Friday, May 30, 2025

የዳግመኛ ምጽአቱ አይነተኛ ሰበብ

የዳግመኛ ምጽአቱ አይነተኛ ሰበብ 



ዳግመኛ ምጽዓት ሊፈጸም የተቀጠረለትን ትክክለኛውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጊዜ በተሻለ ሁኔታ ለመረዳት፣ የዳግመኛ ምጻቱን ተፈጥሮ ከመረዳት ባልተናነሰ የዳግመኛ ምጽአቱን አይነተኛ መግፍኤ ምክንያትም በወጉ መረዳት ያስፈልጋል። በአመዛኙ ኢየሱስ ስለ ብድራት፣ ስለፍርድ፣ ስለ ቁጥጥር ቀን ባስተማረበት ምሳሌዎቹ ይህንን የዳግመኛ ምጽአቱን ሰበብ እንመለኩታለን። ኢየሱስ ስለ ክፉዎቹ የወይን እርሻ ገበሬዎች በተናገረው ምሳሌ ላይ ይህን ጉዳይ በግልጽና በቀጥታ አስተምሮታል።


“ሌላ ምሳሌ ስሙ። የወይን አትክልት የተከለ ባለቤት ሰው [እግዚአብሔር] ነበረ፤ ቅጥርም ቀጠረለት፥ መጥመቂያም ማሰለት፥ ግንብም ሠራና ለገበሬዎችር [እስራኤል] አከራይቶ ወደ ሌላ አገር ሄደ። የሚያፈራበትም ጊዜ ሲቀርብ፥ ፍሬውን [መልካምን ስራ] ሊቀበሉ ባሮቹንል [የብሉይ ኪዳን ነብያት] ወደ ገበሬዎች ላከ። ገበሬዎቹም ባሮቹን ይዘው አንዱን ደበደቡት አንዱንም ገደሉት ሌላውንም ወገሩት። ደግሞ ከፊተኞች የሚበዙ ሌሎች ባሮችን ላከ፥ እንዲሁም አደረጉባቸው። በኋላ ግን፦ ልጄንስ ያፍሩታል ብሎ ልጁን [ኢየሱስ] ላከባቸው። ገበሬዎቹ ግን ልጁን ባዩ ጊዜ እርስ በርሳቸው፦ ወራሹ ይህ ነው፤ ኑ፥ እንግደለውና ርስቱን እናግኝ ተባባሉ። ይዘውም ከወይኑ አትክልት አወጡና ገደሉት [ስቅለቱ]። እንግዲህ የወይኑ አትክልት ጌታ በሚመጣ ጊዜቱ [የኢየሱስ ዳግም ምጽ አጽአት] በእነዚህ ገበሬዎች ምን ያደርግባቸዋል? እነርሱም፦ ክፉዎችን [እስራኤል] በክፉ ያጠፋቸዋል፥ የወይኑንም አትክልት ፍሬውን በየጊዜው ለሚያስረክቡ ለሌሎች ገበሬዎች [ክርስቲያኖች] ይሰጠዋል አሉት። ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፦ ግንበኞች የናቁት ድንጋይ እርሱ የማዕዘን ራስ ሆነ፤ ይህም ከጌታ ዘንድ ሆነ፥ ለዓይኖቻችንም ድንቅ ነው የሚለውን ከቶ በመጽሐፍ አላነበባችሁምን? ስለዚህ እላችኋለሁ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተች [ከእስራኤል] ትወሰዳለች ፍሬዋንም ለሚያደርግ ሕዝብ [ለክርስቲያኖች] ትሰጣለች። በዚህም ድንጋይ ላይ የሚወድቅ ይቀጠቀጣል፤ ድንጋዩ ግን የሚወድቅበትን ሁሉ ይፈጨዋል። የካህናት አለቆችና ፈሪሳውያንም ምሳሌዎቹን ሰምተው ስለ እነርሱ እንደ ተናገረ አስተዋሉ፤” (ማቴዎስ 21፥ 33-45)


ይህ ምሳሌ እንደሚያሳየው፣ የእግዚአብሔር አላማና ፍላጎት እስራኤል ፍሬ እንዲያፈራለት (መልካምን ሥራ እንዲያደርግለት) ነው፣ ያንንም ይጠባበቅ ነበር። “ፍርድን ተስፋ ያደርግ ነበር፥ እነሆም ደም ማፍሰስ ሆነ፤ ጽድቅንም ይተማመን ነበር፥ እነሆም፥ ጩኸት ሆነ።” (ኢሳይያስ 5፥ 7) እንደተባለው፤ በአብዛኛው የእስእስራኤል ታሪክ ውስጥ የሆነው እግዚአብሔር ይጠባበቅ ከነበረው ፍጹም ተቃራኒው ነው። እንዲያውም አንዳንድ ጊዜ እስራኤል በዙርያዋ ካሉ አረማውያን ጎረቤቶቿ ይልቅ በክፋትና በአመጽ ብሳ ትገኛለች። (2ዜና 33፥ 9፣ ሕዝ. 5፥ 6)። እግዚአብሔር እስራኤልን ንስሐ እንዲገቡ ለማድረግ (ወደ እርሱ ይመለሱ ዘንድ) በየጊዜው በርካታ ነቢያትን ልኮላቸዋል። እስራኤል ግን እነዚያን ነቢያት አሳደዱ፣ አንገላተውም ገደሏቸው። በመጨረሻም እግዚአብሔር “በእውነት ልጄንስ ያከብሩታል” (ማቴ. 21፥ 37) ብሎ የገዛ ራሱን ልጅ ላከው። እስራኤል ግን እርሱንም ገደለችው። (ቴክኒካሊ፣ ሮማውያን ኢየሱስን የገደሉት ቢሆንም፣ ያንን የፈጸሙት ግን በአይሁድ ልመናና ጥያቄ መሰረት ነው- ሉቃስ 23፥ 21፣ ዮሐንስ 1፥ 11 ተመልከቱ)። ይህ የመጨረሻው እድላቸው ነበር፣ የእግዚአብሔርም ትእግስት እዚህ ላይ አበቃ። ምሳሌው እንደሚለው፡- “የወይኑ አትክልት ባለቤት በመጣ ጊዜ . . . እነዚያን ክፉዎች በክፉ ያጠፋቸዋል፥ የወይኑንም እርሻ ለሌሎች ፍሬውን በየጊዜው ለሚያስረክቡ ገበሬዎች ያከራያል” (ማቴ. 21፥40-41)።


ይህ እንግዲህ በማቴዎስ መጽሐፍ ውስጥ የምናገኘው የዳግም ምጽአት ትምህርት አንድ ሌላ ማጣቀሻ ነው!


ምሳሌው በመቀጠል “ስለዚህ እላችኋለሁ [እስራኤል]፣ የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተ ትወሰዳለች ፍሬዋንም ለሚያደርግ ሕዝብ ትሰጣለች። (ማቴዎስ 21፥ 43) መንግሥቱ ለየትኛው “ህዝብ” ነው የተሰጠው? ለክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን ነው፣ እርሷም ከእስራኤል ጻድቃን ቅሬታዎች (ጥቂት የተመረጡ) ጋር የአሕዛብ ጻድቃን ቀሪዎችን ያቀፈች ናት።


እግዚአብሔር ከመጀመሪያ ለእስራኤል የነበረው አሳብ ለእርሱ ቅዱስ ሕዝብ እንዲሆኑለት ነበር። እግዚአብሔር አሮጌውን ቃል ኪዳን ሲያቆምላቸው (ይኸውም ከክልበ በ1500 ገደማ ነው)፣ ይህም በመሠረቱ በእግዚአብሔርና በእስራኤል መካከል የተደረገ የቃል ኪዳን ስምምነት ውል ነበር - ያኔም እግዚአብሔር እንዲህ አለ፡- “ቃሌን በእውነት ብትሰሙ ኪዳኔንም ብትጠብቁ፥ ምድር ሁሉ የእኔ ናትና ከአሕዛብ ሁሉ የተመረጠ ርስት ትሆኑልኛላችሁ፤ እናንተም የካህናት መንግሥት የተቀደሰም ሕዝብ ትሆኑልኛላችሁ” (ዘጸአት 19፥ 5-6,) እግዚአብሔር እስራኤል የተቀደሰ (የተለየ) ሕዝብ እንድትሆንለት ነበር የሚፈልገው፣ የቃል ኪዳኑም ግብ ይኸው ነበር። ቃል ኪዳኑ ግን የቆመበት ቅድመ ሁኔታ አለው እርሱም፡- “ቃል ኪዳኔን ብትጠብቁ... ለኔ ልዩ ርስት፣ የተቀደሰ ሕዝብም ትሆኑልኛላችሁ” ይላል። በሙሴ ቃል ኪዳን፣ በኦሪት፣ በሕጉ የተነገሩትት የብሉይ ኪዳን በረከቶች በእስራኤል መታዘዝ ላይ የተመሰረቱ ነበሩ። በሚያሳዝን ሁኔታ ኢየሱስ ስለ እነዚያ ክፉ የወይን ቦታ ገበሬዎች ከፍ ሲል በተናገረው ምሳሌ እንዳመለከተው እስራኤል በቃል ኪዳኑ የተሰጣትን ተስፋ እንዳታገኝ እነዚያን ቅድመ ሁኔታዎቹ መታዘዝ ተስኗታል። እስራኤል በህጉ ኖራ ልታቀርበው የሚገባትን የጽድቅ ፍሬ ማፍራት ተስኗታል። እግዚአብሔርም እርሷን ለማረም በየዘመኑ ነቢያትን ቢልክም እስራኤል ግን አልሰማቻቸውም፣ አሳዳም ገድላቸዋለች። በመጨረሻ የገዛ ራሱን ልጅ ኢየሱስን ቢልከው እስራኤል እርሱንም ገደለችው።


ስለዚህም በምሳሌው እንደተገለጠው የወይኑ እርሻ ባለቤት (እግዚአብሔር) በመምጣቱ እነዚያን ክፉዎች በክፉ ያጠፋቸዋል (ማቴ. 21፥ 40) መንግሥታቸውንም ነጥቆ ለሌላ ሕዝብ ይሰጣል (ቁ. 41)።


የዳግመኛ ምጽአቱ አይነተኛ ምክንያትም ይህ ነው፣ የክፉዎች ፍርድ እና የጻድቃን ብድራት። ይህንን ማስተዋል ለተቻለው ከእንግዲህ የቀረለት፥ የሚጠባበቀው፣ ሌላ ዳግመኛ ምጽአት የ ለውም።


ከላይ እንደተገለጸው፣ ከእስራኤል የተነጠቀ መንግሥትን የተቀበለው አዲሱ ሕዝብ የክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን ተብላ የምትጠራው ናት። እንዲያውም ሐዋርያው ​​ጴጥሮስ እነርሱን እንዴት እንደገለጻቸው አስተውሉ:- “እናንተ ግን [ክርስቲያኖች] ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፣ የንጉሥ ካህናት፣ ቅዱስ ሕዝብ፣ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ” ይላል። ይህ አገላለጽ ቀደም ሲል በዘጸአት 19፥ 5-6 ባለው ላይ እግዚአብሔር እስራኤልን የገለጸበት መንገድ ነው፡ ቅዱስ ሕዝብ፣ የካህናት መንግሥት፣ ርስት። በሌላ አነጋገር የክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን አዲሷ የእግዚአብሔር ቅድስት ሀገር ናት ማለት ነው። ቤተ ክርስቲያን አዲሷ የእግዚአብሔር እስራኤል ናት (ገላ. 6፥ 15-16)። ምንም እንኳን ክርስቲያኖች ብዙውን ጊዜ ራሳቸውን ለመግለጥ በዚህ መጠሪያ ባይጠቀሙም ቤተ ክርስቲያን ግን የአዲስ ኪዳን እስራኤል ልትባል ትችላለች።


ይህንን አትርሱ፣ ይህ አዲስ ህዝብ በመጀመሪያ በአንጾኪያ ክርስቲያን ተብሎ የተጠራው የእምነት ማህበረሰብ ነው (የሐዋርያት ሥራ 11፥ 26)፤ እርሱም ሁለቱንም ማለትም አይሁዳውያንና አሕዛብን ያቀፈ የአማኞች ስብስብ ነው። በመሠረቱ፣ ቤተ ክርስቲያን በመጀመሪያ በተቋቋመችበት ጊዜ፣ “የእስራኤል ልጆች ቁጥር ምንም እንደ ባሕር አሸዋ ቢሆን ቅሬታው ይድናል፤ ጌታ ነገሩን ፈጽሞና ቆርጦ በምድር ላይ ያደርገዋልና ብሎ ስለ እስራኤል ይጮኻል” (ሮሜ. 9፥ 27) እንደተባለ ኢየሱስን የሚያውቁ እና የተከተሉትን አይሁዶችን ብቻ ያቀፈች ነበረች።  


በመጨረሻ ግን፣ “ለአሕዛብም ምልክትን ያቆማል፥ ከእስራኤልም የተጣሉትን ይሰበስባል፥ ከይሁዳም የተበተኑትን ከአራቱ የምድር ማዕዘኖች ያከማቻል።” (ኢሳይያስ 11፥ 12፤) በሚል በብሉይ ኪዳን አንድ ቀን እንደሚፈጸም እንደተነገረው የትንቢት ተስፋ አሕዛብም ወደ ቤተ ክርስቲያን መጨመር ጀመሩ። (በተጨማሪ ኢሳ. 55፥ 5፤ 65፥ 1 ተመልከቱ)። እንግዲህ በዚህ አዲስ ህዝብ ውስጥ፣ ማለትም በቤተ ክርስቲያን፣ በአይሁድ እና በአሕዛብ መካከል ምንም መለያየት የለም (ኤፌ. 3፥ 6)። ኢየሱስ በሁለቱ መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ በሞቱ አፍርሶታልና (ኤፌ. 2፥ 14)። አይሁድና አሕዛብም በክርስቶስ አንድ ናቸው (ገላ. 3፥ 28)። መንግሥቱን የተቀበለውም ይህ አዲስ ሕዝብ ነው!


ብዙ ዘመን ወደኋላ ሄደን ስንመለከት ይህ ክስተት እንዴት እንደተተነበየ መረዳት አስገራሚ ነው። ከክርስቶስ ልደት በፊት በ700 ዓ.ዓ ገደማ፣ ነብዩ ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ተንብዮ ነበር፡- “እግዚአብሔር አምላክ ይገድላችኋልና፣ ባሪያዎቹንም በሌላ ስም ይጠራቸዋል።” ጌታ ኢየሱስ ስለ ክፉዎቹ የወይን አትክልተኞች በተናገረው ምሳሌ ላይ የጠቀሰውም ይህንኑ ነው፡- “ጌታ [እግዚአብሔር] እነዚያን ክፉ ሰዎች በክፉ ያጠፋቸዋል [በመምጣቱ]... መንግሥቱንም ፍሬ ለሚያፈራ ለሌላ ሕዝብ ይሰጣል (ማቴ. 21፥ 41-43) ምንም እንኳን ቅዱሳት መጻሕፍት እንዲህ ባሉ ረጅም ዘመናት መካከል በኖሩ ጸሐፍያን የተጻፉ ቢሆንም፣ ለዚህን ያህል ብዙ ዘመናት እርስ በርሳቸው የማይጣረሱ በአንድነት አንድን ነገር የሚናገሩ ስሙም መሆናቸው የሚያስገርም ተአምር ነው። በተለያዩ ቦታዎች የኖሩ ጸሐፍያን የጻፉት ይህ መጽሐፍ አንድነቱና እና ወጥነቱ፣ በቅዱሳት መጻሕፍት እና በታሪክ ላይ የእግዚአብሔርን እጅ የበላይነት ያሳያል።


የዳግም ምጽአቱን አይነተኛ ምክንያት የሚያሳየው ሌላው የማቴዎስ ምንባብ ማቴዎስ 23፡29-36 ያለው ነው። አሁንም ኢየሱስ እየተናገረ ነው፡-


“እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፥ የነቢያትን መቃብር ስለምትሠሩ የጻድቃንንም መቃብር ስለምታስጌጡና፦ በአባቶቻችን ዘመን ኖረን በሆነስ በነቢያት ደም ባልተባበርናቸውም ነበር ስለምትሉ፥ ወዮላችሁ። እንግዲያስ የነቢያት ገዳዮች ልጆች እንደሆናችሁ በራሳችሁ ላይ ትመሰክራላችሁ። እናንተ ደግሞ የአባቶቻችሁን መስፈሪያ ሙሉ። እናንተ እባቦች፥ የእፉኝት ልጆች፥ ከገሃነም ፍርድ እንዴት ታመልጣላችሁ? ስለዚህ፥ እነሆ፥ ነቢያትንና ጥበበኞችን ጻፎችንም ወደ እናንተ እልካለሁ፤ ከእነርሱም ትገድላላችሁ ትሰቅሉማላችሁ፥ ከእነርሱም በምኵራባችሁ ትገርፋላችሁ ከከተማም ወደ ከተማ ታሳድዳላችሁ፤ ከጻድቁ ከአቤል ደም ጀምሮ በቤተ መቅደስና በመሠዊያው መካከል እስከ ገደላችሁት እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ደም ድረስ በምድር ላይ የፈሰሰው የጻድቅ ደም ሁሉ ይደርስባችሁ ዘንድ። እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ በዚህ ትውልድ ላይ ይደርሳል።” (ማቴዎስ 23፥ 29-36)


ቀደም ሲል ልክ በክፉዎቹ የወይኑ ቦታ ሰራተኞች ምሳሌ ላይ እንደተነገረው ሁሉ፣ እዚህም ላይ ጌታ ኢየሱስ እግዚአብሔር በየዘመናቱ የላከላቸውን ነቢያት በመቃወማቸውና በግፍ በመግደላቸው ምክንያት እስራኤላውያንን ይወቀሳቸዋል። እዚህም ላይ በድጋሚ ፍርዱ “በትውልዱ ላይ” እንደሚመጣ ኢየሱስ ተናግሯል (ማቴ. 23፥ 36) ይህም በ70 ዓ.ም ላይ የመጣባቸውን ጥፋት የሚያመለክት ነው። ይህም የተነገረባቸው “የገሃነም ፍርድ” ነው [ገሃነም በትርጉሙ ብዙ ታሪክ ጸሐፊዎች ከኢየሩሳሌም ከተማ ውጭ ያለ የቆሻሻ መጣያና ማቃጠያ እንደሆነ ያምናሉ። ስለዚህ ኢየሱስ የገሃነምን ፍርድ አንስቶ ሲናገር በ70 ዓ.ም ስለተፈጸመው የጠላቶቹ መጥፋት ትንቢት መናገሩ ነው።


ጌታ ኢየሱስ በማርቆስ ወንጌል ላይ ያችን ፍሬ ያላገኘባትን በለስ ሲረግም ያህንኑ ነጥብ በድጋሚ ተናግሯል። አንድ ቀን ኢየሱስ በተራበ ጊዜ ፍሬ ወደሌላት አንዲት በለስ ላይ ቀረበና እንዲህ አላት፡- “ማንም ዳግመኛ ካንቺ ፍሬ አይብላ…” በማለዳም በዚያ ሲያልፉ ዛፊቱ ደርቃ ሞታ ነበረ። ( ማርቆስ 11፥ 14-21 ) ኢየሱስ ይህችን ዛፍ የረገመበት ምክንያት ማድረግ የሚገባትን ያላደረገች፣ ይኸውም ፍሬ የማታፈራ የማትጠቅም ዛፍ ስለሆነች ነው። ይህች ከንቱ በለስ እስራኤልን ትወክላለች (ኤር. 8፥ 13፤ ሆሴ. 9፥ 10)። የጠወለገችውም ወዲያው (በማለዳ) ነው፤ ይህም የእስራኤል ፍርድ ፈጥኖ እንደሚመጣ ያሳያል! በተጨማሪም “ከዚህ ዛፍ ፍሬ የሚበላ ማንም የለም” ሲል ኢየሱስ እንደተናገረው፣ ይህ ፍርድ በአይነቱ ዘላቂም ጭምር ነው። እስራኤል ከእግዚአብሔር ጋር የነበራት ልዩ መብት እና ያ የከበረ ግንኙነት አሁን (ኢየሱስ ይህንን ሲናገር) ሊያከትም ተቃርቧል ማለት ነው። ይህ ኢየሱስ በነዚህ ክፉ በሆኑ የወይን ቦታ ገበሬዎች ምሳሌ ላይ ከተናገረው ነጥብ ጋር ተመሳሳይ ነው። የወይን እርሻው ባለቤት በመጣ ጊዜ “እነዚያን ክፉ ሰዎችና ከተማቸውን ያጠፋቸዋል” ሲል ተናግሯል። “የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተ ትወሰዳለች ፍሬዋንም ለሚያፈራ ሕዝብ ትሰጣለች።” ( ማቴ. 21፥ 41-43 ) እንግዲህ ልብ አድርጉ በምሳሌው የተነገሩ ሁለቱም ታሪኮች አንድን ነጥብ ያመለክታሉ፣ ይኸውም በቅርቡ በእስራኤል ላይ አይቀሬ የሆነ አስከፊ ፍርድ እየመጣ መሆኑን፣ ፍርዱም የማይቀለበስና ዘላቂ መሆኑን ነው።


አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ተንታኞች እስራኤላውያን አሁንም እንኳ - እንዲሁም ሁልጊዜም ቢሆን በእግዚአብሔር የተመረጡ ሕዝቡ እንደሆኑ ይከራከራሉ። እነዚህ ተንታኞች በ70 ዓ.ም ላይ የተፈጸመው ፍርድ የአይሁድ መሪዎችን ብቻ የሚመለከት እንጂ በጠቅላላው የእስራኤልን ሕዝብ (ብዙሃኑን) የሚመለከት አይደሉም ሲሉ ለመከራከር ይጣጣራሉ። ይሁን እንጂ፣ ጌታ ኢየሱስ ስለ ክፉዎቹ የወይን ቦታ ገበሬዎች በተናገረው ምሳሌና እንዲሁም በበለሲቱ ዛፍ ታሪክ ውስጥ የተናገራቸው ቃላት በግልጽ የሚያስተምሩት ስለጠቅላላው የእስራኤል ህዝብ ነው።


ለዚህ አንድ ተጨማሪ ማስረጃ የሚሆነው ኢየሱስ ተይዞ በፍርድ ችሎት ላይ በቀረበ ጊዜ የሆነውን የህዝቡን ምርጫ ተመልከቱ። ሮማዊው ገዥ ጴንጤናዊው ጲላጦስ ሕዝቡን (ብዙሃኑን የአይሁድን ህዝብ) በየአመቱ እንደሚያደርገው እስረኛን የመፍታት ልማድ ይህንን እድል ለኢየሱስ ሊሰጠው አስቦ ማንን ልፍታላችሁ፣ ኢየሱስን ወይንስ ታዋቂውን ወንጀለኛ በርባንን? ብሎ ሲጠይቃቸው ሕዝቡ በአንድ ድምጽ በርባንን ፍታልን ብሎ እንደመረጠ እዩ! ጲላጦስም፡- “ክርስቶስ የተባለውን ኢየሱስን እንግዲህ ምን ላድርገው” ብሎ ሲጠይቃቸው፣ ሁሉም በአንድነት፡- “ስቀለው”፣ ይሰቀል! የሚል ነበር መልሳቸው። በዚያን ጊዜ አገረ ገዡ፡- “ለምን፥ ያደረገው ክፋት ምንድር ነው?” ሲላቸው፣ እነርሱ ግን፡- “ይሰቀል! ይሰቀል! ደሙ በእኛና በልጆቻችን ላይ ይሁን እያሉ አብዝተው ጮኹ።” (ማቴዎስ. 27፥ 15-26,)


“ደሙ በእኛና በልጆቻችን ላይ ይሁን” የሚለው ይህ የመጨረሻው ዓረፍተ ነገር ሁሉንም ጠቅልሎ ለኢየሱስ በግፍ መገደል ተጠያቂ ያደርጋቸዋል፤ እንጂ ተጠያቂዎች የሆኑት የአይሁድ መሪዎች ብቻ አልነበሩም። በአጠቃላይ አይሁድ በጋራ ስምምነት የኢየሱስን ደም እዳ በምርጫቸው የወሰዱ ነበሩ! የኢየሱስ መገደል በብዙሃኑ ህዝበ ውሳኔ የተቆረጠ ነበር። ሊመጣባቸው የሚችል ፍዳም ካለ ይሁን ሲሉ በቃላቸው ፈርመዋል። ሐዋርያው ​​ዮሐንስም “የእርሱ ​​ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም፤” (ዮሐንስ 1፥ 11) በማለት አይሁድ መሲሀቸውን እንዴት እንደገፉት በጥሩ ሁኔታ ገልጾታል። እንግዲህ ለኢየሱስ ሞት ተጠያቂው ብዙሃኑ ነው፣ በ70 ዓ.ም ላይም በማይለወጥ ቋሚ በሆነ ፍርድ የተዳኙት ብዙሃኑ ነበሩ! መንግሥቱም ከእስራኤል ተወስዶ ለሌላ ሕዝብ ማለትም ለክርስቲያኖች ተሰጠ።


ይህ ማለት ሁሉም አይሁዶች ኢየሱስን አልተቀበሉትም ነበር ማለት እንዳልሆነ ልብ አድርጉ። ከላይ እንደተገለጸው እነዚያ የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች አይሁዶች ነበሩ። ሁሉም ሐዋርያት አይሁዶች ነበሩ። ጌታ ኢየሱስም ራሱ አይሁዳዊ ነበር። ያም ሆኖ እነዚህ ታማኝ የሆኑ አይሁዳውያን በተቀሩት አይሁድ መካከል የተገፉና ጥቂቶች ነበሩ፤ ለዚህም ነው ኢየሱስ በዘመኑ የነበሩትን “አመንዝራ ትውልድ” (ማቴ. 12፥ 39) እና “የማያምን ጠማማ ትውልድ” (ማቴ. 17፥ 17፤ በተጨማሪም የሐዋርያት ሥራ 2፥ 40 እና ፊልጵ 2:፥ 15⁠ን ተመልከቱ) እያለ ይነቅፋቸው የነበረው። በተመሳሳይም በራእይ መጽሐፍ መልአኩ የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን የይሁዲነት እናት የሆነችውን ኢየሩሳሌምን የገለጸው “ታላቂቱ ባቢሎን፣ የጋለሞታዎችና የምድር ርኩሰት እናት” (ራእይ 17፥ 5)፣ በማለት ነበር። ልብ አድርጉ፡- የራዕይ መጽሐፍ ኢየሩሳሌምን ሲገልጽ በተለይ “ምስጢረ ባቢሎን” እየሩሳሌም ሲል ይገልፃታል። እርስዋም ጌታ የተገደለባት ከተማ እየሩሳሌም ነበረች (ራእ. 11፥ 8)። እስራኤል እንደ ህዝብ የአመንዝራነት ሚና ነበራት፣ በታሪኳም ብዙ ጊዜ በነብያቷ “ጋለሞታ” ተብላ ስትጠራ ኖራለች። ምክንያቱም ብዙ ጊዜ ሌሎች አማልክትን ትከተል ነበር (ሆሴ. 9፥ 1፤ ኤር. 2፥ 20-24፤ 3፥ 2-3፤ ዕዝ. 23፥ 14-20፤ ኢሳ. 23፥ 14-20፤ ኢሳ. 1፥ 21፤ 57፥ 9) ኢየሱስ ባገለገለበት ዘመንም ይሁን ራእይ በተጻፈበት ጊዜ የእስራኤል ሁኔታ እንዲሁ ነበር።


ምንም እንኳን ዘመኑ ታማኝነት ያጡ ትውልዶች የበዙበት የነበረ ቢሆንም፣ እንደ ሁል ጊዜው ሁሉ ግን እግዚአብሔር ያኔም ጥቂት የታመኑ ሰዎች ነበሩት። በኖኅ ዘመን እግዚአብሔር በዚያ ክፉ ትውልድ ላይ የጥፋት ውሃ ፍርድን ሲያመጣ ጻድቁ ኖኅ እና ቤተሰቡ በጊዜው እግዚአብሔር ከጥፋት የጠበቃቸው ትሩፋን ነበሩ። ከብዙ መቶ ዘመናት በኋላም፣ ነብዩ ኤልያስ ብቸኛውና በህይወት የቀረው የመጨረሻው ታማኝ እስራኤላዊ እንደሆነ ባሰበ ጊዜ፣ ጌታ እንዲህ አለው፡- “በእስራኤል ዘንድ ጉልበታቸው ለበኣል ያልተንበረከከውን ሁሉ ሰባት ሺህ ጠብቄአለሁ፣” (1 ነገ. 19፥ 18)። በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመንም ጻድቃን የሆኑ ትሩፋን እነዚያ ጌታ ኢየሱስን የታዘዙቱ ነበሩ። ልክ እንደ ኖህ እና ቤተሰቡ ሁሉ የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖችም እግዚአብሔር ለድነታቸው ወዳዘጋጀላቸው ወደ መርከቡ ገቡ። ማለትም ኢየሱስ እንደነገራቸው በኢየሩሳሌም ዙሪያ ያለውን አጥፊ የአህዛብ ሠራዊት ባዩ ጊዜ ከኢየሩሳሌም ፈጥነው እንዲሸሹ አመልክቷቸው ነበርና እንዳዘዛቸውም አደረጉ (ሉቃስ 21፥ 20-21። ራእ. 18፥ 4)። እነዚህ ክርስቲያኖች ለዚህ ሽሽትና ከፍርድ ማምለጥ ይመቻቸው ዘንድ አስቀድመው ንብረታቸውን ሸጠው ተዘጋጅተው ነበር (ሐዋ. 2፥ 45፡ ማቴ. 19፥ 21)፣ ስለዚህ ከኢየሩሳሌም የሸሹበት ሁኔታ ቅጽበታዊ ነበር። በውጤቱም ኢየሱስ በ70 ዓ.ም በክብር ደመና በመጣ ጊዜ በኢየሩሳሌም ላይ ከደረሰው አስከፊ ፍርድ ተርፈዋል።

ግዛቸው።


From Blogger iPhone client

No comments:

Post a Comment