Sunday, April 21, 2024

የዳግመኛ ምጽአቱ ጊዜ ተራዝሟልን?

የዳግመኛ ምጽአቱ ጊዜ ተራዝሟልን?

ጌታ ኢየሱስ በዳግመኛ ምጽአቱ ተመልሶ ለመምጣት በሺህዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት ዘግይቶ እንደሚመለስ አስተምሮ ነበር ወይ? ለዚህ ጥያቄ መልሳቸው  “አዎን! አስተምሮ ነበር” ብለው የሚሉ የቃሉ አንባብያን ብዙውን ጊዜ በማቴዎስ ወንጌል ውስጥ ወደተዘገቡ ወደሚከተሉት ሁለት ምንባባት ጠቅሰው ያመለክታሉ።  በአስሩ ቆነጃጅት ምሳሌ፣ ሙሽራው ራሱ ጌታችንን የሚወክል ሲሆን፣ እርሱም በዚያ ምሽት ሁሉም እንቅልፍ እንቅልፍ እስኪላቸውና እስከ እኩለ ለሊት ድረስ መምጫውን እንዳዘገየ በንባብ ክፍሉ ተነግሯል (ማቴ. 25፥ 1–13)።  በተመሳሳይም፣ መክሊትን በተቀበሉ ባሮች ምሳሌ፣ ጌታው የተባለው ራሱን ጌታችንን የሚወክል ሲሆን ፣ እርሱም ወደ ሩቅ አገር ተጉዞ “ከብዙ ዘመን በኋላ” እንደተመለሰ (ማቴ. 25፥ 14–30) ተነግሯል።  በእነዚህ በሁለቱም ምሳሌዎች ገጸ ባህርዩ በሙሽራው ወይም በጌታው የተወከለው ጌታ ኢየሱስ፣  ረዘም ላለ ጊዜ፣ ምናልባትም (አንዳንድ የድህረ-ሺህ ዓመታት እምነት አራማጆች እንደሚሉት) በሺህዎችና በአስር ሺህዎች ለሚቆጠሩ ዓመታት ሳይመጣ እንደሚዘገይ ወይም ምጽአቱ ከመሆኑ በፊት ብዙ ዘመን እንደሚያልፍ ተናግሯል፣ ሲሉ ይደመጣሉ።

ይህንን መደምደሚያ ውድቅ ለማድረግ ሁለት ዋና ዋና ምላሾችን ከራሱ ከምንባብ ክፍሉ ልንገራችሁ፦ 

# በመጀመሪያ፣ በምሳሌው ውስጥ ሙሽራው ተመልሶ የመጣው እነዚያው ቆነጃጅት በህይወት እያሉ መሆኑን ማስተዋል ይገባል፣ የሚል ነው።  በቆነጃጅቱ ምሳሌ ላይ ሙሽራው የተመለሰው እነዚያው ያልተዘጋጁ ቆነጃጅት ገና በህይወት እያሉና ዘይት ሊገዙ በሄዱበት ወቅት ነው፤ ስለዚህ እነርሱ ገና በሕይወት እያሉ በገዛ ዘመናቸው ያኔውኑ ምጽአቱ ሳይደርስ አልቀረም።  መክሊትን በተቀበሉ ባሮች ምሳሌም ውስጥም ያየነው እንደሆነ ጌታው ሊቆጣጠራቸውና አደራውን ከትርፉ ጋር መልሶ ሊረከብ ተመልሶ የመጣው ወደነዚያው መክሊቱን ወደ ሰጣቸው የሰዎች ቡድን ነው። ወደ እነርሱም ተመልሶ መክሊታቸውን እንዴት እንደተጠቀሙበት ካየ በኋላ ከእነርሱ መካከል በጎ ያደረጉትን ሸልሟቸዋል። ከእነርሱም መካከል ክፉ ያደረጉትን ዘልፎ ቀጥቷቸዋል።  ይህ በግልጽ የሚያሳየን ተመልሶ የመጣው አደራውን በተቀበሉት ሰዎች የሕይወት ዘመን ውስጥ መሆኑን ነው። ጌታ አደራውን ወደተቀበሉት እንጂ አደራውን ሲሰጥ ወዳልነበሩት ሰዎች አልመጣም፣ አይመጣምም።

ጌታ ኢየሱስ ይህንን  በማቴዎስ  ወንጌል የተዘገበ ንግግሩን ሲያደርግ ጊዜው  በ30 ዓ.ም አካባቢ ነበር - ተመልሶ ለመምጣት ተስፋ የሰጠውም እርሱ እየተናገራቸው በነበሩት ሰዎች የሕይወት ዘመን/ትውልድ ውስጥ የመሆኑ እውነታ  ኢየሱስ ስለ ዳግም ምጽአቱ በሌሎች በርካታ የአዲስ ኪዳን ምንባባትና መግለጫዎች ውስጥ  ከተናገራቸው  ሌሎች ንግግሮቹ ጋር ፍጹም ይዛመዳል።  ለምሳሌ፣ በማቴዎስ 16፥ ​28 ላይ፣ ኢየሱስ “እውነት እላችኋለሁ  በዚህ ከሚቆሙት ሰዎች መካከል [የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን አድማጮቹን ነው]፣ የሰው ልጅ በመንግሥቱ ሲመጣ እስኪያዩ ድረስ ሞትን የማይቀምሱ አንዳንድ አሉ” ብሏል። በማቴዎስ 24፥ 30-34 ላይም፣ ኢየሱስ እንዲህ ብሏል፡- “የሰው ልጅ በኃይልና በታላቅ ክብር በሰማይ ደመና ሲመጣ ያዩታል… ይህ ሁሉ (ዳግመኛ ምጽአቱን ጨምሮ) እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም" በማለት ተናግሯል። (በተጨማሪ ማቴዎስ 10፥ 23 እና 26፥ 64 ላይ ያለውን ተመልከቱ)። 

ኢየሱስ በማቴዎስ ወንጌል ባሉት ሁለት ምሳሌዎች ውስጥ ከተናገረውና በነዚህ ንግግሮቹ ከተገለጠው አመጣጡ በተለየ ሊታሰብና ሊገመት የሚችል ሌላ አመጣጥን በሌላ በየትም የንባብ ክፍል ተናገሮ እንደነበር ሊጠቁም የሚችል አንድም የመጽሐፍ ቅዱስ ማስረጃ በየትኛውም የአዲስ ኪዳን ገጽ ማግኘት አይቻልም።  ኢየሱስ በእርግጠኝነት ስለ ሌላ አይነት መምጣት ተናግሮ ቢሆን ኖሮ፣  የወንግሉ ጸሐፊ ማቴዎስም ያንንው በዘገበልን ነበር።  ስለ ዳግም ምጽአቱም ሆነ ተያያዥ ርዕሰ ጉዳዮች በወንጌላዊው የተዘገበ ማንኛውም የኢየሱስ ንግግር  መነበብ ያለበትም በአውዱ ውስጥ ነው፣ እንጂ የራሳችንን ግምትና ትርጉም በምንባቡ ውስጥ ለመሰንቀር ምንም መብት የለንም። እንደዚያ በማድረግ ቃሉን ለራሳችን ፍጆታ ግምቶቻችን ውስጥ የምንፈልገው ከሆነም ይህ  Exegesis [ኤክሰጀሲስ] ሳይሆን Eisegesis [ኢይሴጀሲስ] ይሆናል። [ማስታወሻ፣ Eisegesis ማለት፡- “የአንድን ሰው ቅድመ-ግምት እና የአስተሳሰብ ዝንባሌውን በምንባብ ውስጥ አስገብቶ (ሰንቅሮ) ማንበብ” ማለት ነው።  በሌላ በኩል ግን  Exegesis ፡- “የንባብ ክፍሉ ራሱ ስለራሱ እንዲናገር ማድረግ” ማለት ነው።]

ኢየሱስ በምሳሌዎቹ ውስጥ ስለ ሌላ መምጣት እየተናገረ ቢሆን ኖሮ፣ በእርግጥ ኢየሱስ ራሱ ወይም ማቴዎስ እንዲሁ ያለ ነገር ይናገሩ ነበር!  ያንን ግን አላደረጉም።.

# ሁለተኛ፣ ዳግመኛ ምጽአቱ ረዘም ላለ ጊዜ ይዘገያል እንጂ ቶሎ አይሆንም ሲሉ  ይጠብቁ የነበሩት በኢየሱስ ዘመን የነበሩት ዓመፀኛ ሰዎች ናቸው እንጂ ጻድቃን የሆኑ የቤተክርስቲያን ቅዱሳን አልነበሩም። በምሳሌዎቹ  በክፉ አገልጋይ ምሳሌ የጠቀሳቸው፣ "ጌታዬ እስኪመጣ ይዘገያል" ያሉትን እነዚህን ሰዎች ጌታ ኢየሱስ “ክፉ ባርያዎች” ብሏቸዋል (ማቴ. 24፥ 48)።  ጳውሎስም “የጨለማ ልጆች” በማለት ገልጿቸዋል (1 ተሰ. 5፥ 3-5)።  ጴጥሮስም “ዘባቾች” ብሏቸዋል (2ጴጥ. 3፥ 3-4)።  ጻድቃን ግን ኢየሱስ በቅርቡ እንደሚመጣ ያምኑና ይጠባበቁ፣ ያስጠነቀቁም ነበር (ያዕ. 5፥ 7፣ 1 ጴጥ. 4፥ 17፣ ፊልጵ. 4፥ 5፣ ራዕ. 22፥ 6–12)።

ኢየሱስ በእስሩ ቆነጃጅት ምሳሌ ስለ “መዘግየት” መናገሩ እውነት ነው፣ (ይህም በ30 ዓ.ም ላይ የተነገረ ነው)።  በ60 ዓ.ም ላይ ግን፣ የዕብራውያን ጸሐፊ፦ "ሊመጣ ያለው ከጥቂት ጊዜ በኋላ ይመጣል አይዘገይምም" (ዕብራ. 10:36) ሲል መዘግየት እንደማይኖር በግልጽ ተናግሯል።

የኢየሱስ በምሳሌዎቹ ያነሳው "የመዘግየት" ሀሳብ ለአርባ ዓመት (ለአንድ ትውልድ) የሚቆየውን መዘግየት ነበር፣ እንጂ ይሄን ያህል በሺህዎች ለሚቆጠር ዘመን ሳይመጣ ይቆያል ማለት አይደለም። ይልቁንም፣  ኢየሱስ በፍርድ ከመገለጡ በፊት ለትውልዱ ሰዎች እሱ ማን እንደሆነ ለማወቅና ወደ ንስሃ ለመምጣት የሚያስችል በቂ ጊዜ እየሰጣቸው ነበር፤ ጴጥሮስም ስለዚሁ ነገር ሲያመለክት፦ “ለአንዳንዶች የሚዘገይ እንደሚመስላቸው ጌታ ስለ ተስፋ ቃሉ [ስለ መምጣቱ] አይዘገይም፣ ነገር ግን ሁሉም ወደ ንስሐ እንዲደርሱ እንጂ ማንም እንዳይጠፋ ወዶ ስለእኛ ይታገሣል” (2ጴጥ. 3፥ 9) ብሏል። ይህ ትእግስት ወይም በመዘግየት ሃሳብ የተገለጠ የቆይታ ጊዜ፣  ጌታ ኢየሱስ ፍርዱን ከማምጣቱ በፊት የገዛ ትውልዱ ሰዎች እርሱ ማን እንደሆነ እንዲያውቁና እንዲያምኑበት ዕድል እንዲያገኙ በጊዜው ለነበሩት ሰዎች በምሕረት የተሰጣቸው ነበር።  ሆኖም ጌታ ኢየሱስ ከፍ ሲል በማቴዎስ ወንጌል እንዳየነውና በእነዚያ የጊዜ መግለጫዎች ላይ ደጋግሞ እንደተናገረው ይህ መዘግየት የተባለው የቆይታ ጊዜ ማብቂያው “ይህ ትውልድ” ከተባለው ዘመን አያልፍም።

እዚህ ላይ በግልጽ የሚታየውን ንጽጽር ልብ በሉ፤ ጌታ ኢየሱስ በ30 ዓ.ም አካባቢ የዳግመኛ ምጽአቱን ጊዜ አስመልክቶ የተናገረውን ንግግር አስተያዩ።  በ30 ዓ.ም ላይ፣ ኢየሱስ በአንድ ትውልድ ውስጥ እንደገና ተመልሶ እንደሚመጣ ተናግሮ ነበር (ማቴ. 10፥ 23፤ 16፥ 28፣፤ 24፥ 30–34፤ 26፥64)።  ሆኖም ከሠላሳ አምስት ወይም ከዚያ ከሚበልጡ ዓመታት በኋላ፣ “ይህ ትውልድ” በተባለው ዘመን መሟጠጫ ላይ፣ ኢየሱስ አሁንም በመልአኩ አማካኝነት “እነሆ፣ እኔ በቶሎ እመጣለሁ…" (ራዕይ. 22፥ 7፣ 10). ማለቱን ልብ በሉ።  በመካከል ያለው ወደ ሠላሳ አምስት ዓመት ያህል የሚጠጋ የጊዜ መደብ መሆኑንም አስተውሉ። 

ጌታ ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ እንደሚመጣ በገባላቸው የተስፋ ቃል መሰረት፣ በ70 ዓ.ም ላይ ኢየሩሳሌምና መቅደስዋ በወደሙ ጊዜ፣ ዳግመኛ በፍርድ ተመልሶ መጥቷል። ይህንን የተፈጸመ የዳግመኛ ምጽአቱን የፕሪቴሪስት ነገረ ፍጻሜ አቋማችንን አስረግጠን የምንናገርበት ደርዘን ሙሉ ውስጣዊ የቃሉ ማስረጃና ውጫዊ የታሪክ ምስክርነት ለማወቅ፣ ለመጠየቅና ስታምኑ የኖራችሁትን የመጻኢነት አቋም በቃሉ ሚዛን ላይ አስቀምጦ ለመለካት የሚይስችሏችሁ፣ በዚህም የቃሉ ትምህርት ላይ በተቃውሞ ሊቀርቡ በሚችሉ ልዩ ልዩ ክርክሮች ምካቴ የሚሆኑ ሃሳቦችን የሚጠቁሙ ተጨማሪ ጽሁፎችን ማየት ቢያስፈልጋችሁ፣ ብሎገሬን እንድትጎበኙ እጋብዛለሁ።

https://gizachewkr.blogspot.com/2023/12/blog-post.html?m=1

ግዛቸው።

No comments:

Post a Comment