Monday, October 11, 2021

ሞት ድል በመነሳት ተውጧል

ሞት ድል በመነሣት ተውጧል 

በዚህች ጥፈት፣ ከዳግመኛ ምጽአቱ ፓሮዥያው በፊት እና ከዚያ በኋላ ባለው የሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ፣ የሙታንንና የሕያዋንን መዳረሻ አስመልክቶ ግልጽ መሆን ያለባቸውን ጉዳዮች ላካፍላችሁ መልካም ሆኖ ታይቶኛል። በቃሉ መንገድ የምታስቡ ጥቂቶች ያይደላችሁ እና እምነታችሁን የምትጠይቁ በርካቶች እንደምትጠቀሙበት፣ እንደምትጽናኑበትና፣ እንደምትሞገቱበት አስባለሁ። መልካም ንባብ።  

"ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ይህን እላለሁ፦ ሥጋና ደም የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊወርሱ አይችሉም፥ የሚበሰብሰውም የማይበሰብሰውን አይወርስም።…. ይህ የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሊለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሊለብስ ይገባዋልና። ዳሩ ግን ይህ የሚበሰብሰው የማይበሰብሰውን ሲለብስ ይህም የሚሞተው የማይሞተውን ሲለብስ፥ በዚያን ጊዜ፦ ሞት ድል በመነሣት ተዋጠ ተብሎ የተጻፈው ቃል ይፈጸማል።" (1ኛ ቆሮንቶስ 15፥ 50፣ 53-54)

፩. ሟች አባቶች ከፓሮውዥያው አስቀድሞ
1)ገና የእስራኤል ታሪክ ሳይጀመር በፊት፣ በነበረው ርዥም የአባቶች የታሪክ ምዕራፍ ውስጥ ይኖሩ የነበሩ አማኞች ሁሉ፣ በበርካታ ጊዜያት ከተገለጡ ጥንታዊ ኪዳናት አንጓዎች ስር ተካፋይ የነበሩ ናቸው። ለምሳሌ፦ አዳማዊ ቃል ኪዳን፤ የኖህ ቃል ኪዳን፤ አብርሃማዊ ቃል ኪዳን፤ የሙሴ ቃል ኪዳን ወዘተ እያልን ልንጠቅሳቸው እንችላለን። ከአዳም እስከ አብርሃም ዘመን ያሉት ሁሉም የተመረጡ አማኞች ልዩ ልዩ የምድር ህዝቦች  ነበሩ፣ እስራኤል ዘሥጋ ያኔ ገና አልነበረም። ሟቾች የዚያን ዘመን አባቶች ሁሉ በተስፋ ሞተው በሚቀበሩበት ጊዜ ከሥጋቸው ተለይተው ያለ ተዳሳሹ አካልና፣ ደም፣ ነገር ግን በሌላ አንዳች አይነት አካላዊ ቅርጽና ይዘት ይሄዱ ወይም ይወሰዱና ይከማቹ የነበረው ሼዖል ወደተባለ ስፍራ (ወደሀደስ) ነበር። ተስፋቸውም በፍጻሜ ዘመን ላይ በሙታን ትንሳኤ ከዚያ ከተከማቹበት ሼዖል ወጥተው ወደ እግዚአብሔር ሀልዎት ይገቡ ዘንድ ነበር። 

2)ከክርስቶስ የመስቀል ሞቱ አስቀድሞ፣ ማለትም ከአብርሃም እስከ ክርስቶስ ያሉ አባቶች አብዛኞቹ የተመረጡ አማኞች፣ ደግሞ በአመዛኙ ከአይሁድ ወገን የነበሩ ናቸው። ቃል ኪዳኑም ከአብርሃም ጋር ነበር፣ የቃል ኪዳኑ ህዝብ ዘሩም እስራኤል ነበር። ለእስራኤል ዘሥጋ የተሰጣቸው ኪዳንም ብሉይ ኪዳን ነው። እነርሱም በተስፋ በሚሞቱበት ጊዜ ከሥጋቸው ተለይተው ያለ ተዳሳሹ አካልና፣ ደም፣ ነገር ግን በሌላ አንዳች አይነት አካላዊ ቅርጽና ይዘት የሀደስ የእረፍትና የመጽናኛ ዞን ብለን ወደምንጠራው አብርሃምና አባቶች ሁሉ ወዳሉበት "ሀደስ ገነት" ወይም "የአብርሃም ዕቅፍ" ወደሚባለው ስፍራ ሄደው ከአባቶቻቸው ጋር ይከማቻሉ። በዚያም ክርስቶስ በእርገቱ ማርኮ፣ በዳግመኛ ምጽአቱ የሚቀበሉትን ትንሣኤ ሊጠባበቁ ወደሰማያዊው መቅደስ የደጁ አደባባይ ወዳለው ሥፍራ እስኪወስዳቸው ድረስ፣ ከዚያ የሼዖል እስራት ነጻ የሚያወጣቸውን  መሲሁ ኢየሱስን እየተጠባበቁ ይቆያሉ (ዮሐንስ 20፥ 17) 

3) ከመስቀል እና ከትንሣኤው አንስቶ  በ70 አ.ም ላይ እስከተፈጸመው ዳግመኛ ምጽአቱ ድረስ ባለው መካከኛ ጊዜ በነበረው የሽግግር ወቅት፣ እነዚያ ተፈጥሯዊውን ሞት በተስፋና በእምነት የሞቱ የሽግግሩ ዘመን አማኝ ደቀመዛሙርት፣ ክርስቶስ በእርገቱ፣ ሀደስ ከሆነው ገነት ጋር በምርኮ የወሰዳቸውና በአብርሃም ዕቅፍ የነበሩ የአሮጌው ኪዳን አማኞች ተሰብስበው ወደነበሩበት የጻድቃን መንፈሶች ማህበር  ሊቀላቀሉ ይወሰዱ ነበር። በዚያም በዳግመኛ ምጽአቱ የሚቀበሉትን ትንሣኤ እየተጠባበቁ ይቆያሉ። ይህንን ገነት የተባለ ስፍራ ከክርስቶስ እርገት በኋላ የምናገኘው፣ ሀደስ /ሲዖል በተባለ የቀድሞ መገኛው ሳይሆን ይልቁንም በሦስተኛው ሰማይ እንደሆነ አስተውሉ (2ቆሮንቶስ 12፥ 2-4)። ሲዖልንና መቃብርን ድል ነስቶ ከሃያላን ጋር ምርኮን የተካፈለው ክርስቶስ  በእርገቱ ይህንኛውን የሀደስ ዞን/ ገነትን ማርኮ በመውሰድ ወደ ሰማያዊው ስፍራ የደጁ አደባባይ አምጥቶታልና። በዚያም በዳግመኛ ምጽአቱ የሚገለጠውን የቤዛነታቸውን ቀን ይጠባበቁ ዘንድ አስቀድሞ በእርገቱ የሰበሰባቸውና ከዳግመኛ ምጽአቱ ፓሮዥያው አስቀድሞ በተለያየ ምክንያት ተፈጥሯዊውን ሞት የሞቱ የጻድቃን መንፈሶች ሁሉ ከስጋቸው ተለይተው፣ ያለ ተዳሳሹ አካልና ደም፣  ነገር ግን በሌላ አንዳች አይነት አካላዊ ቅርጽና ይዘት ሆነው  ትንሣኤን እየተጠባበቁ ተከማችተዋል።

4) በተጨማሪም ለየት ባለ ሁኔታ የሽግግሩ ዘመን ሰማዕታትን ጨምሮ፣ በአይነታቸው ለየት ያሉ ጥቂት የማይባሉ የብሉይ ኪዳን ሰማዕታትም ሁሉ፣ ከስጋቸው ተለይተው፣ ያለ ተዳሳሹ አካልና ደም፣  ነገር ግን በሌላ አንዳች አይነት አካላዊ ቅርጽና ይዘት በሰማያዊው መቅደስ በቅድስተ ቅዱሳን የውጭው አደባባይ ደማቸውን በምድር ላይ ባፈሰሱ ገዳዮቻቸው ላይ የእግዚአብሔርን ፍርድና በቀል እየጠየቁ በመሰዊያው ዙርያ ሆነው፣ ትንሣኤን ለማግኘት የክርስቶስን ፓሮዥያ እየተጠባበቁ ነበሩ። እነርሱም ከዳግመኛ ምጽአቱ አስቀድሞ የፍርዱንና የበቀሉን ቀን ለጥቂት ዘመን ታግሰው እንዲጠብቁ ነጩን መጎናጸፊያ የተቀበሉት ናቸው፤ ይኸውም "ጥቂት ዘመን" ጌታ እስኪመጣ ድረስ የነበረው የሽግግሩ ወቅት ሲሆን፣ በዚያ የሽሽግር ወቅት ዮሐንስ ራእዩን እየጻፈ በነበረበት ጊዜ ገና አዳዲስ የሰማዕታት ድል ነሺዎች እየተገደሉ በቁጥራቸው ላይ ሊጨመሩ ያለማቋረጥ ወደዚያ ስፍራ እየገቡ ነበር፤ ስለዚህ  ብዛታቸው ሊቆጠር የማይችል ነበር (ራእይ 4፥ 4፤ 7፥ 9፤ 7፥ 13-14)። 

¶ እንግዲህ ከላይ በተለያየ መልኩ ያየናቸው ሁሉም አይነት አማኝ ሟቾች፣ ከስጋቸው ተለይተው፣ ያለ ተዳሳሹ አካልና ደም፣  ነገር ግን በሌላ አንዳች አይነት አካላዊ ቅርጽና ይዘት ሆነው በዳግመኛ ምጽአቱ ትንሳኤን የሚቀበሉበትን የቤዛነታቸውን ቀን እስከ 70 አ.ም ድረስ መጠበቅ ነበረባቸው። 

# የማያምኑ ሟቾች እድላቸው፦
ከ70 አ.ም በፊት በነበረው የዘመን ምድብ የሞቱ የማያምኑ ሁሉ ግን ከስጋቸው ተለይተው፣ ያለ ተዳሳሹ አካልና ደም፣  ነገር ግን በሌላ አንዳች አይነት አካላዊ ቅርጽና ይዘት በሲኦል የስቃይ ስፍራ ሆነው በ70 አ.ም የሚገለጠውን የመጨረሻውን የክርስቶስን ፍርድ ይጠብቁ ነበር። እነዚህም ሁላቸውም ከአይሁድና ከአህዛብ ወገን የሆኑ ያልዳኑ፣ ያልተዋጁ፣ ያላመኑና ያልተመረጡ ናቸው። እነርሱም በ70 አ.ም በነጩ ዙፋን ፍርድ ይጠፉ ዘንድ ለዘላለም በእሳት ባህር ሊነዱ ፍርዳቸውን ተቀብለዋል። ይህም ማለት በብሉይ ኪዳን ዘመን ላይ እየኖሩ የማያምኑ የነበሩ ሟቾች ሁሉ በሞታቸው ጊዜ ከአጸደ ሥጋ ተለይተው በአጸደ ነፍስ ሳሉ በሀደስ የስቃይ ዞን ሆነው በ70 አ.ም የሚገለጠውን የመጨረሻ ፍርድ ይጠባበቁ ነበር ማለት ነው።

፪. ሟች ቅዱሳን በፓሮውዥያው ወቅት
5) በ70 አ.ም በተፈጸመው የዳግመኛ ምጽአቱ ፓሮውዥያ ወቅት፣ ክርስቶስ ከዚህ በላይ የጠቀስናቸውን እነዚህን ሟች ቅዱሳን ሁሉ በሰማያት ከያሉበት ሰብስቦ በአየር ላይ ወይም በሰማያት መካከል ወዳለ ሊታይ ወደማይቻል ሰማያዊ ስፍራና ግዛት ከራሱ ጋር አምጥቷቸዋል። እነርሱም እስከፍጻሜው ድረስ የታመኑ ሆነው በመገኘታቸው የተፈረደላቸው፣ ለአለምና ለዘላለም ከክርስቶስ ጋር ሊነግሱ እና ሊገዙ መንፈሳዊና ሰማያዊ ሆኖ በከበረ የትንሣኤ አካል ወደ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም የገቡ ናቸው።

6) በ70 አ.ም ላይ በክርስቶስ የዳግመኛ ምጽአቱ ፓሮውዥያ ወቅት ገና ሳይሞቱ በሕይወት የነበሩ እነዚያ ጥቂት የመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ቅዱሳን ደግሞ፣ ጌታ ሲገለጥ በቅጽበተ አይን ተለውጠው ተነጥቀዋል። [መነጠቅ በግሪኩ "harpazo" የተሰኘው ቃል ስትሮንግስ በተሰኘው የግሪክ የቃላት መፍቻ #726  ከሩቅ ፣ ወደ ላይ ይዞ ማንሳት፣ ነቅሎ ወይም ጎትቶ (በኃይል መውሰድ፣ መንጠቅ፣ መንቀል፣ ወደላይ ማንሳት፣ ወይም ይዞ በኃይል ወደላይ መሳብ የሚል ትርጉም ተሰጥቶትታል።] ይኸውም። ተለውጦ መነጠቅ ሥጋዊውን ሞትን መለማመድ ሳያስፈልጋቸው ጌታን በአየር ላይ ወይም በመካከለኛው ሰማይ ላይ መገናኘት የሚያስችላቸው ነው። እነርሱም እስከፍጻሜው ድረስ የታመኑ ሆነው በመገኘታቸው የተፈረደላቸው፣  ለአለምና ለዘላለም ከክርስቶስ ጋር ሊንነግሱ እና ሊገዙ መንፈሳዊና ሰማያዊ ሆኖ በከበረ የተለወጠ አካል ወደ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም የገቡ ናቸው።

"አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት የለም። ቅድስቲቱም ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም፥ ለባልዋ እንደ ተሸለመች ሙሽራ ተዘጋጅታ፥ ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ። ታላቅም ድምፅ ከሰማይ፦ እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው ከእነርሱም ጋር ያድራል፥ እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤ እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና ብሎ ሲናገር ሰማሁ።" (ራእይ 21፥ 1-4)

"ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክና በጉ መቅደስዋ ናቸውና መቅደስ በእርስዋ ዘንድ አላየሁም። ለከተማይቱም የእግዚአብሔር ክብር ስለሚያበራላት መብራትዋም በጉ ስለ ሆነ፥ ፀሐይ ወይም ጨረቃ እንዲያበሩላት አያስፈልጓትም ነበር። አሕዛብም በብርሃንዋ ይመላለሳሉ፥ የምድርም ነገሥታት ክብራቸውን ወደ እርስዋ ያመጣሉ፤ በዚያም ሌሊት ስለሌለ ደጆችዋ በቀን ከቶ አይዘጉም፥ የአሕዛብንም ግርማና ክብር ወደ እርስዋ ያመጣሉ። ለበጉም በሆነው በሕይወት መጽሐፍ ከተጻፉት በቀር፥ ጸያፍ ነገር ሁሉ ርኵሰትና ውሸትም የሚያደርግ ወደ እርስዋ ከቶ አይገባም።" (ራእይ 21፥ 22-27)

በ70 አ.ም ከእርሱ ጋር ያመጣቸው እነዚህ ቅዱሳን ሁሉ በሰማያዊቷ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ከክርስቶስ ጋር የዘላለም ሕይወት አላቸው። በዳግመኛ ምጽአቱ ፓሮውዥያ ወቅት እነዚህ ሁሉ የተለያዩ ቡድኖች የተዋጁ ፣ የተመረጡ የብሉይ ኪዳን እና የሽግግር ወቅት አማኞች አዲሱን፣ የማይበሰብሰውን ፣ የማይሞተውን ፣ የከበረውን ፣ መንፈሳዊውን ፣ ሊታይም የማይችለውን፣ ሰማያዊ አካል በትንሣኤ እና በመለወጥ ተቀብለዋል። "ትንሣኤና ሕይወት" ከሆነው ከኢየሱስ "የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፤" (ዮሐንስ 11፥ 25) የሚል ጽኑ ተስፋ ይዘው፣ በሥጋ ቢሞቱም እርሱ በመጨረሻው ቀን እንደሚያስነሳቸው አምነው ሞተዋል፤ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ሳይሞቱ ቢቆዩ ደግሞ በቅጽበት አይን ተለውጠው እንደሚነጠቁ ተስፋ አድርገው ኖረዋል። በመጨረሻውም ቀን ሙታንን አስነስቶ ከእርሱ ጋር አምጥቷቸዋል፣ ሕያዋንንም ለውጦ በንጥቀት ወስዷቸዋል።

፫. ሟች ክርስቲያኖች ከፓሮውዥያው በኋላ
7) በ70 አ.ም ከተፈጸመው የክርስቶስ ዳግመኛ ምጽአት ፓሮውዥያ በኋላ፣ የአዲሱ ኪዳን የወንጌል መንግስት እርሱም አዲሱ ሰማይና አዲሱ ምድር በሙላት ተመስርቶ ተገልጧል። የአሮጌው ኪዳን አይሁዳዊ የኃይማኖት መስተዳድር እርሱም አሮጌው ሰማይ አልፏል። በመጽሐፍ ቅዱስ እንደ እግዚአብሔር ምርጥ ሕዝብ የሚታወቀው የእስራኤል ሕዝብ፤ የኢየሩሳሌም ከተማ እና መቅደሱ እርሱም አሮጌው ምድር፣ ሁሉም ተደምስሶ አልፏል። ከእንግዲህም በኋላ በእግዚአብሔር ዋጆአዊ እቅድ ውስጥ ፈጽሞ ምንም ቦታ የሌላቸው ሆነዋል። 

ከ70 አ.ም በኋላ ያለን እኛን በክርስቶስ ያመንነውንና፣ ከዚህም በኋላ ለአለምና ለዘላለም በእርሱ እያመኑ ወደአካሉ ህብረት የሚገቡትን ሁሉ ጨምሮ፣ ገና በዚህ ህይወት እያለን እግዚአብሔር የዋጀን ምርጦች ሁላችንም (የተመረጡ አይሁድ እና የተመረጡ አህዛብ ሁሉ) በክርስቶስ የተፈረደልንና የተጠናቀቀ ድነታችንን ፍጻሜና ሙላት የተቀበልን ነን። ዘላለማችንንም በአዲሲቱ ኢየሩሳሌም ከክርስቶስ ጋር ልናሳልፍ በእምነት ወደሀልዎቱ ገብተናል። ክርስቲያኖች ተብለን በክርስቶስ እንደተባበረ አንድ ሕዝብ እና አንድ አካል ነን እንጂ ወደፊት መቼም ቢሆን አይሁድ ወይም አህዛብ ተብለን አንጠራም (ገላትያ 3፥ 16፣ 28-29)። ሁላችንም በየግላችን በእንድ ወይም በሌላ ምክንያት በሥጋ እንሞታለን፣ ያኔም ወዲያውኑ በማይሞተው፣ በማይበሰብሰው፣ በከበረው፣ መንፈሳዊ በሆነው፣ ሊታይ በማይችለው ሰማያዊ አካል፣ ለዘላለም ከክርስቶስ ጋር በሰማያዊ ሀልዎቱ ፊት በክብር ለመሆን ወደ ሰማይ እንሄዳለን። *ትንሣኤና ሕይወት" ከሆነው ከኢየሱስ ዘንድ "ሕያው የሆነም የሚያምንብኝም ሁሉ ለዘላለም አይሞትም" (ዮሐንስ 11፥ 26) የሚል እንዲህ ያለ ጽኑ ቃል ያለን እኛ ይህንን እንዲሁ በጸጋ ያገኘነውን አዲሱን ዘላለማዊ ሕይወት ይዘን እንሞታለን፣ እርሱ ሕያው ስለሆነም ሕያዋን ነንና ለዘላለም አንሞትም።

# የማያምኑ ሟቾች ፍጻሜአቸው፦
ከ70 አ.ም በኋላ ባለው በዚህ ህይወት ሳሉ ባለማመን ጸንተው የሚሞቱ ሁሉ፣ ከላይ እንዳነሳነው እነርሱም አስቀድሞ በዳግመኛ ምጽአቱ ፓሮውዥያው  በተፈጸመው በታላቁ የነጩ ዙፋን ፍርድ ውሳኔ ውስጥ የሚጠቃለሉ ናቸው። እነዚህም ሁላቸው ከ70 አ.ም በኋላ የኖሩና የሞቱ በጠቅላላው የክርስቶስን ወንጌል የገፉ፣ ያልዳኑ፣ ያልተዋጁ፣ ያላመኑና ያልተመረጡ የጠፉ የምድር ህዝቦች ናቸው። ማናቸውም ቢሆኑ በበጉ የሕይወት መጽሐፍ ላይ ስሞቻቸው ያልተጻፉ ናቸው። "በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል" (ዮሐንስ 3፥ 18) እንደተባለ፣ ዘላለማዊው ፍርዳቸው እና ኩነኔያቸውም አስቀድሞ በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የተመደበ እና በይፋ የታወጀ ነው። ኢየሱስ ክርስቶስ በህይወታቸው ጌታቸውና መድሃኒታቸው እስካልሆነ ድረስ ማናቸውም ቢሆኑ በማናቸውም ምክንያት በሚሞቱበት ጊዜ በ70 አ.ም ላይ በይፋ የተገለጠውን ዘላለማዊ ቅጣታቸውን በየራሳቸው ይቀበሉ ዘንድ ከስጋቸው ተለይተው፣ ያለ ተዳሳሹ አካልና ደም፣  ነገር ግን በሌላ አንዳች አይነት አካላዊ ቅርጽና ይዘት ይጠፉ ዘንድ በቀጥታ ወደ እሳት ባህር ይሄዳሉ (ራእይ 21፥ 8)። ስለዚህ ወደ ጸጋው መግባትን ያገኘች ቤተክርስቲያን ሌሎች በውጭ ያሉ በሥጋ ከመሞታቸው በፊት ፈጥነው እንዲገቡ ሰውን ሁሉ በፍቅር እየለመነች ለንስሃ እና ለእምነት በወንጌል ትጣራለች።

በመጨረሻም፣ በዚህ ርዕሰ ጉዳይ የበለጠ ለማሰብ ፍላጎት ካደረባችሁ በፊልጵስዩስ 3፥ 21 ላይ ተመስርቼ፣ "የተዋረደው 'ሥጋችን' ልውጠት" በሚል ርዕስ በጸሎትና በንባብ ያቀረብኩትን ሰፊ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ጊዜ ወስዳችሁ እንድትመለከቱት በአክብሮት እጋብዛለሁ። በውስጡም የሚያጽናና እና የሚሞግት የወንጌል ጸጋ ቀርቦበታልና ትካፈሉት ዘንድ እነሆ ሊንኩ፦  
https://www.facebook.com/1889309531297484/posts/3265218500373240/ 

ግዛቸው ከበደ /ቄስ/