Friday, August 24, 2018

የጌታ ምጽአት መቼ እና እንዴት? ክፍል አንድ

የጌታ ምጽዓት መቼ እና እንዴት ነው?
በማቴዎስ 24 እንደተገለጸ

ማቴ 24÷ 3
“እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ፥ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው። ንገረን፣ ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው? አሉት።”
በዚህ ክፍል ደቀ መዛሙርት ለክርስቶስ የሚያቀርቡለት ጥያቄ ምን እንድሆነ መረዳት የትንቢቱን ተገቢና ትክክለኛ ትርጉም ልማግኘት አይነተኛ መነሻ ነው ነው? እንደሚታወቀው ደቀመዛሙርቱ ያቀረቡት ጥያቄ እርስ በርሳቸው ተያያዥነት ያላቸውን ሦስት ጥያቄዎች ነው፡፡ እነርሱም፣ 1) ይህ መቼ ይሆናል? 2) የመምጣትህ ምልክቱ ምንድን ነው? እና 3) የዓለም መጨረሻስ ምልክቱ ምንድን ነው? የሚሉት ናቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ላነሱአቸው ለእነዚህ ጥያቄዎች መልሱን የምናገኘው ከዚሁ  ምዕራፍ  ውስጥ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ ምዕራፉም ስለዘመኑ ፍጻሜ፣ ስለኢየሩሳሌም ውድመት (የዘመኑ ፍጻሜ ለመድረሱ ምልከቱ በሉቃስ 21÷ 7 እና 20 እንደተገለጸው የኢየሩሳሌም በጦር ኃይል መከበብዋ ከዚህም ጋር ተያይዞ የሚገለጠው የጥፋት ርኩሰት ነው)፣ እንዲሁም ስለ ክረስቶስ ምጽዓት ገለጻ የተብራራበት ነው፡፡ 
የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 24 በተለምዶ የደብረዘይቱ ፍካሬ በመባል ይታወቃል። ይህም የንባብ ክፍል በአዲስ ኪዳን ውስጥ በዮሐንስ ራዕይ መጽሐፍ ከተገለጠው በተጨማሪ ረጅሙ የነገረ ፍጻሜ ትንቢት የሆነና፤ በጌታ ምጽዓት ላይ የሚጠቀስ ዓይነተኛ ክፍል ስለሆነ በክፍሉ ላይ ሰፊ ማብራሪያ ሰጥቶ መተርጎም የግድ ይላል፡፡ ኢየሱስ በወንጌላት ውስጥ ምጽዓቱን አስመልክቶ መቼ እንደሆነ ያስተማረበት አይነተኛ የሆነው ተጠቃሽ ክፍል በተለይ የማቴዎስ 24 ነው፡፡
በዚህ ምዕራፍ ሐዋርያቱ ኢየሱስን ከጠየቁት ትክክለኛ ጥያቄዎች እንጀምራለን፡፡ “መቼ ይመለሳል?” የሚለው ጥያቄ የእነርሱ ብቻ ሳይሆን የእርሱን አመጣጥና የምልክቶቹን አፈጻጸም እስካላወቅን ድረስ እኛም የምንጠይቀው ይሆናል፡፡ በዚህ የንባብ ክፍል ኢየሱስ የሚመለስበትን ጊዜ እጅግ አጥብቦ እንደወሰነው እና ጊዜውን እንዳመለከተው ስትማሩ በጣም ልትገረሙ ትችላላችሁ፡፡ ኢየሱስ ስለሚመለስበት ጊዜ መቼ ነው ብሎ እንዳስተማረ እና በሰጠው ምላሽ ውስጥ ያሉትን ምልክቶች አስቀድሞ መመርመር ተገቢ ነው፡፡
“እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ በዚህ ትውልድ ላይ ይደርሳል ( ማቴ 23÷ 36)።
“ኢየሱስም ከመቅደስ ወጥቶ ሄደ፥ ደቀ መዛሙርቱም የመቅደሱን ግንቦች ሊያሳዩት ቀረቡ እርሱ ግን መልሶ፦ ይህን ሁሉ ታያላችሁን? እውነት እላችኋለሁ፥ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም አላቸው። እርሱም በደብረ ዘይት ተቀምጦ ሳለ፥ ደቀ መዛሙርቱ ለብቻቸው ወደ እርሱ ቀርበው። ንገረን፥ ይህ መቼ ይሆናል? የመምጣትህና የዓለም መጨረሻ ምልክቱስ ምንድር ነው? አሉት” (ማቴ 24÷ 1-3)።
“የሰማያትም ኃይላት ይናወጣሉ። በዚያን ጊዜም የሰው ልጅ ምልክት በሰማይ ይታያል፥ በዚያን ጊዜም የምድር ወገኖች ሁሉ ዋይ ዋይ ይላሉ፥ የሰው ልጅንም በኃይልና በብዙ ክብር በሰማይ ደመና ሲመጣ ያዩታል፤ መላእክቱንም ከታላቅ መለከት ድምፅ ጋር ይልካቸዋል፥ ከሰማያትም ዳርቻ እስከ ዳርቻው ከአራቱ ነፋሳት ለእርሱ የተመረጡትን ይሰበስባሉ። ምሳሌውንም ከበለስ ተማሩ፤ ጫፍዋ ሲለሰልስ ቅጠልዋም ሲያቈጠቍጥ፥ ያን ጊዜ በጋ እንደ ቀረበ ታውቃላችሁ፤ እንዲሁ እናንተ ደግሞ ይህን ሁሉ ስታዩ በደጅ እንደ ቀረበ እወቁ። እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም።  ሰማይና ምድር ያልፋሉ፥ ቃሌ ግን አያልፍም( ማቴ 24÷ 30-35)።
እነዚህን የወንጌሉን ክፍሎች እንደሚገባ ለመረዳት ክፍሎቹ የሚገኙበትን ዐውደ ምንባብ መመልከት የግድ ይላል፡፡ ይህንን ለማድረግ ማን? ምን? መቼ? የት? እና ለምን? የሚሉትን ተገቢ የሥነ-ሐቲት ( ኤክስጀስስ) ጥያቄዎች ማንሳት ተገቢ ይሆናል። በማቴዎስ 24 ያለውን የኢየሱስ ክርስቶስን ንግግር ለመረዳት የታሪኩን ዳራና መቼት ማየትም አስፈላጊ ነው። ምክንያቱም የመጽሐፍ ቅዱሳዊ ሥነ- ሐቲት እና ሥነ- ፍታቴ ብቸኛ ንግስት አውደ ምንባብ ናትና።
ስለዚህም ለአሁኑ የጥናት ፍጆታ እምብዛም ርቀን መሄድ ሳያስፈልገን ሁለት ምዕራፎች ብቻ ወደ ኋላ ተመልሰን ኢየሱስ ወደ  ኢየሩሳሌም በክብር የገባበትን ሁኔታ ከሚነግረን ከምዕራፍ 21 ጀምሮ ማየት ይጠቅመናል፡፡ ወደ ቤተ መቅደስ ሄዶ የሚሸጡትን እና የሚገዙትን ገንዘብ ለዋጮችን አስወጣ፡፡ ከዚያም ሌሊቱን ወደ ቢታንያ ሄዶ እንደገና በማለዳ በመመለስ በቤተ መቅደስ ውስጥ ያስተምር ጀመር (ምዕ 21-23)፡፡ በትምህርቱም ምዕራፍ 23 ላይ ጻፎችንና ፈሪሳውያንን “ግብዞች”፣ “እባቦች”፣ “ክፉ ትውልድ” እያለ በመጥራት ከአገልግሎቱ ሁሉ እጅግ ዘለፋ የበዛበትን ስብከቱን አቀረበ፡፡ በመጨረሻም መልዕክቱን ያጠቃለለው በእነርሱና በኢየሩሳሌም ላይ ሊመጣ ያለውን ፍርድ በመናገር ነው፡፡
በማቴ 23÷ 35 ላይ የአይሁድ ሕዝብም ሆኑ የኅይማኖት መሪዎቹ ስለ ኃጢአታቸውና ስለአባቶቻቸው በደል ጭምር ዋጋ  እንደሚከፍሉ ሲናገር፦ 
“ከጻድቁ ከአቤል ደም ጀምሮ በቤተ መቅደስና በመሠዊያው መካከል እስከ ገደላችሁት እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ደም ድረስ በምድር ላይ የፈሰሰው የጻድቅ ደም ሁሉ ይደርስባችሁ ዘንድ።” ይላል፡፡
በመቀጠልም በቁጥር 36 ላይ ስለ ፍርዱ እንዲህ ይላል፦
“እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ በዚህ ትውልድ ላይ ይደርሳል”
“በዚህ ትውልድ”  የሚለውን ሐረግ ለመተርጎም በተርጓሚዎች ዘንድ በርካታ ሓሳቦች እንደሚሰነዘሩ ይታወቃል። [የቤተመቅደሱን መፍረስ አስመልክቶ ከላይ በማቴ 24÷ 3 ለቀረበለት ጥያቄ ሲመልስ የኢየሱስ ትንቢት በሙሉ ፍጻሜውን የሚያገኘው እርሱ የነበረበት “ይህ” የተባለው ትውልድ ከማለፉ በፊት እንደሆነ በግልጽ የሚያስረዳ በመሆኑ ከዚህ የተለየው ትርጓሜ ሁሉ እዚህ ነጥብ ላይ ውድቅ ይሆናል፡፡ ምክንያቱም ኢየሱስ ይህ ትውልድ እንጂ ያ ትውልድ አላለምን]።
ወንጌላዊው ሉቃስ በዘገበው የደብረዘይቱ ተራራ ትንቢት በምዕራፍ 21÷ 32 “እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም።”  ሲል፤ በማቴ 24÷ 33-34 ደግሞ እንዲህ ይላል“እንዲሁ እናንተ ደግሞ ይህን ሁሉ ስታዩ በደጅ እንደ ቀረበ እወቁ። እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም።” ይላል ። በዚህ ክፍል ይህ ትውልድ ሲል የትኛውን ትውልድ ማለቱ ነው? [ ኢየሱስ ሲናገራቸው ቆመው ይሰሙት የነበሩትና "ይህ ትውልድ" የተባሉት እነዚያው  ራሳቸው “ይህ ሁሉ” የተባለውን ያያሉ፡፡ ኢየሱስ የተዘረዘሩትም ጉዳዮች እርሱ “በደጅ እንደቀረበ” የሚያመለክቱ ሆነው ይቆጠራሉ፡፡ ቤተመቅደሱም የፈራረሰውና የወደመው በ70 ዓ. ም ላይ ነው፡፡ ስለዚህ የተቀሩት “ይህ ሁሉ” የተባሉት ነገሮች በዚያው ጊዜ መፈጸም አለባቸው፣ ማለት ነው፡፡ የሚያካትቱትም “በአለም ሁሉ” የሚሆነውን የወንጌል ስብከት (ቁ 14)፣ “የጥፋት እርኩሰት” መታየት(ቁ 15)፣ “የሰው ልጅ በሰማያት ደመና መምጣት” (ቁ 30)፣ እንዲሁም “የተመረጡት”መሰብሰብ (ቁ 31) ነው፡፡ ˝ኢየሱስ የእርሱ ደቀመዛሙርቱ ሞተው ሳያልቁ ከመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ማብቂያ በፊት እንደሚመጣ ትንቢት እየተናገረ እንደሆነ ይታወቃል፤ አንድ ግራ የገባው የጥናት መምሪያ ግን "ይህ የሚያደናግር ንግግር ነው˝ ሲል  ያትታል፣ [NLT Study Bible (Carol Stream: Tyndale House Publishers, Inc.,2008)፡፡ ሲ. ኤስ ሉዊስ የተባለውም ጸሐፊ ሉቃስ 21÷ 32 ላይ ማብራሪያ ሲሰጥ " ….ተሳስቶአል፡፡ እርሱ (ኢየሱስ) ከማንም የበለጠ ስለ አለም መጨረሻ ምንም እንደማያውቅ ግልጽ ነው፡፡ በእርግጥም ይህ ጥቅስ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ካሉ ጥቅሶች ሁሉ እጅግ አስቸጋሪውና አሰናካዩ ጥቅስ ነው"፣ ብሎአል፡፡ {C,S. Lewis, The World Last Night and Other Essayea (New York: Harcourt Brace & Company, 1973) 98}]።
ስለ ትውልዱስ ምን የተገለጸ ነገር እንመለከታለን ? “ሁሉ እስኪፈጸም” ሲልስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ የተናገራቸውን  ልብ በማለት እናስብ ! የቱን ማለቱ ነው? ኢየሱስ ይለው የነበረው ነገር ሁሉ በዚያው ትውልድ ይፈጸማል ማለቱ ነው፡፡ "የሰው ልጅ መምጣት" ከተባሉት ነገሮች መካከል አንዱና ዋናው ነው (ሉቃ 21÷ 27]
የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቃውንቱ ቃሉ የሚያመለክተው እርሱ ሲናገር ይሰሙት የነበሩትን ሕዝብ ነው ሲሉ ይስማማሉ፡፡ [Gentry, ‘‘The Great Tribulation: Past or Future’’; Kregel publications, 1999 (co-authored with Tommy Ice) ገጽ 20-22; Schwertley,‘Brian ‘‘Mathew 24 and the Great Tribulation’’ ገጽ 6-8]
ለምሳሌ ግን ሚልተን ቴሪ በልማድ። በብዙዎች ዘንድ ሲታመን የኖረውን የአንዳንዶቹን መረዳት ሲጠቅሱ ቃሉ በከፍተኛ ደረጃ የትርጉም ልዩነትን ያስከተለ መሆኑን በማውሳት፣ ጄሮም “መላው የሰው ዘር” ማለቱን፣ ዶረን እና አውበርሌን “የአይሁድ ዘር”  ማለታቸውን፣ [ ከእነዚህም መካከል ደግሞ "ትውልድ" (በግሪኩ genea) ማለት ዘር ማለት ነው ይኸውም "ኢየሱስ በሚመለስበት ጊዜ ገና ወደፊት የአይሁድ ዘር እስከዚያ ዘመን ድረስ በምድር ላይ ይኖራል" ሲሉ ጉዳዩን ከአውዱ ነጥለው ክፍሉን በመለጠጥ ሲተረጉሙ ይደመጣሉ፣ ለምሳሌ፦ Edward E. Hindson and Woodrow Michael Kroll, KJV Bible Commentary (Nashville; Thomas Nelson, 1997, ይመለከቷል] ዮሐንስ አፈወረቅም (ክሪሶሶም) እና ላንግ “የክርስቲያን አማኞች ዘር” ማለታቸውን ሚልተን ቴሪ ያመለክታሉ፡፡ ነገር ግን ይላሉ ቴሪ፣ ይህንን ልማዳዊና አውድ ዘለል ትርጉም ሲተቹ፣ ˝ለማንስ ሰው ቢሆን በተለይም ለኢየሱስ “ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ‘መላው የሰው ዘር’፣ ወይም ‘የአይሁድ ዘር’፣ ወይም ‘የክርስቲያን ሕዝብ’ አያልፍም” ብሎ መናገር ምን ያህል ትርጉም የሌለውና ዋጋ ቢስ ነገር ይሆን! …. በአዲስ ኪዳን የትርጉም ጥናት “ትውልድ” ተብሎ የተተረጎመው “ጌኔኦ” የተሰኘው የግሪክ ቃል በዋናነት የሚያመለክተው በአንድ ወቅት  የኖረን ትልቅ የሕዝብ አካልን - በአብዛኛው አብረው የኖሩበትን (ያው አንዱንንና ተመሳሳዩን) ክፍለ ጊዜ ነው˝ ሲሉ ተቃራኒውን ሃሳብ የጠቁማሉ [Terry Biblical Appocalyptics, ገጽ 244]።

ስለ ትውልድ ስናስብ አንድ ቀላል ጥያቄ እናነሳለን። ይኸውም የአንድ ትውልድ እድሜ ምን ያህል ዓመታት ናቸው? የሚለው ነው። ጆን ዋልቩርድ አንድ ትውልድ ከሠላሳ እስከ አንድ መቶ ዓመታት ያህል ነው ይላሉ፡፡ ከሌሎች ሁሉ የመጽሐፍ ቅዱስ ተንታኞች በተለየ አቀራረብ ጊዜውን እስከ መቶ ዓመታት ድረስ የሚያራዝሙ እኔ የማውቃቸው ብቸኛ ተርጓሚ እሳቸው ናቸው፡፡ መጋቢ በቀለ ወ/ኪዳን “ከሌሊቱ ስንት ሰዓት ነው” በተሰኘው መጽሓፋቸው ይህንኑ ሓሳብ ይጋራሉ። በርካታ የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቃውንት እንደሚያምኑት ከሆነ ግን “አንድ ትውልድ”” በመጽሐፍ ቅዱስ ከሠላሳ እስከ አርባ ዓመታት ያህል ይሸፍናል የሚለው ሓሳብ ሚዛን ይደፋል ። በዚህ ላይ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ አንድ ትውልድ የሚናገረውን ማየት እጅግ የተሻለ ነው፡፡

“እንግዲህ ትውልድ ሁሉ ከአብርሃም እስከ ዳዊት አሥራ አራት ትውልድ፥ ከዳዊትም እስከ ባቢሎን ምርኮ አሥራ አራት ትውልድ፥ ከባቢሎንም ምርኮ እስከ ክርስቶስ አሥራ አራት ትውልድ ነው። (ማቴ 1÷ 17)
በዚህ የትውልድ ሓረግ መግለጫ የአንድን ትውልድ የጊዜ ርዝመት መገመት የሚያስችለንን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ዝርዝር እናያለን፡፡ ከባቢሎን ምርኮ እስከ ክርስቶስ ድረስ አሥራ አራት ትውልድ መሆኑን ይጠቁመናል፡፡ ምርኮው በሴዴቅያስ ዘመነ መንግሥት ከክርስቶስ ልደት በፊት በ586 የሆነ ነበር፡፡ ከ586 ዓ.ቅ.ክ እስከ ክርስቶስ መወለድ ድረስ በጠቅላላ 586 ዓመታት ገደማ ናቸው፣ ይህንንም ለአሥራ አራት ብናካፍለው የአንድ ትውልድ አማካይ የእደሜ ርዝመት 41 ዓመታት ይሆናሉ፡፡
ይህንን ደግሞ እዩ፦
ዛሬ ድምፁን ብትሰሙት፥ አባቶቻችሁ እኔን የፈተኑበት የመረመሩበትም አርባ ዓመትም ሥራዬን ያዩበት በምድረ በዳ በፈተና ቀን በማስመረር እንደ ሆነ፥ ልባችሁን እልከኛ አታድርጉ፤ ስለዚህ ያን ትውልድ ተቆጥቼ። ዘወትር በልባቸው ይስታሉ መንገዴን ግን አላወቁም አልሁ፤ (ዕብ 3÷ 8-10)።
በተጨማሪም፦
የእግዚአብሔርም ቍጣ በእስራኤል ላይ ጸና፥ በእግዚአብሔርም ፊት ክፉ ያደረገ ትውልድ ሁሉ እስኪጠፋ ድረስ አርባ ዓመት በምድረ በዳ ውስጥ አቅበዘበዛቸው። (ዘኁል 32÷ 13)።
አርባ ዓመታት በመጽሐፍ ቅዱስ የታወቀ ቁጥር ነው፡፡ የእስራኤል ልጆች ወደ ተስፋይቱ ምድር ከመግባታቸው በፊት ለአርባ አመታት በምድረ በዳ ተጉዘዋል፡፡ የአዲስ ኪዳንም ቅዱሳን ከሰማይ ወደሆነችው ወደ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ከመግባታቸው አስቀድሞ ከክርስቶስ እርገት እስከ 70 ዓ. ም ድረስ ለአርባ ዓመታት በሽግግር ወቅት ውስጥ ነበሩ፡፡ ስለሆነም ኢየሱስ የተነበያቸው እነዚያ ነገሮች ሁሉ ተፈጻሚ የሚሆኑት በእነዚህ በአርባ ዓመታት ውስጥ ነው፣ አለበለዚያ ሓሰተኛ ነቢይ መሆኑ ነው፡፡ ይህም የሚያካትተው ሁሉንም በማቴዎስ 23 እና 24 የተጠቀሱትን፡- ጦርነቶች፣ ረሃብ፣ የምድር መንቀጥቀጥ፣ የኢየሩሳሌም በጦር ሠራዊት መከበብዋን፣ ክርስቲያኖች ከይሁዳ መሸሻቸውን፣ የሙሴ ዘመን (ዓለም) ፍጻሜን፣ እና የኢየሱስን በኃይልና በታላቅ ክብር ተመልሶ መምጣትን ሁሉ ነው፡፡
ይህ ሁሉ ከአርባ ዓመታት በኋላ በ70 ዓ.ም ላይ በዚያው አንድ ትውልድ ልክ ኢየሱስ እንደተነበየው ያልተፈጸመ ከሆነ፣ እንግዲያውስ ኢየሱስ ሐዋርያቱን እያታለላቸው ነበር ማለት ነው፡፡ ኢየሱስ እውነት መሆኑን (ዮሐ 14። 6)፣ እውነተኛም ሆኖ ለእውነት ሊመሰክር ለዚህ መወለዱን (ዮሐ 18፥ 37) እንጂ፣ ውሸተኛና አታላይ እንዳልሆነ በእርግጥ እናውቃለን፡፡ እርሱ እመለሳለሁ ሲል ተስፋ በሰጠበት ጊዜ እንደተመለሰ ከማመን በቀር ጌታን ኢየሱስን እግዚአብሔር በወንድሞቹ መካከል እንዳስነሳው እንደ እውነተኛ ነብይ ልንሰማው የምንችልበት ሌላ ምንም ዕድል የለንም፡
በቁጥር 38 እንዲህ ይላል “እነሆ፥ ቤታችሁ የተፈታ ሆኖ ይቀርላችኋል”፣ ይህ “ቤት” የተባለው ኢየሱስ  ቆሞ የነበረበት ቤተ መቅደስ ብቻ ሳይሆን፣ ነገር ግን ማናቸውም አይሁዳዊ የሆነው ነገር ሁሉ፣ ጠቅላላውን የይሁዳን ሕዝብ ቤት፣ ኑሮአቸውን፣ ቤተሰቦቻቸውን፣ ምድራቸውን፣ ሕዝባቸውን፣ አገራቸውን፣ የኃይማኖት ሥርዓታቸውን፣ የክህነት አገልግሎታቸውንና የአኗኗር ዘይቤአቸውን ሁሉ የሚያካትት ቃል ነው፡፡ እንደ ኢየሱስ ቃል ከሆነ ይህ ሁሉ ፈጽሞ ሊጠፋ ተመድቦአል። ይህ እንዴት ያለ አስፈሪ ትንቢት ነው! ቃል በቃል አንድም ሳይቀር ትንቢቱ መፈጸሙን የ70ውን ዓም የእስራኤልን ውድመት ከታሪክ መዛግብት ማየት ይገባል።
♦♦♦♦♦♦

No comments:

Post a Comment