዜ፣ ማለትም በ70 ዓ.ም ላይ እስከሆነው የኢየሩሳሌም ውድመት ድረስ  ወደ አርባ አመታት ለሚጠጋ ጊዜ መጠበቅ ነበረባቸው። በብሉይና በሐዲስ የተገለጠውን ሙሉውን እና ፍጹሙን የእግዚአብሔርን ምክር ይዘን እንጂ፣ አንዲት ጥቅስ አንጠልጥሎ ወይም በአንዲት ጥቅስ ተንጠልጥሎ ዶክትሪን አይሰራም።  (GKR)


Sunday, May 22, 2022

የበኩረ ተደራሲያኑ ዋጋ እና አግባብነት

  በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የበኩረ ተደራሲያኑ ዋጋ እና አግባብነት


ጌታችንን በማይጠፋ ፍቅር የሚወዱ አብዛኞቹ ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ክርስትና ሕይወት የሚናገረውን በማንበብ፣ በማጥናትና በማዳመጥ ስፍር ቁጥር የሌላቸውን የጥሞና ሰዓታት ያሳልፋሉ። በዚህ ጽሑፍ ውስጥ ያለኝ ዓላማ፣ የሚማርና የተከፈተ ልብ ያላቸውና የመጽሓፍ ቅዱስ ተማሪ የሆኑ ክርስቲያን አማኞች እንዲህ ባለ ብርቱ  ተግባር ላይ በሚሰማሩበት ጊዜ በተለይ “የበኩረ ተደራሲያኑ ዋጋ እና አግባብነት” የሚለውን ርዕሰ ጉዳይ ለመረዳት እንዲቻላቸው ትኩረት ሰጥተው እንዲያስቡበት መርዳት ነው።


“የበኩረ ተደራሲያኑ ዋጋ እና አግባብነት” ምን ማለት እንደሆነና ፍሬ ነገሩን ለማስረዳት እንዲመቸኝ ከማቴዎስ ወንጌል መጽሐፍ ሃያ አራተኛውን መዕራፍ በወፍ በረር ምልከታ ለመጠቀም መርጫለሁ። በዚህ አንድ ምዕራፍ ላይ በዝርዝር ጽፌ ያስተማርሁበትን ማንበብ ለምትሹ በብሎገሬ ግብታችሁ እንድትካፈሉ በዚህ ጽሁፍ መጨረሻ ላይ ሊንኩን አስቀምጫለሁ።

 

‘ኢየሱስም ከመቅደስ ወጥቶ ሄደ፥ ደቀ መዛሙርቱም የመቅደሱን ግንቦች ሊያሳዩት ቀረቡ። እርሱ ግን መልሶ ….አላቸው”፦ በዚህ ምዕራፍ ውስጥ ስለ “በኩረ ተደራሲያኑ ዋጋ እና አግባብነት” የመጀመሪያ ማሳያ ሊሆን የሚችል ግልጽ ነገር ስላለን እዚህ ቆም ማለት አለብን። ልንጠይቀው የሚገባን መሰረታዊ ጥያቄ ኢየሱስ እየተናገረ ያለው “አላቸው” የተባሉት “እነሱ” እነማን ናቸው? “እነርሱ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው “ደቀ መዛሙርቱን” መሆኑን ከዚህ ምንባብ ክፍል በጣም ግልፅ ነው ብዬ አምናለሁ። በዚህም ኢየሱስ በቀጥታ ይናገር የነበረው የነግግሩ “ተደራሲያን” የነበሩትን - ደቀ መዛሙርቱን ነው።


ካቆምንበት ተነስተን ጥናታችንን ስንቀጥል፣ “ይህን ሁሉ [የቤተመቅደሱን ሕንፃ እያመለከተ] ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ፥ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም አላቸው።” እዚህ ላይ “ታያላችሁን?” በሚል መጠይቅ የተጠቆሙትን  "እናንተ" የተባሉትን እነማን እንደሆኑ መለየት አለብን. “እናንተ” የሚለው ቃል የሚያመለክተው በቁጥር 1 ላይ ግንቦቹን ለማሳየት ወደ ኢየሱስ የቀረቡትን“ደቀ መዛሙርቱን” መሆኑ ግልጽ ነው። በዚህ ምንባቡ ውስጥ ከኢየሱስ ጋር እየተነጋገረ ያለ ሌላ ሰው ወይም ሌላቡድን የለም፣ ስለዚህ እዚህ ላይ ቀደም ሲል እንደነበረው “እናንተ” በማለት የተጠቀሱት “ደቀ መዛሙርቱ” በቻ ናቸው ማለት ነው ብለን መደምደም አለብን። 


በመቀጠልም፦ “እውነት እላችኋለሁ [እኔ ኢየሱስ]፥ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም አላቸው [ደቀ መዛሙርቱን]።” አሁን ተመልከቱ፣ ያ አይነት ንግግር በእውነት ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ የተናገረው አስገራሚና አስደንጋጭ ንግግር ነበር። ኢየሱስ በኢየሩሳሌም የሚገኘውን ታላቁን ቤተ መቅደስ ያነጹት እነዚያ የሚያማምሩ ዕፁብ ድንቅ ድንጋዮችን አስመልክቶ በዚያ የቆሙት አድማጮቹ ሁሉ ቃሎቹን ሲናገር እያዳመጡና እየተመለከቱት አንዱ በሌላው ላይ ተነባብሮ መፍረሱ እንደማይቀር ነገራቸው። ይህ በእርግጠኝነት የወደፊቱን ክስተት የሚያመለክተውንና “ትንቢት” ተብሎ የሚጠራውን መስፈርት ያሟላል እላለሁ!ይህን ትንቢት የተሰኘ ጉዳይ በአምሮአችሁ ይዛችሁ ተከተሉኝ ምክንያቱም በኋላ ላይ ኢየሱስ ይህ ትንቢት የሚፈጸምበትን ጊዜ ለደቀ መዛሙርቱ በግልጽ እንደነገራቸው እንመለከታለን! 


እርሱም [ኢየሱስ] በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ፥ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ [ኢየሱስ] ቀርበው፦ ንገረን፥ [ደቀ መዛሙርቱ] ይህ [የቤተ መቅደሱ ድንጋዮች መፈራረስ] መቼ ይሆናል? የመምጣትህና [እዚህ ላይ “መምጣት” የሚለው ቃል በመጀመሪያው የግሪክ የመጽሐፍ ቅዱስ ቋንቋ “ፓሮዥያ” (“parousia”) ማለት ሲሆን ትርጉሙም “መምጣት” ወይም “መገኘት” ማለት ነው።] የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው? አሉት።  ደቀ መዛሙርቱ ኢየሱስን የጠየቁትሁለት ጥያቄዎችን ነበር፦ (1) ቤተ መቅደሱ መቼ ይፈርሳል? የሚል እና (2) “በዘመኑ” [እዚህ ላይ ልብ አደርጉ፣ የአማርኛ መጽሓፍ ቅዱስ ትርጉሞች እና አንዳንድ ታዋቂ የእንግሊዝኛ ትርጉም መጽሓፍ ቅዱስ ቅጂዎች እንዳሰፈሩት ያለ ”አለም” የሚል ቃል ተገቢ አይደለም] መጨረሻ ላይ የሚፈጸመው የኢየሱስ ፓሮዥያ ምልክቱ ምን ሊሆን ይችላል? የሚሉ ናቸው። እዚህ ላይ ኢየሱስ (1) በኢየሩሳሌም ያለው ቤተ መቅደስ መቼ ይፈርሳል? ለሚለው እና (2) “የዘመኑ ፍጻሜ” ተብሎ በሚጠራው ጊዜ ላይ የሚገለጠው የኢየሱስ ፓሮዥያ ምልክቱ ምን ሊሆን ይችላል? በሚል ደቀ መዛሙርቱ ላቀረቡለት ሁለት ጥያቄዎች ሙሉ ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ልብ ማለት አለብን። በተጨማሪም ደቀ መዛሙርቱ ለኢየሱስ ባነሱለት ጥያቄ ላይ እየተናገሩ ያሉት ስለ የትኛው “ዘመን” እንደሆነ መመርመር ያስፈልገናል። 


ኢየሱስም መልሶ [ለደቀ መዛሙርቱ] እንዲህ አላቸው፦ ማንም [እናንተን] እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ። ብዙዎች፦ እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና፤ ብዙዎችንም ያስታሉ። ጦርንም የጦርንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ [እናንተ] አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠበቁ [እናንተ]፥ አትደንግጡ [ማለትም፣ በእነዚህ ኢየሱስ በሚናገራቸው ነገሮች]፤ ዳሩ ግን መጨረሻው [ማለትም፣ ደቀ መዛሙርቱ ቀደም ሲል በጥያቄአቸው ጠቆም ያደረጉት“የዘመኑ ፍጻሜ”ወይም መጨረሻው ማለት ነው] ገና ነው” በእነዚህ የቅዱሳት መጻሕፍት ቃላት ውስጥ እያደገ የመጣውን ሃሳብ እየከለስን እና እያስታወስን ጥናታችንን እነቀጥል። ኢየሱስ እስካሁን ድረስ ለደቀ መዛሙርቱ ጥያቄዎች መልስ ሲሰጣቸው:- (1) ማንም እንዳያስታቸው መጠንቀቅ እንደ አለባቸው፣ (2) ሌሎች ደግሞ እርሱ ክርስቶስ መሲሑ እኔ ነኝ እያሉ በጊዜው ውስጥ የሚገለጡ እንደሆነ እና   እነርሱ ግን አታላዮች መሆናቸውንና ብዙዎችም እነዚህን አታላዮች እነደሚያምኑዋቸው፣ በተጨማሪም (3) ደቀ መዛሙርቱ ጦርነትንና የጦርነትን ወሬ እንደሚሰሙ፣ ሆኖም ግን ደቀ መዛሙርቱ የዘመኑ መጨረሻ ከመምጣቱ በፊት ሊፈጸሙ በሚገባቸው በነዚህ ጉዳዮች ሊደናገጡ እንደማይገባ ይነግራቸዋል።


ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣልና፥ ራብም ቸነፈርም የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ ይሆናል፤ እነዚህም ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው።”.በዚህ የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 24 የንባብ ክፍል ውስጥ፣ ኢየሱስ ቤተ መቅደሱ ከመፍረሱ በፊት ደቀ መዛሙርቱ የሚያዩአቸውን አንዳንድ “ምልክቶች” (1) ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ የሚነሣ እንደሆነ፤ እንዲሁም (2) ራብ፣ ቸነፈርና የምድርም መናወጥ በልዩ ልዩ ስፍራ እነሚሆን ጨምሮ ተናግሯል። እነዚህ ምልክቶች የሚከናወኑት ቤተ መቅደሱ ከመፍረሱ አስቀድሞ እና የእርሱ ፓሮዢያ ከመከሰቱ በፊት ነው ለማለት እችላለሁ፣ ምክንያቱም እነዚህን ክስተቶች ከ"ምጥ ጣር" ሁነታ ጋር በማመሳሰላቸው ነው፣ ይህም አንዲት ሴት አዲስ ልጅ ከመገላገሏ በፊት የሚያጋጠማትን ህመም በግልፅ የሚያመለክት በመሆኑ ነው። ሁለት ሺህ አመት የሚፈጅ ምጥ የለም።


በዚያን ጊዜ ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋል [እናንተን] (እዚህ ላይ “እነሱ”  የተባሉት ገዳዮች ማንን እነደሚያመለክት አልተገለጸም፣ ነገር ግን በመላው አዲስ ኪዳን ይህንን አሳልፎ የመስጠትና የመግደል ተግባር በደቀ መዛሙርት ላይ ሲፈጽሙ የነበሩትን የአይሁድ የሃይማኖት መሪዎችን እንደሚያመለክት አምናለሁ።)፥ ይገድሉአችሁማል [እናንተን] (ኢየሱስ እየተነገራቸው ለነበሩት ደቀ መዛሙርት ሞት ተጠያቂ የሚሆኑት እነማን እንደሆኑ ከዚህ ቋንቋ መረዳት እንችላለን) ስለ ስሜም በአሕዛብ ሁሉ የተጠላችሁ [እናንተ]  ትሆናላችሁበዚያን ጊዜም (ይህ ሁሉ በደቀ መዛሙርቱ ላይ በሚደርስበት ጊዜ) ብዙዎች ይሰናከላሉ (ይህም ኢየሱስ በአገልግሎቱ ወቅት ሲያስተምር ከነበረው ነገር ሊሆን ይችላል።) እርስ በርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ እርስ በርሳቸውም ይጣላሉ፤ ብዙ ሐሰተኞች ነቢያትም ይነሣሉ ብዙዎችንም ያስታሉ፤ ከዓመፃም ብዛት የተነሣ የብዙ ሰዎች ፍቅር ትቀዘቅዛለች። እስከ መጨረሻ የሚጸና (ይህም ኢየሱስ በአገልግሎቱ ወቅት የተናገረውን በማመን የሚቀጥሉ ናቸው።) ግን እርሱ ይድናል። ለአሕዛብም ሁሉ ምስክር እንዲሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል (ኢየሱስ በአገልግሎቱ ወቅት የሰበከው እና ለደቀመዛሙርቱ ያስተላለፈው መልእክት ነው) በዓለም ሁሉ ይሰበካል፥ በዚያን ጊዜም መጨረሻው ይመጣል።  በዚህ የንባብ ክፍል የምንመለከተውይህ የመጨረሻ ንግግሩ በእጅጉ ጊዜን አመልካች የሆነ ንግግር ነው።. ኢየሱስ አሁን ለደቀ መዛሙርቱ እየነገራቸው ያለው የንግግሩ ርዕሰ ጉዳይ የሆነው መጨረሻው የተባለው ይህ የዘመኑ ፍጻሜ ከቤተ መቅደሱ መፈራረስና ከክርስቶስ የፓሮዥያ ምጽአት ጋር የተቆራኘ በመሆኑ የመንግሥቱ ወንጌል ለህዝቦች ሁሉ “በዓለም ሁሉ” እስኪሰበክና እስኪዳረስ ድረስ ሳይፈጸም የሚጠብቅ እንደሆነ ተናግሯል።


“እንግዲህ በነቢዩ በዳንኤል ዳናኤል. 927፤ 1211 ላይ፣ የተባለውን የጥፋትን ርኩሰት በተቀደሰችው ስፍራ ቆሞ ስታዩ [እናንተ]፥ አንባቢው ያስተውል፥ በዚያን ጊዜ በይሁዳ ያሉት (በዚህ አይነተኛ በሆነ ጉልህ ክስተት ወቅት) ወደ ተራራዎች ይሽሹ፥ በሰገነትም ያለ በቤቱ ያለውን ሊወስድ አይውረድ፥ በእርሻም ያለ ልብሱን ይወስድ ዘንድ ወደ ኋላው አይመለስ። በዚያችም ወራት (ማለትም የጥፋት ርኩሰት በሚፈጸምበት ወቅት) ለርጉዞችና ለሚያጠቡ ወዮላቸው።” በእነዚህ ንግግሮች፣ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ ጥብቅ የሆነ ማስጠንቀቂያና ማሳሰቢያን እየሰጣቸው መሆኑን እንመለከታለን፣ ይህም መልእክት በዚያን ጊዜ ለነበሩ አማኞችና ኢየሱስ ከሞተ እና ከተነሳ በኋላም ወደቤተክርስቲያን ለተጨመሩ ሌሎች አማኞች ሁሉ እንደተሰራጨ በቀላሉ መገመትም እንችላለን። “ነገር ግን ሽሽታችሁ (የእናንተ፣ እነዚህን ምልክቶች አይታችሁ ከተማይቱን ለቃችሁ የምትሄዱ) በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ፤ በዚያን ጊዜ (የጥፋት ርኩሰት በሚታይበት ጊዜ) ከዓለም መጀመሪያ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ያልሆነ እንግዲህም ከቶ የማይሆን ታላቅ መከራ ይሆናልና። እነዚያ ቀኖችስ ባያጥሩ ሥጋ የለበሰ ሁሉ ባልዳነም ነበር፤ ነገር ግን እነዚያ ቀኖች ስለ ተመረጡት ሰዎች ያጥራሉ። በዚያን ጊዜ ማንም፦ እነሆ፥ ክርስቶስ ከዚህ አለ ወይም፦ ከዚያ አለ ቢላችሁ [እናንተን] አትመኑ፤ ሐሰተኞች ክርስቶሶችና ሐሰተኞች ነቢያት ይነሣሉና፥ ቢቻላቸውስ የተመረጡትን እንኳ እስኪያስቱ ድረስ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ያሳያሉ። እነሆ፥ አስቀድሜ ነገርኋችሁ [ለእናንተ]። እንግዲህ፦ እነሆ፥ በበረሀ ነው ቢሉአችሁ [እናንተን] ፥ አትውጡ፤ እነሆ፥ በእልፍኝ ነው ቢሉአችሁ (ሐሰተኞቹ ክርስቶሶችና ሐሰተኞቹ ነቢያት)፥ አትመኑ፤ መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ፥ የሰው ልጅ (ለመሲሁ ከርስቶስ የተሰጠ መጠሪያ) መምጣት (እዚህ ላይ እንደገና ጥቅም ላይ የዋለው የግሪክ ቃል እንደ ቀድሞው “ፓሮውዥያ” የተሰኘው ነው፣ ትርጉሙም “መገኘት” ማለት ነው።) እንዲሁ ይሆናልና፤ በድን ወዳለበት በዚያ አሞራዎች ይሰበሰባሉ። ከዚያች ወራትም መከራ በኋላ ወዲያው ፀሐይ ይጨልማል፥ ጨረቃም ብርሃንዋን አትሰጥም፥ ከዋክብትም ከሰማይ ይወድቃሉ፥ የሰማያትም ኃይላት ይናወጣሉ። በዚያን ጊዜም የሰው ልጅ (መሲሁ ክርስቶስ) ምልክት በሰማይ ይታያል፥ በዚያን ጊዜም የምድር ወገኖች ሁሉ ዋይ ዋይ ይላሉ፥ የሰው ልጅንም (ክርስቶስን) በኃይልና በብዙ ክብር በሰማይ ደመና ሲመጣ ያዩታል (የክርስቶስ ፓሮውዥያ የሚከሰተው በዚህ ከተጠቀሰው የመከራ ወራት በኋላ መሆኑን ልብ አድርጉ)፤ መላእክቱንም ከታላቅ መለከት ድምፅ ጋር ይልካቸዋል፥ ከሰማያትም ዳርቻ እስከ ዳርቻው ከአራቱ ነፋሳት ለእርሱ የተመረጡትን ይሰበስባሉ። ምሳሌውንም ከበለስ ተማሩ፤ ጫፍዋ ሲለሰልስ ቅጠልዋም ሲያቈጠቍጥ፥ ያን ጊዜ በጋ እንደ ቀረበ ታውቃላችሁ፤ እንዲሁ እናንተ ደግሞ ይህን ሁሉ ስታዩ በደጅ እንደ ቀረበ እወቁ። እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም። ሰማይና ምድር ያልፋሉ፥ ቃሌ ግን አያልፍም።” ወይኔ! ይህ የመጨረሻው ዓረፍተ ነገር ቦምብ የሆነ ንግግር አይደለም ትላላችሁ! እስቲ ጠጋ ብለን በዝርዝር እንመልከተው።

"እንዲሁ እናንተ ደግሞ ይህን ሁሉ ስታዩ በደጅ እንደ ቀረበ እወቁ። እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም።" (ማቴዎስ 24፥ 33-34)።

በርካታ ክርስቲያኖች ዛሬ ላይ ቆመው ይህንን የጌታን ንግግር ለመተርጎም ሲሞክሩ ከጠቅላላ ቃሉ ከተነገረበት አውድ ነጥለው፣ ልክ ጌታ ዛሬ ከበርካታ መቶ አመታት በኋላ የመምጣቱ ምልክት ምን እንደሆነና በእኛው ትውልድ ውስጥ ሊሆን ያለውን ለእኛው የነገረን እንደሆነ አድርገው ያስባሉ። ይህ ግን ቃሉን አሳስቶ ከማንበብ የተወለደና ዘመን ያስቆጠረ ድልብ ስህተት ነው፤ እርማት ይፈልጋል። ስለሆነም ወቅታዊውን የአለምን ፓለቲካዊ፣ ወታደራዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳይ፣ በተለይም እንደ እስራኤልና አረቦች ያሉ የመካከለኛው ምስራቅ አገሮችን ውጥረት፣ እንደ አሜሪካና አውሮፓውያን ሸሪኮቿ ያሉ የኃያላን መንግስታትን የውጭ ፓሊሲ፣ እንደ ሩስያና ቻይና ያሉ ከምዕራባውያን በተቃራኒው የቆሙ ኃይሎችንና፣ ትንንሽዬ የኒውክለር ጡንቻ እያበቀሉ ያሉ እንደ ኢራንና ሰሜን ኮርያ ያሉ መንግስታትን ሁኔታ የሚዘግብ ትኩስ የአለም ዜና እያነፈነፉ፣ የመጽሐፍ ቅዱስን ትንቢት በአለም ወሬ እየመተሩ ለመተርጎም የሚደረግ "የስነመለኮት አዋቂ ነን" ባዮች ሙከራ ሁሉ፣ የመጽሐፍ ቅዱስን ትንቢት አውደ ምንባብና የአውደ ተደራስያኑን ዋጋ ያላገናዘበ ብቻ ሳይሆን ከንቱና የማይረባ ሆኖ በክርስቲያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል ለበርካታ የስህተት ትምህርትና የስህተት እምነት መፈልፈያ ሰበብ ነው።

የመጽሐፍ ቅዱስ አውደምንባብ እና የበኩረ ተደራስያኑ ተዛማጅነት ዋጋ ባለው ሁኔታ በቁሙ የሚወሰድ ከሆነ ግን፣ ያኔ በትንቢት ቃል  ምንባብ ላይ ግልጽ እና ቀጥተኛ የሆነ ትርጉም ሊኖረን ይጀምራል። ከተሳሳተ መረዳትና እምነትም እንጠበቃለን። ፍጻሜውንም በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ውስጥ በማስተዋል የመጽናናትን ብዛት፣ የእምነትን ጽናትና የክርስቶስ ታማኝ ምስክርነት የሚሰጠውን ድልና ድፍረት ያለማምደናል። ስለዚህ በዋቢነት ያነሳነው የክርስቶስ ፍካሬ የሆነው ማቴዎስ 24 ምጽአቱ ከመሆኑና ፍጻሜ ከመሆኑ አስቀድሞ በደቀመዛሙርቱ ዘመንና ትውልድ ውስጥ የሚከናወነውን ቀዳሚ ክስተት በዝርዝር ይናገራል

  1. ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ “ይህ ሁሉ” ሲል ያነሳቸው“እነዚህ ሁሉ ነገሮች” እስካልሆኑ ድረስ ትውልዳቸው እንደማያልፍ [ሞተው እንደማያልቁ] ነግሯቸዋል።

  2. ይህ ሁሉ” ወይም “እነዚህ ነገሮች” በሚል ይደርሳሉ የተባሉት ጉዳዮች ምን ምን ናቸው? አውዱ የግድ እንደሚለው የሚከተሉትን ነገሮች ማካተት አለበት፡-

(ሀ) የኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ይፈርሳል።

(ለ) የ“ዘመኑ” መጨረሻ ይሆናል።

(ሐ) ደቀ መዛሙርቱ በዘመናቸው ሐሰተኛ ክርስቶሶችና ሐሰተኛ ነቢያት መነሳታቸውን ወይም መገለጣቸውን ይመሰክራሉ።

(መ) በዚያን ጊዜ ጦርነቶች እና የጦርነት ወሬዎች ይኖራሉ

(ሠ) ረሃብና የመሬት መንቀጥቀጥ ይከሰታል።

(ረ).የመከራ ጊዜ ይኖራል።

(ሰ) ቢያንስ ከደቀ መዛሙርቱ መካከል አንዳንዶቹ 'ይገደላሉ'።

(ሸ) የመንግሥቱ ወንጌል በመላው አለም ለሁሉም ህዝቦች ይሰበካል።

(ቀ) በዳንኤል ትንቢት የተናገረው “የጥፋት ርኩሰት” ይፈጸማል

(በ) ከይሁዳ ከተሞች ወጥተው “ወደ ተራሮች የሚሸሹ የአማኞች ዘጸአት ይኖራል።

(ተ) የክርስቶስ “ፓሮውዥያ” ወይም “መገኘት” /ማለትም “መገለጥ” (ይህም አንዳንድ ክርስቲያኖች “ዳግመኛ ምጽአት” ብለው የሚጠሩት የተባረከው ተስፋ ይፈጸማል።


እነዚሀ ሁሉ ሁኔታዎችና ክንውኖች ተፈጻሚ የሚሆኑት እርሱ ቆሞ ሲናገር በዚያን ጊዜ ይሰሙት የነበሩ ሰዎች ትውልዳቸው ሳያልፍ በገዛ ዘመናቸው እንደሆነ ኢየሱስ ይናገራል። ኢየሱስ ንግግሩን ሲቀጥል፣ በዚያው በጠያቂዎቹ ትውልድና ዘመን ውስጥ ከምጽአቱ አስቀድሞ ስለሚሆኑ ጉዳዮች፣ ምልክቶችና ኹነቶች ከላይ ከ ሀ እስከ ተ በዝርዝር ያየነውን ይነግራቸዋል። በግልጽም የነገራቸው አንድ ጉዳይ እነርሱ እነዚህ ነገሮች ሲሆኑ እንደሚያዩና፣ በዚህም ሲሆኑ በሚያዩዋቸው ምልክቶች አማካኝነት መምጣቱ የቀረበ መሆኑን የሚያውቁ እንደሆነ ነው። ይህንን የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍል በጥንቃቄ የሚያጠኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ቢያንስ ከሚከተሉት መደምደሚያዎች ወደ አንዱ የደርሳሉ፦


  1. ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ የተናገረውን በመናገሩ ተሳስቷል።

  2. ኢየሱስ እነዚህን መግለጫዎች በመስጠት ሆን ብሎ ደቀ መዛሙርቱን አሳስቷቸዋል።

  3. በዚህ ክፍል ውስጥ ኢየሱስ የተናገረው ነገር ሁሉ እውነት እና ትክክለኛ ነገር ነበር፣ ኢየሱስ በተናገረው መሰረትም ተፈጽሟል


ከላይ በተራ ቁጥር 1 ወይም 2 ላይ የተቀመጠው ትክክለኛው አቋም ነው ብሎ የሚደምደም አንባቢ ቅዱሳት መጻሕፍት የሚናገሯቸውን ነገሮች በሙሉ የማይታመኑ አድርጎ በጥርጣሬ ውስጥ ማስቀመጥ ስለሚኖርበት የክርስትና እምነቱን ወደ ኋላ ጥሎ ለመተው የተመደበ ሊሆን ይችላል። ተራ ቁጥር1 ወይም 2 ላይ የሰፈረው ድምዳሜ እውነት ነው ብለህ ካመንክ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከተሰጠው ትመህርት የትኛው እውነት ነው፣ ስህተትም የለበትም ብለህ ልታምን ትችላለህ? በማቴዎስ 24 ኢየሱስ ስለመመለሱ የሰጠው ትንቢት ላይ ማስተባበያ እያቀረብክና ማመን እየተቸገርክ ራሱ ኢየሱስ በዮሓንስ 3 16 ላይ ስለ ድነት እና ስለ ዘላለም ሕይወት የሰጠውን ተስፋስ እንዴት ማመን ይቻልሃል?


ጌታን እየወደድን በክርስቶስ ፍቅር ውስጥ ለምንኖር ሰዎች በተራ ቁጥር 3 ላይ ያለው መደምደሚያ እውነትና ተክክል የሆነ ብቸኛው ምርጫን ነው። ነገር ግን፣ እምነታችንን እና መረዳታችንን ቅዱሳት መጻህፍት ከሚያስተምሩት ጋር ለማስታረቅና ለማስማማት በብዙ የአስተምህሮና የአመለካከት አቋሞቻችን ላይ ተገቢውን እርማት እያደረግን ልማዳዊ እምነቶቻችንን መቀየርና ማረቅ ይጠበቅብናል። ይህ ደግሞ ጌታ ለራራላቸው ለአንዳንድ ክርስቲያኖች ብቻ ቀላል ነው፣ ልማድ ላነቃቸው ለሚበዙት ግን በእውነት ከባድ ነው።


እስካሁን ሳወራው በነበረው መሰረት እያንዳንዱ የመጽሓፍ ቅዱስ አማኝና ተማሪ የሆነ ክርስቲያን ወደ ቅዱሳት መጻሕፍት ሲቀርብ “የበኩረ ተደራሲያኑን ዋጋ እና አግባብነት” መረዳት አለበት ብዬ በጥብቅ የማምንበትን ምክንያት የተረዳችሁ ይመስለኛል። አንዳንድ የቅዱሳት መጻሕፍት ክፍሎች በቀጥታ ለተወሰኑ ሰዎች የተጻፉ ናቸው፤ በመሆኑም እውነትን በሚያከብር እምነትና፣ ተአማኒነቱን ለጥያቄና ለጥርጣሬ በማያጋልጥ ዝግጅት፣ ለሚጠይቁንም ሁሉ መልስ ለመስጠት በምንችልበት አቋም ተጠንቅቀን የቃሉን ትምህርት አክብረን ልንይዘው ይገባናል። አውደ ምንባቡን እና የበኩረ ተደራሲያኑን ዋጋና አግባብነት እየደፈጠጥን ያቆምነውን የመጻኢነት አስተምሀሮ በጊዜ አርመን አግባብነት ወዳለውና ወደ ትክከለኛው ትምህርት ካልተመለስን የምንከተለውና የምንጮህለት ነገረ ፍጻሜ መልሶ እኛው ላይ ይጮህብናል፣ መዘዙንም የሚችለው የለም። መጽሐፍ ቅዱስ በሰነድነቱ በየትኛውም ዘመን ላሉ ለሁሉም ሰዎች የሚሆን መልእክት፣ ትምህርት፣ ተግሳጽ፣ ምክር እና ማጽናናት ያለው የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ነው፣ ዳሩ ግን በየትኛውም ዘመን ላሉ ለሁሉም አይነት ሰዎች በቀጥታ የተጻፈና በአድራሻቸው የተላከ ግን አይደለም፤ የራሱ የሆኑ ታሪክ የሚያውቃቸው ቀጥተኛ ተደራስያን አሉት። እኛ እነርሱን አይደለንም፤ አጠቃላዩን መርህ ተከትለን እንዴት ባለ እምነትና መታዘዝ እንደኖሩ ምሳሌነታቸውን እንማርበታለን እንጂ እነርሱ በትውልዳቸው የኖሩበት አውድና የእኛ አውድ ፈጽሞ ልዩነት አለው። የቅዱሳት መጻህፍት ቃላት ለተወሰኑ ሰዎች ወይም ቡድኖች የተነገሩ ናቸው፣ እኛ ግን ዛሬ አንድን የቅዱሳን መጻሕፍት የንባብ ክፍል ወስደን ከራሳችን ጋር በማዛመድ ትምህርቱን ለማግኘት ጥበብን መጠቀም አለብን። የትኛውንም የቅዱሳት መጻህፍት ምንባብ በአግባቡ ተርጉሞ ለመረዳት ዋናና አስፈላጊ የሆነ አንድ ጉዳይ ቢኖር የምንባባቱን አውድ ማወቅ ነው። ይህም በአይነቱ የጽሁፉ በኩረ ተደራስያን የነበሩበት አጠቃላይ አውድ ማለት ነው። በዋናነትም ምንባቡ አስቀድሞ የተጻፈው ለነማን ነው የሚለውን ማወቅን ያካትታል። ከዚህ በተለየ አብዛኛውን ጊዜ ቅዱሳት መጻህፍትን በትክክል ያለመረዳት ችግር የሚከሰተው አንባቢው ምንባባቱን ለግሉ ወይም ለግሏ እንደተጻፈ አድርገው ሲወስዱ ነው። በመሰረታዊነት አዲስ ኪዳን በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ጸሐፍያን የተጻፈው ለመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖች ሲሆን የተጻፈውም የመጀመሪያውን ክፍለ ዘመን ኹነቶች ለመነጋገር ነው። 


በማቴዎስ 24 ላይ ያቀረብሁትን ጽሁፍና የቪድዮ ትምህርት እንዲሁም “ትንቢትን ለመተርጎም የአውደ ተደራሲያን ፋይዳ ለፕሪቴሪዝም” የተሰኘውን ጽሁፍ እንድትመለከቷቸው ጋበዝኳችሁ፦


https://gizachewkr.blogspot.com/2018/08/24.html

https://gizachewkr.blogspot.com/2018/11/blog-post_60.html

https://gizachewkr.blogspot.com/2018/11/blog-post_33.html

http://gizachewkr.blogspot.com/2018/11/blog-post_91.html

http://gizachewkr.blogspot.com/2018/11/blog-post_95.html

http://gizachewkr.blogspot.com/2018/11/blog-post_32.html

http://gizachewkr.blogspot.com/2018/11/blog-post_93.html

http://gizachewkr.blogspot.com/2018/11/blog-post_43.html

https://www.blogger.com/blog/post/edit/6922722142324655915/8904540573557567607


gkr



 .   













Wednesday, May 11, 2022

ነፍስ

 


 ነፍስ

ክርስቲያን መምህራን በጥቅሉ በሚከተሉት የሥነ ሰብ አስተምህሮ፣ ሰው ስጋና ነፍስ/መንፈስ የሚባሉና በየራሳቸው ያሉ የተለያዩ የማንነት ክፍሎች ያሉት ፍጡር የመሆኑን ጽንሰሃሳብ በብዛት ተቀብለው ያስተምራሉ። በርግጥም ስጋና ነፍስ/መንፈስ የሚባል ርዕሰ ጉዳይ በመጽሓፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኝ ጽንሰ ሃሳብ መሆኑ ብዙም አያከራክርም፤ የሁንና በመካከላቸው ያለውን ጉለህ ልዩነት ወይም አንድነት፣ እንዲሁም የመጨረሻ እጣ ፈንታቸውን በተመለከተ አብዛኛው ሰው የሚረዳበት መንገድ ብዙዎችን ሲያጠያይቅ ኖሮአል። በዋናነትም ነፍስ በርግጥ ከስጋ ሞት በኋላ በቀጣይነት ኢ-መዋቲ (immortal) ሆና በራስ አወቅነት (Consciously) ትኖራለችን? ይህንን አይነቱን አስተሳሰብስ በመጽሓፍ ቅዱስ መደገፉን ለመጠራጠር የሚያስችሉ ምክንያት የሚሆኑ ነገሮች ይኖሩ ይሆንን? የሚለው ጥያቄ አከራካሪ ነው።

[ኢ-መዋቲነት (immortality) ሲተረጎም፣ ያው 'አለመሞት' ነው፤ ይህም በሥርወ-ቃሉም ሆነ በትርጓሜው "መሞት አለመቻል” ተብሎ ሊወሰድ ይችላል። አለመሞትም የአንድን ሰው ሕልውና በሞትም ቢሆን እንኳ የማይገደብ አድርጎ ማስቀጠል ነው። በተለመደው አነጋገር፣ ኢ-መዋቲነት ማለት "ከሞት በኋላ" (after death) እንደማለትም ነው፣ ዳሩ ግን ፍልስፍናዊ በሆነ አነጋገር ሁለቱ ጉዳዮች አንድና ተመሳሳይ ነገሮች እንዳልሆኑ ደግሞ ማስተዋል ያስፈልጋል። ከሞት በኋላ ያለው ሕይወት ቀጣይነቱ ያልተወሰነ ይሁን ወይም አይሁን ብቻ የነፍስ ኢ-መዋቲነት ከስጋ ሞት በኋላ የመኖር ቀጣይነት ነው። ኢ-መዋቲነት ማለት ክርስትና የሚሰጠው ተስፋ እርሱም የዘላለም ሕይወት፣ ማለትም ከሞት ነፃ መሆን፣ እና የማያልቅ ኑሮ፣ የማያልፍ ሕልውና ነው። በአንጻሩም አንዳንድ ዘመናዊ የሆኑ ዝርያዎች በተፈጥሯቸው ባዮሎጂካዊ የሆነ ኢ-መዋቲነት ሊኖራቸው እንደሚችል ይታሰባል። ያም ሆኖ ኢ-መዋቲነት ማለት፣ አካላዊው ሰውነት ሞተም አልሞተም ማለቂያ የሌለውን ሕልውና ያመለክታል። እንደ እውነቱ ከሆነ፣ አንዳንድ የሕክምና ቴክኖሎጂዎች በሚያቀርቡት ሳይንሳዊ መላምት ወይም ልበ-ወለድ ከሞት በኋላ ያለ ቀጣይነትን ባይሆንም እንኳ የአካል አለመሞት ተስፋን ይሰጣሉ።] 

ከክርስቶስ ልደት በፊት ቀደም ብሎ በነበረው የግሪኩ አለም ታዋቂ በሆኑ የፍልስፍና ምሁራን የነፍስን ምንነት ለማብራራት የተደረጉ በርካታ ጥረቶች አሉ። ለምሳሌ ሆሜር የተባለው ፈላስፋ፣ 'ሶማ' የሞተ አካል ነው ሲል፣ ህያው የሆነውን አካል ወይም የአካል ክፍል ለመጥቀስ ግን 'ሜሌአ' የሚለውን ቃል ይጠቀማል፤ 'ሲይኺ' ደግሞ በአካል ብልቶች ውስጥ የሚኖር ዋነኛና አስፈላጊ የሆነ አቅም ሲሆን በእስትንፋስ አማካኝነት የሚታወቅ ህልውና ነው ይላል። 'ስይኼ' ሰውየውን ትቶ ከምድር በታች የሚሄደው በሞት ጊዜ ነው ሲልም ያምናል።

ምናልባት የነፍስን ተፈጥሮ ጠጋ ብሎ ለመረዳት በአይሁድ ሥነ ጽሁፎች ውስጥ የሚገኙትን የበለጠና የተራቀቀ ትንተና ተጠግቶ ማየት ያስፈልግ ይሆናል፤ የሆነ ሆኖ በእስራኤል ሕዝብ ዘንድ ለድርጅት ማንነት (corporate identity) ከሚሰጠው ከፍተኛ ዋጋ የተነሳ ግለሰባዊ ማንነት (individual person) በእስራኤል ጽሑፎች ውስጥ ብዙ ትኩረት ያልተሰጠው መሆኑን ግንዛቤ መያዝ ያስፈልጋል። በተጨማሪም በጊዜ ሂደት እያደገና እየሰፋ በመጣው ግንዛቤ ውስጥ ግን፣ ነፍስ የማንነታችን መደበኛ ቅርጸ-ቁምፊ (font) ወይም ልኬቱ ሆኖ የሚያገለግል ውስጣዊ ኃይል ነው፤ ወይንም ደግሞ ሕይወትን አልያም እራሳችንን ጥልቅ በሆነ እሴት፣ ተዛምዶ፣ ልብ፣ እንዲሁም ግላዊ መገለጫችንን  የምንለማመድበት ጥራት ወይም መስፈርት ተብሎ ሊተረጎም ይችላል። ነፍስ የሚታይ፣ የሚዳሰስና የሚጨበጥ ነገር ስላልሆነ በትርጓሜው ባለ ብዙ ገፅታ እና የማይጨበጥና የማይዳሰስ አይነት ነው። ነፍስ የእኛ ውስብስብ የማንነታችን አንድ ክፍል ተደርጋ ትታያለች። ብዙ ጊዜ የመጽሐፍ ቅዱስ ተርጓሚዎች መጽሐፍ ቅዱስን ከመጀመሪያው ቋንቋ ወደ እንግሊዝኛ ሲተረጉሙ “ነፍስ” ከሚለው ቃል ይልቅ “ልብ” የሚለውን ቃል ሲጠቀሙም ይስተዋላሉ። በአይሁድ ልማድ ውስጥ ነፍስን ለመረዳት የሚቀርቡ በርካታ መግለጫዎች አሉ። የተለመደው የመነሻ ነጥብም ነፍስ እግዚአብሔርን የመገናኛ መስመር ከመሆን ያነሰ አይደለም፣ የሚለው ነው።

ከዚህ በታች በአስረጅነት የቀረቡትን ጥቅሶች ካተዋልን በየምንባባቱ የነፍስን ተፈጥሮና ባህርይ ለመግለጥ የተጠቀመበተን ዘይቤ ማያት እንችላለን፦

ኢሳይያስ 1፥ 14 “መባቻችሁንና በዓላቶቻችሁን ነፍሴ ጠልታለች ሸክም ሆነውብኛል፥ ልታገሣቸውም ደክሜያለሁ።

በዚህ ጥቅስ ላይ ጌታ በሰውኛ ዘይቤ ስናገር ራሱ ነፍስ ያለው መሆኑን እና መታዘዝ በጎደለው የእስራኤል ኃይማኖታዊ ልማድ እንዴት እንደተጎዳ ሰሜቱን ያጋራል። ተመልከቱ ነፍስ የከፉ ምግባር "ጥላቻን" እየገለፀች ሲሆን፣ "እንደተጨነቀች" እና በህዝቡ ድርጊት "እንደደከመችም" ተመላክቷል። 

ኢሳይያስ 38፥ 15 " ምን እላለሁ? እርሱ ተናግሮኛል፥ እርሱ ራሱም ይህን አድርጎአል፤ በዘመኔ ሁሉ ስለ ነፍሴ ምሬት ቀስ ብዬ እሄዳለሁ።

እዚህም ባለው ጥቅስ ላይ ነፍስ እንዴት ባለ ኃዘን ስሜቱ የሚነካ እንደሆነ ተጠቁሟል። ነፍስ “ምሬት” እያጋጠማት እንደሆነም ተመላክቷል።

ማርቆስ 14፥ 34 "ነፍሴ እስከ ሞት ድረስ እጅግ አዘነች፤ በዚህ ቈዩ ትጉም አላቸው።"

ኢየሱስ  በዚህ ጥቅስ ላይ ስለ ነፍሱ ኃዘን ምን እያለ እንደሆነ እዩ፣ ነፍሱ እጅግ በጣም በኃዘን መጎዳትዋን ይገልጣል።። 

ሚክያስ 6፥ 7 "እግዚአብሔርስ በሺህ አውራ በጎች ወይስ በእልፍ የዘይት ፈሳሾች ደስ ይለዋልን? ወይስ የበኵር ልጄን ስለ በደሌ፥ የሆዴንም ፍሬ ስለ ነፍሴ ኃጢአት እሰጣለሁን?"

ነፍስ ኃጢአት መሥራት ትችላለች ማለት ነው። ጥቅሱም ‘’ኃጢአት የምትሠራ ነፍስ’ (ሕዝቅኤል 13፥ 19) ተብሎ እንደተጻፈ ነፍስ ኃጢአትን ትሰራለች ሲል ያረጋግጣል። ተመልከቱ፤ ነፍስ ሆነ ብላ በእቅድ ኃጢአትን ልትሠራ የምትችል እስከሆነ ድረስ ማድረግ ስለምትፈለገው ከፉ ሰራ መረጃን የምታዘጋጅ እና የምታደራጅ እንዲሁም የምታደርገውን ከፉ ስራ እንዴትና መቼ እንደምታደርገው፣ ምን እንደምታደርግ እና እንደማታደርግ ባሉ ጉዳዮች ላይ ውሳኔ ማድረግ ትችላለች ብለን መደምደም እንችላለን። እንዲህ ዓይነቱ ድምዳሜ ደግሞ ነፍስ አእምሮን እና ፈቃድን የያዘች እንደሆነ እንድናምን ያደርገናል። ሰው መልካምን ለማድረግ ፈቃድ ወይም ፍላጎት ሊኖረው ይችል ይሆናል፣ አቅም ግን የለውም፤ ክፉውን ለማድረግ ግን በነፍስያው ውስጥ ዕምቅ አቅም ሸሽጎ ይዟል። ራሱ ውድቀት ከሆነው ከዚህ እውነታ አንጻር ስለ ፍቃድ ጽኑ እስራትና ባርነት ካልሆነ በቀር ሰለ ፈቃድ ነጻነት እና የትብብር አቅም መነጋገር ምንም ትርጉም አይኖረውም። በአስረጅነት ካነሳናቸው ከእነዚህ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባቦች ተነስተን ነፍስ በአእምሮ፣ በፈቃድ እና በስሜቶች የተሠራች እንደሆነ እንረዳለን። 

ነፍስ ለሚለው በብሉይ ኪዳን ጥቅም ላይ የዋለው የዕብራይስጥ ቃል "ነፌሽ" (נֶ֫פֶשׁ‎ / nephesh) የተተኘው ነው። አዳምን ሲያበጀው ቶራህ እንደሚናገረው "እግዚአብሔር አምላክም ሰውን ከምድር አፈር አበጀው፤ በአፍንጫውም የሕይወት እስትንፋስን እፍ አለበት ሰውም ሕያው ነፍስ ያለው ሆነ።" (ዘፍጥረት 2፥ 7) ይላል። የነፍስን ገጽታዎች ለመግለጥ በአይሁድ ኃይማኖታዊ ወግ ውስጥም ከሚያገለግሉ ቃላት መካከል ይህ "እስትንፋስ" የሚለው ቃል አንዱ ነው፤ እርሱም ምንጩ ፈጣሪ ሲሆን፣ ፈጣሪ እንደማይዳሰስ ሁሉ ነፍስም የማይዳሰስ መሆኑን ያሳያል፤ ሕይወትንም ተንቀሳቃሽ /activate/ የሚያደርገው እና የፍጥረት ሁሉ ምንጭ ከሆነው አምላክ ጋር በህያውነት የሚያገናኘው ይኸው የነፍስ መንፈሳዊ ተፈጥሮ ነው። የአይሁድ መምህራን ሲያስተምሩ፦ "እግዚአብሔር አጥናፍ አለሙን እንደሚሞላ ሁሉ እንደዚሁ ነፍስም አካልን ሁሉ ትሞላለች። እግዚአብሔር እንደሚያይ ነገር ግን እርሱ በማንም እንደማይታይ ሁሉ እንደዚሁ ነፍስም ታያለች፣ እርሷ ግን በማንም አትታይም። እግዚአብሔር መላውን አለም እንደሚመግብ ነፍስም እንዲሁ መላውን አካል ትመግባለች። እግዚአብሔር ንጹህ እንደሆነ ሁሉ ነፍስም ንጽህት ናት። እግዚአብሔር በአጥናፍ አለሙ ውስጥ በሁሉ ስፍራ እንደሚኖር ሁሉ ነፍስም በአካል ውስጥ ታድራለች" ይላሉ። 

በእብራይስጥ "እስትንፋስ" የሚለውን ለመግለጥ ሦስት ቃላት ጥቅም ላይ ውለዋል፣ እነርሱም፦ "ነፌሽ"፣ "ሩኼ"፣ እና "ነሻምባ" ናቸው። ይህ "ነፌሽ" የተሰኘ ቃል ከብዙ ትርጉሞቹ መካከል ሥጋን እና ነፍስን እንደ አንድ የማይነጣጠሉ አካላት የሚያመለክት ሆኖ፣ በእብራይስጥ "ሰው" (human being) እንደ ማለት ነው። "ነፌሽ" ወይም ሰው ፣ ከሁሉ በፊት እስትንፋስ ያለው ሕያው ፍጡር ነው። የአንድ ሰው ሕይወት በደሙ ውስጥም ሆነ በአተነፋፈሱ ውስጥ እንደሚኖር ነዋሪ ሆኖ ይታያል (ዘዳግም 12፥ 23፣ 24)፤ ስለዚህም በህጉ እንደተገለጸው፣ ደምን ማፍሰስ ወይም መብላት ፈጽሞ የተከለከለ ነው። 

በአዲስ ኪዳንም ነፍስ ለተሰኘው ቃል የግሪኩ አቻ ሲይኺ (ψυχή / psychí) ሲሆን አንዳንዴም ሱኼይ ወይም ሱኼ ይሰኛል። አንዳንድ ሰዎች ነፍስ ከስጋ የመለየቱ ጽንሰ ሃሳብ ከግሪካውያን አስተሳሰብ የተቀዳና ክርስቲያኖች ከግሪክ ፍልስፍና ተውሰው የራሳቸው ያደረጉት ስህተት ነው ሲሉ ይከራከራሉ። እርግጥ ነው ግሪኮች ሰው በሚሞትበት ጊዜ ሲይኺ ሥጋውን ትታ ከምድር በታች ትሄዳለች ሲሉ ያምናሉ። ክርስቲያኖችም ይህንንው አስተሳሰብ ያስተጋባሉ። በእርግጥ ግን መጽሐፍ ቅዱስ በጉዳዩ ላይ ምን ያስተምራል? በሞት ጊዜ የሰውየው ሥጋ ሞቶ መበስበሱ፣ ነፍሱ ግን በሼዖል ማደርዋ፣ እርሱም የሞት ጥላ መሆኑ ግልጽ ነው። ሆኖም በግሪክ አስተሳሰብ ውስጥ እንዳለው አይነት ኦርቶዶክሳዊ የእስራኤል ሃይማኖት ተብሎ በሚጠራው ውስጥ፣ ከሞት በኋላ ለነፍስ የተለየ ቀጣይ ሕልውና እንዳለው አድርጎ የሚያስተምር ምንም ሀሳብ አይገኝም። እንደ አይሁዳዊው እምነት ከሆነ በሲዖል ማደር ያው መሞት በቻ ነው እንጂ ኢ-መዋቲነትን አያመለክትም። በአይሁድ ዘንድ ሞት የተፈጥሮ ዑደት አንድ ክፍል ተደርጎ ይወሰዳል፣ ይሁንና የሚሞተው ሰው እሱነቱን እስከወዲያኛው የሚያጣበት ስለሆነ ማንም ሰው ቢሆን ሞቱ ፍጹም ደስታን አይሰጠውም። ዘማሪውም በምስጋና ጸሎቱ ውስጥ "ወደ ጥፋት ብወርድ በደሜ ምን ጥቅም አለ? አፈር ያመሰግንሃልን? እውነትህንም ይናገራልን?" (መዝሙር 30፥ 9) ሲል የገዛ ሞቱ ምንም እንደማይጠቅመው ወይም እንደማያስደሰተው ለጌታ ይናገራል። ስለዚህ በአይሁዳዊው አስተሳሰብ ሞት የሁሉም ስሜታዊ ሕይወት መጨረሻ እንደሆነ ይታሰባል። ሰውየው ራሱ ሞተ እንጂ በተናጠል ነፍሱ ሞተ፣ ሥጋው ሞተ የሚባል ነገርም በአይሁድ ዘንድ አይታሰብም።

በብሉይ ኪዳን ነፍስ (nephesh) የተሰኘው ቃል አጠቃቀም አንድ ሶስተኛ የሚሆነው ከነፍስ ሞት ጋር የተያያዘ ነው፤ /በእርግጥም ይህ nephesh የተሰኘ ቃል በብሉይ ኪዳን ውስጥ ከ750 ጊዜ በላይ ተደጋግሞ የተጠቀሰ ሲሆን ከዚህ ውስጥ ከ200 ጊዜ በላይ የሚሆነው ከመሞት ጋር የተያያዘ ነው። ከብዙ በጥቂቱ ለምሳሌ ቀጥሎ የቀረቡትን እነዚህን ምንባባት ብናመሳክር ነፍስ ከሞት ጋር የተቆራኘች እንደሆነ እናያለን፦

"በዚያም ቀን ኢያሱ መቄዳን ያዛት፥ እርስዋንና ንጉሥዋንም በሰይፍ ስለት መታ፤ በእርስዋም ያሉትን ነፍሳት ሁሉ ፈጽሞ አጠፋቸው፥ ከእነርሱም አንዱን ስንኳ አላስቀረም፤ በኢያሪኮም ንጉሥ እንዳደረገ በመቄዳ ንጉሥ አደረገ።" ኢያሱ 10፥ 28፤ 

"ዕለት ዕለትም በቃልዋ ነዘነዘችው አስቸገረችውም፥ ነፍሱም እስከ ሞት ድረስ ተጨነቀች።" መሳፍንት 16፥ 16፤ 

"ነፍሴም ከአጥንቴ ይልቅ መታነቅንና ሞትን መረጠች።" ኢዮብ 7፥ 15፤ 

"ነፍሳቸውን ከሞት ያድን ዘንድ፥ በራብም ጊዜ ይመግባቸው ዘንድ።" መዝሙር 33፥ 19፤ 

"አቤቱ፥ እስከ መቼ ድረስ ታይልኛለህ? ነፍሴን ከክፉ ሥራቸው ብችነቴንም ከአንበሶች አድናት።" መዝሙር 35፥ 17፤ 

"ለቍጣው መንገድን ጠረገ፤ ነፍሳቸውንም ከሞት አላዳናትም፥ እንስሶቻቸውንም በሞት ውስጥ ዘጋ፤" መዝሙር 78፥ 50፤ 

"ስለዚህም እርሱ ብዙዎችን ይወርሳል፥ ከኃያላንም ጋር ምርኮን ይከፋፈላል፤ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ሰጥቶአልና፥ ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና እርሱ ግን የብዙ ሰዎችን ኃጢአት ተሸከመ፥ ስለ ዓመፀኞችም ማለደ።" ኢሳይያስ 53፥ 12፤ 

"ውሸታችሁን ለሚሰሙት ሕዝቤ እየዋሻችሁ ሞት የማይገባቸውን ነፍሳት ትገድሉ ዘንድ በሕይወትም መኖር የማይገባቸውን ነፍሳት በሕይወት ታኖሩ ዘንድ ስለ ጭብጥ ገብስና ስለ ቍራሽ እንጀራ በሕዝቤ ዘንድ አርክሳችሁኛል።" ሕዝቅኤል 13፥ 19፤ 

"እነሆ፥ ነፍሳት ሁሉ የእኔ ናቸው፤ የአባት ነፍስ የእኔ እንደ ሆነች ደግሞ የልጅ ነፍስ የእኔ ናት፤ ኃጢአት የምትሠራ ነፍስ እርስዋ ትሞታለች።" ሕዝቅኤል 18፥ 4፤ 

nephesh የተሰኘው የእብራይስጥ ቃል አንዳንድ ጊዜ ነፍስ ከሚለው የተለየ ትርጉም ይዞ የሚገኝበት ጊዜ አለ። በእነዚህ ከላይ በቀረቡ ምንባባት የአማርኛውም ሆነ የእንግሊዝኛው ትርጉም መጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ነፍስ የሚል ቃል በጉልህ ባይታያችሁ እንኳ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላትና የእብራይስጥ ብሉይ ኪዳን የጥቅስ ማውጫ መርጃ መጻህፍትን ተከትለን ጥቅሶችን በጥንቃቄ ብናነባቸው፣ ይህ nephesh ወይም ነፍስ የሚለውን ቃል በምንባባቱ ውስጥ መኖራቸውን እናስተውላለን። 

በርካታ ሰዎች ከፍጥረታት መካከል ነፍስ ያለው ሰው ብቻ እንደሆነ አድርገውም ያስባሉ፤ ነገር ግን በዘፍጥረት መጻሐፍ ላይ እንስሳትን እንኳ ነፍስ እንዳላቸው እናያለን። በበርካታ ስፍራዎች፣ ለምሳሌ ዘፍጥረት 1፥ 21፣ 24፣ 30 nephesh የሚለውን ቃል ከእንስሳትም ጋር ተገናኝቶና በቋሚነት ህያው ፍጥረት ወይም ህይወት ተብሎ መተርጎሙን  እናየዋለን። 

አንዳንድ ሰዎች ስነ ሰብን (anthropology) ሲተነትኑ ሥጋ፣ ነፍስና መንፈስ አለው ሲሉ ሰውን በሦስት መደብ ከፍለው ያዩታል፣ እነዚህ በአመለካከታቸው ትራይኮቶሚስት ይባላሉ። ጥያቄው ግን ይህ አይነቱ አመዳደብ ምን ያህል መጽሐፍ ቅዱሳዊ ነው? የሚል ነው። በእርግጥ ሥጋ፣ ነፍስና መንፈስ የተባሉ ቃላት በአንድ ላይ ተጠቅሰው ጥቅም ላይ ሲውሉ የምናይበት ጥቂት የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት በአዲስ ኪዳን ይገኛሉ፣ ለምሳሌ 1ኛተሰሎንቄ 5፥ 23 "የሰላምም አምላክ ራሱ ሁለንተናችሁን ይቀድስ፤ መንፈሳችሁም ነፍሳችሁም ሥጋችሁም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጣ ጊዜ ያለ ነቀፋ ፈጽመው ይጠበቁ።" ይላል። በእውነቱ ግን ይህ በራሱ እኛ በአፈጣጠራችን ሦስት መደብ ያለን መሆናችንን አያረጋግጥም። እነዚህ ሦስት ቃላት ጥቅም ላይ የዋሉት የሁለንተናን ፍጽምና አጽንዖት ለመስጠት ነው። መንፈስ እና ነፍስ የተሰኙት ቃላት የአንድን ሰው መንፈሳዊ ይዘት ለማመልከት በተመሳሳይ ጥቅም ላይ ሲውሉ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ይስተዋላሉ። ቃላቱ እዚህና በእብራውያን 4፥ 12 ላይ በአንድነት ሲታዩ በያዙት ትርጉም ምንም አይነት የተለየ ትርጉም ልናገኝባቸው አስቸጋሪ ይሆናሉ። በተለዋጭ መጽሐፍ ቅዱስ በማርቆስ 12፥ 30 ላይ ሌሎች አራት የሚሆኑ መደቦችን ሲገልጥ "ልብ"፣ "ነፍስ"፣ "አሳብ"፣ እና "ኃይል" ሲል መጥቀሱንም አስተውሉ። ታዲያ መደበኛው የስነ ሰብ ምዳቤ የትኛው ነው?

በአዲስ ኪዳንም ነፍስ (Ψυχή / psyche) ማለት "ህይወት" መሆኑን እና ሊሞት፣ ሊገደል ወይም ሊጠፋ የሚችል መሆኑን የሚያሳዩ በርካታ ምንባባት ያሉ መሆናቸው ግልጽ ነው። ለምሳሌ ቀጥሎ ያሉትን ምንባባት ተመልከቱ ፦

ሥጋንም የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚቻለውን ፍሩ።” ማቴዎስ 10፥ 28፤ 

ነፍሴ እስከ ሞት ድረስ እጅግ አዘነች፤ በዚህ ቆዩ ከእኔም ጋር ትጉ አላቸው።” ማቴዎስ 26፥ 38፤ 

ያንም ነቢይ የማትሰማው ነፍስ ሁሉ ከሕዝብ ተለይታ ትጠፋለች አለ።” ሐዋርያት 3፥ 23፤ 

ኃጢአተኛን ከተሳሳተበት መንገድ የሚመልሰው ነፍሱን ከሞት እንዲያድን፥ የኃጢአትንም ብዛት እንዲሸፍን ይወቅ።” ያዕቆብ 5፥ 20፤ 

ሁለተኛውም ጽዋውን በባሕር ውስጥ አፈሰሰ፤ እንደ ሞተም ሰው ደም ሆነ፥ በባሕርም ከሚኖሩት ሕይወት ያለበት ነፍስ ሁሉ ሞተ።” ራዕይ 16፥ 3 

psyche የተሰኘው የግሪክ ቃል (ወይም የቃሉ አመጣጥ) በአዲስ ኪዳን ውስጥ ከ100 ጊዜ በላይ ተደጋግሞ የሚገኝ ሲሆን ከመሞት ጋር በተገናኘ ደግሞ ከ30 ጊዜ በላይ እየተደጋገመ ጥቅም ላይ ውሏል። "ኢ መዋቲ" (immortal) የተሰኘው ቃልም ሆነ ጽንሰሃሳብ ግን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከ"ነፍስ" ጋር ተጋጥሞ የሚገኝበት አንድም ስፍራ የለም። ለእብራይስጡና ለግሪኩ ቃላት ብዙ ዓይነት አጠቃቀሞች ያሉ በመሆናቸው ምክንያት ይህ ትንታኔ እና ድምዳሜ ግራ አጋቢ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን የማስረጃው ቀዳሚነት በእርግጥም ነፍስ ከስጋ ተለይታ የምትኖር አካል አለመሆንዋን ያመለክታል። ከዚያ ይልቅ ነፍስ ሕይወት ወይንም የሕይወት ትርጉም ናት ማለት ነው። ስለዚህ ነፍስ ማለት አንድ ሰው ‘አለኝ’፣ ወይም ‘የኔ’ ከሚለው ነገር በላይ በብዙ የሚያሳየው ራሱ ሰውየውን፣ የሆነውን ወይም ማንነቱን ነው፣ ማለትም እሱነቱ ነው።

ስለዚህ፣ ኢ መዋቲ የሆነ ነፍስ ከሥጋ ሰውነት ተለይቶ ወይም ራሱን ችሎ በራሱ የሚኖር አካል ነው የሚለው መደበኛ የሆነውና የተለመደው እይታ በራሱ ችግር ያለበት ነው። ይህ እይታ በአብዛኛው ራሱን ያቆመው ደካማ በሆኑ ግምቶችና መላምቶች ላይ፣ ወይም በወጉ ባልተብራራ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጥቅስ ላይ በተደገፈ ልማድ ብቻ ላይ ሲሆን፤ ከመጽሐፍ ቅዱስ ውጭ በሆነ እንግዳ የፍልስፍና አስተሳሰብ ተጽዕኖም አርፎበታል። እንግዲህ የነፍስ ኢ መዋቲነት ጽንሰ አሳብ በበርካታ ክርስቲያኖች ዘንድ የተቀዳው ከመጽሐፍ ቅዱስ ሳይሆን ከግሪክ አስተሳሰብ እንደሆነ እናያለን።

ይህ ከሆነ ታዲያ ክርስቲያን የሆነ ሰው በሥጋው አካላዊውን ሞት ሲሞት ምን ይሆናል? በዚህ ነጥብ ላይ በክርስቲያኖች ዘንድ ግራ የተጋቡ አመለካከቶች ይስተዋላሉ። የሚበዛው ክርስቲያን ማህበረሰብ አመለካከቱ አማኝ በሚሞትበት ጊዜ ነፍሳችን "ከጌታ ጋር ልትሆን" ትሄዳለች ሥጋችን ግን እስኪነሳ እና በሰማይ ካለችው ነፍሳችን ጋር እስኪገናኝ ድረስ የመጨረሻውን የትንሣኤ ቀን በመቃብር ሆኖ ይጠብቃል የሚል አመለካከት አላቸው። በዚህ አተያይ "ከጌታ ጋር" የመሆን ጉዳይ በትክክል ብዥታ ያጠላበት ነገር ነው። ከጌታ ጋር መሆን በሰማይ ወይም ሰማይ ባልሆነ ሌላ ስፍራ ሆኖ አንዳንድ ጊዜም የሆነ በጊዜያዊነት የሚቆዩበት ወይም መካከለኛ ስፍራ ወይም ግዛት እንደሆነም ተደርጎ ይታሰባል። አንዳንዶችም፣ ከሞት በኋላ እስከመጨረሻው ፍርድ ድረስ ሁሉም ሰው ያንቀላፋል፣ ከዚያ በኋላ ክርስቲያን የሆኑ እያንዳንዳቸው በትንሳኤ ወደ ሰማይ ወይም ያላመኑቱ በፍርድ ወደ ገሃነም ያላካሉ ብለው ያስባሉ። አማኞች ሞተው ሲቀበሩ በቀብር ስርአታቸው ላይ ሰባክያን የሚሉት ቀዋሚነት የማይታይበት የተለያየ ነገር ብዙዎችን ግራ ያጋባል። ሟቹ ሰው አማኝ ከሆነ ሰባኪው "ወንድማችን አሁን በሰማይ ነው" ወይም አሁን "ከጌታ ጋር ነው" ሲል ሊደመጥ ይችላል። ሟቹ በሰማይ ነው ቢል እንኳ፣ ጉዳዩን አለፍ ብሎ ሊያስረዳ ሲሞክር ሰውየው በእርግጥም ገና በሰማይ እንዳልሆነ ነገር ግን "በመጨረሻው ቀን እስኪነሳ" ወይም እስከመጨረሻው ቀን ድረስ በጊዜያዊ የማቆያ ስፍራ እንዳለ አድርጎ ሊያስብ ወይም ሊናገር ደግሞ ይችል ይሆናል። በዚህ ጉዳይ ቤተክርስቲያን በታሪክ ውስጥ የተለያዩ አስተሳሰቦችን ስታስተናግድ ኖራለች። የሮማ ካቶሊክ ቤተክርስቲያንም ፑርጋቶሪ የምትለው ነፍሳት ከአንዳንድ ኃጢአቶቻቸው እየነጹ የሚቆዩበት ስፍራ የሆነ አንዳች ጽንሰሀሳብ ፈልስፋ ታስተምራለች፤ እንዲህ ያለው አስተሳሰብና ትምህርት ግን በተሃድሶው ወቅት በወንጌላውያን  የፕሮቴስታንት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ የተወገዘ ትምህርት ሆኗል። ስለ ነፍስ የሚደረግ እንዲህ ያለ አጭር ውይይትም በምንደርስበት መደምደሚያ ላይ ጥላውን ያጠላል። 

“አዳም ሲፈጠር የሰው ልጆች በሥጋ እንዳይሞቱ ወይም በአካላዊ ሁኔታ ለዘላለም እንዲኖሩ ሆነው የተፈጠሩ ነበሩ፣ መዋቲ የሆኑት በውድቀት ጊዜ ነው” ብሎ ማሰብም ፈጽሞ ስህተት ነው። መበስበስን እንዳያይ የተስፋ ቃል የነበረው እግዚአብሔር አዘጋጅቶት በድንግል ማርያም ማሕጸን ያደረው የኋለኛው አዳም የኢየሱስ ክቡር ሥጋ ብቻ ነው (ሐዋርያት 2፥ 27፣ 31፤ 13፥ 35)። እብራውያን 9፥ 27 ሰው ከመነሻው ሟች እንደሆነ ሲያመለክት አዳምን ጨምሮ ለሰዎች ሁሉ አንድ ጊዜ መሞት እንደተመደበ ይናገራል፤ ይህንን በኢዮብ 14፥ 5 እና በመዝሙር 139፥ 16 ካለው ጋር በማመሳከር ብናነበው ሰው ለምን በሥጋ እንደሚሞት ግልጽ ያለና አውዱን የጠበቀ ማብራርያ ይሰጠናል ስለዚህ ከቅዱሳት መጻህፍት ትምህርት ጋር የማይታረቀውን በልማድ ላይ የተመሰረተ የማናቸውንም የቤተክርስቲያን ምሁር ነኝ ባይ ትንታኔ ማስቆም ይገባል። ተዳሳሹ አካላችን እንደሆነ ወደ አፈር ሊመለስ ከአፈር ተሰርቷል፣ አለቀ! (ዘፍጥረት 2፥ 7፤ 3፥ 19፤ መዝሙር 90፥ 3)፤ እንሞታታለን እንጂ በአየር ላይ ተንሳፎ መሄድ የለም። ሥጋችንም ከዚያ ያለፈ ምንም የመጨረሻ ዕድል የለውም። በኃጢአት ወደቀም አልወደቀም፣ በበሽታ ተይዞ ወይም በሌላ በማናቸውም ሰበብ በአካላዊው ሞት ማለፍ የሰው ተፈጥሯዊ እጣ ፈንታውና፣ እግዚአብሔር ተገቢ እንደሆነ አስቦ በዘላለማዊ እውቀቱ ወስኖ ያዘጋጀው ነው፤ ተረት አትመኑ፣እውነታው ይሄው ነው።

ካስተዋልነው ከአዳም ኃጢአት አስቀድሞ አዳምና መላው ሕያው ፍጥረት ሁሉ በህይወት የሚኖሩ ብቻ ሳይሆን የሚሞቱም ደግሞ ነበሩ። ልማዳዊ በሆነው ነገረ መለኮትና ትምህርተ ሰብ ውስጥ ይህንን ማስተዋል ብዙዎች እንደሚቸግራቸው ግልጽ ነው፤ ዳሩ ግን የዘፍጥረት መጽሐፍ የመጀመርያዎቹ ጥቂት ምዕራፎች ላይ የሚደረግ ጥልቅ የቃሉ ጥናት ይህንን በብዙ ማስረጃ ያረጋግጣል። እግዚአብሔርም ፍጥረታትን ሁሉ ከፈጠረ በኋላ የፈጠረውን አዳም በገነት አኖረውና ህይወቱን ማቆየት ይችል ዘንድ ከሕይወት ዛፍ ፍሬ እንዲበላ እድል ሰጠው። ይህ እውነታ ብቻውን አዳም ከውድቀቱ በፊትም እንኳ ሊሞት የሚችል እንጂ ኢ መዋቲ እንዳልሆነ ይነግረናል። እንደተቀሩት ሕያዋን ፍጥረታት ሁሉ  አዳምም እንኳ መመገብ ያለበት መኖር እንዲችል ነው፣ ካልበላና ሥጋውን ካላበረታ ተርቦ ይሞታል። ካልሆነ ግን ሆድ ለምን አስፈለገው? ሆድና አጠቃላዩ የምግብ መፈጨት ሥርዓት ደግሞ ከአዳም ውድቀት አስቀድሞም እንኳ ነበር። ኃጢአትን ባደረገ ጊዜ ግን ወደ ሕይወት ዛፍ እንዳይደርስ ነው የተከለከለው፣ "አሁንም እጁን እንዳይዘረጋ፥ ደግሞም ከሕይወት ዛፍ ወስዶ እንዳይበላ፥ ለዘላለምም ሕያው ሆኖ እንዳይኖር፤" (ዘፍጥረት 3፥ 22) ይላልና። ስለዚህ ሥጋዊው ሞት ለአዳምም እንኳ የተፈጥሮ ዑደት ነው እንጂ በአዳም ውድቀት ሰበብ የመጣ አይደለም። 

እንደ ዘፍጥረት 3፥ 19 እና 2፥ 7 ከሆነ አዳም ስሪቱ አካላዊውን ሞት እንዲሞት ተደርጎ ነበር። ውድቀት ከመከሰቱ አስቀድሞ እንኳ ሰው ከምድር አፈር ለአፈር የተፈጠረ፣ ወይንም ወደአፈር ሊመለስ አስቀድሞ ተወስኖ ከምድር አፈር የተሰራ ነበር። ተመልከቱ አዳም ሲፈጠር የተሰራው ከምድር አፈር ነው፣ ሲወድቅም ያው አፈር ነው፤ ስለዚህ አፈርነት፣ ማለትም አፈር መሆን ከመጀመርያ የነበረ ነገር ነው እንጂ የውድቀት ውጤት አይደለም። ለአዳም መሬታዊነት ተፈጥሮው ነው እንጂ የደረሰበት የውድቀት ደረጃው አይደለም፤ የልቁንም በውድቀት ጊዜ አዳም የደረሰበት የሞት አይነትና ደረጃ ግን መንፈሳዊው ሞት ነው። በዘፍጥረት 3 ላይ አዳምና ሄዋን ከተከለከለው ዛፍ ፍሬ በልተው አይኖቻቸው ሲከፈቱ፣ ከራቁትነታቸው የተነሳም ሲያፍሩና እርቃናቸውን ለመሸፈን ሲጥሩ የነበረውን ሁኔታ ስንመለከት፣ ከእግዚአብሔር መለየት የተባለውን ሞት የሞቱት ያኔ እነደሆነና፣ እነርሱም መሞታቸውን አውቀውት እነደነበር እናስተውላለን። ምላሻቸውም እግዚአብሔር ሲቀርባቸው እየሸሹ እና ከፊቱ ለመሰወር እየጣሩ የተገኙበት ነበር። አዳም የሞተው የኃጢአት ሞት ይህ ነበር። በሮሜ 6፥ 23 ጳውሎስ ሲያስተምር "የኃጢአት ደመወዝ ሞት ነው" ይላል። ይህ ሞት አካላዊው ሞት ቢሆን ኖሮና በክርስቶስ በማመን የቀረልንና ይቅር የተባልነው ሞት ቢሆን ኖሮ ታዲያ እስካሁን አካላዊውን ሞት ለምን እንሞታለን? ጉዳዩ ከሥጋዊው ሞት ጋር የተገናኘ ከሆነ እንግዲያውስ ከሥጋዊው ሞት ለማምለጥ ክርስቶስ ከከፈለው በላይ ምን የቀረ ሌላ ያልተከፈለ ዕዳ ይኖር ይሆን? እኛስ ገና ያልሞትን የሞታችንን ቀን እየጠበቅን ነው እንጂ ያው በወረፋችን መሞታችን አይቀርም፣ በከረስቶስ አምነው የሞቱ በርካታ የምናውቃቸው ዘመድ ወዳጆቻችን በወረፋቸው የሞቱትኮ መሞት የተፈጥሮ ዑደት ስለሆነና በከረስቶስ ማመናቸው የሥጋ ሞትን ስላላስቀረላቸው ነው።  ጳውሎስ ግን የሚያወራው አዳም ስላለፈበት አይነት የኃጢአት ሞት፣ እርሱም የተከለከለውን ዛፍ ፍሬ በበላበት ቀን ከእግዚአብሔር ጋር ያለው ሕብረት ስለተቋረጠበት የሞት አይነት እንጂ ስለ ሥጋዊው ሞት እንዳልሆነ ግልጽ ነው።

ይሁንና ግን በስተመጨረሻ ያለን ዕድላችን በአዲሱ የከበረ አካል ሆነን ወደ ሰማይ የምንገባ መሆናችን ሲሆን፣ ይህም አማኞች ያላቸው የመጨረሻ ተስፋና ዕድል ፈንታ ነው። ይህንን ርዕሰ ጉዳይ አስመልክቶ መጽሐፍ ቅዱስ ምን እንደሚያስተምር ለማወቅ ፍላጎቱ ያላችሁ በተለያየ አቀራረብ የጻፍኳቸውን ጽሁፎች በብሎገሬ http://gizachewkr.blogspot.com/ ገብታችሁ እንድትመለከቷቸው እጋብዛለሁ።