Monday, December 28, 2020

አዲሲቱ ኢየሩሳሌም

አዲሲቱ ኢየሩሳሌም


"አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት የለም። ቅድስቲቱም ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም፥ ለባልዋ እንደ ተሸለመች ሙሽራ ተዘጋጅታ፥ ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ። ታላቅም ድምፅ ከሰማይ፦ እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው ከእነርሱም ጋር ያድራል፥ እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤ እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና ብሎ ሲናገር ሰማሁ።" ራእይ 21፥ 1-4


"ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክና በጉ መቅደስዋ ናቸውና መቅደስ በእርስዋ ዘንድ አላየሁም። ለከተማይቱም የእግዚአብሔር ክብር ስለሚያበራላት መብራትዋም በጉ ስለ ሆነ፥ ፀሐይ ወይም ጨረቃ እንዲያበሩላት አያስፈልጓትም ነበር። አሕዛብም በብርሃንዋ ይመላለሳሉ፥ የምድርም ነገሥታት ክብራቸውን ወደ እርስዋ ያመጣሉ፤ በዚያም ሌሊት ስለሌለ ደጆችዋ በቀን ከቶ አይዘጉም፥ የአሕዛብንም ግርማና ክብር ወደ እርስዋ ያመጣሉ። ለበጉም በሆነው በሕይወት መጽሐፍ ከተጻፉት በቀር፥ ጸያፍ ነገር ሁሉ ርኵሰትና ውሸትም የሚያደርግ ወደ እርስዋ ከቶ አይገባም።" ራእይ 21፥ 22-27


ራእይ 21 ላይ ያለውን ይህንን ምንባብ በቁሙ የሚተረጉሙ (literalist) እና በመጻኢነት ነገረ ፍጻሜ ቅኝት የሚረዱት በርካታ ክርስቲያኖች ናቸው። ስለዚህም አዲሱ ሰማይና ምድር ሆነ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ለእነርሱ ወደፊት በሺሁ አመት ማብቂያ ላይ ወይም በዳግመኛ ምጽአት ጊዜ የሚፈጠር አዲስ ፕላኔት እና ዩኒቨርስ፣ በአዲሱ ፕላኔት ላይም የምትሰራ አዲስ ከተማ እንደሆነ አድርገው ያስባሉ። ጉዳዩ ግን እንደእርሱ አይደለም። መንፈሳዊውን ነገር በመንፈስ ማስተዋልና መረዳት ያስፈልጋል። ይህ አዲሱ ሰማይና አዲሱ ምድር ግን ጳውሎስ "አዲስ ፍጥረት" (2ቆሮንቶስ 5፥17) ሲል የሚጠራውን፣ ከእግዚአብሔር ጋር ኪዳን በማድረግ በክርስቶስ በኩል ወደ አዲስ ኪዳን ህብረት የገቡትን የሚወክል መጠርያ ነው። አሮጌው ሰማይና አሮጌው ምድር ደግሞ ያለፈውንና የተሻረውን አሮጌ ኪዳን ይወክላል። አዲሲቱ ኢየሩሳሌምም በቅድስተ ቅዱሳን መልክና ስዕል የቀረበች ራስዋን ቤተክርስቲያንን የበጉን ሙሽራ ናት፤ በዚያም፣ ማለትም በአሁኑ የምድራዊ ህይወት አኗኗር የእግዚአብሔር መቅደስ በሰዎች መካከል የመሆኑን እውነታ ያሳያል።


አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ሁሉም የእግዚአብሔር ሕዝቦች፣ አሁንና ከሞት ወዲያ ማዶ ለዘላለም የሚኖሩባት ሰማያዊት ወመንፈሳዊት መኖርያቸው ናት። በነጻነት የምትኖረው የነጻነት ከተማ ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም እናታችን ናት (ገላትያ 4፥ 26) ሲል ጳውሎስ ያስተዋውቀናል። ጳውሎስ በመዝሙር 87 ላይ ስለ እግዚአብሔር ከተማ የተዘመረውን መዝሙር የሚያመለክት ይመስላል። መዝሙሩም በአዲሱ መደበኛ ትርጉም፦ 


"መሠረቱን በተቀደሱ ተራሮች አቆመ፤   እግዚአብሔር ከያዕቆብ ማደሪያዎች ሁሉ ይልቅ፣ የጽዮንን ደጆች ይወዳል።  የእግዚአብሔር ከተማ ሆይ፤ ስለ አንቺ ክቡር የሆነ ነገር እንዲህ ተብሎ ይነገራል፤  “ከሚያውቁኝ መካከል፣ ረዓብንና ባቢሎንን እጠቅሳለሁ፤ እነሆ፤ ፍልስጥኤምና ጢሮስ ከኢትዮጵያ ጋር፣ ‘ይህ ሰው በዚያ ነው የተወለደው’ ይላሉ።”  በእርግጥም ስለ ጽዮን፣ “ይህም ያም ሰው በእርሷ ውስጥ ተወለዱ፤ ልዑልም ራሱ ያጸናታል” ይባላል።   እግዚአብሔር ሕዝቡን ሲመዘግብ፣ “ይህ ሰው የተወለደው በዚያ ነው” ብሎ ይጽፋል። የሚያዜሙም መሣሪያ የሚጫወቱም፣ “ምንጩ ሁሉ በአንቺ ውስጥ ይገኛል” ይላሉ።" የሚል ነው። 


በእርስዋ ያልተወለዱና ልጆችዋ ለመሆን ያልታደሉ ፈጽሞ አያውቋትም፤ በወንጌሉ ጸጋ በቅዱስ ጥምቀት በእርስዋ የተወለዱ ብቻ ግን "እናታችን ጽዮን" (የድሮው ትርጉም) ሲሉ ይጠሯታል። እርስዋም በቅድስና ተራሮች ላይ ከፍ ብላ የተሰራች አይነ ግቡ ከተማ ናት። የጽዮን ደጆች ሲል እግዚአብሔር በህዝቡ መካከል የሚያድርበትን የመረጠውን ስፍራ መቅደሱን ያመለክታል። ለእኛ ለዳንን የዚያ አገር ዜግነታችን "እኔ ግን በእርስዋ ተወለድሁ" የሚሰኝ ባለ መብት የሚያደርግ ሙሉ የዜግነት ክብር የተሞላ ነው እንጂ፣ "እኔ ይህንን ዜግነት በብዙ ገንዘብ አገኘሁት" (ሐዋርያት 22፥ 27-28 ይመለከቷል) የሚያሰኝ አይደለም። በእርስዋ ተወለድሁ በሚለው ገለጻ የእግዚአብሔር ህዝቦች ለተወለዱበት ስፍራ ቤተሰብ መሆናቸውን ያመለክታል፤ እንደ ኢየሱስ ትምህርት ደግሞ ይህ መወለድ የቅዱስ ጥምቀት ተአምር የሚሰራው ዳግመኛ ልደት ነው (ዮሐንስ 3፥ 3-8)። የዚያ አገር ዜግነት የሚገኘው በልደት ብቻ ነው። እግዚአብሔር በቅድስት ከተማው ውስጥ በአዲስ ልደት በኩል ተወላጅ በመሆን የዜግነት መብት እንዲኖራቸው የሰጣቸውን ሰዎች በመዝገብ ጽፎ በሚያስቀምጥበት አኳኋን ተገልጧል። 


በዚያ የተወለደም ሰው "በዚያ ነው የተወለደው" ተብሎ በሌሎች ይታወቃል። የዚያ አገር ሰዎች የከበሩ ታዋቂዎች ናቸው። እነዚህ ያውቁኛል ተብለው የተዘረዘሩት የአለም ሕዝቦች ከመላው አለም የጸጋው ተካፋይ እንዲሆኑ ተጋብዘው የመጡና ከቅዱሳኑ ጋር እንዲቀላቀሉ የታደሉ የአህዛብ ሙላት ስብስብና ወኪሎች ናቸው። በዚያች ከተማ ውስጥ እንደ ባለ ሙሉ መብት የዜግነት ክብር ስንኖር በእግዚአብሔርና በእርስ በርሳችን ፊት ያለን እውነተኛው ማንነታችን የመጣንበት ዘር፣ የምንናገረው ቋንቋ፣ የቤተሰብ ትስስራችን፣ የቆዳችን ቀለም፣ የሀብትና የእውቀት ደረጃችን፣ ወይም ማናቸውም ምድራዊ ትምክህትና ኩራት አይደለም። እግዚአብሔር የእርሱ የብቻው እንድትሆኑ እናንተን የገዛ ራሱ ብቻ ልጆች ለማድረግ የከፈለው ዋጋ ታላቅ ነው፤ በከበረው የእግዚአብሔር በግ ደም ተዋጅታችሁ፣ በቅድስት ጥምቀት ውሃ ተሻግራችሁ ዜግነት ወዳገኛችሁበት መንግስት ፈልሳችኋል። 


የቅዱሳን ሃገር፣ እርሷም ኢየሩሳሌም ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ተሸልማና በውበትዋ አጊጣ ወርዳለች፣ በመንፈሳዊውም አለም በመካከላችን ናት። "ስለ አንቺ ክቡር የሆነ ነገር እንዲህ ተብሎ ይነገራል" እንደተባለ በእምነትና በመንፈስ የሚያዩ ብቻ ግርማዋንና ውበትዋን ያደንቃሉ። "ነገር ግን ወደ ጽዮን ተራራና ወደ ሕያው እግዚአብሔር ከተማ ደርሳችኋል፥ ወደ ሰማያዊቱም ኢየሩሳሌም፥ በደስታም ወደ ተሰበሰቡት ወደ አእላፋት መላእክት፥ በሰማያትም ወደ ተጻፉ ወደ በኵራት ማኅበር፥ የሁሉም ዳኛ ወደሚሆን ወደ እግዚአብሔር፥ ፍጹማንም ወደ ሆኑት ወደ ጻድቃን መንፈሶች፥ የአዲስም ኪዳን መካከለኛ ወደሚሆን ወደ ኢየሱስ፥ ከአቤልም ደም ይልቅ የሚሻለውን ወደሚናገር ወደ መርጨት ደም ደርሳችኋል።" (ዕብራውያን 12፥ 22-24) ተብሎ እንደ ተጻፈ፣ ወደ እርሷ የደረሱ ብቻ ያውቋታል። 


እግዚአብሔርም ራሱ ብርሃንዋ ሆኖ በዚያ ሁሉን ይገዛል። ወደ ቅድቲቱ ከተማ የዳኑ ብቻ ይገቡባታል እንጂ "ጸያፍ ነገር ሁሉ ርኵሰትና ውሸትም የሚያደርግ ወደ እርስዋ ከቶ አይገባም።" ይልቁንም  "በሕይወትም መጽሐፍ ተጽፎ ያልተገኘው ማንኛውም በእሳት ባሕር ውስጥ ተጣለ" (ራእይ 20፥ 15) ተብሎ እንደተጻፈ የእርኩሳን ሁሉ ዕድል ከከተማይቱ ውጭ ነው። "ስሞቻቸው በሕይወት መይሐፍ የተጻፉት" (ፊልጵስዩስ 4፥ 3)፣ ቅዱሳን የሆኑ አማኞች ሁሉ ግን እያንዳንዳቸው በግላቸው በክርስቶስ ሀልዎት ፊት ለመሆን እድሉ አላቸው። "ለበጉም በሆነው በሕይወት መጽሐፍ ለተጻፉት" እና እግዚአብሔር ለመዘገባቸው፣ ዳግም ለተወለዱ ሁሉ፣ በክርስቶስ ለተቀደሱና ለጸደቁ ለተመረጡት ቅዱሳን ሕዝቡ ሁሉ ክርስቶስ ጌታቸውን በውበቱና በግርማው ፊቱን እያዩ ሊኖሩበት የተሰጣቸው የሚበልጥ ሰማያዊ አገር ይህ ነው። "የወንዝ ፈሳሾች የእግዚአብሔርን ከተማ ደስ ያሰኛሉ፤ ልዑል ማደሪያውን ቀደሰ።" (መዝሙር 46፥ 4)፣ እንደተባለ "ጽድቅና ሰላም በመንፈስ ቅዱስም የሆነ ደስታ" (ሮሜ 14፥ 17) የሚፈልቅባትና የሚፈስባት ምርጥ አገር አለችን። ከእርሱ ጋር ለዘላለም በፊቱ እንዲኖሩ ከተማይቱን አዲሲቱን ኢየሩሳሌምን አዘጋጅቶላቸዋልና፣ በዚያም እግዚአብሔር አምላካቸው ተብሎ ሊጠራ በእነርሱ አያፍርም። "አሁን ግን የሚበልጠውን እርሱም ሰማያዊ አገር ይናፍቃሉ። ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካቸው ተብሎ ሊጠራ በእነርሱ አያፍርም፥ ከተማን አዘጋጅቶላቸዋልና።" (ዕብራውያን 11፥ 16)


ዳግመኛ የተወለዱ አማኞች ሁሉ በአዲሲቷ የኢየሩሳሌም ከተማ የተከፈቱ በሮች፣ በዘላለማዊው የወንጌል ስብከት፣ በእምነትና በንስሃ በማያቋርጠው የሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ በቀጣይነት በቅዱሳት ምስጢራት በኩል በሚታደል ጸጋ ወደፊት እየተጓዙ፣ በመንፈሳዊ ሁኔታ መግባታቸውን አያቆሙም ይቀጥላሉ። ይህም ሊካድ የማይቻል አሁን በዚህ ምድር ላይ በህይወት እያሉ በክርስቶስ ካገኙት ስፍራቸው የተነሳ ወይም ከእርሱ ጋር ካላቸው አንድነትና ግንኙነት የተነሳ ያለው የሚለማመዱት እውነታ ነው፤ ዳሩ ግን ለእያንዳንዳቸው አማኝ ግለሰቦች እስከ ሞታቸው ድረስ፣ ማለትም የማይሞተውን አዲሱን አካል ለብሰው ለዘላለም ከክርስቶስ ጋር ለመኖር ይህንን ስጋቸውን እስከሚለዩበት ቀን ድረስ ገና በፍጹምነት የታወቀላቸውና በሙላት ያገኙት አይደለም። የሞታችን ቀን የማያስፈራን ከዚህ ልምምዳችንና ከዘላለም ህይወት ተስፋ እውነት የተነሳ ነው። በዚያ መሆን የሚሻል እንደሆነ አምነን፣ ሞተን ከጌታ ጋር ለመሆን፣ ልንሄድ ከእርሱም ጋር ልንኖር የምንናፍቅ እኛ የዳንን ብቻ ነን።


እምብዛም የመጻኢነት አመለካከት እንዳልተጫነው አስቤ እየዘመርኩ የምጽናናበትን የወንድማችንን የዘማሪ ሸዋዬ ዳምጤ መዝሙር ልጋብዛችሁና ነገሬን ልጨርስ፤ እነሆ አዝማቹ እንዲህ ይላል፦


በውቢቱ ኢየሩሳሌም፣ በቅድስቲቱ ሃገር

ተስፋ አለን እኛም በጌታ፣ ለዘላለም ልንኖር

አልፈን የሞትን መንደር፣ ከዚያ ወዲያ

አልፈን የሞትን መንደር

ስጋ ከኛ ተገፎ

አሮጌው ሁሉ አልፎ

እንለወጣለን ጌታን እንለብሳለን


ልታነቡ ለምትወዱ "ከዚህ ህይወት በኋላ ለሚያምኑና ለማያምኑ" በሚል ርዕስ የለጠፍኩትን ጽሁፍ ጋበዝኳችሁ። እነሆ ሊንኩ፦

http://gizachewkr.blogspot.com/2019/02/blog-post_28.html


ግዛቸው ከበደ /ቄስ/

Saturday, December 5, 2020

የዲያብሎስ መጨረሻ

የዲያብሎስ መጨረሻ

ኢየሱስ ሲናገር፣ "የዚህ ዓለም (ዘመን) ፍርድ ደርሷል፣ አሁን የዚህ ዓለም (ዘመን) ገዥ ወደ ውጭ ይጣላል፣ /ወይም  ይፈረድበታል / ማለቱን ታስታውሳላችሁ? (ዮሐንስ 12፥ 31 ፤ 16፥ 11)፤ ይኸውም ተሸንፏል፣ አልቆለታል ማለት ነው።  እንደ አዲስ ኪዳን ትምህርት፣ ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሞቱ እና ከሙታን ተለይቶ በመነሳቱ ይህንን ታላቅ የድል ተስፋ ያጎናጸፈን መሆኑ እሙን ነው፤ የዳግመኛ ምጽአቱ ፓሮዥያው ደግሞ ያንን ታላቅ ድል በመጨረሻው መደምደሚያና በፍጻሜ ከፍታ ሙላት ሰጥቶ እና ገልጦ አቀዳጅቶናል። ድሉም ያለ ዳግመኛ ምጽዓቱ ሙላትና ፍጻሜ እንደማይኖረው ግልጽ ነው። ከአሮጌው የብሉይ ኪዳን ዘመን ወደ አዲሱ የቃል ኪዳን ዘመን የተደረገው የሽግግር ጊዜ፣ ልክ እንደ ጥንታዊት እስራኤል የ40 ዓመቱ የምድረ በዳው ጉዞ አይነት፣ ከመስቀል አንስቶ የዳግመኛ ምጽዓቱ ፓሮውዥያ እስከሆነበት 70 ዓ.ም. ድረስ ያለውን የሽግግር ጊዜ ይሸፍናል (ዕብራውያን 8፥ 13 ፤ 9፥ 8)። የብሉይ ኪዳን እስራኤል በፋሲካው ደም ከግብጽ ባርነት አርነት ወጥቶ ከ40 አመታት የምድረ በዳ ጉዞ በኋላ የተስፋይቱን ምድር እንደወረሰ፣ እንዲሁ በመስቀል ላይ በታረደው በግ ደም ቤዛነቱን ያገኘው የአዲሱ ኪዳን ቅዱስ ህዝብ ከሌላ 40 አመታት የስደትና የመከራ ጉዞ በኋላ በዳግመኛ ምጽአቱ የተስፋ ቃሉን ፍጻሜና ሙላት ለማግኘት ጌታን እየጠበቀ መታገስ ነበረበት።

2 ቆሮንቶስ 4፥ 4 "የዚህ አለም / ዘመን/ አምላክ" ስለሆነው አሳዋሪ ይናገራል፣ ይህ አለም የተባለው ግን ዘመኑን ማለት እንጂ ተዳሳሹን ግዑዝ አለም ማለት አይደለም። በ“ዘመን” መጨረሻ ፣ ይኸውም በማቴዎስ 24፥ 3 በተጠቀሰው በብሉይ ኪዳን ዘመን ማብቂያ ፣ ሰይጣን ከገዥነቱ ስልጣን ወርዶ፣ ሉተር እንደሚያስተምረው፣ የተሸነፈ ጠላት ሆኗል፡፡  እንደ እግዚአብሔር ፕሮግራም ከላይ ሆኖ በአየሩ ላይ ይገዛ የነበረው አለቃ እርሱ በማይታዘዙ ልጆች ላይ ከሚገዛበት ከሰማይ (ኤፌሶን 2፥ 2)፣ ከገዥነቱ ሥልጣንና ከፍታ እንደ መብረቅ መውደቅ ነበረበት (ሉቃስ 10፥ 18) የአወዳደቁ ሁኔታ ግን  ያኔ ሂደቱ ገና ጅምር ነበር፣ በዳግመኛ ምጽአቱም ፈጽሞ ተሸንፎ ከኢየሱስ እግሮች በታች መቀጥቀጥ እና መገዛትም ይገባው ነበርና (ሮሜ 16፥ 20 - ዘፍጥረት 15፥ 15 ፤ ራእይ 2፥ 26፣ 27) ፣ እግሮች የተባሉትም የአካሉ ክፍል የሆኑት ናቸው፡፡

ሰይጣን በዘመኑ ላይ የነበረውም አገዛዝ በሽግግሩ ወቅት ላይ በሂደት እየተገለበጠና እየተለወጠ ነበር፣ የሽግግር ዘመን የወንጌል አገልግሎት አንዱና ዋናው ተጽዕኖም ይኸው ነበር (የሐዋርያት ሥራ 17፥ 6)። በራእይ 20፥ 7 ላይ ለጥቂት ጊዜ ከእስራቱ እንዲፈታ በተባለለት አኳኋን፣ ሰይጣን በቄሳር ኔሮ ዙፋን ላይ ሆኖ የመጨረሻውን የመልሶ ማጥቃት በቅዱሳን ላይ አድርሶ ነበር። ዲያብሎስ ራሱ ጥቂት ጊዜ እንደቀረው ያውቅ ስለነበር፣ ያኔ ይሰራ የነበረው፣ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሳ አንበሳ፣ በታላቅ ቁጣ ነበር (ራእይ 12፥ 12፤ 1 ጴጥሮስ 5፥ 8-9)፤ ስለዚህም የመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ቤተክርስቲያን መከራዋ ታላቅና አለም አቀፋዊ ነበር። በሕጉ ስርአት በኩል ጉልበታም ሆኖ የሚሰራው የኃጢአት ኃይል ዋና የማዘዣ ጣቢያው የሚገኘው ደግሞ በቤተ መቅደሱ ነበር፣ "የሞት መውጊያ ኃጢአት ነው የኃጢአትም ኃይል ሕግ ነው" (1 ቆሮንቶስ 15፥ 56) ተብሏልና። የዚያ የአሮጌው ዘመን ስርዓት የሰይጣንን ክስ እና የውንጀላ ስድብን ሁሉ ከእርሱ ጋር ወደታች እያወረደ  የሞትን እና የኩነኔን አገልግሎት ያስፈጽም ነበር። ከዚያም በኋላ ግን ሰይጣን በክርስቶስ ዳግመኛ ምጽአት ዘላለማዊ ሽንፈቱንና  ፍርዱን አገኝቷል (ራእይ 20፥ 10)፣ ይሄ ግን ፈጽሞ እስከወዲያኛው አጥፍቶታል ወይም ወደአለመኖር ቀይሮታል ማለት አይደለም። እርሱ ግን ሁልጊዜ እንደሆነውና እንደነበረው ያው የተፈረደበትና የተጣለ፣ በቁጥጥሩ ስር ያለ የእግዚአብሔር  ዲያብሎስ ሆኖ ይኖራል፡፡  

እኛ አሁን እየኖርን ያለነው ከሽግግሩ ዘመን ማዶ ባለው፣ አሮጌው ዘመን በተሻረበት እና በዳግመኛ ምጽአቱ በተጀመረው በዘላለማዊው ዘመን በአዲሱ ኪዳን ዘመን ውስጥ ነው፣ (ኢሳይያስ 9፥ 7 ፤ ዕብራውያን 13፥ 20)። ይኸውም አዲሱ ሰማይና አዲሱ ምድር ነው። በዚህ ክቡር ዘላለማዊ ኪዳን ስር አድረው ክርስቶስን የሚያከብሩት እነዚያ እርሱ የተቤዣቸው ሕዝቦቹ እና እያንዳንዳቸው ቅዱሳኑ ብቻ ናቸው (መዝሙር 2)፤ እነርሱም ብቻ ድል የነሱ እና የተባረኩ ፣ ከፍ ከፍ ብለው በሰማያዊው ስፍራ ከእርሱ ጋር ያሉ እና ሥልጣንና ኃይል የተሰጣቸው ናቸው።  ከመጀመሪያው ምዕተ-ዓመት ጀምሮ ደግሞም ሁልጊዜ የማይበገሩ ኃያላን ሆነው በሰማያዊው ስፍራ ከክርስቶስ ጋር የነገሱ እና የሚገዙ ክርስቶስን የሚያከብሩ ሕዝቦች እነርሱ ብቻ ናቸው።  ክርስቶስንና የጽድቅ መንግስቱን የሚቃወሙ ማናቸውም የምድር ህዝቦች ተሰብረውና ተደምስሰው፣ እርሱ ከፍ ከፍ ባደረጋቸው፣ ክርስቶስንም ሊያከብሩ በተገባቸውና የእርሱን ጽድቅ በተሸከሙ ሕዝቦቹ እግር ስር ተጥለው ተረግጠዋል ፡፡ ክርስቶስ የዚህ የአዲሱ አለም /ዘመን ጌታና አምላክ ስለሆነ፣ ከኔሮ ዘመን በኋላ በቅዱሳኑ ላይ በዓለም ዙሪያ አለማቀፍ የሆነ ስደት ያልነበረው እና ደግሞም ከዚህ በኋላ በጭራሽ የማይኖረው ለዚህ ነው። ምክንያቱም የነገስታት ንጉስ እና የጌታዎች ጌታ የሆነው የቤተክርስቲያን ራስ ኢየሱስ ክርስቶስ ጠላቶቹን ሁሉ ረግጦ፣ ግዛትና መንግስትም ተሰጥቶት ለቅዱሳኑ ዘላለማዊ እረፍት በአባቱ ዙፋን ላይ ተቀምጦ የሚገዛ በመሆኑ ዘመኑ ተቀይሯል።

ከዚህ ቀደም እንደ ፕሪቴሪስት፣ "እኩይ እና ፍጻሜው" ብዬ በዚሁ ግድግዳ ላይ ለጥፌ ያስነበብሁትን አጭር ጥፈት ለተጨማሪ ግንዛቤ እንዲሆናችሁ የልጥፉ ሊንክ እነሆ:-
https://m.facebook.com/story.php?story_fbid=2021585444607057&id=100002668627386

Saturday, May 16, 2020

አውሬው ማን ነው?

አውሬው ማን ነው?

ወንድም ነብዩ ኢሳይያስ በፌስ ቡክ ገጹ የ666ን ወይም የአውሬውን ማንነት አስመልክቶ በጥሙራውያን (eclecticism) የትርጉም ጎራ ያለውን አስተንትኖ በጽሁፍ በተከታታይ ካቀረበልን በኋላ እንደ ኃላፋውያን አተያይ ወንድማችን ከደረሰበት ድምዳሜ የምንለይበትን መሰረታዊ ምክንያት ማቅረብ አስፈላጊ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። በእውነቱ ጽሁፉ በርካታ ጠቃሚ መረጃዎችን የያዘ በመሆኑ በፍላጎት አንብበው ከተጠቀሙት አንዱ ነኝ። ነብዩንም ለዚህ ትጋቱ ላመሰግነው እወዳለሁ። የነብዩ ጽሁፍ  ላላጋጠማችሁ በዚህ ሊንክ ፈልጉት፦ 


https://m.facebook.com/story.php?story_fbid=3545055902188848&id=100000534203478


https://m.facebook.com/story.php?story_fbid=3551996218161483&id=100000534203478


https://m.facebook.com/story.php?story_fbid=3560230400671398&id=100000534203478


https://m.facebook.com/100000534203478/posts/3576034962424275/?notif_id=1589324735799045&notif_t=close_friend_activity&ref=notif



እንግዲህ በቅርብ እንዳለ ወንድምና ጓደኛ በልብ ስፋት ተደማምጠን በጓዳም ሆነ በአደባባይ የምንሟገትባቸው የሃሳብ ልዩነቶቻችን አሉ ይኖራሉም። ወንድማችን ያስተዋወቀንን ጥሙራውያንንና አመለካከታቸውን ጌታ ቢፈቅድ ብንኖር በሌላ ጊዜ ልመለስበት ይቆየኝ እያልኩ፣ በራእይ 13 የተገለጠውን አውሬ አስመልክቶ ግን ጥሙራውያንን ጨምሮ በበርካታ ተርጓሚዎች ለሚሰነዘሩ የተለያዩ መላምቶች ማጥሪያና ማጥለያ ሆኖ የሚያገለግል ግልጽ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መርህ ማቆም ያስፈልጋል ባይ ነኝ። የዚህች አነስተኛ ክትባት ዋና አላማዋ ግን እንደ ኃላፋውያን አመለካከት ይህ አውሬ በታሪክ ውስጥ የሚታወቅ አንድ ግለሰብ እንጂ ሌላ ምንም ነገር ነው ብሎ ድምዳሜ ላይ እንዳይደረስ በቅዱስ ቃሉ የሚከለክሉ ባለ አምስት ነጥብ የትርጉም መርሆዎችን ማመልከት ብቻ ነው። ነጥቦቹም እነሆ:-


1ኛ/ 666 የተሰኘው የስሙ ቁጥር ግልጽ ሆኖ እንደተጠቀሰው "የሰው ቁጥር" (ራእይ 13 18) መሆን አለበት እንጂ ሌላ ምንም ነገር ሊሆን አይችልም። ሰው ብቻ። ይህም ማናቸውንም አጋንንታዊ ወይም መናፍስታዊ ማነትን፣ አልያም ፍልስፍናዊ አስተሳሰብን፣ ፖለቲካዊ ንቅናቄን፣ ኃይማኖታዊ ተቋማትን፣ ወይም ድርጅትን የሚያመለክትም የሚወክልም አይደለም። በታሪክ ውስጥ የሚታወቅ አንድን ግለሰብ ወይም ሰብአዊ ፍጡር ከመሆን ውጭ ማንኛውንም የዚህ ግዑዝ አለም ስርአተ ማህበርን ትርጉም አድርጎ አያካትትም። ሌላው ቢቀር ወንጌላውያን በሆኑ አንዳንድ የሙሉ ኃላፋውያን መምህራን ዘንድ "አውሬው ከኢየሩሳሌም መደምሰስ በፊት የነበረው አሮጌው የይሁዲነት ስርአት ነው" የሚለውንና ብርቱ ሙግት የሚያቀርበውን ድምዳሜ እንኳ የዚህ ጽሁፍ አቅራቢ "የሰው ቁጥር" ከሚለው መርህ ጋር ማስታረቅ ይቸግረዋል። ኅላፊያን የራእይ 13ቱን አውሬ በታሪክ ውስጥ ከኔሮ ጋር ብቻ አያይዘው  የተፈጸመና ያበቃ ጉዳይ አድርገው ለምን ይተረጉሙታል? ከተባለ፣ አውደ ምንባቡ "የሰው ቁጥር" በሚለው መግለጫው አንድን ግለሰብ ወይም 'ሰውዬ' እንድናስብ ብቻ እንጂ፣ ሌላ ማናቸውንም ጥንታዊና ዘመነኛ የአለም ስርአት እንዳናስብ ስለሚገድበን ነው። "የሰው ቁጥር" ከሁሉ በተለየ የሰው እንጂ የድርጅት፣ የተቋም፣ ወዘተ አይደለም። የራእይ መጽሐፍ በ70 ዓ.ም ላይ ከሆነው የእስራኤል ፍርድና የአይሁድ ህዝብ እልቂት በላይ ሌላ የሚለው ነገር ከሌለው፣ ከዚህ አይነተኛ አውድ ውጭ የሆኑና በታሪክ ውስጥ የሚጠቀሱት የሮም ፣ የጀርመን የናዚ ወዘተ.. ግዛተ - አፄዎች፣ ወይም የሂትለር፣ የሙሶሎኒ የሳዳም ሁሴንን፣ የኦባማ ወዘተ..- መንግሥታት እዚህ ውስጥ ምን ያገባቸዋል? እነዚህ ግዛተ አፄዎች እና መንግስታት የየራሳቸው ክፋት እንዳለባቸው ቢታወቅ እንኳ የራእይ 13ቱን አውሬ ለመሆን ግን አውድ ይገድባቸዋል። 


2ኛ/ በዚህ ቁጥር የሚወከል ይህ 'አውሬ ሰው' ክፉ የሆነ ዘማዊነትን የሚገልጥና በእርኩሰት የሚነዳ የስድብን ተፈጥሮ የተሞላ መሆን አለበት። ይህም በራእይ 13 በተለይም ከቁጥር 4-7 በተዘረዘረው መሰረት ባህርዩን፣ ተግዳሮቱንና የክፋት ስራውን መሰረት አድርገን ከመረመርን በራሱ በዩሐንስም ሆነ በመልእክቱ በኩረ ተደራስያን "እከሌ" ተብሎ ሊለይና ሊገለጽ የሚችል የሚታወቅ 'አውሬ ግለሰብ' ነው።


3ኛ/ ይህ አውሬ ሰው "ታላቅ ሥልጣን" የተሰጠው አንድ ግለሰብ መሆን አለበት (ራእይ 13፥ 2፣ 7)። ይህም በተለይ ትርጉሙን ካላወሳሰብነው በቀር በራሶቹ ላይ ካሉት አስር ዘውዶች የተነሳ ከአንድ ፖለቲካዊ ሥርዓተ ማህበር ባለፈ አንድን የተለየ ፖለትካዊ ስብዕናን በእርግጠኝነት እንድናስብ የግድ የሚል ነው። 


እነዚህ የመጀመርያዎቹ ሦስት ነጥቦች በኃላፋውያን ዘንድ ብቻ ሳይሆን፣ በሌሎች ወንጌላውያን በሆኑ የራዕይ መጽሐፍ ተንታኞች፣ በጥንቶቹም በዘመናውያኑም ዘንድ በስፋት ተቀባይነት ያላቸው ናቸው። ቀሪዎቹ ሁለቱ ነጥቦች ደግሞ በእርግጠኝነት የአውሬውን ማነነትና ተልዕኮውን በተመለከተ ያለውን የመረዳት ስህተት የሚያርሙና፣ በትርጉማችን ላይ ችንካርን እየሰጡ መሰረታዊ ለውጥ የሚያመጡ ያንንም በጽኑ የሚያሳዩ ምክንያቶችን የሚያቀርቡልን ናቸው። እነዚህንም በብዙ ማስረጃ ዘርዝሮ ማሳየት የሚቻል ቢሆንም ከጊዜ አንጻር ግን ነጥቦቹን በማሳየት ብቻ እገደባለሁ።


4ኛ/ ይህ የስሙ ቁጥር የግድ የሚያመለክተው ሐዋርያው ዮሐንስ በኖረበት ዘመን የኖረ አንድን ግለሰብ ነው። ይህንንም ማለት የምንችለው ዮሐንስ በጊዜው የትንቢቱን ፍጻሜ በገዛ ራሱ ዘመን ይጠባበቅ ከነበረበት ጽኑ እምነት በመነሳት ነው። በራዕይ መጽሐፍ የተገለጡና ይሆናሉ የተባሉ ኹነቶች ሁሉ ከጊዜ አንጻር "ቶሎ" ሊሆኑ ያላቸው ነገሮች ናቸው። ዮሐንስም "ዘመኑ ቀርቦአል" እያለ አጽንዖት የሰጠበት ጉዳይ ነው (ራእይ 1፥ 1፤ 3፥ 19፤ 22፥ 6)። ይህንንም ጊዜ ጠቌሚ የሆነ ሃሳብ በጉልህ የሚያሳዩ ማስረጃዎች በመጽሐፉ መግቢያ፣ በራእዩ መካከል እና በማጠቃለያው ባሉ ምዕራፎች ውስጥ ማየት ይቻላል (ራእይ 1፥ 1፣ 3፣ 7፣ 9፣ 10፣ 19፤ 2፥ 16፣ 25፤ 3፥ 10፣ 11፤ 4፥ 1፤ 6፥ 16-17፤ 8፥ 13፤ 10፥ 6-7፤ 11፥ 1-2; 22፥ 6-7፣ 10፣ 12፣ 20 ወዘተ )። አውሬው እንዲሰለጥን የተሰጠውንም የ42 ወራት ጊዜ ይህንንው ሙግት ለማጠናከር በማስረጃነት ማቅረብ ይቻላል። ኃላፋውያን በትርጉማቸው ጊዜ ጠቋሚ የሆኑ ንግግሮችን አስመልክቶ የቀረቡ የራእዩን መግለጫዎች በአግባቡ ይጠቀሙባቸዋል እንጂ አልሞስሙሰው አይዟቸውም። ጊዜን አመልካች የሆነው የራእዩ ንግግር በመጽሐፉ መግቢያ መሐል ላይና በማጠቃለያው ላይ መጠቀሱ ትንቢቱ ሳይነጣጠል በተያዘለት ቀነ ቀጠሮ የሚፈጸምበትን ዓይነተኛ የጊዜ ማዕቀፍ አመላካች ነው። ማንም ተርጓሚ ቢሆን በመጽሐፉ ላይ አውድ ዘለል የሆነ ትርጉምን ተከትሎ ስህተትን ሳይፈጽም የእነዚህን ሁነቶች ፍጻሜ በዘመን ሊከፋፍልም፣ በየዘመኑ ሊደጋግምም ሆነ የትንቢቱን ፍጻሜ በብዙ ዘመን አራዝሞ ሊጠባበቅ አይችልም። አውሬው አንድ ግለሰብ በመሆኑ፣ ይህም ግለሰብ ኖሮ የታወቀበት ዘመንና ትውልድ ያለው በመሆኑና፣ ያም ዘመን አንዱ የዮሐንስ ዘመን በመሆኑ፣ ስለማንነቱ ከሰብአዊነት አውጥተን፣ ዘመኑንም ከመጀመርያው ከፍለዘመን አሳልፈን በሌላ በየትኛውም ዘመን ላይ የሚከሰት ሌላ ማንኛውም ነገር ልናደርገው አንችልም። ይህ መሰረታዊ መመርያ ብቻውን ስለ አውሬው ማንነትና ተልዕኮውን በተመለከተ በየትኞቹም ጥንታዊና ዘመነኛ የመጽሐፉ ተንታኞች ሁሉ የሚሰነዘረውን  አስተያየት በእጅጉ ውድቅ ያደርገዋል። 


ወንድም ነብዩ በጽሁፉ የጥሙራውያንን (eclecticism) ድምዳሜ አጽንዖት ሰጥቶ ሲነግረን ስለ አውሬው የተነገረው ትንቢት "በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ላይ አላበቃም ፣ የቀደመው ዘንዶና የእኩይ ኅይላት በክርስቶስ መመለስ እስኪፈረድባቸው ድረስ በተለያዩ መራሔ መንግሥታት እንዲሁም በተለያዩ ኅይማኖታዊ፣ ፓለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ሁኔታ ውስጥ የሚገለጥን የትኛውንም ዓይነት ፀረ - ክርስቶስና ፀረ- ክርስቲያን አሠራርን ወካይ ቁጥር ነው" ብለው ማመናቸውን፣  ይህም አሠራር በግለሰብ ሆነ በተቋም ሊገለጥ ይችላል" ሲል ትርጉማቸውንና አቋማቸውን አስተዋውቆናል። በዚህም ጥሙራውያን የክርስቶስን መመለስና ፍርዱን ዮሐንስ በራእዩ "ቶሎ" ሲል ከገለጸው የጊዜ ማእቀፍ አውጥተው እንደ መጻእያን-ወታሪካውያን ሁሉ ገና ወደፊት እንደሚፈጸም የሚጠባበቁ መሆናቸውን ሲያመለክት፣ ጨምሮም "የሠይጣን፣ የራሱ የእኩይና የእኩይ ኅይላት ማብቂያ የክርስቶስ ደግመኛ መመለስ ነው" ብሎ፣ "እኩይና የእኩይ ኅይል ማብቂያ ጊዜ ወደ ፊታችን አለ" በማለት ሃሳቡን ያጸናል። ጥሙራውያን በሚከተሉት ትርጉምም አውሬው 'ሰው አውሬ' በመሆን የተገደበ ብቻ ሳይሆን፣ ይልቁንም ከሰብዓዊ ተፈጥሮ ያለፈና በስርዓተ ማህበር የሚወከል ሌላ 'አውሬ መንግስት'፣ 'አውሬ ኃይማኖት'፣ 'አውሬ ፖለቲካ'፣ 'አውሬ ኢኮኖሚ' ወይም 'አውሬ ማህበራዊ ሁኔታ' እንዳለ ወይም ገና እንደሚገለጥ የሚጠባበቁ መሆናቸውን ያመለክታል። ያየነውን ሁሉ "አውሬው" የሚል ስም እየሰጠን እንዴት እንዘልቀዋለን? በእውነቱ እንዲህ ካለውንስ የሽብር ኃይማኖት በክርስቲያኑ ማሕበረሰብ ውስጥ አሾልኮ ያገባው ማን ነው? በጊዜ መዳቢነት (DespensetionLism) የሚዘወረው የመጻኢነት ነገረ ፍጻሜ (Futurist Eschatology) አይደለምን? እንግዲህ ይህንን የጥሙራውያንን መጽአዊ ድምዳሜ ራእዩ ስለ ፍጻሜው በግልጽ ባቀረበልን የጊዜ ማዕቀፍና በዚያ አውድ ብርሃን ስንመረምረው ከቅዱስ ቃሉ እውነተኛ ምስክርነት ርቆና ልማድ ወለድ ብቻ ሆኖ ቆሞ እናየዋለን። በአለም የሰው ልጆች ታሪክ የሚከሰቱትንና በትንሿ ሬድዮናችን የምንሰማቸውን ፓለቲካዊ፣ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ኃይማኖታዊ ወዘተ ጉዳዮች ይዘን ወደ ቃሉ ትምህርት እየቀረብን ትንቢትን በእነርሱ ልንፈታም ሆነ እነርሱን በቃሉ ልንተረጉም ብንደፍር እንስታለን። ቃሉ ከቃሉ ጋር ተመሳክሮ ብቻ እንጂ፣ በክራንች አይቆምም፤ በራሱ ቆሞ ራሱን ይመሰክራል! አለቀ!! ሌላ ምስክር አያሻውም።



በዚህም ላይ ጥሙራውያን እንዲህ ባሉ የትንቢት ዓይነቶች ላይ ከአንድ ጊዜ በላይ በአለም ታሪክ በተደጋጋሚ ሊፈጸሙ እንደሚችሉ ዘመን ተሻጋሪ ክስተቶች (multiple occurrence) ባህርይ አላቸው ማለታችውም ብዙ አያስኬድም፤ ምክንያቱም  ጽንሰኣሳቡ የድግምግሞሽ ፍጻሜን የሚያቀነቅን ትወራ ነውና። ይህ አይነቱ ትወራ ግን መጽሐፍ ቅዱሳዊውን አውድ የዘለለና፣ ሁለትና ከዚያ በላይ የሆነን የትንቢት ፍጻሜ እንድንጠባበቅ በር መክፈቱ ዋናው ችግሩ ነው። የአንድ ትንቢት ፍጻሜ ሁለቴ ይደገማል ብለን ካመንን፣ በራእይ 13 የተገለጠውም አውሬ በየዘመናቱ በተለያየ የአለም ሁናቴ ተደጋግሞ ሊገለጥ ይችላል ካልን፣ ታዲያ የሚደጋገመው ምነው አውሬው ብቻ? ሦስተኛ፣ ወይም አራተኛ ወይም አምስተኛ የክርስቶስ ምጽአት፣ ወይም ተደጋጋሚ የአለም ፍጻሜ ወዘተ እያልን ከመቀጠል የሚያስቆመን ምንም ነገር አይኖርም። እንዲህ አይነቱ ግራ የተጋባ የነገረ ፍጻሜ እሳቤ የትንቢት ፍጻሜን በተመለከተ በእጅጉ የተጨናበረና ለቃሉ እንግዳ የሆነን ሁሉንም አይነት እብድ ትወራ ወደ ቃሉ ትምህርት ይጋብዛል። መጽሐፍ ቅዱስ ግን በነገረ ፍጻሜ አስተምህሮው የሚያውቀው አንዱን የክርስቶስ መመለስ፣ አንዱን የአለም ፍጻሜ፣ አንዱን የመጨረሻ ትንሳኤና ፍርድ ብቻ ከሆነ፤ እንግዲያውስ በመጨረሻው ዘመን ተገልጦ በክርስቶስ ዳግመኛ ምጽአት በፍርድ እንደሚወገድ መጽሐፍ ቅዱስ የሚናገርለት የራዕይ 13ቱ አውሬም አንድ ብቻ ነው።  ሁለት ወይም ሦስት ወይም አራት የለም። ትንቢትም በአፈጻጸሙ ዘመን ተሻጋሪ፣ አሻሚ ሳይሆን ይልቁንም በዘመኑ፣ በተቀጠረው ጊዜ ሊፈጸም የታመነ ነው። ይህ አይነቱ የዘመን ተሻጋሪ ክስተቶች (multiple occurrence) ትወራ በነገረ ፍጻሜ የራእይ መጽሐፍ ትርጉም የታሪካውያንን (“Historicist”) አቀራረብ ከ "Realized Eschatology" (የብዝሃ ምጽአት) እሳቤ ጋር ያፈጣጠመ ትርጉም ነው። ሁሉም እነዚህ ትወራዎች ጊዜን አመልካች የሆኑትን የራእዩን ቃላትና ሀረጎች አልሞስሙሰው የሚያልፉ ናቸው። ኃላፍያን ግን አጽንዖት ሰጥተው ነገረ ፍጻሜን ሲያስተምሩ፣ የትንቢት ፍጻሜ ተፈጥሮና ባህርይ እሳቤው በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ላይ ለትንቢት ፍጻሜ ከተቀጠረው ጊዜ ጋር የሚስማማ መሆን እንዳለበት አስረግጠው ይመሰክራሉ። ኃላፍያን በነገረ ፍጻሜ አስተምህሮአቸው ለትንቢት ፍጻሜ የተቀጠረውን ጊዜና ጊዜ ጠቋሚ የሆኑትን የትንቢቱን ቃላትና ሀረጎች በተገቢው ደረጃ ይጠቀሙባቸዋል። ለትንቢት ፍጻሜ የተቀጠረው ጊዜ ላይ ትክክለኛ ግንዛቤ ከተያዘ፣ እንግዲያውስ ትንቢቱ በምን አይነት መንገድ እንደሚፈጸም ባህርዩንና ተፈጥሮውን በተመለከተ አንሳሳትም።



5ኛ/ የቁጥሩ ስም በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ላይ በእስያ ለነበሩና ዮሐንስ ለሚጽፍላቸው ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት (ራዕይ 1፥ 4፣ 11) በአግባቡ የሚታወቅ አንድ ግለሰብ መሆን አለበት። እርሱም የሚጽፍላቸውን ራእይ አስተውለው እንዲሰሙና እንዲጠብቁ (ራዕይ 1፥ 3) የአውሬውንም የስሙን ቁጥር እንዲያሰሉ (ራእይ 13፥ 18) ይጠይቃቸዋል። ታዲያ አውሬው እነርሱ ከነበሩበት ዘመንና አውድ ርቆ ያለ፣ ከሰብዓዊ ተፈጥሮ ያለፈ እና በስርዓተ ማህበር የሚወከል፣ በነበሩበትም አውድ ውስጥ ለእነርሱ በግልጽ ሊታወቅ የማይችል አንዳች ጥላ ቢስ ነገር ቢሆን ኖሮ ይህንን ቁጥሩን የማስላትና አውሬውን የመለየት ጥበብ እንዴት ይቻላቸው ነበር?


እንግዲህ እነዚህ በተራ ቁጥር 4 እና 5 የተገለጡ መርሆዎች የአውሬውን ማንነት በትክክል ለመረዳት መሰረታዊ ነጥቦች ናቸው ብዬ አምናለሁ። ከጊዜ አንጻር በስፋት ልሄድባቸው ቢያስቸግረኝም በርዕሰ ጉዳዩ ላይ አጠቃላዩን የመጽሐፉን አውድ ጠብቀው ሊያጠኑ ለሚፈልጉና እርስ በርሱ ከተሳከረ መላ ምት መጠበቅ ለሚወዱ መጠነኛ መንደርደርያና መጽሐፍ ቅዱሳዊ የስነ ፍታቴ ማዕቀፍ ይሰጣቸዋል ብዬም ተስፋ አደርጋለሁ። የአውሬውን ማንነት ጨምሮ በዮሐንስ ራእይ መጽሐፍ ላይ ልንከተለው የሚገባንን ትርጉም በአጠቃላይ መግቢያ ደረጃ በጽሁፍ ለጥፌ philologus66 የፌስ ቡክ ገጼ ላይ ከአመታት በፊት በተከታታይ ያካፈልኩትን ልታዩ ከወደዳችሁ እነሆ ሊንኩ፦


https://www.facebook.com/1889309531297484/posts/2194553230773111/


https://www.facebook.com/1889309531297484/posts/2197517777143323/


https://www.facebook.com/1889309531297484/posts/2211453562416411/


https://www.facebook.com/1889309531297484/posts/2215447248683709/


https://www.facebook.com/1889309531297484/posts/2217465978481836/


https://www.facebook.com/1889309531297484/posts/2218770848351349/


https://www.facebook.com/1889309531297484/posts/2222609127967521/


ቸር ሰንብቱ 

ከክፋት ሁሉ ተጠበቁ 

በክርስቲያን አዕምሮ ሞግቱ።


ግዛቸው ከበደ / ቄስ/



Monday, March 16, 2020

ቅዱስ ጥምቀትን የሕጻናት ጥምቀት መጽሐፍ ቅዱሳዊነት

ወንድም ስሜ ታደሰ "ሕፃናት መጠመቅ የለባቸውም!!!" በሚል ርእስ አቋም ይዞ፣ በተለይ የእኛን የሉተራውያንን የጥምቀት ትምህርትና ልምምድ ለማብጠልጠል፣ የመጥምቃውያንንም ትምህርት ትክክል ለማድረግ  በፌስ ብክ ገጹ ላይ ያቀረበውን ጽሁፍ ከተመለከትሁ ብኋላ እምነታችንን መረር ብዬ ለመከላከል አንድ ነገር ለማለት ሳስብ ቆይቻለሁ። በዚህም መሰረት የዚህች ትንሽ ጽሁፍ አብይ ሃሳብ አንባብያን በሁለቱ ወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል ያለውን የአስተምህሮ ልዩነት እንዲያውቁትና በጥምቀት አንጻር ማንኛችን በቃሉ መሰረት ላይ እንደቆምን፣ የማንኛችን አስተምህሮ ደግሞ ከቃሉ የተፋለሰ እንደሆነ እንዲረዱ ነው እንጂ፣ ፓስተሩ በጽሁፉ ስለ ኦርቶዶክስም ሆነ ስለ ሉተራውያን ያነሳውን ጉዳይ ሁሉ መተቸትና ማረም አይደለም። በአጭሩ ግን የጥምቀትን መሰረተ እምነት አንስቼ በተለይ የሕጻን ጥምቀት መጽሐፍ ቅዱሳዊነት እና አስፈላጊነት ላይ በማተኮር ከዳግመኛ አጥማቂው መጋቢ ስሜ ታደሰ የተሰነዘረውን ተቃውሞ እንደ ሉተራዊ ቄስ እመክታለሁ። የመጋቢ ስሜ ታደሰን ልጥፍ ላላያችሁ እነሆ ሊንኩ   https://m.facebook.com/story.php?story_fbid=3263258677035110&id=100000530293951

የጥምቀት መሰረተ እምነት
ጥምቀት በእግዚአብሔር ፈቃድ የታዘዘና የተመሰረተ (ማቴዎስ 28) በውኃ ውስጥ ያለ የእግዚአብሔር ቃል ወይም ጳውሎስ እንዳለው "በቃሉ መታጠብ" (ኤፌሶን 5፥ 26) ነው እንጂ፤ በሰው የተፈቀደና የተመሰረተ፣ በውኃ ውስጥ ያለ ምትሃት፣ ወይም በውሃ መታጠብ ወይም ሌላ ማንኛውም ነገር አይደለም። ቅዱስ አውግስጢኖስም ከዚህ በመነሳት "ቃሉ በምልክቱ ላይ ይጨመር፣ ውጤቱም ቅዱስ ምሥጢር ይሆናል" ብሎአል። ከዚህ በተለየ ግን የእግዚአብሔር ትእዛዝ የሆነውን ቃሉን በመዘንጋት እግዚአብሔር ኃጢአትን ሊያጥብ የሚችል አንዳች መንፈሳዊ (ምትሃታዊ) ኃይል በውኃ ውስጥ አስቀምጦአል፣ በውኃውም አማካኝነት ኃጢአትን ያጥባል፣ ጥምቀትም ኃጢአትን የሚያጥበው በመለኮታዊ ፈቃድ እርዳታ አማካይነት ነው፣ ይህም ማለት እጥበቱ የሚከናወነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ብቻ እንጂ በቃሉም ሆነ በውኃው አይደለም ብለው የሚያምኑና የሚያስተምሩ ፈጽሞ ተቀባይነት የላቸውም። ምክንያቱም ጥምቀት የተጸለየበት ውኃ፣ የውሃ ጥምቀት፣ ወይም የተደገመበት የአስማት ውኃ ወይም ሌላ ምናቸውም ነገር ሳይሆን ጥምቀት የእግዚአብሔር ትዕዛዝ የሆነው የእግዚአብሔር ቃል የተዋሃደው ውኃ ነው እንጂ ውኃ ብቻ አይደለም። እርሱም የአዲስ ልደት መታጠብ ነውና ጥምቀትንም ጥምቀት የሚያሰኘው ይኸው ነው። 

እደግመዋለሁ፣ ጥምቀት ተራ ውሃ ወይም የውሃ ጥምቀት ሳይሆን በእግዚአብሔር ቃልና ትእዛዝ ዐውድ የተቀመጠና በእነርሱም የተቀደሰ ውሃ ማለት ነው። ውሃው በራሱ ከሌሎች ውሃዎች የበለጠ የከበረ ሆኖ ሳይሆን የእግዚአብሔር ቃልና ትእዛዝ ስለተጨመሩበት መለኮታዊ ውሃ፣ ደግሞም ቅዱስ ጥምቀት እንጂ ሌላ ነገር አይደለም። ውሃው ምልክት ነው፣ ከጥምቀቱ ውሃ ጋር ተዋህዶ ያለውን የእግዚአብሔርን ቃል ቅዱስነት ባለማስተዋል ጥምቀት ቅዱስ በሚል ተቀጥላ መጠራት አይገባውም የሚሉ  አናባፕቲስቶች ግን ስተዋል። ቤተ ክርስቲያን ስታጠምቅ ውሃን ትጠቀማለች፣ በቤተ ክርስቲያን እጅ የሚያጠምቀው እግዚአብሔር ግን በስሙና በቃሉ በተቀደሰው ውሃ በኩል ኃጢአተኛውን በመንፈስ ቅዱስ ያጠምቃል። ስለዚህ ጥምቀት ከሰውና በሰው ሳይሆን ሙሉ በሙሉ ከእግዚአብሔር ነው፣ ከእግዚአብሔር የሆነ ማናቸውም ነገር ደግሞ ቅዱስ ነው፣ ስለዚህም ውሃው ቅዱስ ጥምቀት ነው።

የህጻን ጥምቀት
ይህ "የህጻን ጥምቀት" የሚለው ሐረግም ሆነ "የአዋቂ ጥምቀት" የሚለው ሐረግ በቃሉ ውስጥ ፈጽሞ አይገኝም፤ በታሪካዊው ትምህርተ ጥምቀት አስተንትኖም እንዲህ ያለ የአዋቂ ጥምቀት የሕጻን ጥምቀት የሚባል ቅዱስ ጥምቀትን በእድሜ የመመደብና የመገደብ አስተሳሰብ ፈጽሞ የማይታወቅ ሆኖ ኖሮአል። ዳሩ ግን ሰዎች፣ ግለሰቦች፣ ቤተስቦች ሲጠመቁ በአዲስ ኪዳን ውስጥ በተደጋጋሚ እናነባለን። መቼም የቆርነሌዎስ ቤተሰብ (ሐዋርያት 11፥ 13-14)፣ የልድያ ቤተሰብ (ሐዋርያት 16፥ 15)፣ የፍልጵስዩስ ወህኒ ቤት ጠባቂ ቤተሰብ (ሐዋርያት 16፥ 33)፣ የቀርስጶስም ቤተሰብ (ሐዋርያት 18፥ 8)፣ የእስጢፋኖስ ቤተሰብ (1ቆሮንቶስ 1፥ 16) ሲጠመቁ እዚያ ሕጻናት ልጆች አልነበሩም፣ ቢኖሩም እድሜአችሁ ለአቅመ ጥምቀት አልደረሰም ተብለው ከጥምቀት ተከልክለዋል የሚል ዘገባ ምንም የለም። አናባፕቲስቶች የሕጻናት ጥምቀትን ሲቃወሙ ምንም እንኳ መጽሑፍ ቅዱስ  ቤተሰብ እያለ ቢናገርም ይህ ልጆችን አያካትትም የሚል ውሃ የማያነሳ መከራከርያ ያቀርባሉ። ምናልባት እነዚያ ቤተሰቦች ሕጻናት ልጆች ላይኖሩባቸው ይችላል ቢባል እንኳ፣ ልጆች አልነበሩአቸውም ብሎ በድርቅና መገመትም መገገምም አይቻልም። እነዚህ አምስት የተለያዩ ቤተሰቦች በተለያየ ጊዜና አውድ ሲጠመቁ ከቤተሰቦቻቸው ጋር ተጠመቁ የሚለው ዘገባ ሳይታሰብበት እንዲያው ባጋጣሚ የተጻፈ አይደለም። እንዲያውም ሌሎችም በርካታ ቤተሰቦች እንደተጠመቁ መገመትና ማስተዋል እንችላለን። በእርግጥም እነዚያ ቤተሰቦች ውስጥ ሕጻናት ልጆች እንደነበሩና የጥምቀትም ተካፋዮች እንደነበሩ መገመትና ማሰብ አያስቸግርም። እንዲያውም ቤተሰብ የተሰኘውን ቃል በእስራኤል አውድና ትርጓሜ ያየነው እንደሆነ በአንድ ቤት ውስጥ አብረው የሚኖሩትን እያንዳንዳቸውን የሚያካትት ነው፤ ልጆችም እዚያ የቤተሰብ ቁጥር ውስጥ ይካተታሉ። ስለዚህ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ቤተሰብ የተሰኘው ስብስብ ምን ግዜም ቢሆን ሕጻናት ልጆችንም የሚያካትት እንደሆነ መገንዘብ ይኖርብናል። እግዚአብሔር ከሰዎች ጋር ስላደረጋቸው ቃል ኪዳናትም በመጽሐፍ ቅዱስ ስናነብ ምንግዜም ቢሆን ቃል ኪዳኑ ልጆችን ያላካተተ ሆኖ አያውቅም፤ መላው የእስራኤል ማህበረሰብ ወንዶችን፣ ሴቶችን፣ እና ልጆችን ያካተተ ሲሆን እያንዳንዱም የቃልኪዳኑ ተካፋይ ነው። ወደመርከቡ ገብተው ከጥፋት ውሃ የዳኑት ኖህና ቤተሰቡ ናቸው (ዘፍጥረት 7፥ 1)፤ አብርሃምና መላው ቤተሰቡ ግዝረትን ተቀብለዋል፣ ይስሃቅ ደግሞ በተለይ ገና የስምንት ቀን ሕጻን እያለ የዚህ ኪዳን ተካፋይ ሆኖአል (ዘፍጥረት 17፥ 23፤ 21፥ 4)። በርካታ ምሳሌዎችን ማቅረብ አያስቸግረንም፤ መጽሐፍ ቅዱስ ግን ቤተሰብ በሚልበት ጊዜ ሕጻናት እዚያ ውስጥ አይደመሩም የሚለው መከራከርያ ረጅም ርቀት አያስኬድም።

የህጻናትን ጥምቀት ትክክለኛነትና ተገቢነት መከራከርያ በኖረው የክርስቲያን አስተምህሮና ልምምድ ላይ ብንመሰርተው እንኳ ይህንን ያህል ዘመን በቤተክርስቲያን ውስጥ ያለጥያቄ ብሎም በማንም ሳይጠረጠር መኖሩ አስገራሚ ይሆንብናል። የሕጻናት ጥምቀት ከቤተክርስቲያን ጅማሬ አንስቶ ሲለመድ የኖረ፣ ከሐዋርያቱ ጊዜ አንስቶ ያልተቋረጠ፣ እኛም እስካለንበት ዘመን ድረስ ቦታና ጊዜ ሳይወስነው የዘለቀ፣ ክርስትናም በተስፋፋባቸው ሃገሮች በየዘመናቱ ሁሉ በመላው አለም በክርስቲያኖች ዘንድ ቅቡልነት ያለው ሉል አቀፋዊ እምነት፣ ልምምድና ወግ ነው።  ስለሆነም ይህ የቤተ ክርስቲያን የአንድነቷ ወግና ልማድ የሆነው ምስክርነት ከራሱ በላይ ወደ ቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነት አድልቶ ያመላክታል። ስለ ሕጻናት ጥምቀት ያለን አቋምና ውሳኔም በቅዱሳት መጻህፍት ምስክርነት ላይ የተመሰረተ ደግሞ ነው እንጂ በወግና ልማድ ላይ የተንጠለጠለ ብቻ አይደለም። በድነትና በጥምቀት ጉዳይ እድሜን እንደ ቅድመ ሁኔታ የሚያየው የአናባፕቲስቶች ትምህርት ግን ትንታኔውን አድጌአለሁ አገናዝባለሁም ለሚል የሰው አእምሮ እንዲመች አድርጎ ከማቅረብ በቀር፣ መሰረቱን በእግዚአብሔር ቃልም ሆነ በታሪካዊው የስነ መለኮት አውድ ውስጥ ማግኘት የሚቸግረው እንደሆነ ግልጽ ነው።

ይልቁንም መጽሐፍ ቅዱስ በድነት ጉዳይ፣ አይደለም የእድሜ ልዩነት ይቅርና በምንም የማይታረቀውን የአይሁድ አህዛብ ልዩነት እንኳ የሻረ ክርስትናን ሰጥቶን እያለ በሰውና በሰው መካከል አድልዎ ለማድረግ፣ ህጻናት ሰዎችንም ከእግዚአብሔር ጸጋ እንዲዘገዩ ለማድረግ በነፍሳት ላይ እኛን ማን ሾሞናል? እንደ ሉተራውያን የወንጌል አማኝ በኦግስቡርግ የእምነት መግለጫ በግልጽ እንደተብራራው በጥምቀት  በኩል ለኃጢአተኛ ሰው የድነት ጸጋ የሚሰጥ በመሆኑ፣ ሕጻናትም ኃጢአተኛ ሰዎች በመሆናቸው እንደሌሎች ሰዎች ሁሉ ተጠምቀው የእግዚአብሔርን ጸጋ እንዲቀበሉ መፍቀድ እንዳለብን፣ በዚህም ጥምቀት አማካኝነት በክርስቶስ በኩል ለእግዚአብሔር አደራ የሚሰጡና እርሱን ደስ ለማሰኘት የሚችሉ የተወደዱ ልጆቹ ሊሆኑ ከእርሱ እንደሚወለዱ እናምናለን እናስተምራለንም።

ይህንን ስናምንና ስናስተምርም የዳግመኛ ጥምቀት አስተምህሮና አስተማሪዎች "ህጻናትን ማጥመቅ ልክ አይደለም፣ ህጻናት ያለጥምቀት ሊድኑ ይችላሉ" ብለው ፍጹም ተቀባይነት የሌለውን ስህተት በአማኞች መካከል አሾልከው እያስገቡ የብዙ ያልተማሩ ምዕመናንን ህይወት ስለሚያቃውሱ በእኛ ዘንድ ፈጽሞ የተወገዙ ናቸው። በዚህም መሰረት ያልተጠመቁ ሕጻናት በእግዚአብሔር ፊት ኃጢአተኞች አይደሉም፣ ይልቁን ግን (በተፈጥሮ) ጻድቃንና የዋሆች ናቸው፣ በየዋህነታቸውም አመክንዮአቸውን ሙሉ በሙሉ ወደሚጠቀሙበት ደረጃ ስላልደረሱ ያለጥምቀት ይድናሉ፣ ስለዚህም ጥምቀት ለሕጻናት አስፈላጊ አይደለም፣ ወይም ሕጻናት በአመክንዮ ወደመጠመቅና በራሳቸው ወስነው እምነታቸውን ወደ መግለጥ የእድሜ ደረጃ እስኪደርሱ ድረስ መጠመቅ አይገባቸውም የሚለው አስተሳሰብ፣ የእግዚአብሔርን ጸጋ የሚያሳንስ፣ በእግዚአብሔር ጸጋም ብቻ ሳይሆን ድህነትን በሰው የማገናዘብ ችሎታና በማወቅ አቅሙ ላይ የሚመሰርት በመሆኑ፣ እንዲህ ያለውን የትብብር ድነት ፈጽሞ የማንታገሰውና በቤተ ክርስቲያናችን ተቀባይነት የሌለው ነው። 

አናባፕቲስቶችና ልምምዳቸውን የሚከተሉ ሌሎች መጥምቃውያን ሁሉ በትንሹ ከሦስት እስከ ስድስት ወር የሚቆይ "የጥምቀት ትምህርት" ካላስተማሩ በቀር አያጠምቁም፤ መጽሐፍ ቅዱስ ግን ጥምቀትን በአጣዳፊነቱ እያመለከተ ያመኑት ወዲያውኑ እንደተጠመቁ ያስተምረናል እንጂ ማንንም በጥምቀት ትምህርት ስም ከጥምቀት ሲያዘገይ አናይም። ሕጻናትንም በእድሜ ብስለት ለአቅመ ማገናዘብ እስኪደርሱ በማለት ከጥምቀት አናዘገይም። ክርስትናን ሲቀበል "ወዲያውም …...፤ ተነሥቶ ተጠመቀ፥" የተባለለት ሳውል እንዴት ባለ አጣዳፊ ትእዛዝ እንዲጠመቅ እንደተነገረው ስሙ "አሁንስ ለምን ትዘገያለህ? ተነሣና ስሙን እየጠራህ ተጠመቅ ከኃጢአትህም ታጠብ።"

ህጻናት በተፈጥሮ ጻድቃንና የዋሆች ናቸው የሚለው ይህ አስተሳሰብ መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ የሚያስተምረውን መላውን የውርስ ኃጢአት ትምህርትና ከእርሱም ጋር የተያያዘውን ማንኛውንም ነገር ገደል የሚከት አስተሳሰብ ነው። የእምነትንም ተፈጥሮ የሚያሳስት የአስተምህሮ ስህተት ነው። ማንም ቢሆን ላለማመን እንጂ ለእምነት የሚመች ወይም የቀረበ ተፈጥሮ የለውም። ማመን የሚችል የሚሆንለት ሕጻን የሌለውን ያህል ማመን የሚችል የሚሆንለት አዋቂ የለምና። እምነት ለሁሉ አይሆንም፣ "ሁሉ ተሳስተዋል በአንድነትም የማይጠቅሙ ሆነዋል፤ ጻድቅ የለም አንድ ስንኳ፣ እግዚአብሔርንም የሚፈልግ ማንም የለም" የተባለው ያለ እድሜ ልዩነት ለሁሉ ነው። ኃጢአተኝነት እና መዘዙ ሁሉ የሰው ዘር እጣ ክፍል ነው። ኃጢአተኝነት አስቀድሞ የተደረገ ሳይሆን የተወረሰ ነው። ወላጆች ሞት የሚገባቸው ኃጢአተኛ እፉኝቶች ከሆኑ ልጆችም ርህራሄ የማይደረግላቸው  ኃጢአተኞች፣ እፉኝት የእፉኝት ልጆች ናቸው። እግዚአብሔር ብቻ ሊያድናቸው ሊለውጣቸውም ይችላል እንጂ ከጥምቀት በቀር የሚድኑበት፣ ዳግመኛም ተወልደው የሚለወጡበት ሌላ መንገድ የለም። የሚድኑትም ከውርስ ኃጢአትና ያንን ኃጢአት ተሸርጦ ሊገድላቸው ከሚያደባ የዲያብሎስ ወጥመድ ነው። ጥምቀት ሕፃኑን በሰይጣን ከተያዘበት፣ የኃጢአትና የቁጣ ልጅ ከሆነበት ጽኑ እስራት ይፈታውና፣ ፈጽሞ የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎ ያትመዋል፤ እንጂ ኃይማኖታዊ የውሃ ስርአት (የውሃ ጥምቀት) የሚፈጸምለት አይደለም።  
የውርስ ኃጢአትና መዘዙን የሚያቃልሉ ሰዎች ግን የጥምቀትን ዋጋ ያቃልላሉ። የሕጻን ጥምቀት በእጅጉ የውርስ ኃጢአትን እና መዘዙን ከማስወገድ ጋር የተቆራኘ ነው። የሕጻናትን ጥምቀት የማይቀበሉ ቡድኖች ግን የውርስ ኃጢአትን እውነታ በመካድ ከጸኑ ጴላግዮሳውያንና ማኒቄያውያን ስህተት ጋር ይደመራሉ። አርሜንያኒዝምም የውርስ ኃጢአትን እውነታ በመካድ የዚህ ስህተት አባቱ ነው። አናባፕቲስቶችም የውርስ ኃጢአትን እውነታ "አይኔን ግንባር ያርገው" በሚል ክህደት ዘመኑ ያፈራቸው አርሜንያን ወይም ከፊል ጴላግዮሳውያን ሆነውብናል።

የአምላክን ስም ጠርተን ሕጻኑን በቅዱስ ውሃ ስናጠምቅ ክፉውንና የእድሜ ልክ ጠላት የሆነውን ዲያብሎስን በመቃወም፣ እንቦቀቅላውን ሕፃን በአምላክ ስም ከእጁ እንናጠቀዋለን። የውርስ ኃጢአት፣ እርሱም የአዳም ኃጢአት ሞትን ለሰው ሁሉ ያደረሰ መዘዘኛ ውድቀት ሲሆን፣ ምንም የማያውቁ ሕፃናትም ቢሆኑ እንኳ ሰለባው ናቸው። ታዲያ ይህንን የሞት ፍርድ በአንገቱ ላይ ተጠምጥሞ ያለበትን ሕጻን እንዲድን ምን ያህል ዘመን እንታገሳለን? ሕፃናት ምንም ክፋት የሌለባቸው፣ በተፈጥሮም ንጹህና ጻድቃን ናቸው፣ ያለጥምቀትም ይድናሉ አትበሉ። "እነሆ፥ በዓመፃ ተፀነስሁ፥ እናቴም በኃጢአት ወለደችኝ።" የሚለው የዳዊት ምስክርነት ለማንኛውም ለተጸነሰና ለተወለደ ሁሉ ይሰራል። ማናችንም ብንሆን ከአባታችን አዳም ኃጢአት የተነሳ ወደ እግዚአብሔር ያለን አቋቋማችን የጠላትነት አቋቋም ነው። በኃጢአት መወለድ ማለት በአመጸኛው የሰው ዘር ትውልድ ውስጥ መወለድ ማለት ነው። ይህም አዳም እግዚአብሔርን በመቃወም ያቋቋመውና የመሰረተው የጨለማ መንግስት ክፍል ወይም አካል የመሆን ጉዳይ ነው። የአዳም ልጆች እንደመሆናቸው መጠን የሰው ዘር ሁሉ፣ ህፃናትም ቢሆኑ ያለልዩነት የዚያ ኃጢአት ተካፋይና አድራጊ በመሆን እግዚአብሔርን እምቢ ብሎ ለመግፋት በልደታቸው የመረጡ ናቸው። በዚህ አለም የሚወለደው ሕፃን ሁሉ የእግዚአብሔር ቁጣ የሚገባው የእግዚአብሔር ጠላት ሆኖ የተወለደ ነው። እግዚአብሔር ግን በጥምቀት በኩል ለእርቅ እጁን ዘርግቶለታል።

ይህ አለም አቀፋዊ ኃጢአተኝነትና ለክፋት የተሰጠ ዝንባሌ ሥነ ሰብን ባጠኑ አለማዊ ጠበብት እንኳ የሚታመንና ተቀባይነት ያለው ነው። እነዚህም ጠበብት በጥናቶቻቸው ሰነድ ላይ እንዳሰፈሩት፣ ክፋት ገና ጡት ባልጣሉ ሕፃናት ዘንድ እንኳ ሊገኝ እንደሚችል ያመለክታሉ። ጥናቶቹንም ካደረጉ ማዕከላት መካከል አንዱ እንዳረጋገጠው፣ ወንጀል የሚስፋፋው ከሰው ተፈጥሮአዊ ባህርይና ዝንባሌ እየተወለደ ገና ከሕፃንነት ወራት ጀምሮ አብሮ በሚያድግና በሚኖር ተፈጥሮ እንደሆነ ያሳያል።

ሁሉም ሕጻን ሕይወትን የሚጀምረው በትንሽ አረመኔነት ወይም ጭካኔ ነው። ፈጽሞ ራስ ወዳድና ራስ ተኮር የሆነም ፍጥረት ነው። የሚፈልገውን ማናቸውንም ነገር፣ ጡጦውን ይሁን፣ የእናቱን ቀልብና ልብታ ይሁን፣ አጫዋች አሻንጉሊቱን ይሁን፣ የእንግዳና የሰው ዕቃ ሰአቱን ወይም የሞባይል ስልኩን ይሁን፣ የሚፈልገውን ማንኛውንም ነገር የሚፈልገው በሚፈልግበት ሰአት ነው። እነዚህን ፍላጎቶቹን በተከለከለ ጊዜ በዚያ ደካማና ምስኪን አቅመ ቢስነቱ ውስጥ ሆኖም እንኳ ገዳይ ሊሆን በሚችልበት ዝንባሌ በእጅጉ ተናዶና ተቆጥቶ ይመለከታል። ሕጻን መንጻት የሚያስፈልገው የቆሸሸ ሰው ነው፤ ምንም ስነ ምግባር የለውም፣ እውቀት የለውም፣ ጥበብ የለውም። ይህ ማለት እንደዚህ የሆኑት አንዳንድ ልጆች ብቻ ሳይሆኑ ሁሉም ልጆች የሚወለዱት ዱርዬና ወሮበላ ሆነው ነው። አጥኝ ጠበብቶቹ እንደደረሱበት ድምዳሜ አንድ ሕፃን ራስ ተኮር በሆነው የልጅነት ዓለሙ ውስጥ እንዲቀጥል ቢፈቀድለትና ቢተው፣ ፍላጎቶቹንም በራሱ መንገድ እንዲያሟላ ለዚያ ችኩል ስሜቱ ፈቃድ ቢሰጠው፣ ማንኛውም ሕጻን ወንጀለኛ፣ ሌባ፣  ነፍሰ ገዳይ፣ አስገድዶ ደፋሪ ሆኖ ያድጋል። 

ስለውርስ ኃጢአት ወይም ስለመጀመርያው ኃጢአት በእግዚአብሔር ቃል የሰፈረው ትምህርትም ከዚህ ጋር ይስማማል። ኃጢአት ወደ ሰው ሁሉ የደረሰው አዳም በግሉ በሰራው ኃጢአት አማካኝነት ነው። የሰው ልጆችም በእግዚአብሔር ፊት ሞት የሚገባቸው ኃጢአተኞች የሆኑት በውክልና በተሰራ ኃጢአት ነው። አዳም የሁላችን ፌደራል ሄድ ነውና። በዚህ ምክንያት የሰዎች ልጆች ገና ሲጸነሱና ሲወለዱ  ጀምሮ ከእግዚአብሔር የተለዩ ጠላቶቹ ሆነው ተወልደዋል። ሁላችንም ሞት የሚገባን ርህራሄም የማይገባን ኃጢአተኞች ሆነን የተወለድን ነን። ለዚህ ነው ሕጻን መጠመቅ ያለበት። ሕጻን መጠመቅ የለበትም የሚለው እቋም በ"ወንጌላውያን" መጥምቃውያን ዘንድ በወጉ ያልታሰበበት አደገኛ ውሳኔ ነው። ሕጻን መጠመቅ የለበትም ማለት ሊገድለው በአንገቱ ላይ የተጠመጠመበት የኃጢአት ሞት ይግደለው ብሎ እንደመፍረድ ነው፤ ልክ የተጸነሰና በማህጸን ያለ ልጅ በውርጃ እንዲጨነግፍ የመፍቀድን ያህል የህጻንን ጥምቀት መከልከል ንስሃን የሚጠይቅ አደገኛ ውሳኔ ነው።

የክርስቲያኖች ልጆችም ቢሆኑ ከክርስቲያን አማኞች ወላጆች የተወለዱ በመሆናቸው ያለ ጥምቀትና፣ ወይም ከጥምቀት በፊትም ቢሆን ቅዱሳንና የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው በሚል አስተሳሰብ የዳግመኛ ጥምቀት አስተምህሮን ለመደገፍና የሕጻን ጥምቀትን ውድቅ ለማድረግ የሚቀርበው መከራከርያ በራሱ ዋጋ የሌለውና፣ ክርስትናን ሊሰጠን የተከፈለውን የክርስቶስን ሞት የሚያቃልል የስድብ ትምህርት ነው። ጋራዥ የተወለደ ሁሉ መካኒክ አይሆንም፣ መካኒክ ሊደረግ ግን ይችላል፤ እንዲሁ በክርስቲያን ቤት የተወለደ ሁሉ ክርስቲያን አይሆንም፣ ክርስቲያን ግን ሊደረግ ይችላል። ክርስትናን ባዮሎጂካል ለማድረግ አታስቡ፣ ክርስትና መንፈሳዊ ነው። አንድ ሕጻን ክርስቲያን ሊደረግ የሚችልበት መንፈሳዊ ልደትን ሊሰጠው ከሚችል ጥምቀት በቀር ሌላ ምንም መንገድም እድልም የለም።  ማንም ሰው ማንንም ክርስቲያን ሊያደርገው አይችልም፣ እግዚአብሔር ግን ብቻውን ይችላል፤ እግዚአብሔር ይህንን የሚያደርገው ኃጢአትን በጥምቀት እያጠበ ነው። ጥምቀትም ያድናል ስንል ስርአቱ ያድናል እያልን ሳይሆን ክርስቶስ ለአዲስ ልደት ባዘዘው ጥምቀት በኩል ኃጢአታችንን እያጠበ ያድናል ማለታችን ነው እንጂ ሌላ አይደለም። ስለዚህ ጥምቀት ኃይማኖተኛ ሰዎች የሚፈጽሙት ኃይማኖታዊ ተግባር ሳይሆን፣ እግዚአብሔር ሊመረመር በማይችል አደራረጉ ኃጢአትን እያጠበ አዲስ ልደትን የሚሰጥበት የጸጋ መንገድ ነው። የክርስቲያን ጥምቀት በተገለጠበት በየትኛውም የአዲስ ኪዳን ምንባብ አብሮት ያለውን ልዕለ ተፈጥሮአዊ ተግባር ባለማስተዋል ነገሩን የስርዓት አፈጻጸም ጉዳይ ብቻ አድርጎ መውሰድ ካለመማርና የጥምቀትን ትርጉም ካለመረዳት የሚመጣ ስህተት ነው።

በመሆኑም በክርስቶስ የተገኘው ለሰዎች ሁሉ (ቲቶ 2፥ 11) የሆነው የቤዛነት ሥጦታ እነርሱንም የሚመለከት ነው እንጂ ነጥሎ ያገለላቸው ስላልሆነ ሕጻናትን ማጥመቅ ይገባናል፤ ይህንን የእግዚአብሔርን ስጦታ ወደ ሕጻናቱ እንዳይደርስ የምትከላከል ቤተክርስቲያን ደግሞ የታላቁ ተልዕኮ (ማቴ 28፥ 19) እንቅፋት በመሆን የእግዚአብሔርን ፈቃድ ትቃወማለች። ምክንያቱም ጥምቀት በእምነት በኩል ከክርስቶስ ጋር በመተባበር በአምላክ ስም አጠራር፣ በአብ፣ በወልድ፣ በመንፈስ ቅዱስ ስም ወደ ክርስቲያኑ ምኅበረሰብ የምንቀላቀልበት የመጀመርያ እርምጃ ነው። እግዚአብሔር በሉአላዊ ፍቃዱ ሰውን ሲገናኘው እከሌ ትልቅ እከሌ ደግሞ ትንሽ ብሎ አያደላም፤ በበርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት አይደለም የተወለዱ ሕጻናት ይቅርና ገና በእናታቸው ማህጸን እያሉ መለኮት በሉአላዊነቱ የጎበኛቸውን መጥቀስ ይቻላል። በመሆኑም ማንም ያልተጠመቀ መጠመቅ ይገባዋል አለበለዚያ ድነት በሌላ በማናቸውም መንገድ አይታሰብም። ስለዚህ ጥምቀት በአምላክ ስም የሚከናወን የአምላክ ትዕዛዝ እንጂ በዋዛ የሚታለፍ የጨዋታ ነገር አይደለም። በእግዚአብሔር ስም መጠመቅ ደግሞ በሰዎች መጠመቅ ሳይሆን በራሱ በእግዚአብሔር መጠመቅ ነው። መጠመቅም በሰዎችም እጅ የሚከናወን የእግዚአብሔር ሥራ ነው። 

በታሪክ፣ እንግዳው የአና ባፕቲዝም አስተሳሰብ በክርስቲያኖች መካከል ሳያቆጠቁጥ በፊት፣ ቤተክርስቲያን በዘመኗ ሁሉ ያለ ጥያቄና፣ ደግሞም ለአፍታ እንኳ ሳትጠራጠር ሕጻናቶችዋን እያጠመቀች ወደ ቅዱሳን ማህበር ስትቀበል ኖራለች።  ከጊዜ በኋላ የመጣው መጤ የእምነት ቡድን ግን ጥምቀትን በሚያቃልል ድምጸት፣ መጠመቅ ውጫዊ ነገር እንደሆነና፣ ውጫዊ ነገሮች ደግሞ ምንም እንደማይጠቅሙ በጩኸት እየተናገረ ለቤተክርስቲያን መከፋፈል ምክንያት ሆኖአል። ነገር ግን ጥምቀት ምንም ያህል ውጫዊ ምልክት ተደርጎ ቢታይም ልዩነት አያመጣም፣ ምክንያቱም ጥምቀትን ያቋቋመልንን፣ የመሰረተልንን እና ያረጋገጠልንን የእግዚአብሔርን ስም የተሸከመው የእግዚአብሔር ቃልና ትእዛዝ ጸንቶ ይኖራልና። እግዚአብሔር የመሰረተውና ያዘዘው ነገር ጥቅም የሌለው ከንቱ ነገር ሊሆን አይችልም። እግዚአብሔር በክርስቶስ የሻራቸው በርካታ የብሉይ ኪዳን የመንጻት ስርአቶች የመኖራቸውን ያህል ጥምቀት ደግሞ የአዲስ ልደት መታጠብ ሆኖ እግዚአብሔር  በክርስቶስ ሞትና ትንሳኤ ለዘላለም ያጸናው አገልግሎትና የጸጋ ስራ ነው። ልንፈጽማቸው የሚያስቸግሩንን ከባባድ የሆኑትን የብሉይ ኪዳን ስርአቶች አስቀርቶልን ልንፈጽመው የምንችለውን ቀላል "የጥምቀት ስርአት" እንደሰጠን የሚመስላቸው ቃሉን በወጉ ያልተማሩ አላዋቂ ሳሚ ሆነው ያስቸግራሉ። ጥምቀት የአፈጻጸም ስነ ሥርአት ሊኖረው ይችላል፣ ኃይማኖታዊ ስርአት ግን አይደለም፤ ጥምቀትን በስርአት ደረጃ አዋርዶ መረዳት በእውነት አላዋቂነት ነው።
 
የክርስቲያን ጥምቀት የህግ ስራ ሳይሆን የእምነትና የጸጋ ስራ፣ የሰው ስራ ሳይሆን የእግዚአብሔር ስራ የሆነ መለኮታዊ አገልግሎት ነው። ጥምቀት እንደዚያ መሆኑን የማያውቁ ወይም የማይቀበሉ ቡድኖች ሰው ያለጥምቀትም ቢሆን ክርስቲያን ሊሆን እንደሚችል ይመስላቸዋል፤ ይህ ግን ስህተት ነው። ያለጥምቀት ክርስቲያን መሆን አይቻልም ማለት  ያለእምነት መዳን አይቻልም ማለት ነው። በእምነትና በመጠመቅ መካከል ያለው አንድነት እንደ አንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ያለ አንድነት ሆኖ እንጂ፣ እንደ ደረጃና ቅደም ተከተል መታየት የለበትም። በአብዛኛው ቃሉን ለማሳከር የሚፈልጉ ሰዎች በማርቆስ የተዘገበውን የታላቁን ተልዕኮ ትዕዛዝ እየጠቀሱ እምነትን ቀዳሚ ጥምቀትን ተከታይ ለማድረግ ሲሞክሩ ይስተዋላሉ፤ ታላቁ ተልዕኮ ግን በማቴዎስም ተዘግቦልናል፣ ማቴዎስ ጥምቀትን አስቀድሞ እምነትን ወይም መማርን አስከትሎ መጻፉን አያስተውሉም። ያም ሆኖ ግን የሁለቱ ወንጌላውያን ትኩረት ልንከተለው የሚገባንን ቅደም ተከተል ማስቀመጥ ሳይሆን፣ ይልቁንም እምነትና ጥምቀት ወይም ጥምቀትና እምነት እንደ አንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ የማይነጣጠሉ ጉዳዮች መሆናቸውን ማጽናት ነው። እምነት ስንልም የተጻፈውን የእግዚአብሔር ቃል ማመን ማለታችን እንጂ የማመን ብቃትና ችሎታ ማለታችን አይደለም። 

ወደር የማይገኝለትን የእግዚአብሔርን የጸጋውን ባለጠግነት እያሳየ አድናቆትን ከሚሞላኝ መለኮታዊ አገልግሎት መካከል አንዱና ዋናው የሕጻናት ጥምቀት ነው። ሁልጊዜም "ምስጋና ስለ ጥምቀትህ" እያለ ያዘምረኛል። በጸጋው ብቻ እንዲሁ አድኖኛል እንጂ የእኔን የማመን ችሎታና ብቃት አይከታተልም። እኔ ማመን ባልችል እንኳ ቃሉ የታመነ ሆኖ ይኖራል። ስለዚህ ዐብዩን ትኩረትም በተጠመቂው ግለሰብ፣  ህጻን ይሁን አዋቂ፣ በማመን አለማመኑ ላይ ማድረግ አያስፈልግም። ይልቁንም ትኩረታችን ጥምቀቱ ዋጋ ያለው እንዲሆን በሚያደርገው በእግዚአብሔር ቃልና ትእዛዝ ላይ ጥገኛና ተደጋፊ ሆኖ በመፈጸሙ ላይ ነው እንጂ። ጥምቀትን የሚፈጥረው የኔ ማመን አይደለም፣ እምነት ጥምቀትን ይቀበላል እንጂ ፈጣሪው አይደለምና። ጥምቀትም የተያያዘው ከእምነታችን ጋር ወይም ከአቅመ ማገናዘባችን ጋር ሳይሆን ጸጋን ከተሞላው ከቃሉ ጋር ብቻ ነውና። የእግዚአብሔርን የጸጋ አሰራር ለአእምሮአችን በሚመቸንና እኛን በሚመጥነን የሰብዓዊ ማገናዘብ ልክ ማለትም በውድቀታችን ደረጃ ልንወስነው አንድፈር። እግዚአብሔር በሰጭነቱ የጸጋው ክብር የሚመሰገንበትን፣ ጽድቅንም በመፈጸም ረገድ የሰው ድርሻና ክፍል የሌለበትን ቅዱስ ጥምቀት ሰጥቶናል፤ የማይሰራውን ኃጢአተኛም ሊያድነው የሚችለው ሰራተኛ የሆነው የጸጋው ታላቅነት ብቻ ነው። ቅዱስ ጥምቀትን የምንረዳው በዚያ መንገድ ነው።

እደግመዋለሁ! ሕጻናት ባያምኑ እንኳ፣ (አያምኑም ለማለት ግን አልደፍርም፣ ምክንያቱም ማቴዎስ 18፥6፤ ማርቆስ 9፥42፤ መዝሙር 22፥9 ወዘተ፣ እነዚህን የመሳሰሉ ምንባባት የሕጻናትን እምነት ይመሰክራሉ) በእግዚአብሔር ስም የተቀበሉት ጥምቀት ትክክለኛ ስለሆነ፤ ካደጉም በኋላ ቢሆን ማንም ዳግመኛ እንዲያጠምቃቸው አያስፈልጋቸውም፤ የምን "ጣመኝ ድገመኝ" ነው? የጥምቀት ኪዳን እንደሆነ ለዘላለም ይኖራል። እኛ ግን ከጸጋው ወድቀን ኃጢአትን ብንሰራ መልሰን በድል የምንነሳበትና የምንታደስበት ወደ ጥምቀት ኪዳናችንም የምንመለስበት የንስሃ እድል ተሰጥቶናል እንጂ እንደገና ውሃ ውስጥ መግባት አያስፈልገንም። መቶ ጊዜ በውሃ ውስጥ ብንዘፈዘፍም ከአንዲት ጥምቀት የበለጠ ሊሆንልን አይችልም። ይህንን ባለመረዳት ከእናት ቤተክርስቲያናቸው እየተሰረቁ ኃጢአትን እንደሚፈጽሙ ያህል በግላጭ ሳይሆን ተሸሽገው በመሄድ በዳግመኛ አጥማቂዎች የእምነት ተቋማት ጥምቀታቸውን የሚደግሙ በርካቶች የመኖራቸውን ያህል፣ በዚያው ልክ ከዳግመኛ አጥማቂዎቹ ዘንድ ወደ እናት ቤተክርስቲያናችን እየቀረቡ ለህጻናቶቻቸው የጥምቀት ጥያቄ የሚያቀርቡ ወላጆችም ቁጥር ቀላል አይደለም።

በተነሳው ርዕሰ ጉዳይ ላይ ከዚህ በበረታ መልኩ ምካቴ ሊጽፉ የሚቻላቸው ከደርዘን በላይ የሆኑ ኢትዮጵያውያን የሉተራን አማኞች መምህራን እንዳሉ አውቃለሁ። እነርሱ ዝም ስላሉና የአዋቂ ጥምቀት አቀንቃኞች "የጣመኝ ድገመኝ" ትምህርታቸውን ስላስጮሁት የጮኸ ሁሉ እውነት ነው ማለት አይቻልም። በህጻናት ጥምቀት ለምታምኑ ሉተራውያን የወንጌል አማኞች ይህች ትንሽ ጽሁፍ እምነታችንን ከአናባፕቲስቶች ጥቃት ለመከላከል መንደርደርያ ልትሆናችሁ ስለምትችል ትጠቀሙባት ዘንድ እየመከርሁ፣ ለሁሉ እንዲደርስ ሼር፣ ላይክ እያደረጋችሁ ወዳጆቻችሁን ሁሉ ታግ አድርጉ።

ይህችን አጭር ምካቴ ሳዘጋጅ ግብአት ሆነው ያገዙኝን፦ The Book of Concord, The Confessions of the Evangelical Lutheran Church; The Theology of Martin Luther; Salvation In Christ, A Lutheran- Orthodox Dialogue; እንዲሁም The Bondage of the Will; የተሰኙትን መጻህፍት ተጠቅሜአለሁ። መምህር ነብዩ ኢሳይያስም በሃሳብ አግዞኛል።
ግዛቸው ከበደ /ቄስ/

Saturday, January 11, 2020

ጊዜ ጠቋሚ የሆኑ የንባብ ክፍሎች ለፕሪቴሪዝም

ጊዜ ጠቋሚ የሆኑ የንባብ ክፍሎች ለፕሪቴሪዝም
የመጀመርያው ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖች ኢየሱስ በእነርሱ የህይወት ዘመን ተመልሶ እንደሚመጣ የነበራቸው መጠባበቅና፣ ይህንን አይነት መጠባበቅ እንዴት ሊኖራቸው እንደቻለ፣ ከየትስ እንዳገኙት፤ ማንንም ቢሆን፣ ከሃዲውንም ሆነ አማንያኑን ሁልጊዜ ሲያስገርም የሚኖር ጉዳይ ነው። በእኔ ግምጋሜ ይህ የዳግመኛ ምጽአቱ ተስፋ  ለመጀመርያው ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖች በልዩነት  የተሰጠ መሆኑን ማየት የቻሉት በአመዛኙ ከአማንያኑ ይልቅ ከሃድያኑ ሆነው አግኝቻቸዋለሁ። ይህም የከሃድያኑ እይታ ትንቢቱ በተያዘለት የጊዜ ማእቀፍ ውስጥ ያልተፈጸመ መሆኑን በማራገብ ክርስትናችንን ውሸት ለማድረግ በአማንያኑ ላይ የሚሰነዘር ብርቱ የማጥቂያ መሳርያ ሆኗቸዋል። አማንያኑም ቢሆኑ ይህንን ጥቃት የሚመክቱበትንና በከሃድያኑ ትችት ፊት በጽናት ቆመው እምነታቸውን የሚከላከሉበትን አቅም ከዚያው እድሜ ጠገብ ከሆነው ልማዳዊ አመለካከታቸው ስለሚፈልጉት ሊቋቋሙት አልቻሉም። በአመለካከታችን የመጻኢነትን ነገረ ፍጻሜ ሙጭጭ ባልን ቁጥር ክፉኛ የሚያገኘን የከሃድያኑ በትር ነው።

መፍትሄው ግን ያ ለጥንት ቤተክርስቲያን ሰዎች ክርስቶስ በገዛ ትውልዳቸው ተመልሶ እንደሚመጣ በቃል የተነገራቸውም ሆነ በመልእክት የተጻፈላቸው ቃል በመንፈስ ቅዱስ የተመራ ንግግርና ጽሁፍ የሆነውን ያህል፤ እንዲሁ እነዚያው የጥንት ክርስቲያኖች የጌታን ቀን ይናፍቁና ይጠባበቁ የነበረበት ያ ተስፋ፣ እምነትና ናፍቆት በመንፈስ ቅዱስ የተመራ እንደነበር አውቀን፣ ተስፋውም ለእነርሱ የተሰጠና የተፈጸመ መሆኑን መቀበል ብቻ ነው። ለእምነት ቤተሰብ ይህንን ለመቀበል ምንም ውጫዊ ማስረጃ ማቅረብ ሳያስፈልገን (ደርዘን ውጫዊ ማስረጃ ሳይኖረን ቀርቶ አይደለም) በቅዱስ ቃሉ ብቻ መሞገት እንችላለን።

ክርስቶስ ተመልሶ የሚመጣው "መቼ" እንደሆነ ክርስቶስ ራሱና ሐዋርያቱ ተናግረው ነበር ወይ? አዎን በግልጽ ተናግረው ነበር። ይህም በመንፈስ ቅዱስ እየተመሩ በጻፉትና ባስተማሩት ሁሉ ውስጥ በግልጽ የሚገኝ "ጊዜ ጠቋሚ የሆኑ የንባብ ክፍሎች" በምንላቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ውስጥ በግልጽ የሚታይ እውነት ነው። ታዲያ መቼ ነው ተመልሶ ይመጣል ያሉት? ከዚህ ቀጥሎ ከብዙ በጥቂቱ በማቀርባቸው በእነዚህ ዝርዝር ምንባባት ውስጥ የተገለጠውንና በጣም በቅርብ እንደሚሆን የነበረውን ስሜት ልብ ብላችሁ ተመልከቱ፦

ማቴ 10፥ 23 "በአንዲቱ ከተማም መከራ ቢያሳዩአችሁ ወደ ሌላይቱ ሽሹ፤ እውነት እላችኋለሁና፥ የሰው ልጅ እስኪመጣ ድረስ የእስራኤልን ከተማዎች አትዘልቁም።"

ማቴ 16፥ 27፣28 "የሰው ልጅ ከመላእክቱ ጋር በአባቱ ክብር ይመጣ ዘንድ አለውና፤ ያን ጊዜም ለሁሉ እንደ ሥራው ያስረክበዋል። እውነት እላችኋለሁ፥ የሰው ልጅ በመንግሥቱ ሲመጣ እስኪያዩ ድረስ እዚህ ከሚቆሙት ሞትን የማይቀምሱ አንዳንድ አሉ።"

ማቴ 24፥ 34 " እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም።"

ያዕ 5፥ 8 " እናንተ ደግሞ ታገሡ፥ ልባችሁንም አጽኑ፤ የጌታ መምጣት ቀርቦአልና።"

1ጴጥ 4፥ 7 "ዳሩ ግን የነገር ሁሉ መጨረሻ ቀርቦአል። እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ፥"

ራእይ 1፥ 1-3 "ቶሎ ይሆን ዘንድ የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ ያሳይ ዘንድ እግዚአብሔር ለኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠው በእርሱም የተገለጠው ይህ ነው፥ ኢየሱስም በመልአኩ ልኮ ለባሪያው ለዮሐንስ አመለከተ፥ እርሱም ለእግዚአብሔር ቃልና ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ላየውም ሁሉ መሰከረ። ዘመኑ ቀርቦአልና የሚያነበው፥ የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁት ብፁዓን ናቸው።"

ራእይ 22፥ 6-7 "እርሱም፦ እነዚህ ቃሎች የታመኑና እውነተኛዎች ናቸው፥ የነቢያትም መናፍስት ጌታ አምላክ በቶሎ ሊሆን የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ እንዲያሳይ መልአኩን ሰደደ። እነሆም፥ በቶሎ እመጣለሁ። የዚህን መጽሐፍ ትንቢት ቃል የሚጠብቅ ብፁዕ ነው አለኝ።"

ራእይ 22፥ 10 "ለእኔም፦ ዘመኑ ቀርቦአልና የዚህን መጽሐፍ ትንቢት ቃል በማኅተም አትዝጋው።"

ራእይ 22፥ 12 "እነሆ፥ በቶሎ እመጣለሁ፥ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር አለ።"

ራእይ 22፥ 20 "ይህን የሚመሰክር፦ አዎን፥ በቶሎ እመጣለሁ ይላል። አሜን፥ ጌታ ኢየሱስ ሆይ፥ ና"

በግሌ እነዚህ ምንባባት ያላቸውን ትርጉምና የያዙትን መልእክት ከመጀመርያው ክፍለ ዘመን አውድ ነጥሎ በመረዳት ጌታን ኢየሱስን በቃሉ የማይታመን አድርጎ በማየት ፈተና ውስጥ መውደቅ አልፈልግም። ስለዚህ እንዲህ ስል አጥብቄ እጠይቃለሁ፣በዚያው ትውልድ ውስጥ ለመመለስ የሰጠውን የተስፋ ቃል ኢየሱስ ጠብቋል ወይ? ቃሉንስ አላጠፈምን? ሐዋርያቱስ ቢሆኑ በመንፈስ ቅዱስ እየተመሩ ክርስቶስ በራሳቸው የሕይወት ዘመን በቅርቡ ተመልሶ እንደሚመጣ ሲናገሩ የነበረው ንግግራቸው ትክክል ነበር ወይ? አልተሳሳቱም ነበርን? እነዚህና መሰል ጥቅሶች ሁልጊዜም ቢሆን ተጠራጣሪ የሆኑና ማገናዘብ የሚጎድላቸውን "የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች" የሚረብሹና ምቾት የማይሰጡአቸው ናቸው፤ የሥነ መለኮት "አዋቂዎች" ለሚባሉ የለዘብተኝነትን አቋም ለያዙ ሊቃውንት ነን ባዮች ደግሞ የብዙዎችን እምነት ለመገልበጥ ይጠቀሙባቸዋል። ክርስትናችንን ለሚሳደቡ ከሃድያንም "እነዚህ ምንባባት ይፈጸማሉ በተባሉበትና እንዲፈጸሙ በተነገረላቸው የጊዜ ወሰን (በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ትውልድ ወቅት) አልተፈጸሙም፣ ስለዚህ ኢየሱስም ሆነ የአዲስ ኪዳን ጸሓፍያን በትንቢታቸው ወድቀዋል፣ በመሆኑም ቃሎቻቸውን በመንፈስ ቅዱስ በመነዳት የተሰጡና ስህተት የሌለባቸው ናቸው ለማለት አንችልም" ሲሉ የቅዱሳት መጻሕፍትን እውነተኛነት ለመንቀፍና ስህተት የለባቸውም ስንል የምናምነውን የእኛን እምነት ለማጥቃትና ለመተቸት ይጠቀሙባቸዋል። 

የፕሪቴሪዝም ትርጉምና አመለካከት ግን በዚህ ሁሉ ነቀፋና ትችት ፊት በጽናት ቆሞ፣ ይህንን ለመቃወምና አቋሙን ለማስረዳት የቅዱሳት መጻህፍትን አስተምህሮ ብቻ ጠቅሶ የሚያቀርበው ሙግትና ማብራርያ፣ መጻእያን ከሚያቀርቡት ከየትኛውም እርስ በርሱ የተሳከረ የትርጉም መንገድ ይልቅ ጌታ ኢየሱስን እግዚአብሄር በወንድሞቹ መካከል ቀብቶ እንዳስነሳው ነብይና እንደ እውነተኛ የእግዚአብሔር ልጅ የሚያከብረው ነው፤ የቅዱሳት መጻህፍትንም ተአማኒነት የሚያረጋግጥ፣ ቅዱሳት መጻህፍትም ለተሰጡበት አውድ ታማኝ ሆኖ የትርጉም ቀዋሚነትን (consistency) የሚጠብቅ እንደሆነ አይኑን ያልጨፈነ ሁሉ ሊያረጋግጠው ይችላል። 

ለምሳሌ፣ ከትውልድ ሃገሬ ርቄ ባለሁበት አገር ቤት ላሉ ለሚወዱኝና ሊያዩኝ ለሚናፍቁ ወዳጅ ዘመዶቼ፣  "ቶሎ ብዬ እመጣለሁ፣ በቅርቡ ወደ አገሬ እመለሳለሁ" ብዬ ቃል ብገባ፣ ቃሌ እውነተኛና ታማኝ ሊሆን የሚችለው እኔም ሆንኩ ወዳጅ ዘመዶች በህይወት እያለን የሰጠሁትን ተስፋ የፈጸምሁ እንደሆን ብቻ ነው። ለኢየሱስም እንደዚያው ነው፣ ተስፋ የሰጣቸው ሰዎች ካለፉ በኋላም ገና እስካሁን ካልመጣና ገና አሁንም ብዙ ዘመን ይመጣል ተብሎ የሚጠበቅ ከሆነ "እነሆ በቶሎ እመጣለሁ" ብሎ እንዲጠብቁት መንገሩ ትርጉም የሌለው ከመሆኑም ባሻገር፣ ተስፋውን ለመፈጸም በሰጠው ጊዜ ባለመፈጸሙ ኃሰተኛ ያደርገዋል።

እነዚህ ጥቅሶች የክርስቶስን ዳግመኛ ምጽአት ከኢየሩሳሌም ውድቀት፣ ከቤተ መቅደሱ ውድመት፣ እንዲሁም በ70 አ.ም ላይ ከሆነው የአይሁድ ህዝብ እልቂትና የብሉይ ኪዳን የመስዋዕቱ ስርዓት ፍጻሜ ጋር ባለው ግንኙነት አንጻር የሚናገሩና የሚያስተምሩ ናቸው። እነዚያ የቤዛነት ትእይንት የመጨረሻ ኹነቶች ልክ እርሱ ይሆናሉ ሲል እንደተናገረው ተፈጽመው አልፈዋል እንጂ ገና ወደፊት የሚፈጸም፣ ሳይፈጸም የቀረና የዘገየ ተስፋ የለባቸውም። ስለዚህ ጊዜን አመልካች የሆነውን የትንቢቶቹን አቀራረብ ቸል ብሎ፣ "ትንቢቱ ገና ወደ ፊት ይፈጸማል እንጂ እስከ አሁን ገና አልተፈጸመም" ሲል፣ ሳይፈጸም እንደቀረ ወይም እንደዘገየ የሚያስተምረውን እድሜ ዘልዛላ አመለካከት ለማብራራትም ሆነ ለመተንተን መሞከር በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ውስጥ ጊዜው ያለፈበትና ምንም አስፈላጊነት የሌለው ነው። ስለዚህም ነው፣ "ላለፉት ሁለት ሺህ አመታት ለመጀመርያው ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖች የተነገረውንና "እነሆ በቶሎ ይመጣል" የሚለውን ይህንን በግልጽ አማርኛ የተነገረ ቃል እያነበብን፣ አሁንም ለእኛ የተባለ ያህል ቆጥረን ምጽአትን ገና የምንጠብቅ ከሆነ፣ በእውነት አስቀድሞ የሚያስፈልገን የአማርኛ መዝገበ ቃላት እንጂ መጽሐፍ ቅዱስ አይመስለኝም።" ስል የምናገረው። በመጽሐፍ ቅዱስ ካልተግባባን ደግሞ ቢያንስ በአማርኛ የቋንቋ አገባብ እንግባባ ይሆናል ብዬ አስቤ ነው እንጂ የቃሉ ቡጢ ያነገለውን ቃሉ ራሱ ካልፈወሰው በቀር መዝገበ ቃላት ይፈውሰዋል ብዬ አይደለም።

ይህንን ልብ አንቀጥቅጥ የሆነ እውነት አንብባችሁ የኖረውን እድሜ ዘልዛላ አመለካከት ልትሞግቱ ከፈለጋችሁና ሙሉውን የጽሁፉን ይዘት ማየት ከወደዳችሁ እነሆ ሊንኩ፣ 
https://gizachewkr.blogspot.com/2018/08/blog-post.html