Friday, May 30, 2025

የዳግመኛ ምጽአቱ አይነተኛ ሰበብ

የዳግመኛ ምጽአቱ አይነተኛ ሰበብ 



ዳግመኛ ምጽዓት ሊፈጸም የተቀጠረለትን ትክክለኛውን መጽሐፍ ቅዱሳዊ ጊዜ በተሻለ ሁኔታ ለመረዳት፣ የዳግመኛ ምጻቱን ተፈጥሮ ከመረዳት ባልተናነሰ የዳግመኛ ምጽአቱን አይነተኛ መግፍኤ ምክንያትም በወጉ መረዳት ያስፈልጋል። በአመዛኙ ኢየሱስ ስለ ብድራት፣ ስለፍርድ፣ ስለ ቁጥጥር ቀን ባስተማረበት ምሳሌዎቹ ይህንን የዳግመኛ ምጽአቱን ሰበብ እንመለኩታለን። ኢየሱስ ስለ ክፉዎቹ የወይን እርሻ ገበሬዎች በተናገረው ምሳሌ ላይ ይህን ጉዳይ በግልጽና በቀጥታ አስተምሮታል።


“ሌላ ምሳሌ ስሙ። የወይን አትክልት የተከለ ባለቤት ሰው [እግዚአብሔር] ነበረ፤ ቅጥርም ቀጠረለት፥ መጥመቂያም ማሰለት፥ ግንብም ሠራና ለገበሬዎችር [እስራኤል] አከራይቶ ወደ ሌላ አገር ሄደ። የሚያፈራበትም ጊዜ ሲቀርብ፥ ፍሬውን [መልካምን ስራ] ሊቀበሉ ባሮቹንል [የብሉይ ኪዳን ነብያት] ወደ ገበሬዎች ላከ። ገበሬዎቹም ባሮቹን ይዘው አንዱን ደበደቡት አንዱንም ገደሉት ሌላውንም ወገሩት። ደግሞ ከፊተኞች የሚበዙ ሌሎች ባሮችን ላከ፥ እንዲሁም አደረጉባቸው። በኋላ ግን፦ ልጄንስ ያፍሩታል ብሎ ልጁን [ኢየሱስ] ላከባቸው። ገበሬዎቹ ግን ልጁን ባዩ ጊዜ እርስ በርሳቸው፦ ወራሹ ይህ ነው፤ ኑ፥ እንግደለውና ርስቱን እናግኝ ተባባሉ። ይዘውም ከወይኑ አትክልት አወጡና ገደሉት [ስቅለቱ]። እንግዲህ የወይኑ አትክልት ጌታ በሚመጣ ጊዜቱ [የኢየሱስ ዳግም ምጽ አጽአት] በእነዚህ ገበሬዎች ምን ያደርግባቸዋል? እነርሱም፦ ክፉዎችን [እስራኤል] በክፉ ያጠፋቸዋል፥ የወይኑንም አትክልት ፍሬውን በየጊዜው ለሚያስረክቡ ለሌሎች ገበሬዎች [ክርስቲያኖች] ይሰጠዋል አሉት። ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፦ ግንበኞች የናቁት ድንጋይ እርሱ የማዕዘን ራስ ሆነ፤ ይህም ከጌታ ዘንድ ሆነ፥ ለዓይኖቻችንም ድንቅ ነው የሚለውን ከቶ በመጽሐፍ አላነበባችሁምን? ስለዚህ እላችኋለሁ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተች [ከእስራኤል] ትወሰዳለች ፍሬዋንም ለሚያደርግ ሕዝብ [ለክርስቲያኖች] ትሰጣለች። በዚህም ድንጋይ ላይ የሚወድቅ ይቀጠቀጣል፤ ድንጋዩ ግን የሚወድቅበትን ሁሉ ይፈጨዋል። የካህናት አለቆችና ፈሪሳውያንም ምሳሌዎቹን ሰምተው ስለ እነርሱ እንደ ተናገረ አስተዋሉ፤” (ማቴዎስ 21፥ 33-45)


ይህ ምሳሌ እንደሚያሳየው፣ የእግዚአብሔር አላማና ፍላጎት እስራኤል ፍሬ እንዲያፈራለት (መልካምን ሥራ እንዲያደርግለት) ነው፣ ያንንም ይጠባበቅ ነበር። “ፍርድን ተስፋ ያደርግ ነበር፥ እነሆም ደም ማፍሰስ ሆነ፤ ጽድቅንም ይተማመን ነበር፥ እነሆም፥ ጩኸት ሆነ።” (ኢሳይያስ 5፥ 7) እንደተባለው፤ በአብዛኛው የእስእስራኤል ታሪክ ውስጥ የሆነው እግዚአብሔር ይጠባበቅ ከነበረው ፍጹም ተቃራኒው ነው። እንዲያውም አንዳንድ ጊዜ እስራኤል በዙርያዋ ካሉ አረማውያን ጎረቤቶቿ ይልቅ በክፋትና በአመጽ ብሳ ትገኛለች። (2ዜና 33፥ 9፣ ሕዝ. 5፥ 6)። እግዚአብሔር እስራኤልን ንስሐ እንዲገቡ ለማድረግ (ወደ እርሱ ይመለሱ ዘንድ) በየጊዜው በርካታ ነቢያትን ልኮላቸዋል። እስራኤል ግን እነዚያን ነቢያት አሳደዱ፣ አንገላተውም ገደሏቸው። በመጨረሻም እግዚአብሔር “በእውነት ልጄንስ ያከብሩታል” (ማቴ. 21፥ 37) ብሎ የገዛ ራሱን ልጅ ላከው። እስራኤል ግን እርሱንም ገደለችው። (ቴክኒካሊ፣ ሮማውያን ኢየሱስን የገደሉት ቢሆንም፣ ያንን የፈጸሙት ግን በአይሁድ ልመናና ጥያቄ መሰረት ነው- ሉቃስ 23፥ 21፣ ዮሐንስ 1፥ 11 ተመልከቱ)። ይህ የመጨረሻው እድላቸው ነበር፣ የእግዚአብሔርም ትእግስት እዚህ ላይ አበቃ። ምሳሌው እንደሚለው፡- “የወይኑ አትክልት ባለቤት በመጣ ጊዜ . . . እነዚያን ክፉዎች በክፉ ያጠፋቸዋል፥ የወይኑንም እርሻ ለሌሎች ፍሬውን በየጊዜው ለሚያስረክቡ ገበሬዎች ያከራያል” (ማቴ. 21፥40-41)።


ይህ እንግዲህ በማቴዎስ መጽሐፍ ውስጥ የምናገኘው የዳግም ምጽአት ትምህርት አንድ ሌላ ማጣቀሻ ነው!


ምሳሌው በመቀጠል “ስለዚህ እላችኋለሁ [እስራኤል]፣ የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተ ትወሰዳለች ፍሬዋንም ለሚያደርግ ሕዝብ ትሰጣለች። (ማቴዎስ 21፥ 43) መንግሥቱ ለየትኛው “ህዝብ” ነው የተሰጠው? ለክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን ነው፣ እርሷም ከእስራኤል ጻድቃን ቅሬታዎች (ጥቂት የተመረጡ) ጋር የአሕዛብ ጻድቃን ቀሪዎችን ያቀፈች ናት።


እግዚአብሔር ከመጀመሪያ ለእስራኤል የነበረው አሳብ ለእርሱ ቅዱስ ሕዝብ እንዲሆኑለት ነበር። እግዚአብሔር አሮጌውን ቃል ኪዳን ሲያቆምላቸው (ይኸውም ከክልበ በ1500 ገደማ ነው)፣ ይህም በመሠረቱ በእግዚአብሔርና በእስራኤል መካከል የተደረገ የቃል ኪዳን ስምምነት ውል ነበር - ያኔም እግዚአብሔር እንዲህ አለ፡- “ቃሌን በእውነት ብትሰሙ ኪዳኔንም ብትጠብቁ፥ ምድር ሁሉ የእኔ ናትና ከአሕዛብ ሁሉ የተመረጠ ርስት ትሆኑልኛላችሁ፤ እናንተም የካህናት መንግሥት የተቀደሰም ሕዝብ ትሆኑልኛላችሁ” (ዘጸአት 19፥ 5-6,) እግዚአብሔር እስራኤል የተቀደሰ (የተለየ) ሕዝብ እንድትሆንለት ነበር የሚፈልገው፣ የቃል ኪዳኑም ግብ ይኸው ነበር። ቃል ኪዳኑ ግን የቆመበት ቅድመ ሁኔታ አለው እርሱም፡- “ቃል ኪዳኔን ብትጠብቁ... ለኔ ልዩ ርስት፣ የተቀደሰ ሕዝብም ትሆኑልኛላችሁ” ይላል። በሙሴ ቃል ኪዳን፣ በኦሪት፣ በሕጉ የተነገሩትት የብሉይ ኪዳን በረከቶች በእስራኤል መታዘዝ ላይ የተመሰረቱ ነበሩ። በሚያሳዝን ሁኔታ ኢየሱስ ስለ እነዚያ ክፉ የወይን ቦታ ገበሬዎች ከፍ ሲል በተናገረው ምሳሌ እንዳመለከተው እስራኤል በቃል ኪዳኑ የተሰጣትን ተስፋ እንዳታገኝ እነዚያን ቅድመ ሁኔታዎቹ መታዘዝ ተስኗታል። እስራኤል በህጉ ኖራ ልታቀርበው የሚገባትን የጽድቅ ፍሬ ማፍራት ተስኗታል። እግዚአብሔርም እርሷን ለማረም በየዘመኑ ነቢያትን ቢልክም እስራኤል ግን አልሰማቻቸውም፣ አሳዳም ገድላቸዋለች። በመጨረሻ የገዛ ራሱን ልጅ ኢየሱስን ቢልከው እስራኤል እርሱንም ገደለችው።


ስለዚህም በምሳሌው እንደተገለጠው የወይኑ እርሻ ባለቤት (እግዚአብሔር) በመምጣቱ እነዚያን ክፉዎች በክፉ ያጠፋቸዋል (ማቴ. 21፥ 40) መንግሥታቸውንም ነጥቆ ለሌላ ሕዝብ ይሰጣል (ቁ. 41)።


የዳግመኛ ምጽአቱ አይነተኛ ምክንያትም ይህ ነው፣ የክፉዎች ፍርድ እና የጻድቃን ብድራት። ይህንን ማስተዋል ለተቻለው ከእንግዲህ የቀረለት፥ የሚጠባበቀው፣ ሌላ ዳግመኛ ምጽአት የ ለውም።


ከላይ እንደተገለጸው፣ ከእስራኤል የተነጠቀ መንግሥትን የተቀበለው አዲሱ ሕዝብ የክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን ተብላ የምትጠራው ናት። እንዲያውም ሐዋርያው ​​ጴጥሮስ እነርሱን እንዴት እንደገለጻቸው አስተውሉ:- “እናንተ ግን [ክርስቲያኖች] ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፣ የንጉሥ ካህናት፣ ቅዱስ ሕዝብ፣ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ” ይላል። ይህ አገላለጽ ቀደም ሲል በዘጸአት 19፥ 5-6 ባለው ላይ እግዚአብሔር እስራኤልን የገለጸበት መንገድ ነው፡ ቅዱስ ሕዝብ፣ የካህናት መንግሥት፣ ርስት። በሌላ አነጋገር የክርስቲያን ቤተ ክርስቲያን አዲሷ የእግዚአብሔር ቅድስት ሀገር ናት ማለት ነው። ቤተ ክርስቲያን አዲሷ የእግዚአብሔር እስራኤል ናት (ገላ. 6፥ 15-16)። ምንም እንኳን ክርስቲያኖች ብዙውን ጊዜ ራሳቸውን ለመግለጥ በዚህ መጠሪያ ባይጠቀሙም ቤተ ክርስቲያን ግን የአዲስ ኪዳን እስራኤል ልትባል ትችላለች።


ይህንን አትርሱ፣ ይህ አዲስ ህዝብ በመጀመሪያ በአንጾኪያ ክርስቲያን ተብሎ የተጠራው የእምነት ማህበረሰብ ነው (የሐዋርያት ሥራ 11፥ 26)፤ እርሱም ሁለቱንም ማለትም አይሁዳውያንና አሕዛብን ያቀፈ የአማኞች ስብስብ ነው። በመሠረቱ፣ ቤተ ክርስቲያን በመጀመሪያ በተቋቋመችበት ጊዜ፣ “የእስራኤል ልጆች ቁጥር ምንም እንደ ባሕር አሸዋ ቢሆን ቅሬታው ይድናል፤ ጌታ ነገሩን ፈጽሞና ቆርጦ በምድር ላይ ያደርገዋልና ብሎ ስለ እስራኤል ይጮኻል” (ሮሜ. 9፥ 27) እንደተባለ ኢየሱስን የሚያውቁ እና የተከተሉትን አይሁዶችን ብቻ ያቀፈች ነበረች።  


በመጨረሻ ግን፣ “ለአሕዛብም ምልክትን ያቆማል፥ ከእስራኤልም የተጣሉትን ይሰበስባል፥ ከይሁዳም የተበተኑትን ከአራቱ የምድር ማዕዘኖች ያከማቻል።” (ኢሳይያስ 11፥ 12፤) በሚል በብሉይ ኪዳን አንድ ቀን እንደሚፈጸም እንደተነገረው የትንቢት ተስፋ አሕዛብም ወደ ቤተ ክርስቲያን መጨመር ጀመሩ። (በተጨማሪ ኢሳ. 55፥ 5፤ 65፥ 1 ተመልከቱ)። እንግዲህ በዚህ አዲስ ህዝብ ውስጥ፣ ማለትም በቤተ ክርስቲያን፣ በአይሁድ እና በአሕዛብ መካከል ምንም መለያየት የለም (ኤፌ. 3፥ 6)። ኢየሱስ በሁለቱ መካከል የነበረውን የጥል ግድግዳ በሞቱ አፍርሶታልና (ኤፌ. 2፥ 14)። አይሁድና አሕዛብም በክርስቶስ አንድ ናቸው (ገላ. 3፥ 28)። መንግሥቱን የተቀበለውም ይህ አዲስ ሕዝብ ነው!


ብዙ ዘመን ወደኋላ ሄደን ስንመለከት ይህ ክስተት እንዴት እንደተተነበየ መረዳት አስገራሚ ነው። ከክርስቶስ ልደት በፊት በ700 ዓ.ዓ ገደማ፣ ነብዩ ኢሳይያስ እንዲህ ሲል ተንብዮ ነበር፡- “እግዚአብሔር አምላክ ይገድላችኋልና፣ ባሪያዎቹንም በሌላ ስም ይጠራቸዋል።” ጌታ ኢየሱስ ስለ ክፉዎቹ የወይን አትክልተኞች በተናገረው ምሳሌ ላይ የጠቀሰውም ይህንኑ ነው፡- “ጌታ [እግዚአብሔር] እነዚያን ክፉ ሰዎች በክፉ ያጠፋቸዋል [በመምጣቱ]... መንግሥቱንም ፍሬ ለሚያፈራ ለሌላ ሕዝብ ይሰጣል (ማቴ. 21፥ 41-43) ምንም እንኳን ቅዱሳት መጻሕፍት እንዲህ ባሉ ረጅም ዘመናት መካከል በኖሩ ጸሐፍያን የተጻፉ ቢሆንም፣ ለዚህን ያህል ብዙ ዘመናት እርስ በርሳቸው የማይጣረሱ በአንድነት አንድን ነገር የሚናገሩ ስሙም መሆናቸው የሚያስገርም ተአምር ነው። በተለያዩ ቦታዎች የኖሩ ጸሐፍያን የጻፉት ይህ መጽሐፍ አንድነቱና እና ወጥነቱ፣ በቅዱሳት መጻሕፍት እና በታሪክ ላይ የእግዚአብሔርን እጅ የበላይነት ያሳያል።


የዳግም ምጽአቱን አይነተኛ ምክንያት የሚያሳየው ሌላው የማቴዎስ ምንባብ ማቴዎስ 23፡29-36 ያለው ነው። አሁንም ኢየሱስ እየተናገረ ነው፡-


“እናንተ ግብዞች ጻፎችና ፈሪሳውያን፥ የነቢያትን መቃብር ስለምትሠሩ የጻድቃንንም መቃብር ስለምታስጌጡና፦ በአባቶቻችን ዘመን ኖረን በሆነስ በነቢያት ደም ባልተባበርናቸውም ነበር ስለምትሉ፥ ወዮላችሁ። እንግዲያስ የነቢያት ገዳዮች ልጆች እንደሆናችሁ በራሳችሁ ላይ ትመሰክራላችሁ። እናንተ ደግሞ የአባቶቻችሁን መስፈሪያ ሙሉ። እናንተ እባቦች፥ የእፉኝት ልጆች፥ ከገሃነም ፍርድ እንዴት ታመልጣላችሁ? ስለዚህ፥ እነሆ፥ ነቢያትንና ጥበበኞችን ጻፎችንም ወደ እናንተ እልካለሁ፤ ከእነርሱም ትገድላላችሁ ትሰቅሉማላችሁ፥ ከእነርሱም በምኵራባችሁ ትገርፋላችሁ ከከተማም ወደ ከተማ ታሳድዳላችሁ፤ ከጻድቁ ከአቤል ደም ጀምሮ በቤተ መቅደስና በመሠዊያው መካከል እስከ ገደላችሁት እስከ በራክዩ ልጅ እስከ ዘካርያስ ደም ድረስ በምድር ላይ የፈሰሰው የጻድቅ ደም ሁሉ ይደርስባችሁ ዘንድ። እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ በዚህ ትውልድ ላይ ይደርሳል።” (ማቴዎስ 23፥ 29-36)


ቀደም ሲል ልክ በክፉዎቹ የወይኑ ቦታ ሰራተኞች ምሳሌ ላይ እንደተነገረው ሁሉ፣ እዚህም ላይ ጌታ ኢየሱስ እግዚአብሔር በየዘመናቱ የላከላቸውን ነቢያት በመቃወማቸውና በግፍ በመግደላቸው ምክንያት እስራኤላውያንን ይወቀሳቸዋል። እዚህም ላይ በድጋሚ ፍርዱ “በትውልዱ ላይ” እንደሚመጣ ኢየሱስ ተናግሯል (ማቴ. 23፥ 36) ይህም በ70 ዓ.ም ላይ የመጣባቸውን ጥፋት የሚያመለክት ነው። ይህም የተነገረባቸው “የገሃነም ፍርድ” ነው [ገሃነም በትርጉሙ ብዙ ታሪክ ጸሐፊዎች ከኢየሩሳሌም ከተማ ውጭ ያለ የቆሻሻ መጣያና ማቃጠያ እንደሆነ ያምናሉ። ስለዚህ ኢየሱስ የገሃነምን ፍርድ አንስቶ ሲናገር በ70 ዓ.ም ስለተፈጸመው የጠላቶቹ መጥፋት ትንቢት መናገሩ ነው።


ጌታ ኢየሱስ በማርቆስ ወንጌል ላይ ያችን ፍሬ ያላገኘባትን በለስ ሲረግም ያህንኑ ነጥብ በድጋሚ ተናግሯል። አንድ ቀን ኢየሱስ በተራበ ጊዜ ፍሬ ወደሌላት አንዲት በለስ ላይ ቀረበና እንዲህ አላት፡- “ማንም ዳግመኛ ካንቺ ፍሬ አይብላ…” በማለዳም በዚያ ሲያልፉ ዛፊቱ ደርቃ ሞታ ነበረ። ( ማርቆስ 11፥ 14-21 ) ኢየሱስ ይህችን ዛፍ የረገመበት ምክንያት ማድረግ የሚገባትን ያላደረገች፣ ይኸውም ፍሬ የማታፈራ የማትጠቅም ዛፍ ስለሆነች ነው። ይህች ከንቱ በለስ እስራኤልን ትወክላለች (ኤር. 8፥ 13፤ ሆሴ. 9፥ 10)። የጠወለገችውም ወዲያው (በማለዳ) ነው፤ ይህም የእስራኤል ፍርድ ፈጥኖ እንደሚመጣ ያሳያል! በተጨማሪም “ከዚህ ዛፍ ፍሬ የሚበላ ማንም የለም” ሲል ኢየሱስ እንደተናገረው፣ ይህ ፍርድ በአይነቱ ዘላቂም ጭምር ነው። እስራኤል ከእግዚአብሔር ጋር የነበራት ልዩ መብት እና ያ የከበረ ግንኙነት አሁን (ኢየሱስ ይህንን ሲናገር) ሊያከትም ተቃርቧል ማለት ነው። ይህ ኢየሱስ በነዚህ ክፉ በሆኑ የወይን ቦታ ገበሬዎች ምሳሌ ላይ ከተናገረው ነጥብ ጋር ተመሳሳይ ነው። የወይን እርሻው ባለቤት በመጣ ጊዜ “እነዚያን ክፉ ሰዎችና ከተማቸውን ያጠፋቸዋል” ሲል ተናግሯል። “የእግዚአብሔር መንግሥት ከእናንተ ትወሰዳለች ፍሬዋንም ለሚያፈራ ሕዝብ ትሰጣለች።” ( ማቴ. 21፥ 41-43 ) እንግዲህ ልብ አድርጉ በምሳሌው የተነገሩ ሁለቱም ታሪኮች አንድን ነጥብ ያመለክታሉ፣ ይኸውም በቅርቡ በእስራኤል ላይ አይቀሬ የሆነ አስከፊ ፍርድ እየመጣ መሆኑን፣ ፍርዱም የማይቀለበስና ዘላቂ መሆኑን ነው።


አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ተንታኞች እስራኤላውያን አሁንም እንኳ - እንዲሁም ሁልጊዜም ቢሆን በእግዚአብሔር የተመረጡ ሕዝቡ እንደሆኑ ይከራከራሉ። እነዚህ ተንታኞች በ70 ዓ.ም ላይ የተፈጸመው ፍርድ የአይሁድ መሪዎችን ብቻ የሚመለከት እንጂ በጠቅላላው የእስራኤልን ሕዝብ (ብዙሃኑን) የሚመለከት አይደሉም ሲሉ ለመከራከር ይጣጣራሉ። ይሁን እንጂ፣ ጌታ ኢየሱስ ስለ ክፉዎቹ የወይን ቦታ ገበሬዎች በተናገረው ምሳሌና እንዲሁም በበለሲቱ ዛፍ ታሪክ ውስጥ የተናገራቸው ቃላት በግልጽ የሚያስተምሩት ስለጠቅላላው የእስራኤል ህዝብ ነው።


ለዚህ አንድ ተጨማሪ ማስረጃ የሚሆነው ኢየሱስ ተይዞ በፍርድ ችሎት ላይ በቀረበ ጊዜ የሆነውን የህዝቡን ምርጫ ተመልከቱ። ሮማዊው ገዥ ጴንጤናዊው ጲላጦስ ሕዝቡን (ብዙሃኑን የአይሁድን ህዝብ) በየአመቱ እንደሚያደርገው እስረኛን የመፍታት ልማድ ይህንን እድል ለኢየሱስ ሊሰጠው አስቦ ማንን ልፍታላችሁ፣ ኢየሱስን ወይንስ ታዋቂውን ወንጀለኛ በርባንን? ብሎ ሲጠይቃቸው ሕዝቡ በአንድ ድምጽ በርባንን ፍታልን ብሎ እንደመረጠ እዩ! ጲላጦስም፡- “ክርስቶስ የተባለውን ኢየሱስን እንግዲህ ምን ላድርገው” ብሎ ሲጠይቃቸው፣ ሁሉም በአንድነት፡- “ስቀለው”፣ ይሰቀል! የሚል ነበር መልሳቸው። በዚያን ጊዜ አገረ ገዡ፡- “ለምን፥ ያደረገው ክፋት ምንድር ነው?” ሲላቸው፣ እነርሱ ግን፡- “ይሰቀል! ይሰቀል! ደሙ በእኛና በልጆቻችን ላይ ይሁን እያሉ አብዝተው ጮኹ።” (ማቴዎስ. 27፥ 15-26,)


“ደሙ በእኛና በልጆቻችን ላይ ይሁን” የሚለው ይህ የመጨረሻው ዓረፍተ ነገር ሁሉንም ጠቅልሎ ለኢየሱስ በግፍ መገደል ተጠያቂ ያደርጋቸዋል፤ እንጂ ተጠያቂዎች የሆኑት የአይሁድ መሪዎች ብቻ አልነበሩም። በአጠቃላይ አይሁድ በጋራ ስምምነት የኢየሱስን ደም እዳ በምርጫቸው የወሰዱ ነበሩ! የኢየሱስ መገደል በብዙሃኑ ህዝበ ውሳኔ የተቆረጠ ነበር። ሊመጣባቸው የሚችል ፍዳም ካለ ይሁን ሲሉ በቃላቸው ፈርመዋል። ሐዋርያው ​​ዮሐንስም “የእርሱ ​​ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም፤” (ዮሐንስ 1፥ 11) በማለት አይሁድ መሲሀቸውን እንዴት እንደገፉት በጥሩ ሁኔታ ገልጾታል። እንግዲህ ለኢየሱስ ሞት ተጠያቂው ብዙሃኑ ነው፣ በ70 ዓ.ም ላይም በማይለወጥ ቋሚ በሆነ ፍርድ የተዳኙት ብዙሃኑ ነበሩ! መንግሥቱም ከእስራኤል ተወስዶ ለሌላ ሕዝብ ማለትም ለክርስቲያኖች ተሰጠ።


ይህ ማለት ሁሉም አይሁዶች ኢየሱስን አልተቀበሉትም ነበር ማለት እንዳልሆነ ልብ አድርጉ። ከላይ እንደተገለጸው እነዚያ የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች አይሁዶች ነበሩ። ሁሉም ሐዋርያት አይሁዶች ነበሩ። ጌታ ኢየሱስም ራሱ አይሁዳዊ ነበር። ያም ሆኖ እነዚህ ታማኝ የሆኑ አይሁዳውያን በተቀሩት አይሁድ መካከል የተገፉና ጥቂቶች ነበሩ፤ ለዚህም ነው ኢየሱስ በዘመኑ የነበሩትን “አመንዝራ ትውልድ” (ማቴ. 12፥ 39) እና “የማያምን ጠማማ ትውልድ” (ማቴ. 17፥ 17፤ በተጨማሪም የሐዋርያት ሥራ 2፥ 40 እና ፊልጵ 2:፥ 15⁠ን ተመልከቱ) እያለ ይነቅፋቸው የነበረው። በተመሳሳይም በራእይ መጽሐፍ መልአኩ የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን የይሁዲነት እናት የሆነችውን ኢየሩሳሌምን የገለጸው “ታላቂቱ ባቢሎን፣ የጋለሞታዎችና የምድር ርኩሰት እናት” (ራእይ 17፥ 5)፣ በማለት ነበር። ልብ አድርጉ፡- የራዕይ መጽሐፍ ኢየሩሳሌምን ሲገልጽ በተለይ “ምስጢረ ባቢሎን” እየሩሳሌም ሲል ይገልፃታል። እርስዋም ጌታ የተገደለባት ከተማ እየሩሳሌም ነበረች (ራእ. 11፥ 8)። እስራኤል እንደ ህዝብ የአመንዝራነት ሚና ነበራት፣ በታሪኳም ብዙ ጊዜ በነብያቷ “ጋለሞታ” ተብላ ስትጠራ ኖራለች። ምክንያቱም ብዙ ጊዜ ሌሎች አማልክትን ትከተል ነበር (ሆሴ. 9፥ 1፤ ኤር. 2፥ 20-24፤ 3፥ 2-3፤ ዕዝ. 23፥ 14-20፤ ኢሳ. 23፥ 14-20፤ ኢሳ. 1፥ 21፤ 57፥ 9) ኢየሱስ ባገለገለበት ዘመንም ይሁን ራእይ በተጻፈበት ጊዜ የእስራኤል ሁኔታ እንዲሁ ነበር።


ምንም እንኳን ዘመኑ ታማኝነት ያጡ ትውልዶች የበዙበት የነበረ ቢሆንም፣ እንደ ሁል ጊዜው ሁሉ ግን እግዚአብሔር ያኔም ጥቂት የታመኑ ሰዎች ነበሩት። በኖኅ ዘመን እግዚአብሔር በዚያ ክፉ ትውልድ ላይ የጥፋት ውሃ ፍርድን ሲያመጣ ጻድቁ ኖኅ እና ቤተሰቡ በጊዜው እግዚአብሔር ከጥፋት የጠበቃቸው ትሩፋን ነበሩ። ከብዙ መቶ ዘመናት በኋላም፣ ነብዩ ኤልያስ ብቸኛውና በህይወት የቀረው የመጨረሻው ታማኝ እስራኤላዊ እንደሆነ ባሰበ ጊዜ፣ ጌታ እንዲህ አለው፡- “በእስራኤል ዘንድ ጉልበታቸው ለበኣል ያልተንበረከከውን ሁሉ ሰባት ሺህ ጠብቄአለሁ፣” (1 ነገ. 19፥ 18)። በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመንም ጻድቃን የሆኑ ትሩፋን እነዚያ ጌታ ኢየሱስን የታዘዙቱ ነበሩ። ልክ እንደ ኖህ እና ቤተሰቡ ሁሉ የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖችም እግዚአብሔር ለድነታቸው ወዳዘጋጀላቸው ወደ መርከቡ ገቡ። ማለትም ኢየሱስ እንደነገራቸው በኢየሩሳሌም ዙሪያ ያለውን አጥፊ የአህዛብ ሠራዊት ባዩ ጊዜ ከኢየሩሳሌም ፈጥነው እንዲሸሹ አመልክቷቸው ነበርና እንዳዘዛቸውም አደረጉ (ሉቃስ 21፥ 20-21። ራእ. 18፥ 4)። እነዚህ ክርስቲያኖች ለዚህ ሽሽትና ከፍርድ ማምለጥ ይመቻቸው ዘንድ አስቀድመው ንብረታቸውን ሸጠው ተዘጋጅተው ነበር (ሐዋ. 2፥ 45፡ ማቴ. 19፥ 21)፣ ስለዚህ ከኢየሩሳሌም የሸሹበት ሁኔታ ቅጽበታዊ ነበር። በውጤቱም ኢየሱስ በ70 ዓ.ም በክብር ደመና በመጣ ጊዜ በኢየሩሳሌም ላይ ከደረሰው አስከፊ ፍርድ ተርፈዋል።

ግዛቸው።


From Blogger iPhone client

Sunday, February 2, 2025

የነገረ ፍጻሜ አቋማችን፣ ፕሪቴሪዝም!

የነገረ ፍጻሜ አቋማችን 

(ፕሪቴሪዝም)

  • መግቢያ

የአለም ፍጻሜ ቀርቦአልን? የምንኖረውስ በመጨረሻዎቹ ቀናት ወይም በመጨረሻው ዘመን ውስጥ ነውን? የክርስቶስ መመለሻስ ቀርባልን? ከዚህስ በኋላ ቶሎ የሚሆን ይመስላችኋልን? በግምት ላለፉት 150 አመታት በምእራቡ አለም አብያተ ክርስቲያናት ያለማቋረጥ የተስተጋባ አንድ ጉዳይ አለ፤ ይኸውም፣ የምንኖረው በአለቀና በተሟጠጠ ዘመን ውስጥ እንደሆነ ሲነገረን የኖረው ጉዳይ ነው። ክርስቶስም ተመልሶ ሊመጣ በደጅ እንደቀረበና ጊዜው እንደደረሰ በብዙዎች ዘንድ የተያዘ እምነት ሆኖ ኖሯል። በእኛም አገር አስራ አንደኛው ሰአት ላይ ነን የሚሉ መምህራን በየአትሮንሱ ላይ ተሰይመው ይደመጣሉ። በክርስቲያኑ ማህበረሰብ ላይ ተጭኖና ተተብትቦ ከኖረው ልማዳዊ አመለካከት የተነሳ፣ ሳይሳኩ መና ሆነው የቀሩ በትንበያ ላይ ትንበያ፣ በሃሰተኛ ተስፋ ላይ ሌላ ሃሰተኛ ተስፋ የመጨማመሩ አባዜ "አገር ያወቀው ጸሐይ የሞቀው" ጉዳይ ነው። ከዚህ አይነቱ አዙሪት የተነሳ በርካታ የተታለሉ ክርስቲያኖች ከነዚህ አጉል ትንበያዎችና ኃሰተኛ ተስፋዎች የተነሳ ተጭበርብረው ሀብት ንብረቶቻቸውን የተዘረፉ ሲሆኑ፣ ከዚህ በከፋ ሌሎቹ ደግሞ እምነትን እስከመተው የደረሱና በተስፋ መቁረጥ ራሳቸውን ከህይወት ቃል እስከማጉደል ድረስም መጨረሻቸው የማያምር ሆነዋል። ይህም በአብያተ ክርስቲያናት ሰፊ መሰረት ያለውና ከቁጥጥር ውጭ የወጣው የመጨረሻው ዘመን መላምታዊ አስተንትኖ ለበርካታ ማህበራዊና ሥነ ምግባራዊ ውድቀት ብዙዎችን ዳርጓል። አዘውትረው ስህተትን የሚፈልጉ አለማዊ የመገናኛ ብዙሃንም ክርስትናን የሚያሳጡበት፣ የሚያጠለሹበትንና የሚያዋርዱበትን የስድብ ምክንያት አግኝተዋል። 

በመጽሐፍ ቅዱሳዊው የትንቢት አስተምህሮ ልማዳዊ አመለካከት ዙርያ በተርጓሚዎች ዘንድ አንድ የተሳሳተ ነገር መኖሩ ግልጽ ነው። ያ ችግር ምን ይሆን? እምነታችንን ከስድብና ከነቀፋ ለመከላከል ሲባል የመጨረሻው ዘመን ነገረ ፍጻሜአዊ የሆኑ አጠቃላይ ጉዳዮችን፣ የኖረውን አስተምህሮታዊ አቋምና ልማዳዊ አመለካከቶቻችንን እንደገና ማየት፣ መከለስ፣ መፈተሽና እርማት ማድረግ ለይደር የሚቀመጥ ጉዳይ አይደለም። 

መጽሐፍ ቅዱስም፦

(ማቴ 13፥ 11)"ለእናንተ የመንግሥተ ሰማያትን ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቶአችኋል፥ ለእነርሱ ግን አልተሰጣቸውም" 

ይላል፤ መጽሐፍ ቅዱሳዊውን የትንቢት ቃል መረዳትና ማወቅ በእውነትም ለተጠሩትና ለተመረጡቱ የሚቻል ነው። መጻኢያን (Futurists) የሆኑ ተርጓሚዎች ግን ከሚከተሉት የትርጉም አካሄድ ስህተት የተነሳ፣ ማለትም፦ ጽንፍ በያዙበት የተዳሳሽ ወይም በቁሙ የሆነ አቀራረባቸው የተነሳ፣ በምሳሌአዊ ወይም ምስል ከሳች በሆነው ቋንቋ እና በቁሙ በሚወሰድ የቋንቋ ዘይቤ መካከል ልዩነት ለማድረግ ካለመቻላቸው የተነሳ፣ እንዲሁም የትንቢቶችን ታሪካዊ - ሰዋሰዋዊ - ባህላዊ የሆነውን አውዳቸውን (በተለይም ለበኩረ ተደራስያኖቻቸው ምን ማለት እንደነበሩ) በትክክል ወስዶ ለመተርጎም ካለመቻላቸው የተነሳ ትንቢትን በወጉ መተርጎምና መረዳት ከቶ አልሆነላቸውም። ባደመጥናቸውና የጽሁፍ ሥራዎቻቸውን ባነበብን ቁጥር ሁሉ የመጽሐፍ ቅዱስን ተአማኒነት ዝቅ አድርገው የሚያዋርዱ ትንታኔዎቻቸውን እስክናፍር ታዝበናል። 

ከዚህም ግራ የገባው ትምህርት የተነሳ በእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በነገረ ፍጻሜ አስተንትኖ እርስ በርሳቸው የተለያዩ ለቁጥር የሚያታክቱ አመለካከቶች ተፈልፍለዋል። በአብዛኛው ታዋቂ ከሆኑት መካከል፦ የአልቦ ሺህ አመት መንግስት (Amillennialism) አመለካከት፣ የድህረ ሺህ አመት መንግስት (Post Millennialism) አመለካከት፣ የታሪካውያን (Historicism) አመለካከት፣ የታሪካዊ ቅድመ ሺህ አመት መንግስት (Historic Premillennialism) አመለካከት፣ የዘመን ቆጣሪው የቅድመ ሺህ አመት መንግስት (Dispensational Premillennialism) አመለካከት፣ የቅድመ መከራ ንጥቀት (Pre- Tribulation Rapture) አመለካከት፣ ወይም የቅድመ ቁጣ ንጥቀት (Pre Wrath Rapture) አመለካከት፣ የከፊል ንጥቀት (Partial Rapture) አመለካከት፣ በመከራው መካከል የመነጠቅ (Mid Tribulation Rapture) አመለካከት፣ የድህረ መከራ ንጥቀት (Post Tribulation Rapture) አመለካከት ወዘተ.. የሚጠቀሱት ናቸው። ማለቂያ የሌለው የነገረ ፍጻሜ የአመለካከት ልዩነቶች ቀድሞም ነበሩ፤ የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎች ለአተረጓጎማቸው ካልተጠነቀቁ እንዲህ ያሉ የአስተምህሮ ህጸጾች ወደፊትም ይኖራሉ። ያው ዞሮ ዞሮ ግን ሁሉም ማጠቃለያቸው መጻኢነት መሆኑ ግልጽ ነው። ሁሉንም በተወሰነ ዝርዝር አንድነታቸውንና ልዩነታቸውን የዳሰስኩበትን ጽሁፍ ሊንኩን ተጭናችሁ ልትመለከቱ ትችላላችሁ፦

https://m.facebook.comstoryphp?story_fbid=1932248943670209&id=1889309531297484

ወደተነሳሁበት ሃሳብ ስመለስ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትንቢቶችን የምናጠናበትና የምንተረጉምበት አቀራረባችን በእውነት ትክክለኛና ተገቢ ከሆነ፣ በጣም ከባድና አስቸጋሪ የሚመስሉ ትንቢታዊ ምንባባት እንኳ መልእክታቸው ግልጽ ይሆንልናል። ስለዚህም አቋሞቻችንን እና እድሜ ጠገብ የሆኑ ልማዳዊ አመለካከቶቻችንን የምንፈትሽባቸው አንዳንድ አማራጮችን ለመመልከት አሁን ጊዜው ነው። የኃላፋውያን (Preterists) ምልከታ ደግሞ አማራጫችን ብቻ ሳይሆን እምነታችንን ከጥቃት ለመከላከልና በነገረ ፍጻሜ አስተንትኖ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ሆኖ ለመገኘት በጣም ወሳኝ የሆነ አስተምህሮ ነው። በዚህ ጥናት የነገረ ፍጻሜ አቋማችንን የሚመለከት ትምህርት እንማራለን፤ ይኸውም ኃላፋዊነት (Preterism) ይሰኛል። ከዚያ በፊት ግን እስቲ በጥቂቱ ስለ ኢስካቶሎጂ እንነጋገር። እንደው ለመሆኑ ኢስካቶሎጂ ምንድን ነው? እንዴት ትገልጹታላችሁ?

  • ትርጉም

የሜሪይየም-ዌብስተር መዝገበ-ቃላት Definition of eschatology ብሎ በዚህ መንገድ ይገልጸዋል፣ እንዲህ ወደ አማርኛ መልሼዋለሁ፦

1ኛ በዓለም ወይም በሰው ልጅ ታሪክ ውስጥ የመጨረሻዎቹን ክስተቶች ወይም ኩነቶች የሚመለከት አንድ የስነ-መለኮት ጥናት ዘውግ ነው ይለዋል። [ይህ ግን ከመሰረቱ ስህተት የሆነ ትርጓሜ ነው፣ ምክንያቱም መጽሃፍ ቅዱስ የሚያስተምረው ስለ “ዘመን” የመጨረሻ ክስተቶች እንጂ ስለ ግኡዙ ዓለም መጨረሻ አይደለምና ነው።] በመቀጠልም መዝገበ ቃላቱ 2ኛ ስለ ሞት፣ ስለ አለም ፍጻሜ፣ ወይም የሰው ልጅ የመጨረሻ እጣ ፈንታን በተመለከተ ያለ እምነት ነው ይላል፤ [ይህም ስህተት ነው፣ ምክንያቱም የዘመኑ ፍጻሜ የሚባል ትምህርት እንጂ የአለም ፍጻሜ የሚባል የነገረ መለኮት ጥናት የለምና ነው]። መዝገበ ቃላቱ አክሎም፥ በተለይ፡ ስለ ዳግም ምጽአት፣ ስለ ሙታን ትንሳኤ፣ ወይም ስለ መጨረሻው ፍርድ ማንኛውም አይነት የክርስትና አስተምህሮዎችን የሚተነትን ትምህርት ነው ይላል።

ዞንደርቫን አካዳሚክ የተሰኘ የድረገጽ መረጃ ደግሞ እንዲህ ሲል ይተረጉመዋል፣ “ኢስካቶሎጂ ስለ መጨረሻዎቹ ነገሮች ያለ ጥናት ነው። ይህም የኢየሱስን ዳግም ምጽአት የሚመለከቱ ዅነቶችን፣ ማለትም የኢየሱስ ዳግም ምጽአት ከመሆኑ በፊት የሚከናወነውን እና የኢየሱስ ዳግም ምጽአት ከሆነ በኋላ የሚከናወነውን ጉዳይ ያካትታል” ይላል። [ይህ ጥሩና ተገቢ የሆነ ትርጓሜ ነው።]

ኢስካቶሎጂ የተሰኘው ቃል የመጣው eschatos ከሚለው የግሪክ ቃል ሲሆን ትርጉሙም "የመጨረሻ" ወይም "የፍጻሜ" ማለት ነው፤ እሱም የነገሮችን የመጨረሻ ወይም የፍጻሜ ጥናትን ይመለከታል።

  • የኃላፋውያን አመለካከት ምንድን ነው? 

ጌታ ኢየሱስና ሐዋርያቱ ስለ መጨረሻው ቀንና ስለ ፍጻሜ ጉዳዮች ያስተማሩት አንድም ሳይቀር ሙሉ በሙሉ ያኔ በዚያው ትውልድና ዘመን ውስጥ ሁሉ ተፈጽሟል ብሎ የሚያምነውና የሚያስተምረው የነገረ ፍጻሜ አመለካከት ኃላፋዊነት (preterism) ይሰኛል። preterist የተሰኘው ቃል የተወረሰው praeter ከተሰኘው የላቲን ቃል ሲሆን ትርጉሙም "አልፎአል"፣ "አልፎ ሄዶአል" ማለት ነው። "ኃላፋዊ" ማለት የትንቢት ፍጻሜ አልፎአል፣ ካለፈም ቆይቶአል ማለት ሲሆን፤ መጻእያን ማለት ደግሞ የትንቢት ፍጻሜ ገና ወደ ፊት የሚጠበቅ ነው ማለት ነው። በመሰረቱ የኃላፋዊነት አመለካከት ማለት በሁሉ ረገድ የመጻኢነት አመለካከት ተቃራኒው ማለት ነው። መጻኢያን፣ አብዛኛዎቹ የመጨረሻው ዘመን ትንቢቶች (በተለይም ዋና ዋና የሆኑቱ) ገና ወደ ፊት ይፈጸማሉ እንጂ እስካሁን አልተፈጸሙም ብለው ያምናሉ፣ ያስተምራሉም። ኃላፋውያን ደግሞ በበኩላቸው ሁሉም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትንቢቶች በክርስቶስና ቀጣይ በሆነው የክርስቶስ ቤተክርስቲያን እድገትና መስፋፋት ውስጥ ተፈጽመዋል ብለው ያምናሉ፣ ያስተምራሉ።

ኃላፍያን የተሰኘው ስምም ሆነ ኃላፊ የተሰኘው ግስ ለኃላፊ ጊዜ አነጋገር የሚያገለግል ነው። ስለሆነም መጽሐፍ ቅዱሳዊ የነገረ ፍጻሜ ጥናትን በተመለከተ የኃላፋውያን እይታ፣ የጌታን ዳግም ምጽአት ጨምሮ ሁሉም ትንቢት፣ የሙታን ትንሣኤና ፍርድ እኛ እየኖርንበት ካለነው ከዚህ ዘመን በፊት አስቀድሞ ድሮ ገና ተፈጽሞአል ብሎ ያስተምራል። ፕሪተርሪዝም በፍጻሜው ዘመን ሊከናወኑ በትንቢት የተነገሩ ክስተቶች ሁሉ በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ላይ ተፈጽመው እንዳለፉ የሚያምንና የሚያስተምር የኢስካቶሎጂ ምልከታ ነው። ለኃላፍዊው ነገረ ፍጻሜ ትንቢት ሁሉ ያለፈ ታሪክ ነው። ይህንንም ለማስረዳት የቅዱሳት መጻህፍትን አስተምህሮ ጠቅሶ የሚያቀርበው ማብራርያ ከየትኛውም የትርጉም መንገድ ይልቅ ጌታ ኢየሱስን እግዚአብሄር በወንድሞቹ መካከል ቀብቶ እንዳስነሳው ነብይና እንደ እውነተኛ የእግዚአብሔር ልጅ የሚያከብረው፣ የቅዱሳት መጻህፍትንም ተአማኒነት የሚያረጋግጥ፣ ቅዱሳት መጻህፍትም ለተሰጡበት አውድ ታማኝ ሆኖ የትርጉም ቀዋሚነትን (consistency) የሚጠብቅ እንደሆነ አይኑን ያልጨፈነ ሁሉ ሊያረጋግጠው ይችላል።  

ፕሪተሪዝም፣ የመጨረሻው ፍርድ፣ የሙታን ትንሳኤ እና የጌታ ዳግም ምጽአት እነዚህ በትንቢት የተነገሩ ትላልቆቹ ጉዳዮች በ70 ዓ.ም ላይ በሆነው በታሪካዊው የኢየሩሳሌም ጥፋት ወቅት እንደተፈጸሙ የሚገልጽ ትምህርት ነው። ፕሪተሪዝም በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሚገኙትን ጊዜ ጠቋሚ የሆኑ መግለጫዎችን ፍፁም በሆነ ዋጋ ወስዶ ጌታ ኢየሱስ ልክ ራሱ በተናገረው መሰረትና እመለሳለሁ ባለበት ጊዜ በዚያው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በትውልዱ እንደተመለሰ ፍርጥም ብሎ ያምናል። በርካታ መጻኢያን ግን ከሚከተሉት የትንቢት ትርጉም አካሄድ የተነሳ፣ ክርስቶስ በመንግስቱ ምስረታ ሙሉ በሙሉ ተሳክቶለታል ብለው በእውነት ለማመንም ሆነ ለመመስከር ይቸገራሉ።

የመጽሐፍ ቅዱሳዊው ትንቢት የኃላፋውያን ትርጉም ከመላው የክርስትና እምነት ጋር ተስማሚ የሆነና፣ ደግሞም ልባቸውን እልከኛ ካላደረጉ በቀር "የእግዚአብሔር ቃል ብቻ" (Sola Scriptura) የተሰኘውን የተሃድሶ አቋም ባነገቡ በሁሉም ቤተ እምነቶች ውስጥ ሊያዝና ሊንጸባረቅ ሰፊ እድል ያለው ደግሞም የሚችል እምነት ነው። እንደ Christianity Today, Christian News, World Magazine በመሳሰሉት እና በሌሎችም በበርካታ ታዋቂና ተነባቢ የህትመት ስራዎች ሲጠቀስ ኖሮአል። በመላው አለም በሚደመጡ የራድዮና የቴሌቭዥን ፕሮግራሞች የኃላፍያንን ምልከታ የሚያንጸባርቁ የትምህርት ስርጭቶች፣ በየወሩና በየሶስት ወሩ ታትመው ለንባብ የሚበቁ በርካታ የህትመት ውጤቶች አሉት። በርካታ የኃላፋውያን መጻህፍት፣ በራሪ ወረቀቶች፣ የቪድዮና የኦዲዮ ትምህርቶች ተዘጋጅተው የሚበዙት ስራ ላይ ውለዋል። የኃላፍያንን መጻህፍት ጽፈው የሚያዘጋጁ ጸሐፍያን በተለያዩ የሬድዮ ማሰራጫዎች እየቀረቡ ለብዙ ጊዜያት ቃለ ምልልስ ተካሂዶላቸዋል። የኃላፋውያን አመለካከት በመላው የምእራቡ አለም የሥነመለኮት መምህራንና ተማሪዎች ዘንድም ብቻ ሳይሆን፣ በክርስቲያናዊው ማህበረ ሰብ ውስጥ ወደታች ወርዶ ከፍተኛ ትኩረት እየሳበ ያለና፣ በተለይ በድረ ገጽ የማህበራዊ መገናኛ ብዙሃን (በዩቲዩብ፣ በፌስ ቡክ) እንደ ሰደድ እሳት እየተዛመተ ያለ ጉዳይ ነው።

  • የነገረ ፍጻሜ ትምህርት አስፈላጊነት

የነገረ ፍጻሜ ትምህርት አስፈላጊ ነው ወይ? ብዙውን ጊዜ እንዲህ ያለው ጥያቄ ከተለያዩ ሰዎች ይቀርብልኛል፤ በተለይ በነገረ ፍጻሜ ምልከታችን የተፈጸመውን ወንጌል ስናበስር እና ከተለመደው የአብያተ ክርስቲያናት የቆየ ምልከታ ጋር በአቋማችን ስንለይ የሙግታችንን ጭብጥ መመከት የተሳናቸው ወገኖች ከክርከሩ ለማፈግፈግ የሚዳዳቸው “ኢስካቶሎጂ ያን ያህል አስፈላጊ ነው ወይ?” በሚል ጥያቄ ነው። "ይህ ለምን ያስፈልጋል? የነገረ ፍጻሜ ትምህርት ለምን አስፈላጊ ይሆናል? ያን ያህል ዋነኛ ጉዳይኮ አይደለም" ሲሉም ይደመጣሉ። የእኔ መልስ ግን ሁሌም ጥያቄውን በጥያቄ የሚያስተናግድ ነው፤ "እውነት አስፈላጊ ነው ወይ?" ብዬ እጠይቃለሁ። በእውነቱ እንደዚያ ካልሆነ መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናትም አያስፈልገንም ማለት ነው። ነገር ግን እውነት አስፈላጊ ከሆነ፥ እንግዲያውስ የነገረ ፍጻሜ ትምህርትም አስፈላጊ ነው።

የኢስካቶሎጂ ጉዳይ በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ትልቍ ሥነ-መለኮታዊ ጉዳይ በመሆኑ ርዕሰ ጉዳዩ ዋና አስፈላጊ ጉዳይ ነው። አር.ሲ. ስፕሮል ሲያስተምሩ የአዲስ ኪዳን ሁለት ሦስተኛው በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ነገረ ፍጻሜአዊ ነው ይላሉ። ሌሎች የጥናቱ ባለሙያዎች እንደሚናገሩት ደግሞ ከ25 እስከ 30 በመቶ የሚሆነው አጠቃላይ የመጽሐፍ ቅዱስ ርዕሰ ጉዳይ ነገረ ፍጻሜአዊ ነው ይላሉ።

ጄምስ ቦይስ እንዲህ ሲሉ ጽፈዋል፡- “በመላው አዲስ ኪዳን ከሃያ አምስት ቁጥሮች ውስጥ አንዱ ቁጥር የጌታን ዳግም ምጽዓት የሚናገር ጥቅስ ነው። በአዲስ ኪዳን ውስጥ በሚገኙ 260 ምዕራፎች ውስጥ 318 ጊዜ የተጠቀሰው ይኸው የጌታ ዳግም ምጽአት ነው። ይኸውም የተለየ የአስተምህሮ ተግዳሮትን ከሚዳሠው ለገላትያ ሰዎች ከተጻፈው መልዕክትና፣ እንደ 2ኛና 3ኛ ዮሐንስ እንዲሁም እንደ ፊልሞና ባሉ በጣም አጫጭር በሆኑ የቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ካልሆነ በቀር፣ በሁሉም የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት ውስጥ በሰፊው ተጠቅሷል፣ " [The Epistles of John (Zondervan), ገጽ 96]

ሬይ ስቴድማን እንዲህ ሲሉ ጽፈዋል፡- “ምናልባት ይህ ርዕሰ ጉዳይ በመላው አዲስ ኪዳን ውስጥ በእጅጕ እየተደጋገመ የተጠቀሰ እውነት መሆኑን መጽሐፍ ቅዱሳችሁን በማንበብ ተረድታችሁ ይሆናል። ይህ በአዲስ ኪዳናችን በሁሉም ገፆች ላይ የሚገኝ ታላቅ ተስፋ፣ እርሱም የኢየሱስ ክርስቶስ ዳግም መገለጥ በአዲስ ኪዳን ውስጥ ያሉትን ሁሉንም እውነቶች አጽንቶ የሚመሰርታቸው ነው ማለት ይቻላል።

የክርስቶስ ዳግም ምጽአት በጣም አስፈላጊና ጠቃሚ ርዕሰ ጉዳይ ነው። ልንረዳውም የሚገባን ጉዳይ ነው። በአዲስ ኪዳን ውስጥ በተደጋጋሚ የተጠቀሰውን እንዲህ ያለውን ጉዳይ እንዴት ቸል ልንል እንችላለን? በአዲስ ኪዳን 260 ምዕራፎች ውስጥ 318 ጊዜ የተገለጸውን ነገር ለመረዳት እንዴት አይገደንም?

  • እኔና ፕሪቴሪዝም

ከሁለት አስርት አመታት በፊት ስለ ክርስቶስ ዳግም ምጽአት እንደገና በወጉ ማሰብ የጀመርኩበትን ወቅት አስታውሳለሁ። በጊዜው በመካነ የሱስ ሴሚናሪ የስነ መለኮት የማታው ትምህርት ፕሮግራም እየተከታተልሁ ቄስ ሆኜ እንዳገለግል በጠራችኝ ማሕበረ መእመናን ወንጌልን አገለግል ነበር። የኖርኩበት ሉተራዊ እምነቴ በነገረ ፍጻሜ አስተምህሮቱ የአልቦ ሺህ አመት አመለካከትን እንደሚቀበል እረዳ የነበረው በጥቂቱ ቢሆንም፣ በመላው የአገራችን ቤተክርስቲያን የናኘው የዘመን ቆጣሪያን (Dispensationalist) አመለካከት ግን ተጽእኖ አሳድሮብኝ ኖሯል። ነገረ ፍጻሜም ያን ያህል የሚያሳስበው ባልሆነ ማህበረ ሰብ መካከል በመኖሬ በግሌ የተፈጠሩብኝን በርካታ ሥነመለኮታዊና መጽሓፍ ቅዱሳዊ ጥያቄዎቼን ማስተንፈስ የምችልበት እድልና ሁኔታ አልነበረኝም። በሴምናሪ በነበረኝ ቆይታም በቤተ መጻህፍቱ ለመጠቀም በነበረኝ ዕድል በውስጤ ይላወስብኝ ከነበረው እረፍት አልባ ሙግት ጋር የሚፋጠጡ መጻህፍትን ለማንበብ ሞክሬአለሁ። የሉተራውያኑም የነገረ ፍጻሜ አቋም ሊሻል ይችላል ብዬ አርፌ በተቀመጥኩበት አንድ አጋጣሚ ግን አንድ ወዳጄ የወንጌላዊ ጆን ኤል ብሬይን “Jesus is Coming soon” የተሰኘች አንዲት ትንሽዬ ቡክሌት አዋሰኝና አነበብኳት። እጥር ምጥን ብላ የተዘጋጀችው ያቺ ቡክሌት ልቋቋመው የማልችለውን ብርቱ ሙግት ብትገጥመኝም ወንጌላዊው የሚያስተምሩትን ጉዳይ የበለጠ ለማወቅ ግን ረሃቤን ቀሰቀሰችብኝ። ቡክሌቷ ላይ ባገኘሁት መረጃም ከሚልተን ተሪ ጋር ተዋውቅሁ፤ ወደቤተ መጻህፍት ሄጄም ስጎረጉር አቧራ የጠገበና ብዙም ሳይነበብ መደርደሪያው ላይ የተረሳ “Biblical Apocalyptics” የተሰኘ ዳጎስ ያለ ጥራዝ አግኝቼ በውሰት ወሰድኩትና ያን ሁሉ ገጽ ፎቶ ኮፒ አስደርጌ በርጋታ ማንበቤን ቀጠልሁ፤ መጽሃፍ ቅዱሳዊ ትንቢትን ለመረዳት ከዚህ በፊት ያልነበረኝን ጥልቅ ፍላጎት ያጫረብኝ ከመሆኑም በላይ የቀደመውን አመለካከቴን እና አስተሳሰቤን መለወጥ አስችሎኝ ነበር።     

ቀድሞ በነበረኝ መረዳት እንደ አብዛኞቹ ክርስቲያኖች፣ የክርስቶስ ዳግም ምጽአት ምድርን የሚቀይር አካላዊና ተዳሳሽ ክስተት ነው ብዬ አምንም እጠባበቅም ነበር። ይኸውም የዚህ የምናውቀው ተዳሳሽ ዓለም ፍጻሜ፣ አስደንጋጭ የምድር ቃጠሎ፣ አጠቃላይ የሕይወት ውድመት ሆኖ ይታየኝ ነበር። አስተሳሰቤን የለወጠው ግን የዳግም ምጽአቱን ጊዜ ጠቋሚ የሆኑ የአዲስ ኪዳን ምንባባት ናቸው። ብበመጽሐፍ ቅዱስ ጥናቴም የአዲስ ኪዳን ቅዱሳት መጻህፍት ስለ ዳግም ምጽአቱ በሚናገሩበት ጊዜ ሁሉ “ጊዜ ጥቋሚ” የሆኑ ንግግሮችን እንደሚጠቀሙ በጉልህ ማየት ጀመርኩ። ዳግመኛ ምጽአት በእነዚያ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን በነበሩ አማኞች የሕይወት ዘመን፣ እንዲያውም በዚያ ከኢየሱስ ጋር ቆመው የነበሩት አንዳንዶቹ ገና በሕይወት እያሉ (ማቴ. 16፥ 28) ተፈጽሟል፣ ሆኗልም ብዬ እንዳምን የሚያስገድዱኝን የቅዱሳት መጻህፍት ቃላት ለዘመናት ከያዝኩትና በአብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ከሚታወቀው የተለመደ ትምህርት በላይ ማክበር ነበረብኝ። እነደ አዲስ ኪዳን ትምህርት ከሆነ፣ ያ የኢየሱስ ትውልድ ገና ሳያልፍ፣ ለዚያው ትውልድ ቅርብ በነበረ መጨረሻ ኢየሱስ ለእነርሱው ቶሎ ይመጣል ብሎ ለማመን የሚያስችለኝን እውነት ማየት የቻልኩትን ያህል፣ ኢየሱስ አሁን በእኛ ዘመነም ይሁን ገና ወደፊ ተመልሶ ይመጣል በሚል አምነው የነበረው አስተሳሰቤን የሚደግፍልኝ አንድም ጥቅስ ማግኘት ተሳነኝ።

  • አውደ ምንባባዊ አግባብ

መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብ፣ የበኩረ ተደራስያኑን አውድ ዋጋ የሚሰጥ የትርጉም መርሆን በአእምሯችን መያዝ አለብን። ይህ አስፈላጊ አካሄድ እነዚያ የመጀመሪያዎቹ ተደራስያን አንድን የንባብ ክፍል ምን ማለት እንደሆነ በአውዳቸው የተረዱበትን መንገድ ለማወቅ ጥረት ያደርጋል። ወንጌል አማኝ የሆነ የቅዱሳት መጻህፍት ተርጓሚ ዋጋ የሚሰጠው ጉዳይ የአንድን የንባብ ክፍል ሰዋሰው ከበኩረ ተደራሲያኑ ታሪካዊ ሁኔታዎች እና ከአውዳቸው አንፃር መረዳት ነው።

የዳግም ምጽአቱ ጊዜ ያኔ ገና በአንደኛው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ “ቅርብ” ነው ከተባለ፣ “ቶሎ” ነው፣ “በደጅ ነው” ከተባለ፣ እንግዲያውስ የዳግም ምጽአቱ ተፈጥሮ ሥጋዊ፣ አካላዊና ተዳሳሽ መሆን የለበትም። ይህንንም የምናውቀው አካላዊና ተዳሳሽ ለውጥ ባለመኖሩ ነው። ለምሳሌ ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ሰዎች በጻፈው መልዕክቱ ላይ፣ ዳግም ምጽአቱን በተመለከተ የሚናገረው ሥጋዊ ወይንም ተዳሳሽ በሆነ መልኩ አድርጎ እንዳልነበር እናያለን። አንዳንድ አውድ ለማግኘት ጳውሎስ ለተሰሎንቄ ሰዎች የጻፈውን ሁለተኛ መልእክት በመጠኑ ማየት እንጀምር።

2ኛ ተሰሎንቄ 1፥ 4 “ስለዚህ በምትታገሱበት በስደታችሁና በመከራችሁ ሁሉ ከመጽናታችሁና ከእምነታችሁ የተነሣ በእግዚአብሔር አብያተ ክርስቲያናት ስለ እናንተ ራሳችን እንመካለን”

ጳውሎስ ይህንን መልእክት በተሰሎንቄ ላለች ቤተ ክርስቲያን በ50-51 ዓ.ም. በጻፈበት ጊዜ፣ የተሰሎንቄ አማኞች በክርስቶስ ስላላቸው እምነት መከራ ይቀበሉ የነበረበት ጊዜ ነው። ስለዚህም ጳውሎስ እንዲህ ሲል ያጽናናቸዋል።

2ተሰሎንቄ 1፥ 6-8 “ጌታ ኢየሱስ ከሥልጣኑ መላእክት ጋር ከሰማይ በእሳት ነበልባል ሲገለጥ፥ መከራን ለሚያሳዩአችሁ መከራን፥ መከራንም ለምትቀበሉ ከእኛ ጋር ዕረፍትን ብድራት አድርጎ እንዲመልስ በእግዚአብሔር ፊት በእርግጥ ጽድቅ ነውና። እግዚአብሔርን የማያውቁትን፥ ለጌታችንም ለኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል የማይታዘዙትን ይበቀላል፤”

ጌታ ኢየሱስ ከሰማይ ከኃያላን መላእክቱ ጋር ሲገለጥ (ማለትም፣ ዳግም ሲመጣ) ያኔ እረፍትን ሊያገኙ ነው። The NIV Cultural Background Study Bible የተሰኘ የማጥኛ መጽሃፍ የዚህን ደብዳቤ ጭብጥ ሲያብራራ፡- “ከአዲሶች አማኞች ጋር በአካል አብሯቸው መሆን ያልቻለው ጳውሎስ እምነታቸውን በዚህ ቃል ያበረታታል፣ እንዲሁም የክርስቶስን መምጣት በቅርቡ በመመልከት ተስፋቸውን ያጠናክራል” ይላል።

ይህ ደብዳቤ የተፃፈው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በተሰሎንቄ ለነበሩና መከራን እየተቀበሉ ላሉ አማኞች ነው፣ እነርሱም በዳግመኛ ምጽአት ጊዜ ስለሚቀቡሉት እረፍት ተስፋቸውን የሚነግራቸው ቃል ነው። እንግዲህ የዳግመኛ ምጽአቱ ጊዜ ገና አሁንም ወደፊት የሚጠበቅ ከሆነ፣ ይህ ተስፋ ያኔ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በከባድ መከራ ውስጥ እያለፉ ለነበሩት በተሰሎንቄ ላሉት አማኞች እረፍትን ሊሰጣቸው የሚችለው እንዴትና በምን አግባብ ነው? እነዚያ አማኞች እረፍታቸው በክርስቶስ ዳግም ምጽዓት ብቻ ነበር። ክርስቶስ ስላልመጣ እነርሱ እስካሁን አላረፉም ማለት የነበራቸውን ተስፋ ሃሰተኛ ተስፋ አያደርገውምን? ቀጥሎ ጳውሎስ፦ 

2ተሰሎንቄ 2፥ 1-2 “ነገር ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣትና ወደ እርሱ ስለ መሰብሰባችን፥ በመንፈስ ወይም በቃል ወይም ከእኛ እንደሚመጣ በመልእክት፦ የጌታ ቀን ደርሶአል ብላችሁ፥ ከአእምሮአችሁ ቶሎ እንዳትናወጡ እንዳትደነግጡም እንለምናችኋለን።” ይላል

ጳውሎስ በምዕራፍ 1 ላይ ስለ ዳግም ምጽአቱ እየተናገረ ነበር፣ አሁን ደግሞ “ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት” ይላል። አሁንም ከዚያው ርዕሰ ጉዳይ ሳይወጣ ስለ ዳግመኛ ምጽአቱ መናገሩን እንደቀጠለ ነው። The Complete Jewish Bible ቁጥር 2 ላይ ያለውን በዚህ መንገድ ያስቀምጣል። “not to be easily shaken in your thinking or anxious because of a spirit or a spoken message or a letter supposedly from us claiming that the Day of the Lord has already come” (ሲተረጎምም፣ “የጌታ ቀን መጥቶአል በምትል ከእኛ በተጻፈች መልእክት ወይም በሐሳባችሁ በቀላሉ አትናወጡ ወይም አትጨነቁ” የሚል ነው።) ሕያው ቃል አዲስ ኪዳን ትርጉምም “አንዳንድ ሰዎች ጊዜው ደርሷል በማለት በሚያወሩት ወሬ አትታወኩ፣ ሥጋትም አይግባችሁ” ይለዋል። አዲሱ መደበኛ ትርጉምም “የጌታ ቀን ደርሷል ብላችሁ ፈጥናችሁ ከአእምሮአችሁ አትናወጡ፣ አትደንግጡም” ይለዋል።

እንግዲህ እነዚያ የተሰሎንቄ ሰዎች የዳግመኛ ምጽአት ተፈጥሮው ምድርን ቡን አድርጎ የሚያቃጥል፣ ምድርንም ሙሉ በሙሉ የሚያጠፋ አይነት አመጣጥ ነው ብለው የሚያምኑ ከነበሩ፣ም ይህ ሁሉ የምድር ውድመት ሳይሆን በፊት “መጥቶአል” በሚል ቃል ስለ መምጣቱ እንዴት ሊታለሉ ይችላሉ? የዳግም ምጽአቱ ተፈጥሮ ዛሬ ብዙዎች እንደሚመለከቱትና እንደሚጠባበቁት አይነት ከሆነ፣ ጳውሎስ ምን ብሎ ሊጽፋቸው ይችል እንደነበር አስቡ፡- “እስቲ በመስኮት ተመልከቱ፣ ምድር እንደሆነ አሁንም አለች፣ ገና አልጠፋችም፤ ስለዚህም ጌታ አልመጣም ማለት ነው”። እነዚያ የተሰሎንቄ ሰዎች የጌታ ቀን አስቀድሞ የሆነ መስሏቸው ስለነበር ዛሬ ብዙዎቹ ሰዎች ከሚያዩበት በተለየ መልኩ ሳይመለከቱት አልቀረም። በዚህ ትስማማላችሁ? ለዚህ ምድር ፍጻሜ የሚሰጥ የዳግም ምጽአት ምሳሌ የሌለ መሆኑን ለማሰብ በጥቂቱ መፍቀድ ከቻልን፣ ምናልባት የዳግመኛ ምጽአቱን መጽሓፍ ቅዱሳዊ እውነታ መረዳት ልንጀምር እንችላለን።


መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብ እኛ ካለንበት ዘመን ራቅ ባለ ጊዜ እና ለእኛ እንግዳ በሆኑ ባሕሎች ውስጥ እንደተጻፈ መረዳት አለብን። ጸሐፊው ምን እያለ እንደሆነ የንግግሩን ትርጉም ለማወቅ በምንሞክርበት ጊዜ፣ በዘመኑ ከነበሩት ሰዎች እንደ አንዱ ሆነን ጽሑፎቹን ማንበብና መማር አለብን። ይህንንም ለማድረግ እነርሱ ታናካህን (የአይሁድ ቅዱሳት መጻሕፍትን) እንደሚረዱት ሆነን መረዳት አለብን። ለምሳሌ፣ ራዕይ 1ን እንመልከት።

ራእይ 1፥ 7 “እነሆ፥ ከደመና ጋር ይመጣል፤ ዓይንም ሁሉ የወጉትም ያዩታል፥ የምድርም ወገኖች ሁሉ ስለ እርሱ ዋይ ዋይ ይላሉ። አዎን፥ አሜን።”

አብዛኞቹ የዘመናችን ክርስቲያኖች ይህንን አይነቱን አመጣጥ እንደ አካላዊና ተዳሳሽ መምጣት አድርገው ይመለከቱታል። ታናካህን (የአይሁድ ቅዱሳት መጻሕፍትን) ግን የምናውቅ ከሆነ ግን ከዚህ በተለየ ጌታ ብዙ ጊዜ በደመና ላይ ተቀምጦ የሚጋልብ እነደሆነ እናውቃለን (ለምሳሌ፣ መዝሙር 18፥ 7-15፤ 68፥ 4፤ 104፥ 3፤ እንዲሁም ናሆም 1፥ 3 ተመልከቱ)። መጽሐፍ ቅዱሳዊውን ምስል በጥንታዊው የመካከለኛው ምስራቅ ግንዛቤ ውስጥ አድርገን ስንመለከተው፣ የእግዚአብሔር ደመና እርሱ የሚጋልበው ሰረገላው እንደሆነ እንገነዘባለን። ተመልከቱ፦

ኢሳይያስ 19፥ 1 “ስለ ግብጽ የተነገረ ሸክም። እነሆ፥ እግዚአብሔር በፈጣን ደመና እይበረረ ወደ ግብጽ ይመጣል፤ የግብጽም ጣዖታት በፊቱ ይርዳሉ፥ የግብጽም ልብ በውስጥዋ ይቀልጣል”

እግዚአብሔር አሦራውያንን በግብፅ ላይ የቁጣው መሣሪያ አድርጎ እንደተጠቀመባቸውና እንዳመጣባቸው ከምዕራፍ 20 እናውቃለን፣ ነገር ግን ይህንን ፍርድ “እግዚአብሔር በፈጣን ደመና ላይ ተቀምጧል… ግብጽም በፊቱ ትንቀጠቀጣለች” በሚል አገላለጽ ያቀርበዋል። አዎ እግዚአብሔር ለፍርድ ወደ ግብፅ መጥቷል። ዳሩ ግን በአካልና በተዳሳሽ መልኩ ነው ወደ ግብፅ የመጣው? በጭራሽ አይደለም። ታዲያ እንዴት ነው ወደ ግብፅ “የመጣው"? በፍርድ መጣ፣ ማለት መገኘቱ በፍርዱ ታወቀ ማለት ነው። ነገር ግን ቃል በቃል በዚያ የተገኙት የእግዚአብሔር የፍርድ መሳሪያዎች ግን አሦራውያን ነበሩ።

ልክ እንደዚሁ፣ አዲስ ኪዳንም ኢየሱስ በደመና ላይ ሲመጣ ያለው ስዕል፣ ይህ ተፈጥሮአዊ የዝናብ ክምችት በሰማይ ላይ የሚፈጠረው ነጭ፣ ለስላሳና የጥጥ ባዘቶ መሳይ የደመና ክምችት እንዳልሆነ እንረዳለን። ከዚህ ይልቅ ግን በተቃራኒው በፍርድ የሚገለጥበትን የጭፍራ ማዕበል የሚወክል ደመና ነው። ታናካህን (የአይሁድ ቅዱሳት መጻሕፍትን) የበለጠ በተረዳን መጠን በዚያው ልክ የአዲስ ኪዳንን ቋንቋ በደንብ እንረዳለን።

  • የምጽአቱ ጊዜ እና ተፈጥሮው

የጌታ ዳግም ምጽአት ተስፋ ለተሰጣቸው ለመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች በትውልዳቸው ወስጥ ቶሎ ለመፈጸም የተቀጠረ ከሆነና ጌታችንና ሐዋርያቱ ዳግመኛ ምጽአቱ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ውስጥ እንደሚሆን በግልጽ ካስተማሩ እንግዲያውስ የዳግም ምጽአቱ ተፈጥሮ ሥጋዊ አካላዊና ተዳሳሽ ሳይሆን መንፈሳዊ መሆን አለበት ማለት ነው። አዲስ ኪዳንም ስለክርስቶስ መምጣት መቃረብ እንደሚናገር ግልጽ ነው።

አብዛኞቹ ክርስቲያኖች የምድርን የወደፊት ዕጣ ፈንታ ያመለክታል ብለው የሚያስቡት የመጽሐፍ ቅዱስ አንድ መጽሐፍ በተለይ የዮሓንስ ራዕይ መጽሐፍ ነው። ነገር ግን መጽሐፉ በትክክል ለሚናገረው ነገር ትኩረት ሰጥታችሁ ብትከታተሉት፣ በግልጽ የሚናገረው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ ሊሆኑ ስላሉ ነገሮች እንደሆነ ግልጽ ይሆንላችኋል።

ራእይ 1፥ 1-3 “ቶሎ ይሆን ዘንድ የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ ያሳይ ዘንድ እግዚአብሔር ለኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠው በእርሱም የተገለጠው ይህ ነው፥ ኢየሱስም በመልአኩ ልኮ ለባሪያው ለዮሐንስ አመለከተ፥ እርሱም ለእግዚአብሔር ቃልና ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ላየውም ሁሉ መሰከረ። ዘመኑ ቀርቦአልና የሚያነበው፥ የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁት ብፁዓን ናቸው።”

የራእይ መጽሐፍ በቀጥታ የተጻፈው ለማን ነው? ዛሬ ዛሬ አብዛኞቹ ክርስቲያኖች በቀጥታ ለእነርሱ የተጻፈላቸው ይመስላቸዋል። ልክ አሁን የደረሰ ትኩስ ዜና እንደሚያስነብብ ጋዜጣ ነው የሚመለከቱት። ነገር ግን ዮሐንስ በትንሿ እስያ ያሉትን ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ጠቅሶ ለማን እንደጻፈው በግልፅ ይነግረናል።

ራእይ 1፥ 4-5 “ዮሐንስ በእስያ ላሉት ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት፤ ካለውና ከነበረው ከሚመጣውም፥ በዙፋኑም ፊት ካሉት ከሰባቱ መናፍስት፥ ከታመነውም ምስክር ከሙታንም በኵር የምድርም ነገሥታት ገዥ ከሆነ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን”

እነዚህ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በትንሿ እስያ የነበሩ ሰባት እውነተኛ አብያተ ክርስቲያናት ነበሩ። በምዕራፍ 1 ላይ ሰባቱንም አብያተ ክርስቲያናት በስም ይጠቅሳቸዋል።

ራእይ 1፥ 10-11 “በጌታ ቀን በመንፈስ ነበርሁ፥ በኋላዬም የመለከትን ድምፅ የሚመስል ትላቅ ድምፅ ሰማሁ፥ እንዲሁም፦ የምታየውን በመጽሐፍ ጽፈህ ወደ ኤፌሶንና ወደ ሰምርኔስ ወደ ጴርጋሞንም ወደ ትያጥሮንም ወደ ሰርዴስም ወደ ፊልድልፍያም ወደ ሎዶቅያም በእስያ ወዳሉት ወደ ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ላክ አለኝ።”

አስተውሉ ዮሐንስ በዚህ በሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን ላይ በአዲስ አበባ ለምትገኝ ለየትኛዋም ቤተክርስቲያን መለልእክት እንዲልክ አልተነገረውም። ይህ መጽሐፍ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን በትንሿ እስያ ላሉ ሰባት አብያተ ክርስቲያናት የተላከ ለመሆኑ የደብዳቤው ተቀባዮች የሆኑትን አብያተ ክርስቲያናት በስም ጠቅሷል። ለምሳሌ

በትያጥሮን ላለችው ቤተ ክርስቲያን ኢየሱስ እንዲህ ብሎ ነበር።

ራእይ 2፥ 25 “ነገር ግን እስክመጣ ድረስ ያላችሁን ጠብቁ”

ኢየሱስ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በትያጥሮን ቤተ ክርስቲያን ይኖሩ የነበሩትን አማኞች “እኔ እስክመጣ ድረስ ያላችሁን ጠብቁ” ብሏቸዋል። ቋንቋውን ካላወሳሰብነው በቀር “እስክትሞቱ ድረስ አጥብቃችሁ ያዙ” ጨርሶ አይልም። ቋንቋው ለማንኛውም ትርጉም የተጋለጠና እኛን የመሰለንን የትኛውንም ነገር ማለት ከሆነ እንግዲያውስ ይህ በየትኛውም የሕይወት ዘመን ውስጥ እርሱ ይመጣል ማለት ይሆናል፣ ይህ ግን እንደርሱ ማለት አይደለም? ራዕይን እንተነትናለን የሚሉ አብዛኞቹ ተንታኞች የበኩረ ተደራስያኑን አስፈላጊነት እና አግባብነት ያለውን መሠረታዊ የትርጓሜ መርሆ ብዙ ጊዜ ሲጥሱ ይደመጣሉ። 

በራዕይ 1፥ 1 ላይ በግልጽ እንደተመለከተው፣ ዮሐንስ በተለይ የራዕዩ ትንቢቶች መፈፀም የሚጀምሩት በ”ቶሎ” እንደሆነ ተናግሯል።

ራእይ 1፥ 1 “ቶሎ ይሆን ዘንድ የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ ያሳይ ዘንድ እግዚአብሔር ለኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠው በእርሱም የተገለጠው ይህ ነው፥ ኢየሱስም በመልአኩ ልኮ ለባሪያው ለዮሐንስ አመለከተ፥”

ይህንን በቶሎ የተሰኘ እውነታ በተለያዩ መንገዶች ተመሳሳይ ቋንቋን እየተጠቀመ አጽንኦት ይሰጠዋል። ተመልከቱ በጉዳዩ ላይ ሊፈጠር የሚችለውን ግራ መጋባት ለማስወገድም የአገላለጾቹን መንገድ በጥንቃቄ ይለዋወጣል። በራእይ 1፡1 ላይ “ቶሎ” በሚል የተተረጎመው የግሪክ ቃል ‘tachos’ ይሰኛል። እንደ አርንድት እና ጊንሪች ሌክሲከን (የግሪክ መዝገበ ቃላት)፣ይህ ‘tachos’ የተሰኘ ቃል በሰባ ሊቃናት የብሉይ ኪዳን ትርጉምና በአንዳንድ ቀኖናዊ ባልሆኑ ጽሑፎች ውስጥ “ፍጥነት፣ ፈጣንነት፣ ፍጡንነት፣ ችኩልነት” በሚል አግባብ ጥቅም ላይ ውሏል። ዮሐንስም በራዕይ 2፥ 16; 3፥ 11; 22፥ 6፣ 7፣ 12፣ 20 የተጠቀመው ተመሳሳዩን ቃል ነው። ዮሐንስ በራእይ 1፥ 3 እና 22፥ 10 ላይ “ቀርቧል” ተብሎ ለተተረጎመው ቃልም ‘engus’ የተሰኘውን የግሪክኛ ቃል ተጠቅሟል። 

ራእይ 1፥ 3 “ዘመኑ ቀርቦአልና የሚያነበው፥ የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁት ብፁዓን ናቸው”

ይህ ቃል የሚያመለክተው ጊዜያዊና ወቅታዊ መቃረብን ነው። ዮሐንስ የመጽሐፉን መልዕክት ለማያያዝ ይጠቀምበታል። በመጽሐፉ ውስጥ የምናየው ጊዜ አመልካች የሆነው ሦስተኛው የግሪክ ቃል ‘mello’ ነው። ይህም በራዕይ 1፥ 19 እና 3፥ 10 ላይ “ሊሆን ያለው” ተብሎ ተተርጉሟል። ይህ በምዕራፍ 1፥ 19 ላይ ያለው ሀረግ፡ ፊት ለፊት ባለው ትርጉሙ በጊዜው ቅርበትና በዚያ አይነተኛ ወቅት ውስጥ “ሊፈጸሙ ያሉ ነገሮች” መሆኑን ያመለክታል። 

ራእይ 1፥ 19 “እንግዲህ ያየኸውን አሁንም ያለውን ከዚህም በኋላ ይሆን ዘንድ ያለውን ጻፍ”

ይህ ሜሎ የተሰኘው ቃል በራእይ 3፥ 10 ላይም በድጋሚ ይከሰታል፤ እንዲህ ሲል፦

ራእይ 3፥ 10 “የትዕግሥቴን ቃል ስለ ጠበቅህ እኔ ደግሞ በምድር የሚኖሩትን ይፈትናቸው ዘንድ በዓለም ሁሉ ላይ ሊመጣ ካለው ከፈተናው ሰዓት እጠብቅሃለሁ።”

“በዓለም ሁሉ ላይ ሊመጣ ያለው” የሚለው የአማርኛ አረፍተ ነገር ‘ሜሎ’ የተሰኘውን የግሪክ ቃል በመተርጎም ረገድ ምናልባትም ከአንዳንድ የእንግሊዝኛ ትርጉሞች በተሻለ ይገልጠዋል። ቃሉን ስንተረጉም የቡኩረ ተደራስያኑን አግባብነትና ጠቀሜታ የትርጉም መርህ በጥንቃቄ ተግባራዊ ማድረግ ከተቻለን እነዚያ የመጀመሪያዎቹ የመልክቱ አንባቢዎች ይህንን ቃል ሲያነቡ ምን ሊያስቡ እንደሚችሉ እናስተውል ነበር። ዮሐንስ እነዚህን ቃላት በመጽሐፉ መግቢያና በመደምደሚያው ላይ ስልታዊ በሆነ መንገድ ተጠቅሞባቸዋል። ዮሐንስ ሰባቱን አብያተ ክርስቲያናት ሲያስጠነቅቅ እነዚህ ይፈጸማሉ፣ ይሆናሉ የተባሉ ነገሮች እነርሱ በነበሩበት ወቅትና አውድ ውስጥ በማንኛውም ጊዜ ሊከሰት የሚችሉ እንደሆነና ተግተው እንዲጠብቁአቸው እየነገራቸው ነበር። ይህንን ‘mello’ የተሰኘው የግሪክ ቃል ከትንቢት ፍጻሜ ጠቀሜታው አንጻር በዝርዝር የተመለከትንበትን ጥናት ማንበብ ቢያስፈልጋችሁ በብሎገሬ የተለጠፉውን ጽሁፍ እንድታዩ እጋብዛለሁ፤ ሊንኩም፦ https://gizachewkr.blogspot.com/2021/09/blog-post_26.html?m=1

ስለዚህ፣ በእነዚህ ጊዜ ጠቋሚ በሆኑ መግለጫዎች እና ሌሎች በርካታ ነገሮች ላይ በመመስረት፣ ኢየሱስ እንደተናገረው ተመልሶ የመጣው በ70 ዓ.ም ላይ እንደሆነ ለማስተዋልና እንደዚያ ለማመን አይጎረብጠንም። ከፊል ሀላፋውያን ይህንን የ70 ዓ.ም መምጣት ከመምጣቶች አንዱ እንደሆነ እንጂ እውነተኛውና የመጨረሻው የትንቢት ፍጻሜ የሆነው ዳግመኛ ምጽአቱ እንደሆነ ለማመን ስለሚቸግራቸው አሁንም ገና ወደፊት የክርስቶስን ዳግመኛ መምጣት ይጠባበቃሉ። ነገር ግን ይህ በራእይ መጽሐፍ መጀመሪያ ላይ ጥቅም ላይ የዋለው ተመሳሳይ ጊዜ ጠቋሚ የሆነው ቃል በመጽሐፉ መጨረሻም ላይ ጥቅም ላይ መዋሉን ማስተዋል ከቻሉ መጽሐፉ ተጀምሮ እስኪጠናቀቅ ድረስ የሚያወራው ስለ አንዱ ፍጻሜና ስለ አንዱ ምጽአት እንደሆነ ማየት ይችላሉ። ተመልከቱ በመጽሐፉ መዝጊያም ላይ እንዲህ ይላል፦

ራእይ 22፥ 6-7 “እርሱም፦ እነዚህ ቃሎች የታመኑና እውነተኛዎች ናቸው፥ የነቢያትም መናፍስት ጌታ አምላክ በቶሎ ሊሆን የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ እንዲያሳይ መልአኩን ሰደደ። እነሆም፥ በቶሎ እመጣለሁ። የዚህን መጽሐፍ ትንቢት ቃል የሚጠብቅ ብፁዕ ነው አለኝ።”

ራእይ 22፥ 10 “ለእኔም፦ ዘመኑ ቀርቦአልና የዚህን መጽሐፍ ትንቢት ቃል በማኅተም አትዝጋው።”

ራእይ 22፥ 12 “እነሆ፥ በቶሎ እመጣለሁ፥ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር አለ።”

በመጨረሻዎቹ 16 ቁጥሮች ውስጥ ብቻ በትንሿ እስያ ላሉ ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት በቅርቡ ወደ እነርሱ እንደሚመጣ አምስት ጊዜ ያህል እያከታተለ ይነግራቸዋል። ከፊል ሀላፋውያን ይህ እንደሚያስቸግራቸው ግልጽ ነው። እኔም ብሆን ከፕሪቴሪዝም ጋር ስተዋወቅ ለመጀመሪያዎቹ ጥቂት አመታት ይህንን በእግዚአብሔር ቃል ማየት ስለተሳነኝ ሙሉ ሀላፋዊነትን ለመቀበል ያስቸግረኝ ነበር። አንዱም ምክንያት እንደዚህ የሚያምንና የሚያስተምር ሌላ ሰው አለማወቄ ነበር

ደግሜ እላለሁ፣ እነዚህ የመጨረሻዎቹ ጥቅሶች ለከፊል ሀላፋውያን በጣም ከባድ መሆን አለባቸው። ጊዜ ጠቋሚ የሆኑ እነዚህ መግለጫዎች ጠቅላላውን ይህንን መጽሐፍ በቅንፍ የሚያደርጉት ሲሆን፣ በመጽሐፉ ውስጥ ያሉትን ሁሉንም ነገሮች ማለትም ዳግም ምጽአትን፣ አጠቃላዩን ፍርድንና የሙታን ትንሳኤን ሁሉ ያጠቃላሉ። ለነዚያ የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ተደራስያን ሁሉም ነገር በቅርቡ የሚፈጸሙና በትውልዳቸው ቀነ ቀጠሮ የተያዘላቸው ነበሩ። ከፊል ሀላፋውያንን የሚገልጽ አንድ ቃል ይገኝ ከሆነ ያው መጻኢነት ነው። ከፊል ሀላፋውያን ማለት እነርሱም ጠባቂ መጻእያን ናቸው። 

  • የጥንት ክርስቲያኖችና ምጽአት

መጽሐፍ ቅዱስን ስናነብ፣ የበኩረ ተደራስያኑን አውድ ያገናዘበ የትርጉም መርሆን በአእምሯችን መያዝ አለብን። መፅሃፍ ቅዱስ "ለእኛ" (for us) ተብሎ እንደተፃፈ መረዳት አለብን እንጂ በቀጥታ "ለእኛ" (to us) አልተጻፈም። የትኛውም የቅዱሳት መጻሕፍት ምንባብ ከሁሉ አስቀድሞ ለበኩረ ተደራሲያኑ ምን ማለት እንደሆነ ለመረዳት አጥብቀን መፈለግ አለብን፤ ከዚያ በኋላ የህይወት ተዛምድውን ወስደን በራሳችን ላይ ተግባራዊ ማድረግ እንችላለን። 

የመጀመርያው ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖች ኢየሱስ በእነርሱ የህይወት ዘመን ተመልሶ እንደሚመጣ የነበራቸው መጠባበቅና፣ ይህንን አይነት መጠባበቅ እንዴት ሊኖራቸው እንደቻለ፣ ከየትስ እንዳገኙት ሁልጊዜ ሲያስገርም የሚኖር ጉዳይ ነው። ለጥንት ቤተክርስቲያን ሰዎች ክርስቶስ በትውልዳቸው ተመልሶ እንደሚመጣ በቃል የተነገራቸውም ሆነ በመልእክት የተጻፈላቸው ቃል በመንፈስ ቅዱስ የተመራ ንግግርና ጽሁፍ የሆነውን ያህል፣ እንዲሁ እነዚያው የጥንት ክርስቲያኖች የጌታን ቀን ይናፍቁና ይጠባበቁ የነበረበት ያ ተስፋ፣ እምነትና ናፍቆት በመንፈስ ቅዱስ የተመራ ነበር። ክርስቶስ ተመልሶ የሚመጣው መቼ እንደሆነ ክርስቶስ ራሱና ሐዋርያቱ ተናግረው ነበር ወይ? ታዲያ መቼ ነው ተመልሶ ይመጣል ያሉት? 

ለምሳሌ የሚከተሉትን ጥቅሶች ስትመለከቱ የሚከተሉትን ጥያቄዎች ራሳችሁን ጠይቁ፡ ይህ የተፃፈው ለማን ነው? መቼስ ነው የተጻፈው? እነርሱስ ክርስቶስ መቼ ይመጣል ብለው ጠብቀው ነበር?

ኢየሱስ ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ ብሏቸው ነበር፦

ማቴዎስ 10፥ 23 “በአንዲቱ ከተማም መከራ ቢያሳዩአችሁ ወደ ሌላይቱ ሽሹ፤ እውነት እላችኋለሁና፥ የሰው ልጅ እስኪመጣ ድረስ የእስራኤልን ከተማዎች አትዘልቁም።

ማቴዎስ 16፥ 27-28 “የሰው ልጅ ከመላእክቱ ጋር በአባቱ ክብር ይመጣ ዘንድ አለውና፤ ያን ጊዜም ለሁሉ እንደ ሥራው ያስረክበዋል። እውነት እላችኋለሁ፥ የሰው ልጅ በመንግሥቱ ሲመጣ እስኪያዩ ድረስ እዚህ ከሚቆሙት ሞትን የማይቀምሱ አንዳንድ አሉ።”

ማቴዎስ 24፥ 34 “እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም።

ኢየሱስ ለጴጥሮስ ይህንን ብሎት ነበር፦

ዮሐንስ 21፥ 21-22 “ጴጥሮስም ይህን አይቶ ኢየሱስን፦ ጌታ ሆይ፥ ይህስ እንዴት ይሆናል? አለው። ኢየሱስም፦ እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ፥ ምን አግዶህ? አንተ ተከተለኝ አለው።”

ጳውሎስ ለሮሜ ክርስቲያኖች ይህንን ብሎ ነበር፦

ሮሜ 13፥ 11-12 “ከእንቅልፍ የምትነሡበት ሰዓት አሁን እንደ ደረሰ ዘመኑን እወቁ፤ ካመንንበት ጊዜ ይልቅ መዳናችን ዛሬ ወደ እኛ ቀርቦአልና። ሌሊቱ አልፎአል፥ ቀኑም ቀርቦአል። እንግዲህ የጨለማውን ሥራ አውጥተን የብርሃንን ጋሻ ጦር እንልበስ።”

ሮሜ 16፥ 20 “የሰላምም አምላክ ሰይጣንን ከእግራችሁ በታች ፈጥኖ ይቀጠቅጠዋል። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከእናንተ ጋር ይሁን።

ጳውሎስ በቆሮንቶስ ለነበሩ ክርስትያኖች እንዲህ ብሎ ነበር፦

1ቆሮንቶስ 1፥ 7-8 “እንደዚህ የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን መገለጥ ስትጠባበቁ አንድ የጸጋ ስጦታ እንኳ አይጎድልባችሁም፤ እርሱም ደግሞ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቀን ያለ ነቀፋ እንድትሆኑ እስከ ፍጻሜ ድረስ ያጸናችኋል።”

1ቆሮንቶስ 7፥ 29-31 “ዳሩ ግን፥ ወንድሞች ሆይ፥ ይህን እናገራለሁ፤ ዘመኑ አጭር ሆኖአል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሚስቶች ያሉአቸው እንደሌላቸው ይሁኑ፥ የሚያለቅሱም እንደማያለቅሱ፥ ደስ የሚላቸውም ደስ እንደማይላቸው፥ የሚገዙም ምንም እንደሌላቸው፥ በዚችም ዓለም የሚጠቀሙ በሙሉ እንደማይጠቀሙባት ይሁኑ፤ የዚች ዓለም መልክ አላፊ ነውና።”

1ቆሮንቶስ 10፥ 11 “ይህም ሁሉ እንደ ምሳሌ ሆነባቸው፥ እኛንም የዘመናት መጨረሻ የደረሰብንን ሊገሥጸን ተጻፈ።

1ቆሮንቶስ 15፥ 51-52 “እነሆ፥ አንድ ምሥጢር እነግራችኋለሁ፤ ሁላችን አናንቀላፋም ነገር ግን የኋለኛው መለከት ሲነፋ ሁላችን በድንገት በቅጽበተ ዓይን እንለወጣለን፤ መለከት ይነፋልና ሙታንም የማይበሰብሱ ሆነው ይነሣሉ እኛም እንለወጣለን።

እዚህ ላይ “እኛ” የተባሉት ጳውሎስ እና በቆሮንቶስ የነበሩ የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመንአማኞች ናቸው። 

ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ክርስቲያኖችም ይህንን ይላል፦

ፊልጵስዩስ 1፥ 6 “በእናንተ መልካምን ሥራ የጀመረው እስከ ኢየሱስ ክርስቶስ ቀን ድረስ እንዲፈጽመው ይህን ተረድቼአለሁና፤

ፊልጵስዩስ 4፥ 5 “ገርነታችሁ ለሰው ሁሉ ይታወቅ። ጌታ ቅርብ ነው።”

ጳውሎስ በተሰሎንቄ ለነበሩ ክርስቲያኖችም ይህንን ይላል

1ተሰሎንቄ 4፥ 15 “በጌታ ቃል የምንላችሁ ይህ ነውና፤ እኛ ሕያዋን ሆነን ጌታ እስኪመጣ ድረስ የምንቀር ያንቀላፉቱን አንቀድምም፤

1ተሰሎንቄ 5፥ 23 “የሰላምም አምላክ ራሱ ሁለንተናችሁን ይቀድስ፤ መንፈሳችሁም ነፍሳችሁም ሥጋችሁም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጣ ጊዜ ያለ ነቀፋ ፈጽመው ይጠበቁ።

ጳውሎስ ለጢሞቴዎስም እንዲህ ብሎታል፦

1ጢሞቴዎስ 6፥ 14 “ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እስኪገለጥ ድረስ ያለ እድፍና ያለ ነቀፋ ሆነህ ትእዛዙን ጠብቅ፤

ጳውሎስ ለቲቶም እንዲህ ብሎት ነበር፦

ቲቶ 2፥ 12-13 “ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤

ጳውሎስ ለእብራውያን ክርስቲያኖችም እንዲህ ብሏቸው ነበር፦

እብራውያን 9፥ 28 “እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ፥ የብዙዎችን ኃጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ፥ ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታይላቸዋል።”

እብራውያን 10፥ 37 “ገና በጣም ጥቂት ጊዜ ነው፥ ሊመጣ ያለውም ይመጣል አይዘገይምም፤

"ገና ጥቂት ጊዜ ነው" የሚለው እዚህ ላይ ያለው የግሪኩ አገባብ በጣም ገላጭ እና አጽንዖት የሚሰጥ ንግግር ነው። ጸሐፊው በንግግሩ “ጥቂት” ሲል “ሊመጣ ላለው”፣ “ለሚመጣው” ጉዳይ በልዩነት የቀረ “ትንሽ ጊዜ”ን የሚያመለክት ቃል ተጠቅሟል፤ ነገር ግን ይህንን የቀረ በጣም ትንሽ ጊዜ የበለጠ አጽንዖት ሲሰጠው “በጣም” የሚልን አጠናካሪ ተቀጥላን ያያይዛል። ትርጉሙም ላቅ ያለ ነውና “በጣም” በማለቱም የቀረውን ጊዜ አጭርነት የበለጠ አጠናክሮታል። ስለዚህም ይህንን ሐረግ ቃል በቃል፡- “ገና በጣም ጥቂት ጊዜ አለ፥ የሚመጣውም ይመጣል” ሲል ይገልጸዋል። ይህም “ለሚጠባበቁት” ወይም ይጠባበቁት ለነበሩት ነው።

ጴጥሮስም ለክርስቲያኖች ሲጽፍ የሚከተለውን ይላል፦

1ጴጥሮስ 1፥ 13 “ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና በመጠን ኖራችሁ፥ ኢየሱስ ክርስቶስ ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ።

1ጴጥሮስ 4፥ 7 ”ዳሩ ግን የነገር ሁሉ መጨረሻ ቀርቦአል። እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ፥”

1ጴጥሮስ 4፥ 17 “ፍርድ ከእግዚአብሔር ቤት ተነሥቶ የሚጀመርበት ጊዜ ደርሶአልና፤ አስቀድሞም በእኛ የሚጀመር ከሆነ ለእግዚአብሔር ወንጌል የማይታዘዙ መጨረሻቸው ምን ይሆን?

እነዚህ ጥቅሶች የክርስቶስን ዳግመኛ ምጽአት ከኢየሩሳሌም ውድቀት፣ ከቤተ መቅደሱ ውድመት፣ እንዲሁም በ70 አ.ም ላይ ከሆነው የአይሁድ ህዝብ እልቂትና የብሉይ ኪዳን የመስዋዕቱ ስርዓት ፍጻሜ ጋር ባለው ግንኙነት አንጻር የሚናገሩና የሚያስተምሩ ናቸው። እነዚያ የቤዛነት ትእይንት የመጨረሻ ኹነቶች ልክ እርሱ ይሆናሉ ሲል እንደተናገረው ተፈጽመው አልፈዋል፣ ስለዚህ ጊዜን አመልካች የሆነውን የትንቢቶቹን አቀራረብ ቸል ብሎ፣ "ትንቢቱ ገና ወደ ፊት ይፈጸማል እንጂ እስከ አሁን ገና አልተፈጸመም" ሲል፣ ሳይፈጸም እንደቀረ ወይም እንደዘገየ የሚያስተምረውን እድሜ ዘልዛላ አመለካከት ለማብራራትም ሆነ ለመተንተን መሞከር በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ውስጥ ጊዜው ያለፈበትና ምንም አስፈላጊነት የሌለው ነው።

ይልቁን ግን በኩረ ተደራስያኑ አንድን የንባብ ክፍል ምን ማለት እንደሆነ የተረዱበትን መንገድ ለማወቅ አውዳቸውን ከግምት ውስጥ ማስገባት አለብን። ጌታ ለእነርሱ በቅርቡ እንደሚመጣ ተናግሯል፣ ስለ መምጣቱም ሲናገር እነሆ "በደጅ" ነው ብሏል። ስለዚህ የሚመጣው ወይም ሊመጣ ያለው በእነዚያ በሚናገራቸው ሰዎች የሕይወት ዘመን ነው ማለት ነው። "በትውልዳቸው ውስጥ" እንደሚመጣ ተናግሯቸዋል። ክርስቶስ በዘመናቸው በቅርቡ ተመልሶ ለመምጣት የሰጣቸውን ተስፋ እና እነርሱ የነበሩበትን የመጠባበቅ ሁኔታ፣ በመንፈስ ቅዱስም የተመራውን ናፍቆታቸውን አጥርታችሁ ሳታዩ አዲስ ኪዳንን ማንበብም ሆነ መረዳት አትችሉም። ለብዙዎች ችግር የሚፈጥርባቸውም ይህ ነው። ይህንንም ባለመረዳት በሥነ ፍታቴአቸውና እንከተለዋለን በሚሉት ሥነመለኮት ላይ ባቆሙት የነገረ ፍጻሜ አስተንትኗቸው ጌታ ኢየሱስን እና የአዲስ ኪዳን ጸሃፍያንን ለከሃዲያን ስድብ አሳልፈው ይሰጣሉ። 

ያዕቆብን ደግሞ ስሙት፦

ያዕቆብ 5፥ 7-9 “እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ታገሡ። እነሆ፥ ገበሬው የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ እስኪቀበል ድረስ እርሱን እየታገሠ የከበረውን የመሬት ፍሬ ይጠብቃል። እናንተ ደግሞ ታገሡ፥ ልባችሁንም አጽኑ፤ የጌታ መምጣት ቀርቦአልና። ወንድሞች ሆይ፥ እንዳይፈረድባችሁ እርስ በርሳችሁ አታጉረምርሙ፤ እነሆ፥ ፈራጅ በደጅ ፊት ቆሞአል።”

በኩረ ተደራስያኑ በቀጥታ ለእነርሱ የተጻፈላቸውን ጉዳይ የያዘ አንድን የንባብ ክፍል ምን ማለት እንደሆነና ምን ትርጉም እንደሰጣቸው እነርሱ የተረዱትን ለማወቅ የጽሁፉን አውደ ምንባብ እና የበኩረ ተደራሲያኑን አግባብነት ማስታወስ አለብን። ጌታ ቶሎ እንደሚመጣ ነግሯቸዋል፤ የእርሱ መምጣትም "በደጅ" መሆኑን ነግሯቸዋል፣ ሊመጣ ያለውም እነዚያ እርሱ የሚናገራቸውና ንግግሩን ቆመው ይሰሙ በነበሩ ሰዎች የሕይወት ዘመን መሆኑን ነግሯቸዋል። "በትውልዳቸው" እንደሚመጣም ነግሯቸዋል። እንግዲህ እነርሱ አዲስ ኪዳንን የጻፉልንና መልእክቶቻቸውን ያነበቡ የመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ክርስቲያኖች ለክርስቶስ ዳግመኛ መምጣት የነበራቸውን የቅርብ ጊዜ ተስፋ እና ያንን በመንፈስ ቅዱስ የተመራ መጠባበቅ አጥርታችሁ ሳታዩ አዲስ ኪዳንን ማንበብም ሆነ መረዳት አትችሉም። ለብዙ ወዳጆቼ ችግር የሚፈጥርባቸው ይህ እንደሆነ እረዳለሁ። 

  • የክህደት ጥግ

በዚያው ትውልድ ውስጥ ለመመለስ የሰጠውን የተስፋ ቃል ኢየሱስ ጠብቋልን? ቃሉንስ አላጠፈምን? ሐዋርያቱስ ቢሆኑ ክርስቶስ በራሳቸው የሕይወት ዘመን በቅርቡ ተመልሶ እንደሚመጣ ሲናገሩ የነበረው ንግግራቸው ትክክል ነበርን? አልተሳሳቱም ነበርን? እነዚህ ከፍ ሲል ያየናቸውና ሌሎች መሰል ጥቅሶች ሁልጊዜም ቢሆን የመጽሐፍ ቅዱስ ተማሪዎችን የሚረብሹና ምቾት የማይሰጡአቸው እንደሆኑ ግልጽ ነው። የሥነ መለኮት "አዋቂዎች" ነን ለሚሉ የለዘብተኝነትን አቋም ለያዙ ሊቃውንት ነን ባዮችና ለከሃድያን ደግሞ የቅዱሳት መጻሕፍትን እውነተኛነት ለመንቀፍና ስህተት የለባቸውም ስንል የምናምነውን የእኛን እምነት ለማጥቃት ይጠቀሙባቸዋል። "እነዚህ ምንባባት ይፈጸማሉ በተባሉበትና እንዲፈጸሙ በተነገረላቸው ጊዜ (በመጀመርያው ክፍለ ዘመን ትውልድ ወቅት) አልተፈጸሙም፣ ስለዚህ ኢየሱስም ሆነ የአዲስ ኪዳን ጸሓፍያን በትንቢታቸው ወድቀዋል፣ በመሆኑም ቃሎቻቸውን በመንፈስ ቅዱስ በመነዳት የተሰጡና ስህተት የሌለባቸው ናቸው ለማለት አንችልም" ሲሉ ይተቻሉ።

ራሱን “አምላክ የለሽ” ብሎ የሚጠራው በርትራንድ ራስል፣ “Why I Am Not A Christian” (ለምን ክርስቲያን አልሆንኩምም) በተሰኘው የክህደት መጽሐፉ ላይ ይህን ግልጽ መደምደሚያ ተጠቅሟል፡-

"በወንጌል ትረካ ውስጥ እንደተገለጸው በእጅጉ አሳሳቢ የሆነ የክርስቶስ ንግግር አለ፤ በዚያም በጣም ጥበብ የሚጎድላቸው የሚመስሉ ነገሮችን ማንም ሰው ሊያስተውል ይችላል። ዳግመኛ ምጽአቱን በተመለከተ እየደጋገመ በእርግጠኝነት የተናገረው በክብር ደመና ታጅቦ በዚያን ጊዜ ይኖሩ የነበሩት ሰዎች ሁሉ ከመሞታቸው በፊት እንደሚመጣ አስቦ ነበር። ይህን የሚያረጋግጡ ብዙ ምንባባት አሉ፣…. የጥንቶቹ ተከታዮች እምነትም ያ ነበር፣ ይህም ንግግሩ እርሱ ላስተማረው የጥሩ ሥነ ምግባራዊ ትምህርት መሠረቱ ነበር” (ገጽ 16)።

ራስል ኢየሱስ ከቃሎቹ የተነሳ የእግዚአብሔር ልጅ ሊሆን እንደማይችል ለማስረዳት በአዲስ ኪዳን ውስጥ “በቶሎ” ሊፈጸሙ የተሰጡ ትንቢታዊ ምንባባትን እንደ “ማስረጃ” አድርጎ ተጠቅሞባቸዋል። የዘመናችን ክርስትናም፣ በአጠቃላይ፣ ከሃዲያን ከሆኑ አምላክ የለሾች እና በጥቅሉ ክርስቲያን ካልሆኑ ሰዎች ለሚሰነዘሩበት ተቃውሞ በቂ ምላሽ መስጠት አለመቻሉ ያሳዝናል። ይልቁንም መጻኢነት ይህንን ክህደት ለመመከት በቆመበት የሸንበቆ ምርኩዝ በሆነው የነገረ ፍጻሜ አስተምህሮው ሲውተረተር ክርስትናንና ትምህርቱን ለማስቀጥቀጥ ዱላ አቀባይ ሆኖት አርፏል። አማኞች ግን ዛሬ ክርስቶስ ስለ ፍጻሜ ዘመን ያቆመውን አስተምህሮ ከጥቃት ለመመከትና በጥቅሉ በክርስትናው አለም ያለውን ሰፊ ​​ነገረ ፍጻሜአዊ አለመግባባት ለመፍታት በትምህርታቸውና በእምነታቸው ላይ የክለሳ ስራ ማድረግ አለባቸው።

ማቴ 24፥ 34 “እውነት እላችኋለሁ፥ ይህ ሁሉ እስኪሆን ድረስ ይህ ትውልድ አያልፍም።

ኢየሱስ በግልጽ እና በማያሻማ ሁኔታ እነዚያ የጠቀሳቸው ነገሮች በሙሉ በትውልዳቸው ውስጥ እንደሚፈጸሙ ለደቀ መዛሙርቱ ነግሯቸዋል። ዐውደ-ምንባቡን በጥንቃቄ ካጠናችሁ ይህ በትውልዳቸው ውስጥ እንደሚፈጸም የነገራቸው ዝርዝር፣ የወንጌልን በዓለም ሁሉ መሰበክ፣ የጥፋት እርኩሰት መቆምን፣ የታላቁ መከራ ክስተትን፣ እና የክርስቶስ ዳግም ምጽአትን እንደሚጨምር ታያላችሁ። ይህ በጣም ግልፅ ከመሆኑ የተነሳ በልማዳዊው አስተምህሯቸው ውስጥ ሲያምኑትና ሲከተሉት ከኖሩት ስነመለኮታቸው ጋር ስለሚጣረስ የመጻኢነትን ነገረ ፍጻሜ ለሚያቀነቅኑ ወገኖች ይህ በእጅጉ ያስቸግራቸዋል። ባወጣው ባወርደው አልገባህ፣ አልከሰትልህ ያለኝ አንድ ነገር፣ ኢየሱስ እንደተናገረው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ ይጠባበቁት ለነበሩ ለትውልዱ ዘመን አማኞች በክብር እንደተመለሰ፣ በዚያው ዘመን አመጸኛይቱ እስራኤል ላይም በእሳት ፍርድ እንደተገለጠ፣ የዳግመኛ ምጽአቱም ተስፋ ያኔ እንደተፈጸመ መቀበል የሚቸግራቸው ወንጌል አማኝ መጻኢያንክርስቲያኖች በእውነት የሚያነቡት መጽሐፍ፣ መጽሐፍ ቅዱስን ነውን፣ ወይስ መጽሐፈ ደሮ?

ሲኤስ ሉዊስ “The World's Last Night" በተሰኘው ድርሰቱ ስለ ማቴዎስ 24፥ 34 ሲናገር አንዲህ በማለት አንድ ተቃውሞ አቅርቧል፦

"የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች አቡቀሉምሲሳዊ እምነቶቻቸው ሀሰት መሆናቸው ተረጋግጧል። ሁሉም ገና በሕይወት እያሉ ዳግመኛ ምጽአቱ እንደሚፈጸም ይጠባበቁ እንደነበር ከመላው አዲስ ኪዳን ግልጽ ነው። ይባስ ብሎም ለዚህ የተሳሳተ እምነት አብይ ምክንያት እንደነበራቸው፣ አንዱንና ዋናውን ጉዳይ ማየት ትችላላችሁ። ይህም በጣም አሳፋሪ የሆነው ነገር ይህንን እየደጋገመ ይነግራቸው የነበረው ጌታቸው መሆኑ ነው። እርሱ ግን ከማንም በላይ ስለ አለም ፍጻሜ ምንም የሚያውቀው ነገር አልነበረም።"

ሉዊስ አክሎም እንዲህ ይላል

"ይህ በእውነት በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ካሉት እጅግ አሳፋሪ ጥቅሶች መካከል አንዱና ዋናው ነው። ነገር ግን በተነገሩት ዝርዝሮች ውስጥ እንዲህ ያለው መሳቂያ የሆነ መግለጫ እንዴት እንደሚሰነቀር ተመልከቱ። ደግሞኮ “ስለዚያች ቀንና ስለዚያች ሰዓት ግን ከአባት ብቻ በቀር የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ ልጅም ቢሆን የሚያውቅ የለም” ይላል። አንደኛው የስህተት ማሳያ ሲሆን አንዱ ደግሞ የድንቁርና ኑዛዜ ሆኖ ጎን ለጎን በቅለው አብረው ይታያሉ” [Essay "The World's Last Night" (1960), found in The Essential C.S. Lewis, p. 385]

ስለዚህም ሉዊስ በድፍረት “ይህ ትውልድ” ሲል የተናገረውን የኢየሱስን ንግግር ጠቅሶ ቃሉ አሳፋሪና “ስህተት” ነው ሲል ያላግጣል። ሉዊስ እንዳለው ኢየሱስ ተሳስቶ ነበርን? እኔ በግሌ ጌታ ኢየሱስን ለዘላለም ሕይወት እንደተቀበለ አማኝ ያንን የሉዊስን የድፍረት ድምዳሜ መቀበል አልችልም? ይህ የሉዊስ እና የመሰሎቹ ምሁራዊ ቅርሻት በጌታዬ ፊት ላይ ሲተፋ ማየትም አይሆንልኝም። 

ደስ የሚለው ግን ክርስቶስ እንደተናገረው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ትውልድ ውስጥ ተመልሶ ለመምጣት የገባውን ቃል መጠበቁ ነው። የክርስቶስ ዳግም ምጽአት መንፈሳዊ በሆነ መልኩ ተፈጽሟል - እርሱም እመጣለሁ ባለበት መንገድ - በ70 ዓ.ም ላይ በሆነው በኢየሩሳሌም ጥፋት ተገልጧል። ይህም የተረጋገጠ ታሪካዊ ክስተት ለኃጢአት ፍጻሜውን የሰጠ፣ የዘላለም ስርየትን ያስገኘ ሲሆን፣ በትውልዶች ሁሉ ውስጥ ላሉ ክርስቲያኖችም ከእግዚአብሔር ሳይለዩ በምድርም ሆነ በሰማይ ለዘላለም መኖራቸውን ያረጋገጠ ነው።

እዚህ ላይ አሁን የሚከተለውን ጥያቄ ታነሱ ይሆናል፡- ጌታ በ70 ዓ.ም ተመልሶ ከመጣ፣ ታዲያ ቤተክርስቲያን በእነዚህ ሁሉ ዓመታት ይህንን እንዴት ልታውቅ አልቻለችም? እንዴት ተመልሶ መጥቶ ሳለ ቤተ ክርስቲያን ይህንን ያላወቀችው ከምን የተነሳ ነው? እኔ እንደሚገባኝ እዚህ ላይ ያለው አንዱ ትልቁ ችግር አስቀድሞ አእምሯችንን የገዛና ሲታሰብ የኖረው ሐሳብ ነው። እንዲህ ላሉ ጥያቄዎች መልስ መስጠት የተሳነን ለዘመናት ተንጠላጥለን ካለንበት፣ እውነት መስሎን ከያዝነው ልማዳዊ አሳባችን አልወርድ ከማለታችን የተነሳ ነው። ምክንያቱም፣ እኛን ሲመስለን ዳግመኛ ምጽአቱ ምድርን ቡን አድርጎ የሚያቃጥል፣ ሰማይን እንደ ሰም የሚቀልጥ፣ ዓለምን በሞላው ከፍጥረቱ የሚቀይር ክስተት አድርገን እናስበዋለን። ስለዚህም ይህ አስቀድሞ ሊከሰት ካልቻለ ዳግመኛ ምጽአቱ ሊሆን አይችልም ብለን ባለማወቅ ላይ የቆመ ግምትና ግግምና ይዘናልና።

እኔ ግን ጥያቄ ልጠይቃችሁ፣ የተሳሳተው ማን ነው? ቅዱሳት መጻህፍት ስህተት አለባቸው ለማለት እንደፍራለንን? ቅዱሳት መጻህፍቱ ጊዜ ጠቋሚ በሆኑ የንባብ ክፍሎቻቸው ስለ ዳግም ምጽአቱ የተናገሩት ስህተት ነበርን? ወይስ በተቃራኒው እኛ ስለ ዳግም ምጽአት ተፈጥሮ የነበረን እይታ ነው ስህተት? ከሁለቱ የትኛውን ትመርጣላችሁ፣ የትኛውስ ምቾት ይሰጣችኋል? በስህተት የተሞላው ልማዳዊ ምልከታችሁ ወይስ ስህተት የሌለባቸው ቅዱሳት መጻሕፍት?

  • ፕሪቴሪዝም የተፈጸመው ወንጌል

ክርስቶስ ጠላቶቹን ሁሉ ድል ነስቶ መንግስቱን ሰጥቶናል። አሁን በክርስቶስ "የዘላለም ሕይወት" አለን። የዘላለምን ሕይወት ለማግኘት እስከ ትንሳኤ እና የፍርድ ቀን ድረስ በሀደስ ውስጥ የቤዛነታችንን ቀን እየጠበቅን መቆየት አያስፈልገንም። ያ ያስፈልጋቸው የነበሩት የብሉይ ኪዳን ቅዱሳን ነበሩ። እኛ ያመንን ግን በክርስቶስ ስራ ከፍርድ ወጥተን ወደ ዘላለማዊው መንግስት ሕይወት ተሸጋግረናል። እነዚህ በክርስቶስ አሁን ያሉን እና የተገኙ ከኛም ጋር በውስጣችን የሚኖሩ ባርኮቶቻችንና ጥቅሞቻችን ናቸው እንጂ፣ "ላም አለኝ በሰማይ ወተትዋንም አላይ" አይነት፣ ተስፋችን የተራበ ሰው እንደሚጓጓለት ርቆ እንደ ተሰቀለ እንቁልልጬ ዳቦ አይደለም። ቅዱስ ቃሉ፦ "የምትዘገይ ተስፋ ልብን ታሳዝናለች፤ የተገኘች ፈቃድ ግን የሕይወት ዛፍ ናት" (ምሳሌ 13፥ 12) ይላልና። መላው የራእይ መጽሐፍም የተፈጸመ መጽሐፍ ሲሆን፣ የሚታየውም መጽሐፉ በተጻፈበት ዘመን፣ በጸሐፊውና በበኩረ ተደራስያኑ ታሪካዊ አውድ ብቻ ነው። የመጽሐፉ አጠቃላይ ተዛምዶም በክርስቶስ ካገኘነውና ከተካፈልነው ከመንግስቱ ጋር የተቆራኘ ነው።

ቀጥተኛውና ግልጹ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትርጉም ይህ ነው። ትንቢትም ትርጉም የሚሰጠን አቀራረባችን በዚህ መንገድና አተያይ የሆነ እንደሆነ ብቻ ነው። ይህ አቀራረብ "የእግዚአብሔር ቃል ብቻ" (Sola Scriptura) በተሰኘው ብቸኛ የተሃድሶ ብርሃን እየተመራ በርካታ አወንታዊ፣ ገንቢና ተጨባጭ የሆነን ንጽረተ አለም ይሰጠናል። ይህ አይነቱ የትንቢት አቀራረብ በአቋሙ ወንጌላዊ የሆነውን ወግ አጥባቂነት የጨበጠ፣ በክርስቶስ ብዙ መጽናናትን የሚሰጥና ግርማ የሞላውን የክርስትናን የድልና የከፍታ ሕይወት የሚያለማምድ፣ በትርጉሙ ቀዋሚነት (consistency) ያለው፣ ብሩህ አመለካከትን ይዞ ጨለምተኛ ያልሆነ፣ ኃላፊነትና ተጠያቂነት የሚሰማው አቀራረብ ነው። ጣፋጩን የክርስትናን ሕይወት አጣጥሞ ከመኖርና አለምን በወንጌል ከመድረስና ከመለወጥ ያለፈ ሌላ ምኞትም ሆነ የተሰወረ ፍላጎት እንዳይኖረን የሚያደርገን ንጹህ ትምህርት ነው። በእግዚአብሔር መንግስት መንፈሳዊ ተፈጥሮ ላይ ትኩረቱን ያደረገ ትርጉም ነው፣ እንጂ የእግዚአብሔርን መንግስት በተዳሳሽ አካላዊነት፣ በቁሳዊነት፣ በፍልቅ ሞቅታና በስሜታዊነት ፍንደቃ አይለካም አይተረጉምም። ለሌላ ጊዜ በተላለፈና ገና ወደ ፊት እንደሚገባበት የገነት መንገድ ስሜታዊ በሆነ ደስታ ከሚያደክምና ከሚያሰለች ተስፋ ይልቅ፣ አሁን በክርስቶስ የሆነውንና የተገኘውን የተረጋገጠ መዳንን እና የቤተ ክርስቲያንን እውነታነት ያስተምራል። የትንቢትን ፍጻሜ ከመጀመሪያው ክፍለ ዘመን የታሪክ ሰነድ ገጾች ጋር እያገናዘበ ታሪክን የኋሊት ይመለከታል እንጂ ስለ መጻኢው ደንግጦ ባፈጠጠና በፈራ አይን ያንንም ይሄንንም እየገመተ "ምን ይመጣብኝ ይሆን" እያለ ራሱን በስጋትና በቁም ቅዠት አይጠምድም፤ የመጻኢነት ትንተናም እያቀረበ ማንንም አያሸብርም። ይህ አለም እንደሆነ ከረጅም ጊዜ ጀምሮ (ካስፈለገም ለዘላለም) እንዲሁ እንዳለ ይኖራል። የምስራች ልንገራችሁ፣ እግዚአብሔር ይህንን ግዑዝ አለም ሊያወድም ምንም እቅድ የለውም። የሰው ልጆች ቢፈልጉ እንኳ፣ ቢቆጡና ቢሞክሩ ይህንን ግዑዝ የእግዚአብሔር አለም ሊያጠፉት አይችሉም። ስለዚህ "ይህ አለም ይጠፋል" በሚል ተላላነት እየተደናበርን፣ በማህበረሰቡ ውስጥ ሊኖረን ከሚገባ ተሳትፎና በጎ ተጽእኖ በጨለምተኝነት ከማፈግፈግ፣ ብሎም ከዚህ ነባራዊ አለም ለመውጣትና ማምለጫን በመፈለግ በከንቱ ከምንደክም፣ ይህ አለም የእግዚአብሔርና የሰው ልጆች አለም ነውና፣ ለልጆቻችንና ለልጅ ልጆቻችን የተሻለ የመኖርያ ስፍራ እንዲሆን የማድረግ ኃላፊነታችንና አገልግሎታችንን በትጋት ብንቀጥል የእግዚአብሔርን ፈቃድ እናደርጋለን። 

ባለፉት 300 አመታት ውስጥ አንዳንድ ታላላቅ የሥነ መለኮት ሰዎችና ሊቃውንት ይህንን አመለካከት ይዘው እንደ ነበር ግልጽ ነው፤ ነገር ግን የሚበዙት ክርስቲያኖች የሮማውን ካቶሊክ ጳጳስ ወይም ጳጳሳዊ ስርአቱን "የክርስቶስ ተቃዋሚው" ነው፣ ደግሞም የሮምን ቤተክርስቲያን የራእይ መጽሐፍ "ባቢሎን" ናት በሚል ወይም በሌላ አይነት የመጻኢነት አስተሳሰብና ትርክት ተይዘው ሲያስተምሩና ሲጽፉ ኖረዋል። በዋናነትም በታሪካውያን (Historicism) እና በአልቦ ሺህ አመት መንግስት (Amillennialism) የነገረ ፍጻሜ ተርጓሚዎች ዘንድ ይህ አይነቱ ትርክት የተለመደ ነው። ያ ግን አሁን ጊዜው ያለፈበት አስተሳሰብ ሆኖ አጥብቀው በሚጠይቁና አድምተው በሚመረምሩ የቃሉ ተማሪዎች እየተተቸ በብዙ ተለውጦአል። አሁን ያለው ትውልድ (መደዴውን ማለቴ አይደለም) ከቀድሞው ይልቅ እምነቱንና አመለካከቱን አጥብቆ የሚጠይቅና የሚፈትሽ ነው ብዬ አስባለሁ። መቼም እነ ዊልያም ሚለር፣ ደርባይ፣ ረስል፣ ሩትፎርድ፣ ስኮፊልድ፣ ዋልቩርድ እና ሃል ሊንድሴይ በዘመን ቆጣሪነት (Despensationalism) ትርክት በብዙ ተታለው ሌሎችንም እንዳሳሳቱ እኛ በቀላሉ የምንሞኝ አይደለንም። በተደጋጋሚ ያለማቋረጥ ሲቆለል የኖረው የአስተምህሮ ውሸትና እስካሁንም ብዙዎች በትንቢት ትርጉማቸውና በአስተምህሮታቸው የሚያራግቡት የሃሰት ትንበያ የበለጠ ጠያቂና ጠርጣሪ አድርጎናል። ከቅዱስ ቃሉ በቀር እንደወረደ የምንቀበለው፣ ሳናላምጥ የምንውጠው፣ የማንጠረጥረውና የማንጠይቀው ነገር የለንም። "ነገሩ እንደዚሁ ይሆንን?" (ሐዋ 17፥ 11) የሁልጊዜ ጥያቄአችንን ምርመራችን ነው።

ከመቶ አመታት በፊት በእንግሊዝ አገር የባይስወተር ማህበረ ምእመናናዊት ቤተክርስቲያን መጋቢ የነበሩ ዶክተር ጀምስ ስቱዋርት ረስል (1816-1895) The Parousia - A Critical Inquiry Into The NT Doctrine Of Our Lord’s Second Coming በሚል ርእስ መጽሐፍ ጽፈው ነበር። ይህ መጽሐፍ አሁንም እንደገና በብዙ ቅጅ እየታተመ ሲሆን በአሜሪካን አገርና በሌሎችም አገሮች በበርካታ የክርስቲያን መጻህፍት መሸጫ ሱቆች ውስጥ በየሸልፉ ላይ ተሰድሮ ይገኛል። ይህ መጽሐፍ ቆየት ካሉትና የኃላፋውያንን አመለካከት ደግፈው ከተጻፉት መጻህፍት መካከል ዋነኛው ነው። በአውሮፓ የሚኖሩ በርካታ ክርስቲያናዊ የሥነ መለኮት ሰዎችም ተመሳሳይ አቀራርብን ይዘው ተስተውለዋል፤ በመሆኑም ከረስል ጋር በተመሳሳይ ዘመን ይኖሩ የነበሩ ተርጓሚዎች ተመሳሳይ የሆነን ነገር ሲናገሩ ቢደመጡና ስለመጽሐፉም ጥሩ ጥሩ ነገር ቢናገሩ የሚያስገርም አይደለም፤ ለምሳሌ ኤፍ. ደብልዩ. ፌረር "ሙሉ ለሙሉ የሚጠቀስና እንዲጠና የሚጠቆም" ብሎለታል። Biblical Hermeneutics የተሰኘ መጽሐፍ የጻፉትና ከራስል መጽሐፍ ብዛት ያላቸውን ማጣቀሻና ማጣቆሚያ የተጠቀሙት የረስል ዘመን ሰው ሚልተን ቴሪ በስነ መለኮቱ አለም የነገረ ፍጻሜ ስነ ትርጓሜ ጥናት ዘርፍ ሰፊ ተቀባይነትን ባተረፉ ሥራዎቻቸው የረስልን የኃላፋዊ አቀራረብ ተከትለዋል። ስለ ረስል እና ስለ ኃላፋውያን አመለካከት ከተናገሩ እጅግ ታዋቂ ከሆኑ ሊቃውንት መካከል አንዳንዶች የተናገሩትን እዚህ ላይ በጥቂቱ ልጥቀስ፦

"አስቀድሞ አእምሮአችሁን ይዞት ከነበረው የነገረ ፍጻሜ ስርአተ ትምህርት ጋር የሚጣጣሙ ባለመሆናቸው የተነሳ፣ ኢየሱስ ተመልሶ የሚመጣበትን ጊዜ ጠቋሚ የሆኑትንና እንዲህ ያሉ አንዳንድ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት ለመተርጎም ምን ያህል ጊዜ ስትታገሉ ኖራችኋል? The Parousia የተሰኘው የረስል መጽሐፍ የክርስቶስን መመለሻ ጊዜ ቅርበቱን በሚናገርበት ጊዜ መጽሐፍ ቅዱስን በዋዛ የሚመለከተው አይደለም። መጽሐፍ ቅዱስን እንዳለ በቁሙ እንተረጉማለን የሚሉ ሰዎች ሆን ብለው ወይም ሳያስቡት ቅዱሳት መጻህፍት በግልጽ ከሚሉት በተቃራኒው ሌላ ትርጉም እየሰጡ የነዚህን ጊዜ አመልካች የሆኑ ምንባባትን ግልጽ ትርጉም ዘለው ያልፉታል። የራስልን መጽሐፍ ማንበብ ማለት በጭስ በታፈነ ክፍል ውስጥ ንጹህ አየር እንደ መተንፈስና በግልጽ የሥነ ፍታቴ መስታወት አጥርቶ እንደማየት ነው።" (Gary DeMar - Author of Last Days Madness)

"የራስል መጽሐፍ ማለት መጽሐፍ ቅዱሳዊው የነገረ ፍጻሜ ጥናት በአግባቡ የታየበት ለዛሬዋ ቤተክርስቲያን ተዘጋጅቶ ከቀረቡላት እጅግ አስፈላጊ ስራዎች መካከል አንዱ ነው። በአዲስ ኪዳን ውስጥ ስለ ዳግመኛ ምጽአቱ የተገለጸውና የፓሮዥያውን የጊዜ ማእቀፍ አመላካች የሆኑ ጥቅሶችና ምንባባት በዚህ ጥራዝ ውስጥ ተነስቶ በወጉ የተባለው ነገር ሁሉ ጠቀሜታው ለነገረ ፍጻሜአዊ ጥናት ብቻ ሳይሆን፣ ወደ ፊት በተቀደሰው መጽሐፍ ንጽህናና ታማኝነት ላይ በተቃውሞ ለሚነሱ ክርክሮች ሁሉ ፍቱን መድሃኒት ነው።" (Dr. R. C. Sproul - Chairman, Ligonier Ministries)

"ምንም እንኳ የጄ. ስቱዋርት ረስል The Parousia የተሰኘው መጽሐፍ ከደረሰበት ድምዳሜ ጋር ሙሉ በሙሉ እስማማለሁ ባልልም፣ ነገር ግን ይህንን በወጉ የተደራጀና የተሰናሰለ፣ ክርክሩንም በጥንቃቃቄ ያቀረበ፣ ለእውነተኛና በሳል ለሆኑ የመጽሐፍ ቅዱስ ወዳጆችና አጥኝዎች የኃላፍያንን የነገረ ፍጻሜ ምልከታ በመከላከል የተጻፈ ዝርዝርና እምቅ የጽሁፍ ሃብት እንዲነበብና እንዲጠና በአንክሮ አሳስባለሁ። በነገረ ፍጻሜ ርዕሰ ጉዳይ ላይ ካነበብኩአቸው መጻህፍት መካከል በእጅጉ አሳማኝ የሆነና የያዝኩትን አቋም በኃይል የተገዳደረ፣ በገዛ ራሴም የኖረና የቀደመ አስተሳሰቤ ላይ ታላቅ ተጽእኖን ያሳደረ አንዱ መጽሐፍ ነው። ይህ የረስል የአዲስ ኪዳን ነገረ ፍጻሜ መጽሐፍ ቅዱሳዊውን የሥነ መለኮት ጥናት የጥራት ደረጃ ከፍ አድርጎታል።" (Dr. Kenneth L. Gentry, Jr. - Author of Before Jerusalem Fell)

በእርግጥም የራስል መጽሐፍ የመጽሐፍ ቅዱሳዊውን ትንቢት ለመረዳት እጅግ የሚረዳ ሃብት ነው፣ ብዙዎች ግን ይህንንም መጽሐፍ ሳያነቡ በገዛ ራሳቸው መጽሐፍ ቅዱስን ብቻ በግላቸው እያነበቡና እያጠኑ ወደ ኃላፍያን ምልከታ እንደደረሱ እናውቃለን። እነርሱም አሁን የመጽሐፍ ቅዱሳዊው ትንቢት ትርጉምና መልእክት በርቶላቸዋል። መጽሐፍ ቅዱሳዊ ትንቢቶች ፍጻሜአቸው ገና ድሮ ያለፈ መሆኑን እስካሁን ገና ያላወቀና ያልባነነ የቃሉ ወዳጅና ተማሪ ከሆናችሁ፣ የምትነቁበትና የምትባንኑበት ጊዜው አሁን ነው ልላችሁ እወዳለሁ።

  • ያልተጻፈ የሚያነቡ ክርስቲያኖች

ቅዱሳት መጻሕፍት ብዙዎች ከያዙት እምነት በተቃራኒው ይህ ግዑዙ ፍጥረተ አለም መቼም እንደሚጠፋ የሚያስተምሩበት አንድም ሥፍራ የለም። ከኖኅ ዘመን የጥፋት ውኃ በኋላ እግዚአብሔር ምን ብሎ እንደተናገረ ልብ አድርጉ።

ዘፍጥረት 8፥ 21 “እግዚአብሔርም መልካሙን መዓዛ አሸተተ፤ እግዚአብሔርም በልቡ አለ፦ ምድርን ዳግመኛ ስለ ሰው አልረግምም፥ የሰው ልብ አሳብ ከታናሽነቱ ጀምሮ ክፉ ነውና፤ ደግሞም ከዚህ ቀድሞ እንዳደረግሁት ሕያዋንን ሁሉ እንደ ገና አልመታም”

የሚገርመው ሰዎች የተጻፈውን ቸል ብለው ያልተጻፈ እያነበቡ፣ እግዚአብሔር ምድርን አንድ ጊዜ በውሃ አጥፍቷት ነበር በሚቀጥለው ጊዜ ደግሞ በእሳት ያጠፋታል ለማለት ይደፍራሉ። እግዚአብሔር የገባው ቃል ግን “ምድርን ዳግመኛ … አልረግምም፥…ሕያዋንን ሁሉ እንደ ገና አልመታም” የሚል ነው እንጂ ሁሉን የማጥፋት ዘዴውን ከውሃ ሙላት ወደ እሳት ቃጠሎ አልለወጠውም። በውሃስ ፈንታ በእሳት አቃጥሎ ማጥፋት ምቾት ይሰጠዋልን? ወይስ ዳግመኛ ምድርን ላለማጥፋት ነው ቃል የገባው?

መዝሙር 148፥ 4-6 “ሰማየ ሰማያት፥ አመስግኑት፤ የሰማያት በላይም ውኃ። እርሱ ብሎአልና፥ ሆኑም፤ እርሱም አዝዞአልና፥ ተፈጠሩም፤ የእግዚአብሔርን ስም ያመስግኑት። ለዘላለም ዓለም አቆማቸው፤ ትእዛዝን ሰጠ፥ አያልፉምም”

እግዚአብሔር ሰማይና ምድር አያልፉም ብሎ ለዘለአለም እንዲመሰርቱ የሰጠው ትእዛዝ ምን እንደነበር ተመልከቱ። ኦሪት ዘፍጥረት 8፣ 21 ላይ እግዚአብሔር ሕያዋን ፍጥረታትን ዳግመኛ እንደማያጠፋ ተናግሯል። እግዚአብሔር ሊታመን ይችላልን? ቃሉንሥ ይጠብቃልን? በቅርቡ እንደሚመጣሥ ተናግሮ አልነበረምን? ያንንስ አላደረገውምን?

አሁን እንግዲህ እርግጠኛ ነኝ፣ ክርስቶስ ኢየሱስ እንደተናገረው ያኔውኑ በመጀመርያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ ተመልሶ ከሆነ፣ እንግዲያውስ አሁን የምንኖረውና እየኖርን ያለነው በአዲሱ ሰማይ እና ምድር ውስጥ ነው ማለት ነው።

ራእይ : 21፥1-2 “አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት የለም። ቅድስቲቱም ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም፥ ለባልዋ እንደ ተሸለመች ሙሽራ ተዘጋጅታ፥ ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ”

ተዳሳሽ ሰማይና ምድር ለሚጠባበቁ ተላላ ክርስቲያኖች ይህንን መቀበል ከባድ እንደሆነ ይታወቃል። እንዴት ነው በአዲስ ሰማይ እና ምድር ውስጥ ነን ማለት ይምንችለው? ሲሉም ይጠይቃሉ። 

  • አዲሱ ኪዳን፣ አዲሱ ሰማይና ምድር

አዲሱ ሰማይ እና አዲሱ ምድር ግን በክርስቶስ ተመርቆ የተሰጠን አዲሱ ኪዳን መሆኑን ሲረዱ ያኔ ይህን ለመቀበል ቀላል ይሆንላቸዋል።

ገላትያ 4፥ 22-26 “አንዱ ከባሪያይቱ አንዱም ከጨዋይቱ የሆኑ ሁለት ልጆች ለአብርሃም እንደ ነበሩት ተጽፎአልና። ነገር ግን የባሪያይቱ ልጅ እንደ ሥጋ ተወልዶአል፥ የጨዋይቱ ግን በተስፋው ቃል ተወልዶአል። ይህም ነገር ምሳሌ ነው፤ እነዚህ ሴቶች እንደ ሁለቱ ኪዳኖች ናቸውና። ከደብረ ሲና የሆነችው አንዲቱ ለባርነት ልጆችን ትወልዳለች፥ እርስዋም አጋር ናት። ይህችም አጋር በዓረብ ምድር ያለችው ደብረ ሲና ናት፤ አሁንም ያለችውን ኢየሩሳሌምን ትመስላለች፥ ከልጆችዋ ጋር በባርነት ናትና ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም ግን በነጻነት የምትኖር ናት እርስዋም እናታችን ናት”

እናታችን የሆነችው ይህች "ላይኛይቱ ኢየሩሳሌም" በእውነት ማን ናት? እዚህ ላይ ያለው ንጽጽር በሁለቱ ኪዳኖች መካከል ያለ መሆኑን ልብ በሉ። ምድራዊቷ ኢየሩሳሌም ብሉይ ኪዳንን ትወክላለች፣ ስለዚህ ይህቺ ሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም ደግሞ አዲሱን ኪዳንን ትወክላለች ማለት ነው።

ራእይ 21፥ 9 “ሰባቱም ኋለኛዎች መቅሠፍቶች የሞሉባቸውን ሰባቱን ጽዋዎች ከያዙት ከሰባቱ መላእክት አንዱ መጥቶ፦ ወደዚህ ና፥ የበጉንም ሚስት ሙሽራይቱን አሳይሃለሁ ብሎ ተናገረኝ”

“ሙሽራይቱ” የተባለችው “የበጉ ሚስት” ለመሆኑ ማን ናት? ቤተክርስቲያን አይደለችምን! መልአኵ ለዮሐንስ “የበጉን ሚስት” እያሳየው ነው። ይህን እያሰባችሁ የሚቀጥለውን ጥቅስ አስተውሉ።

ራእይ 21፥ 10 “በመንፈስም ወደ ታላቅና ወደ ረጅም ተራራ ወሰደኝ፥ የእግዚአብሔርም ክብር ያለባትን ቅድስቲቱን ከተማ ኢየሩሳሌምን ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አሳየኝ፤

“ወደዚህ ና፥ የበጉንም ሚስት ሙሽራይቱን አሳይሃለሁ ብሎ ተናገረኝ” ይልና “ቅድስቲቱን ከተማ ኢየሩሳሌምን አሳየኝ” ይላል የበጉ ሚስት አዲሲቷ ኢየሩሳሌም፣ እርስዋም ቤተ ክርስቲያን ናት። አሮጌዋ ኢየሩሳሌም ሥጋዊቷ እስራኤል ነበረች አዲሲቷ ኢየሩሳሌም ደግሞ የክርስቶስ ሙሽራ ናት። ላይኛይቱ እየሩሳሌም "የበጉ ሚስት" ነች፣ እርስዋም ቤተክርስቲያን ነች፣ እርስዋም አዲሱ ኪዳን ናት፣ የግዚአብሔር ከተማም ናት። የዕብራውያን መልዕክት የጽዮንን ተራራና ሰማያዊቷን ኢየሩሳሌምን በንጽጽር ባቀረበ ጊዜ ይህንን ይጠቁሟል።

ዕብራውያን 12፥ 22-24 “ነገር ግን ወደ ጽዮን ተራራና ወደ ሕያው እግዚአብሔር ከተማ ደርሳችኋል፥ ወደ ሰማያዊቱም ኢየሩሳሌም፥ በደስታም ወደ ተሰበሰቡት ወደ አእላፋት መላእክት፥ በሰማያትም ወደ ተጻፉ ወደ በኵራት ማኅበር፥ የሁሉም ዳኛ ወደሚሆን ወደ እግዚአብሔር፥ ፍጹማንም ወደ ሆኑት ወደ ጻድቃን መንፈሶች፥ የአዲስም ኪዳን መካከለኛ ወደሚሆን ወደ ኢየሱስ፥ ከአቤልም ደም ይልቅ የሚሻለውን ወደሚናገር ወደ መርጨት ደም ደርሳችኋል።”

የጽዮን ተራራ ካለ በኋላ “እና” በሚለው ቃል ምትክ “ይኸውም” ወይም “ይህችም” የሕያው እግዚአብሔር ከተማ መባል ነበረበት። ደብረ ጽዮን ወይም የጽዮን ተራራ የእግዚአብሔር ከተማ እርስዋም ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ናት። ስለዚህ፣ የጽዮን ተራራ፣ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም፣ የሕያው እግዚአብሔር ከተማ፣ የሚያመለክተው ቤተ ክርስቲያንን ነው። እነርሱም ኋላ ላይ በቁጥር 28 ላይ እንቀበለዋለን የተባለው የማይናወጥ መንግሥት የሚያመለክተው በክርስቶስ አካል የተዋጁትን ሁሉ ነው። በሌላ አነጋገር እነዚህ የአዲስ ኪዳን አማኞች በሰማያትም የተጻፉ የበኵራት ማኅበር ማለት ናቸው።

  • ቃሉን በወጋችን ላይ እናንግስ

በወጋችንና በቅዱሳት መካከል ምርጫ እንድናደርግ የቀረበልንን ጥሪ ቸል አንበል። ሰዎች ተጣብቋቸው ባለው ወግ እና በቅዱሳት መጻሕፍት መካከል አንዱን መምረጥ አለባቸው - ምርጫውም ቀላል እና ግልጽ መሆን አለበት። የዳግመኛ ምጽአቱ እውነትን አይቀሬነት የቅዱሳት መጻህፍት ትምህርት ነው፤ ይህንን የዳግመኛ ምጽአቱን እውነታ መካድ ማለት ደግሞ ቅዱሳት መጻሕፍት በመንፈስ ቅዱስ በመነዳት የተሰጡ መሆናቸውን መካድ ነው። በዚህ ትስማማላችሁን? እንግዲህ፣ ዳግም ምጽአቱ ፍጻሜ እንዲያገኝ በመለኮት የተቀጠረለት ጊዜ ልክ እንደ ዳግም ምጽአቱ የቅዱሳት መጻህፍት እውነታ የማያሻማ እና ግልጽ ነው ብዬ አምናለሁ። ልክ እንደዚሁ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ዳግም ምጽአት ፍጻሜ የሚሰጠውን የጊዜ መግለጫ መካድ ደግሞ በመንፈስ ቅዱስ በመነዳት የተሰጠውን ቃል መካድ ነው ብዬ አምናለሁ። ይህስ ያስማማናልን? ይፈጸማል የተባለው ዳግም ምጽአትና ለፍጻሜው የተመደበለት የጊዜ ወሰን ሁሉቱም በመንፈስ ቅዱስ በመነዳት የተሰጡ፣ ሊካዱም የማይችሉ ናቸው።

ምናልባት ይህንን የምታነቡ ወገኖች ይህ አመለካከት ሰምታችሁትም አስባችሁትም የምታውቁት አዲስና እንግዳ ከሆነባችሁ፣ በጌታ ፍቅርና በትህትና የምለምናችሁ እንዳትደነብሩ ነው፤ ይልቁንም እያልኩ ያለሁት ምን ያህል የቃሉ ድጋፍ እንዳለው በግልፅ እና በታማኝነት እንድትመለከቱት እጠይቃለሁ። አንድ ነገር እውነት ነው፣ እርሱም በአዲስ ኪዳን ውስጥ ባለው በእያንዳንዱ መጽሐፍ ማለት በሚቻልበት ደረጃ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ የተነገረው እርሱ “በቅርቡ” እና “ቶሎ” ተመልሶ እንደሚመጣ ያሉው ትምህርት ነው። ይህንንም በየትኛውም ሥነ መለኮት ማስተባበል አይቻልም። በማንኛውም የሥነ ትርጓሜ እና የሥነ ፍታቴ መርህ ይህንን “በቅርቡ” እና “ቶሎ” የተሰኘ ጊዜ አመልካች መግለጫ ወደ 2,000 ዓመታት ለሚጠጋ እና ከዚያ ለሚያልፍ ዘመን ማራዘም በጣም ከባድ ነው። የየትኛውም ቋንቋ መዝገበ ቃላትም እነዚህን “በቅርቡ” እና “ቶሎ” የተሰኙ ጊዜ አመልካች ቃላት ሲተረጉሙ እንዲህ ያለውን የተራዘሙና የተለጠጠ የጊዜ ወሰን አያደርጉለትም። ከመጀመሪያው መቶ ክፍለዘመን ጀምሮ እስከዚህ እኛ እስካለንበት ሃያ አንደኛው መቶ ክፍለ ዘመን ድረስ “በቅርቡ” እና “ቶሎ” የተሰኙት ቃላት ትርጉማቸውንም ሆነ የዜ ወሰናቸውን አልለወጡም። ከዚህ ሁሉ በላይ ግን ለእኔ ዋጋ ያለውና ዋናው ጉዳይ ቅዱሳት መጻሕፍት በመንፈስ ቅዱስ በመነዳት የተሰጡ መሆናቸው ነው። ቅዱሳት መጻህፍት አይዋሹም። ጌታችን በቅዱሳት መጻህፍት ያስተማረውን ውድ እውነት እድሜ ጠገብ የሆነው የሰዎች ትውፊት እና የኖረ ልማድ እንዲነጥቃችሁ አትፍቀዱ። እነዚህ የተባሉ ነገሮች በእርግጥም እንደዛ እንደተባሉት መሆናቸውን ለማየት ቅዱሳት መጻህፍትን በየቀኑ እየመረመራችሁ በልብ ስፋት የቤርያ ሰዎችን ሁኑ።

በዚህ ጽሁፍም ሆነ በሌሎቹ ትምህርቶቼ ላይ ጥያቄዎች ቢኖሯችሁ ጻፉልኝ፤ ጸጋው ባገዘኝ ልክ መልሼ እጽፍላችኋለሁ። ብሎገሬን መጎብኘትም አትርሱ። ይጠቅመናል የምትሉትን ማናቸውንም ጽሁፍ በማናቸውም መንገድ ያለገደብ መጋራትና ማጋራት እንድትችሉም ፈቃዴ ነው።

ሰላምና ጸጋ ይብዛላችሁ!!

(ግዛቸው ከበደ)

gizachewkr@gmail.com
















From Blogger iPhone client

Friday, January 3, 2025

ቅድስት ሥላሴ

ቅድስት ሥላሴ


 


እንደ መነሻ በተወሰኑ ምንባባት ርዕሰ ጉዳያችንን መመልከት እንጀምር። 


ማርቆስ 1፥ 9-11 ”በዚያ ወራትም ኢየሱስ ከገሊላ ናዝሬት መጥቶ ከዮሐንስ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ። ወዲያውም ከውኃው በወጣ ጊዜ ሰማያት ሲቀደዱ መንፈስም እንደ ርግብ ሲወርድበት አየና፦ የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል የሚል ድምፅ ከሰማያት መጣ።“


በዚህ የአዲስ ኪዳን ጥቅስ ውስጥ ሥላሴን በሙላት በተግባራቸው ላይ የሚያሳየንን አንቀጽ እናገኛለን። ተመልከቱ እግዚአብሔር ወልድ ሲጠመቅ፣ እግዚአብሔር አብ ከሰማይ ይናገር ነበር፣ መንፈስ ቅዱስም በዕርግብ አምሳል ይወርድ ነበር። ሦስቱንም የሥላሴ አካላት በሌሎች ጽሑፎች ውስጥም በአንድነት እናያቸዋለን፡-


ማቴ 28፥ 19 “እንግዲህ ሂዱና አሕዛብን ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው፥ ያዘዝኋችሁንም ሁሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው፤”


2 ቆሮንቶስ 13፥ 4 “በድካም ተሰቅሎአልና፥ ነገር ግን በእግዚአብሔር ኃይል በሕይወት ይኖራል። እኛ ደግሞ ከእርሱ ጋር እንደክማለንና፥ ነገር ግን ስለ እናንተ በሆነ በእግዚአብሔር ኃይል ከእርሱ ጋር በሕይወት እንኖራለን።”


መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆነው ክርስቲያናዊ ግንዛቤ ከመሠረቱ ሥላሴአዊ ግንዛቤ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ ከእግዚአብሔር የተገኘ፣ ክርስቶስን ማእከል ያደረገ እና በመንፈስ ቅዱስ መሪነት የተጻፈ መጽሓፍ ነው። ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን በተመለከተ ከሁሉ የተሻለው ፍቺም ‘መጽሐፍ ቅዱስ አብ ስለ ልጁ በመንፈስ ቅዱስ አማካይነት የሰጠው ምስክርነት ነው’ የሚል ሲሆን፣ ይህም ሥላሴአዊ ያደርገዋል።


ሥላሴ፣ የጥንት ቤተክርስቲያን ከነበረችባቸው ከመጀመሪያዎቹ ምዕተ-አመታት ጀምሮ እግዚአብሔርን በተመለከተ እንደ ክርስቲያናዊ ፅንሰ-ሀሳብ ዋና እና ልዩ ገጽታ፣ የክርስትና እምነትም ማዕከላዊ ምስጢር እንደሆነ ተደርጎ የሚወሰድ እጅግ ወሳኝ የሆነ ርዕሰ ጉዳይ ነው። ይህም ጥልቅ የሆነውን የክርስትናን እውነት በወጉ ለማስቀመጥ እና ለማደራጀት የሌሎቹም ሁሉ የክርስትና አስተምህሮ ዘርፎች ሥርና መሰረት ሆኖ የሚያገለግል፣ ነገር ግን ርዕሰ ጉዳዩን በበቂ ሁኔታ ለመግለጽና ለማስረዳት በእጅጉ አስቸጋሪ የሆነ መሆኑ እናገኛለን።


እንደ ማቴዎስ 28፥ 19 እና 2ኛ ቆሮንቶስ 13፥ 14 ባሉት ምንባባት ርዕሰ ጉዳዩን በጉልህ የሚጠቁሙ ንግግሮች ያሉ ቢሆንም፣ ነገር ግን በቅዱሳት መጻህፍት ውስጥ ፅንሰ አሳቡን እናገኛለን እንጂ፣ ስላሴ የተሰኘ እንዲህ ያለ ቃል የትም ቦታ በግልፅ አልተቀመጠም። በቤተክርስቲያን ውስጥ በኢየሱስ ክርስቶስ ያለውን መገለጥ የክርስቶስ ማህበር የሆነች ቤተክርስቲያን በእግዚአብሔር ላይ ያላትን እምነትዋን በተገቢው መንገድ ለማብራራትና ለመተርጎም ሲያስፈልጋት ያኔ ትምህርቱ በአባቶች ተቀርጿል። ቅድስት ስላሴ አንድ አምላክ ነው። አንዱም አምላክ በአብ፣ በወልድ እና በመንፈስ ቅዱስ በሶስት አካል ተገልጦ ለዘላለም ይኖራል። በምዕራቡ ዓለምም ትምህርቱን ለማብራራት ደረጃውን የጠበቀ የቃላት አገባብ ሲያስፈልግ በሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ ጽንሰ አሳቡን እና ስያሜውን እቆራኝቶ (“God is una substantia, [one being or nature], et tres personae, [three "personae]") በማለት ለመጀመሪያ ጊዜ የተናገረውን ተርቱሊያንን በቀዳሚነት እናገኛለን።


ትምህርቱን እንደ ቤተክርስቲያን ይፋዊ አስተምህሮ ለማቋቋምና ለማጽናት ወሳኝ የሆኑ እርምጃዎች የተወሰዱት ግን ከአሪያኒዝም ጋር በነበረው የአስተምህሮና የእምነት ተፋልሶ ግጭት ምክንያት በመጀመሪያዎቹ ሁለት ጠቅላላ የቤተክርስቲያን ጉባኤዎች ወቅት ነው (እነርሱም በ325 ዓ.ም በተካሄደው የኒቂያ ጉባኤና ኋላም በ381 ዓ.ም በተካሄደው የቁስጥንጥንያ ጉባኤ ናቸው)። እነዚህ ሁለቱም ጉባኤዎች ኢየሱስ ክርስቶስ ፍጡር ሳይሆን እውነተኛ አምላክ፣ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን፣ መንፈስ ቅዱስም ከእግዚአብሔር አብ እና ከእግዚአብሔር ወልድ ጋር አምልኮን የሚቀበል ፍፁም አምላክ መሆኑን፣ ይህም የሚታመነውና የሚመሰከረው አንዱን አምላክ ሳይከፋፍሉ እንደሆነ አረጋግጠዋል። በዚህም የእምነትና የአስተምህሮ መሠረት ላይ የተገነቡት በምስራቅ እና በምዕራብ ያሉ አብያተ ክርስቲያናት ተጨማሪ ማብራሪያዎችን አደራጅተዋል። ምናልባት በርዕሰ ጉዳዩ ላይ የጥንት ቤተክርስቲያን ምን ያህል እንደተጋችና አስተምህሮታዊ ድንበሯን ለማስከበር እንዴት እንደተጋደለች በሰፊው ማንበብ ለሚወዱ ዊልያም ጂ ሩስች ያዘጋጁትን The Trinitarian Controversy የተሰኘውን ግሩም መጽሃፍ እንዲያነቡ እመክራለሁ። በዚህች አጭር ዝግጅት ግን ስላሴን በተመለከተ ቤተክርስቲያን በታሪኳ ያስተናገደቻቸውን ልዩ ልዩ ክርክሮች መዳሰስ ዋና አላሜዬ አይደለም። ይሁንና ግን በዋናነት የትምህርቱን መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሰረት በማሳየት ከታሪካዊው የቤተክርስትያን ጉባኤዎችና ከውሳኔዎቻቸው ትሩፋት በመጠኑ እየጨለፍሁ ለእምነት ቤተሰብ የሚመጥነውን ብቻ በገባኝ ልክ ለማመልከት እወዳለሁ።


በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ስለ እግዚአብሔር ለመጀመሪያ ጊዜ የተጠቀሰው በብዝሃ ቁጥር እንደሆነ አስተውላችኋልን? ተመልከቱ፡-


ዘፍጥረት 1፥ 1 “በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ።”


እዚህ ላይ እግዚአብሔር ተብሎ የተተረጎመው ቃል በእብራይስጡ “ኤሎሂም” ነው። ይህ የዕብራይስጥ ቃል በዘፍጥረት 1፥ 1 ላይ የተጠቀሰ የእግዚአብሔር መጠሪያ ሲሆን፣ ቃሉ በተለምዶ “አምላክ” ተብሎ ይተረጎማል። የቃሉ ተራ ስሜት ግን በብዝሃ አገባብ "አማልክት" እንደማለት ነው። ከአመታት በፊት በትምህርተ ክርስቶስ ላይ ያነበብኩትና ጸሓፊውን በስም የማላስታውሰው ጽሁፍ አይሁድ በሃይማኖታቸው አንድ አምላክን የሚያመልኩ (Monotheistic) ቢሆኑም፣ ነገር ግን ከአህዛባዊ የብዝሃ አማልክት (Polytheistic) ጽንሰ አሳብ ርቀው ለዘመናት ለራሳቸው ብቻ ሸሽገው የያዙትን የአንዱን አምላክ የብዝሃነት መገለጥ በተወሰነ ብርሃን ያውቁ እንደነበር ያትታል። እንግዲህ ብሉይ ኪዳን በዚህ ላይ “ኤሎሂም” ከሚለው የአምላክ ስም ጀምሮ አልፎ አልፎ እግዚአብሔር ስለራሱ “እኛ” እያለ መናገሩንና እንደ አብርሃም ካሉ ቅዱሳኑ ጋር በብዝሃነቱ ያደረጋቸውን መስተጋብሮች ስንመለከት ይህ ስለ አይሁድ የተነገረውን ጉዳይ በቀላሉ የምናየው አይሆንም። 


ይህ “እግዚአብሔር” የሚለው መጠሪያ በዕብራይስጡ “ኤሎሂም” ግሱ የ”ኤል” ብዙ ቁጥር ነው፤ ቃሉም "ሀይል፣ ብርታት፣ ስልጣን" የሚል ትርጉምን ይይዛል። “ኤሎሂም” ብዝሃ ነው፣ ግን የቋንቋ ሰዋሰዋዊ ሊቃውንት ቃሉን ሞርፎሎጂያዊ ብዝሃ ብለው ይጠሩታል። [ሞርፎሎጂካል ብዝሃነት በቋንቋ ዘይቤዎች ውስጥ የቃላትን መልክ በመቀየር፣ በተለይም በሥርዓተ-ሞርፎሎጂ ሂደት ውስጥ የ"ከአንድ በላይ" ጽንሰ-ሐሳብን የሚገለጹበትን መንገድ ያመለክታል።] በ"im" የሚጨርሱ የዕብራይስጥ ስያሜዎች ብዝሃ ናቸው። በአብዛኛዎቹ ጉዳዮች ግን በታናካህ ውስጥ ትርጉማቸው ነጠላ ይሆናል። ጉዳዩ ግን በብሉይ ኪዳንና በአይሁድ እምነት ላይ ኮምጨጭ ያለ ጥናትና ምርምር የሚጠይቅ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። በእኔ እምነት የኢየሱስን ወይም የሥላሴን አምላክነት የሚክድ ሰው ግን ክህደቱ የዕብራይስጥ ቅዱሳት መጻህፍትን ካለመረዳት የሚመጣ ነው ብዬ እወስደዋለሁ።


ምንም እንኳን ይህ “ሥላሴ” የተሰኘው ቃል በብሉይም ሆነ በአዲስ ኪዳን የቅዱሳት መጻሕፍት ገጾች በአንዳቸውም ውስጥ ፈጽሞ ባይገኝም፣ ትምህርቱ ግን በቅዱሳት መጻሕፍት ሁሉ፥ በታናክም ሆነ በአዲስ ኪዳን ውስጥ የሚሰጥ ግልጽ ትምህርት ነው። "ሥላሴ" በሦስት የተለያዩ አካላት በህላዌነት የሚኖረውን የእግዚአብሔርን አንድነት ለመግለጽ የሚያገለግል አይነተኛ ቃል ነው፤ ይኸውም የመለኮትን አንድነት የሚገልጽ ቃል ነው። ሥሉስ ብዝሃ የሆኑ፣ በዘላለማዊ አንድነት አብረው ያሉ፣ አብረው ዘላለማዊ የሆኑ፣ አንድ አይነት እኩል ማንነት ያላቸው፣ እያንዳንዳቸውም በየራሳቸው “እኔ” ማለት የሚችሉ፣ የየራሳቸው አካላዊ ማንነት ያላቸው ሆነው በአካል የተለያዩ፣ በመለኮታዊ ማንነታቸው ግን አንድ የሆኑ ናቸው። ይህንን ማንነት አመክንዮ በሚተነትነው መረዳት አውቆ መጨረስ አይቻልም። ሆኖም ግን ሥላሴ በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ራሱን የገለጠውን የአንዱን እውነተኛ አምላክ ማንነት ሙሉ በሙሉ በግልፅ ለመተረክ ይመቻት ዘንድ ትምህርቷን ስትቀርጽ ቤተክርስቲያን የፈጠረችው አይነተኛ ቃል ነው። የቃሉም ትርጉም ሦስትነት እንደማለት ሲሆን ሦስትነትም አንድነት ነው።


እንደ ክርስቲያን፣ እግዚአብሔር ተብሎ የሚታወቅ አንድ ዘላለማዊ ማንነት ያለና የሚኖር እንደሆነ ከእግዚአብሔር ቃል እናረጋግጣለን። በእግዚአብሔርም ቃል መሰረት ይህ አንድ ዘላለማዊ ማንነት ቅዱስ ስሉስ በሆኑ ዘላለማዊ አካላት ማለትም በአብ፣ በወልድ እና በመንፈስ ቅዱስ ተገልጦ ይኖራል፣ ይሰራልም (ማቴዎስ 28፥ 19 እና 2ቆሮንቶስ 13፣ 14)። በአመክንዮ፣ የሰው አእምሮ ሊያስብ በሚችልበት አቅምም ይህ አንድ ማንነት በሶስት አካላት እንዴት ሊኖር እንደሚችል ሙሉ በሙሉ መረዳት ከቶ አይቻለንም። ሆኖም፣ እንደ ክርስቲያን፣ ይህ እውነት የማይለወጥ ዘላለማዊ የእግዚአብሔር ቃል እውነት መሆኑን በእምነት አረጋግጠናል፤ ጠንቅቀን አውቀነዋል ለማለት ባንደፍርም እንኳን ከዘላለም ሥሉስ ሆኖ ያለና የሚኖረውን አንዱን እውነተኛ አምላክ እናመልካለን!


በዚህ መለኮታዊ፣ ወሰንና ዳርቻ በማይገኝለት ህላዌ ውስጥ፣ አብ፣ ቃል ወይም ወልድ፣ እና መንፈስ ቅዱስ የተባሉ ሦስት አካላት በአንድ መለኮታዊ ማንነት፣ በአንድ ኃይል እና በዘላለማዊነት አብረው አሉ ይኖራሉም። እያንዳንዳቸውም ያልተከፋፈለ ሙሉ መለኮታዊ ይዘት ያላቸው ናቸው፤ አብ በማንም አልተሰራም፥ አልተወለደም ወይም ከማንም አልተገኘም፤ ወልድ ከዘላለም ከአብ የተወለደ ነው፤ መንፈስ ቅዱስም ከዘላለም ከአብና ከወልድ የሚሰርጽ ነው። ቅድስት ስላሴ የማይወሰኑ ናቸው፣ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፣ ደግሞም አንድ አምላክ፣ በባህርይና በማንነት ፈጸሞ የማይከፋፈል፣ ነገር ግን በበርካታ ልዩ አንጻራዊ ተግባራት እና ግላዊ ግንኙነቶች ተለይተው፣ አብ የራሱ አካል ኖሮት፣ ወልድም የራሱ አካል ኖሮት፣ መንፈስ ቅዱስም የራሱ አካል ኖሮት በመለኮታዊ አንድነት የሚታወቁ ናቸው። ይህ ስለ ሥላሴ ያለን መጽሃፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ ከእግዚአብሔር ጋር ላለን ኅብረት ቋሚ መሠረት እና በእርሱ ላይ ለሚያርፈው እምነታችን ጽኑ መታመን ነው። (1 ዮሐንስ 5፥ 7፤ ማቴዎስ 28፥ 19፤ 2 ቆሮንቶስ 13፥ 14፤ ዘጸአት 3፥ 14፤ ዮሐንስ 14፥ 11፤ 1 ቆሮንቶስ 8፥ 6፤ ዮሐንስ 1፥ 14፣ 18፤ ዮሐንስ 15፥ 26፤ ገላትያ 4፥6 ይመለከቷል)።  


በመጽሓፈ ስምምነት የሉተራውያን የእምነት መግለጫ ገጽ 417 እንደተብራራው፣ ይህ የቅድስት ሥላሴ ምሥጢር እጅግ የላቀው ምስጢር ሲሆን (1ጢሞቴዎስ 3፥ 16)፣ እርሱም ብቸኛ መጽናናታችን፣ ሕይወትና ድነታችን ያረፈበት ምስጢር ነው፣ ይለዋል። እንደሚታወቀው ሥላሴ በክርስትና ውስጥ በዋናነት ከተያዙ ትምህርቶች መካከል አንዱ እና ልዩ አስተምህሮ ነው። ይህ የከርስትና ትምህርት ግን ገና ከሦስተኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ መምህራን ነን በሚሉ በተለያዩ ግለሰቦችና ቡድኖች ጥቃት ሲደርስበት የቆየ ትምህርት ነው። በሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የመጀመሪያዎቹ አስርት ዓመታት ውስጥ የእስክንድርያው ካህን የነበረው አርዮስ ኑፋቄውን ማስተማር ጀመረ፤ እንዲህ ሲል፦ “ወልድ እውነተኛ የእግዚአብሄር ልጅ ከሆነ፣ እንግዲያውስ አባቱ ከእርሱ በፊት ነበረ ማለት ነው፤ ስለዚህ መለኮት የሆነው አብ መለኮት ከሆነው ወልድ በፊት አስቀድሞ የነበረ ሲሆን፤ ወልድ ደግሞ ከእርሱ አስቀውድሞ በነበረው በግዚአብሔር አብ የተፈጠረ ፍጡር ነው፤ ወልድ ከእግዚአብሔር ፍጥረታት ሁሉ ታላቍ እና የመጀመሪያው እንደሆነ እርሱም አምላክ እንደሆነና ነገር ግን አሁንም የተፈጠረ መሆኑን በድፍረትና በግልጽ ተናገረ። ስለዚህ፣ ቀደም ሲል እንዳልነበሩ እንደ ፍጥረታት ሁሉ ወልድም ከዘላለም ያልነበረበት ጊዜ ነበር” ሲል አስተማረ።


አርዮስም፣ የእግዚአብሔር ቃል ከእግዚአብሔር ጋር አብሮ ዘላለማዊ ነው ብሎ ከሚያምነውና ቃሉ በእግዚአብሔር የተፈጠረ ነው የሚለውን የአርዮስን ትምህርት ውድቅ ካደረገው የእስክንድርያው ጳጳስ እስክንድር ጋር ተጋጨ። በአርዮስ አነጋገር “እርሱ (ወልድ) በዘላለም ውስጥ ያልነበረበት ጊዜ ነበረ” ማለት ነው። አርዮሳውያን ከዚህ በመነሳት ክርስቶስ ከዓለም ፍጥረት በፊት የነበረ ቢሆንም ዳሩ ግን እርሱ ራሱ የአብ ፍጥረት ነው ሲሉ ሸምጥጠዋል።


እስክንድሮስም ይህ አስተምሀሮ ለቤተ ክርስቲያን አደገኛ መሆኑን ስለተረዳ የአርዮስን ትምህርት በአደባባይ አውግዞ ከቤተ ክርስቲያን አገልግሎትና ጥሪ እንዲወገድ አደረገ። ይህም ሂደት በታሪክ የመጀመርያው የሆነውን የቤተክርስቲያን ጉባኤ፣ እርሱም የኒቂያ ጉባኤ እንዲጠራ ምክንያት ሆነ። በጉባኤውም ከተመከረ በኋላ የአርዮስ ትምህርት በይፋ ተወግዟል። ክርክሩ ግን በጉባኤው ከግንቦት 20፣ 325 ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሰኔ 19፣ 325 ድረስ ለአንድ ወር የዘለቀ ነበር፤ የኒቂያ የሃይማኖት መግለጫ የመነሻ አሳብም ያኔ ተዘጋጀ፣ እርሱም የአርዮሳዊነትን አስተምህሮ ያወገዘ እና የሥላሴን ትምህርት ያቋቋመ መግለጫ ነበር። በመግለጫው ስላሴ ተኮር የሆነውን አንቀጽ ተመልከቱ፦


ሁሉን በሚችል ሰማይንና ምድርን፣ የሚታየውንና የማይታየውን በፈጠረ አንድ አምላክ በሚሆን በእግዚአብሔር አብ አምናለሁ። እርሱ ብቻ የአብ ልጅ በሚሆን፣ ዓለም ሳይፈጠር ከአብ በተወለደ፣ ከአምላክ በተገኘ አምላክ፣ ከብርሃን በተገኘ ብርሃን፣ ከእውነተኛ አምላክ በተገኘ እውነተኛ አምላክ፣ በህልውናው ከአብ ጋር አንድ የሆነ፣ በተፈጠረ ሳይሆን በተወለደ፣ ሁሉ በእርሱ በሆነ፣ ስለ እኛ ስለ ሰዎች ስለ ደህንነታችንም ከሰማይ በወረደ፣ በመንፈስ ቅዱስ ከድንግል ማርያም ሥጋ ነስቶ ሰው በሆነ፣ …. ለመንግሥቱም ፍጻሜ በሌለው በአንድ ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ አምናለሁ። ከአብና ከወልድ ጋር በሚሰገድለትና በሚከበር፣ ከአብ በሚሠርጽ፣ በነቢያት በተናገረ፣ የሕይወት ጌታና ሰጪ በሆነ፣ በመንፈስ ቅዱስም አምናለሁ። …።


ምንም እንኳ ቤተክርስቲያን በዚህ የእምነት መግለጫ ቆማ የመጣባትን የኑፋቄ ተግዳሮት መመከት ቢቻላትም የአርዮስ ትምህርት ግን ወዲያውኑ ፍጻሜና ማብቂያ አላገኘም ነበር፤ እንዲያውም በአብያተ ክርስቲያናቱና በየገዳማቱ ትልቅ ተጽዕኖ ማሳደሩን ቀጥሎ ነበር። በእርግጥም በቤተክርስቲያን ጉባኤ የተወገዘው የአሪዮስ ትምህርተ ክርስቶስ እየገነነ በሁሉ ዘንድ ይደመጥ ነበር። ከኒቂያ ጉባኤ በኋላ ብዙም ሳይቆይ እስክንድር ሲሞት በእርሱ አገልግሎት አትናቴዎስ በፈንታው ተተካ። ቅዱስ አትናቴዎስም ቤተክርስቲያን ካፈራቻቸው ታላላቅ የወንጌል ተጋዳዮች አንዱ እንደነበር ይታወሳል።


አስቀድሞ የተዘጋጀው የኒቂያ ጉባኤ አስተምህሮ በአትናቴዎስ እና በሌሎች አባቶች የቃላት ጥበብ እና አገላለጽ ተከሽኖ በድጋሚ በቁስጥንጥንያው ጉባኤም አጽንዖት ተሰጥቶታል። ስለዚህ “ክርስቶስ ያልነበረበት ጊዜ ነበረ” የሚለው የአርዮስ አስተምህሮ እንደገና ውድቅ ሆነ፣ የክርስቲያን ቤተክርስቲያንም ክርስቶስ ያልነበረበት ጊዜ እንደሌለ በጽኑ በመግለጽ፤ እርሱ ከመጀመሪያው ነበር፣ አብ ያለውን (‘ለ’ ሲጠብቅ) እና የሆነውን አይነት መሰረታዊ የመለኮት ባህርይ ነበረው፣ ከዘላለምም ከአብ ተወለደ እንጂ እርሱ የሆነውን በማንም አልሆነም፣ በማንምም አልተፈጠረም ስትል የጉባኤውን ውሳኔ ደግፋ ለመቆም በቅታለች። እነዚያ ሁለቱም ታሪካዊ ጉባኤዎች ሆሞኡስየስ [homoousia] (መሰረታዊ ማንነቱ ወይም መሰረታዊ ይዘቱ") የተሰኘውን እውነታ መስርተው አቁመውታል። በሌላ አነጋገር፣ ኢየሱስ በመሰረታዊ ማንነቱ፣ በባህርዩ እና “በተፈጥሮው” ይዘቱ ከአብ ጋር አንድ ነው፣ ከአብ ጋር “ተመሳሳይ መሰረታዊ ማንነት” አለው። እርሱ አብን አይደለም፣ ነገር ግን ከአብ ጋር አንድ ነው፤ አብም በማንነቱ የሆነውና ያለው ሆኖ ወልድ በማንነቱ የሌለውና ያልሆነው ነገር የለም ሲሉ የኢየሱስ ክርስቶስን ፍጹም አምላክነት አውጀዋል።


ከላይ ለማለት እንደሞከርኩት በዚህ ጽሁፍ ታሪካዊውን አስተምህሮታዊ ክርክር መዳሰስ አላማዬ ባይሆንም፣ በቅዱስ አትናቴዎስ የኃይማኖት መግለጫ አንቀጽ 3-26 ስለ ቅድስት ስላሴ የሰፈረውን ግልጽና ግሩም ማብራሪያ እዚህ ላይ መጥቀስ ግን ተገቢ ነው፣ አንባቢዎችም በእያንዳንዱ አንቀጽ ስለ ስላሴ የተቀመጠውን በስነ መለኮት ንጽህና የዳበረውንና አስደናቂ በሆነ የቋንቋ ውበት የሰፈረውን መግለጫ በአንክሮ ሊመለከቱት ይገባቸዋል፦ 


በሦስትነቱ አንድነቱን፥ በአንድነቱም ሦስትነቱን አምነን አንድ አምላክን እናመልካለን። ይህም እውነተኛ የክርስትና ሃይማኖት ነው።

ይህንንም የምናደርገው አካላቱን ሳንደባልቅ መለኮታዊ ህልውናውንም ሳንከፍል ነው።

ምክንያቱም የአብ አካል ለብቻው የወልድ ለብቻው፥ የመንፈስ ቅዱስም ለብቻው ስለሆነ ነው።

ሆኖም የአብ፥ የወልድና የመንፈስ ቅዱስ መለኮት አንድ ነው፥ ክብሩ ሥልጣኑም እኩል ሆኖ ይኖራል።

ወልድ በህልውናው እንደ አብ ነው፥ መንፈስ ቅዱስም እንደዚሁ ነው።

አብ አልተፈጠረም፥ ወልድ አልተፈጠረም፥ መንፈስ ቅዱስም አልተፈጠረም።

አብ ወሰን የለውም፥ ወልድ ወሰን የለውም፥ መንፈስ ቅዱም ወሰን የለውም።

አብ ዘላለማዊ ነው፥ ወልድ ዘላለማዊ ነው፥ መንፈስ ቅዱስም ዘላለማዊ ነው።

ቢሆነም ዘላለማዊ የሚሆን አንድ እንጂ ሦስት አይደሉም።

ያልተፈጠረና ወሰን የሌለው ሦስት እንዳልሆነ እንደዚሁም ያልተፈጠረና ወሰን የሌለው አንድ ነው።

እንዲሁም አብ ሁሉን የሚችል ነው፥ ወልድ ሁሉን የሚችል ነው፥ መንፈስ ቅዱስም ሁሉን የሚችል ነው።

ቢሆንም፥ ሁሉን የሚችል አንድ አንጂ ሦስት አይደሉም።

ስለዚህ አብ አምላክ ነው፥ ወልድ አምላክ ነው፥ መንፈስ ቅዱስም አምላክ ነው።

ሆኖም አንድ አምላክ እንጂ ሦስት አማልክት አይደሉም።

ስለዚህ አብ ጌታ ነው፥ ወልድ ጌታ ነው፥ መንፈስ ቅዱስም ጌታ ነው።

ሆኖም አንድ ጌታ እንጂ ሦስት ጌቶች አይደሉም።

ምክንያቱም የክርስትና እምነት እውነተኛነት እያንዳንዱ አካል አምላክና ጌታ መሆኑን እንድናምን እንደሚያስገድደን ሁሉ የክርስትና ሃይማኖት ሦስት አማልክት ወይም ሦስት ጌቶች እንዳንል ይከለክለናል።

አብ በማንም አልተሠራም፥ አልተፈጠረም፥ አልተወለደምም።

ወልድ ከአብ ተወለደ እንጂ አልተሠራም አልተፈጠረምም።

መንፈስ ቅዱስ አልተሠራም፥ አልተፈጠረም፥ አልተወለደምም፥ ነገር ግን ከአብ የሚሠርጽ ነው።

ስለዚህ አብ አንድ ስለሆነ ሦስት አብ አይደለም፥ ወልድም አንድ አንጂ ሦስት ወልድ አይደለም፥ መንፈስ ቅዱስም አንድ እንጂ ሦስት አይደለም።

ከሦቱ አካላት አንዱ ከሌላው ቀዳሚነት ወይም ደኃሪነት የለውም፤ አንዱም ከሌላው የሚበልጥ ወይም የሚያንስ አይደለም።

ስለሆነም፥ ሦስቱ አካላት በእኩልነትና በዘላለማዊነት አንድ ናቸው። ከዚህ የተነሣም ከፍ ብሎ እንደተጠቀሰው ሦስቱ አካላት በአንድ መለኮት አንድ አምላክም በሦስት አካላት ይመለካል።


ሥላሴ ክርስትናን ልዩ ከምያደርጉ አስተምህሮዎች አንዱና ዋነኛው ነው። ቤተክርስቲያን በታሪኳ ከላይ በተጡቀሱት ጉባኤዎች እና የጉባኤዎቿ ትሩፋት በሆኑ የእምነት ሙግለጫዎቿ ሥላሴን በተመለከተ ለትውልድ ሁሉ የሚሆን ችንካር የሆነ አስተምህሮዋን ቀርጻልናለች። ማናችንም ብንሆን የህንን ታሪካዊ ሥነመለኮት ተቀብለን በዚህ አስተምህሮ ካልጸናን በቀር ስለ እግዚአብሔር አለን የምንለው፣ አካላቱን የሚደባልቅ፣ መለኮታዊ ህልውናውን የሚከፍል ማናቸውም መረዳት እና እምነት፣ ኑፋቄ ይሆናል። 


ናታን ቡሴኒትዝ የተባሉ ጸሓፊ አሪየስ ያስከተለውን ተፅእኖ በዚህ መልኩ ጠቅለል አድርገው አቅርበውታል፡-


“በጥንት ጊዜ የአርዮስ አስተምህሮዎች ለክርስትና ኦርቶዶክሲ ዋነኛና ቀዳሚ ስጋት ሆኖ ነበር፤ - ለዚህም ነው እንደ አሌክሳንደር ማካይ ያሉ የታሪክ ተመራማሪዎች አርዮስን 'ጥንታዊ መናፍቅ' ብለው የሰየሙት። ይህም የክርስቶስን አምላክነት የሚክደውን ማናቸውንም ትምህርት ቤተክርስቲያን ምን ያህል አደገኛ ትምህርት እንደሆነ መመልከቷን አስመልክቶ የተወሰነ ሀሳብን ይሰጠናል።”.

በሰባተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ አሪያኒዝም ጨርሶ ጠፋ፣ ነገር ግን በ16ኛው እና በ17ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሶሲኒያውያን የተባሉ ክፍሎች በዮሐንስ 14፥ 28 ላይ “ከእኔ አብ ይበልጣልና” የሚለውን ጥቅስ እንደ ማረጋገጫ እየተጠቀሙበት የክርስቶስን አምላክነት ክደው ማስተማር ጀመሩ። እነዚህ ሶሲኒያውያን የሥላሴን አስተምህሮ እና ሌሎች መሰረታዊ የክርስትና አስተምህሮዎችን ውድቅ ያደረጉ ቡድኖች ናቸው።


“ጥንታዊቷ የክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን የተነሳባትን የአርዮሳዊነትን ተግዳሮት ለማጥፋት ከፍተኛ ጥረት ብታደርግም እስከ ዛሬ ድረስ ግን የዚያን ኑፋቄ ዘር ተከትለው መንፈቅ የቀጠሉ የእምነት ቅርንጫፎች በዙርያው አሉ። እነዚህም ኑፋቄዎቻቸውን አሹልከው እያስገቡ በወንጌል የማናውቀውን ሌላ ባዕድ አምላክ ያስተዋውቃሉ። ከእነዚህ መካከል አንዱ ራሳቸውን የይሖዋ ምሥክሮች ሲሉ የሚጠሩት ናቸው። እነዚህ የይሖዋ ምሥክሮች በዚህም ከህደታቸው ያው አርዮሳውያን ናቸው። በትምህርተ ክርስቶስ የተገለጠውን የወልድን ዘላለማዊነት በጽኑ እንደሚክዱ ሁሉ በትምህርታቸው ሥላሴንም ይክዳሉ። የእግዚአብሔርን ልጅ አምላክነትም አይቀበሉም። ሞርሞኖችም የእግዚአብሔርን ልጅ እንደ እግዚአብሔር ልጅ ቢያዩትም ዘላለማዊነቱን ባለመቀበል አምላክነቱን ይክዳሉ። የሥላሴን መሰረታዊ የክርስትና ትምህርትም አይቀበሉም።” ሲሉ ሪያን ተርነር የተባሉ ጸሓፊ አስረግጠው ተናግረዋል።


እኔ እንደማስበውና ለራሴም ጥሩ ልማድ አድርጌ እንደምወስደው ከታሪካውያኑ የቤተክርስቲያን የእምነት መግለጫዎች ድንበር ውጪ “በእግዚአብሔር ቃል ጥናት ብቻ” የሥላሴን ትምህርት ለመዋጥ በእጅጉ አስቸጋሪ ሆኖ የሚተናነቅ በመሆኑ ማንም እንደዚያ እንዲያጠና አልመክርም። ሥላሴ ለሰው አእምሮ በቀላሉ ለመረዳት አስቸጋሪ በመሆኑ ብቻ ግን አስተምህሮው በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የሌለ ሊመስለንም አይገባም፣ እንደ እርሱም ማሰብም ሆነ ከሃዲያን መሆን አይኖርብንም።  


ማቴዎስ እግዚአብሔርን በፍጹም አሳባችን መውደድ እንዳለብን ሲነግረን፡-


ማቴዎስ 22፥ 37 “ ኢየሱስም እንዲህ አለው፦ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም አሳብህም ውደድ” ይላል።


አስተውሉ፣ ክርስትና ፍጹም ልብ፣ ፍጹም ነፍስ እና ፍጹም አሳብን የሚጠይቅ፣ ዲቮሽናችንን እና ዓእምሯችንን የሚፈልግ ምሁራዊ ነው። ክርስትና የሚያስቡ ሰዎች እምነት፣ የጠያቂ አማኞችም መንገድ ነው። እንደ ዕርግብ የዋሃን በሆንበት በስብከት ሞኝነት ያመንን እኛ “ነገሩ እንዲህ ይሆንን?” እያልን በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርቶች ውስጥ የሚያስቡ፣ እምነታቸውን የሚጠይቁ ብልሆች ልንሆን ደግሞ ይጠበቅብናል። እንደ ቤርያ ሰዎች እንድንሆንም ያስፈልጋል። በርግጥ ደግሞ ሥላሴ የምሁራዊ ነገር ብቻ አይደለም፤ ከፍ ሲል በተጠቀሰው የአትናቴዎስ የእምነት መግለጫ አንቀጽ 26 ላይ ምን እንደሚል ተመልከቱ፦ 


“ለመዳን የሚፈልግ ሁሉ ስለ ሥላሴ እንደዚህ ማሰብ የገባዋል” 


ይህ ታላቅ ምሥጢር ከድነታችን ጋር ያለው ግንኙነት መሰረታዊ ነው። በመጽሓፈ ስምምነት የሉተራውያን የእምነት መግለጫ ገጽ 521 እንደተብራራው፣ “መላው ሥላሴ እግዚአብሔር አብ፣ ወልድ እንዲሁም መንፈስ ቅዱስ የአብን የዘላለም ምርጫ ሊሹበት ወደሚገባቸው የሕይወት መጽሓፍ ወደሆነው ክርስቶስ ሰዎችን ሁሉ ይመራሉ። ምክንያቱም ክርስቶስ ራሱ “በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም” [ዮሓንስ 14፥ 6] እንዳለው እግዚአብሔር ሊያድናቸው የፈለጋቸውን በክርስቶስ በኩል ሊያድናቸው እንደሚፈቅድ ከዘላለም ወስኗል።” ሲል የህንንው እውነት ያስረግጣል። ልጆቹ ፈጽመው የእርሱ መሆናቸውን እንዲያረጋግጡና ሙሉ ዋስትና እንዲኖራቸው እግዚአብሔር ይፈልጋል፣ በጥርጣሬና እርግጠኝነት በሌለው ፍርሃት ውስጥ እንድንኖርም ከቶ አይፈልግም። ስለዚህ፣ እያንዳንዱ የሥላሴ አካል በዚህ ጉዳይ ማረጋገጫን እየሰጠ ሊኖረን ለተገባው ዋስትና አስተዋጽኦን ያበረክታል። እግዚአብሔር አብ ስለ እግዚአብሔር ወልድ ሥራ የተናገረውን ቃል የሚያረጋግጠው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ የሚሰጠው ምስክርነት ነው።


ቅዱሳት መጻሕፍትን ስንመረምር፣ ሥላሴን በተመለከተ እውነት የሆኑ ቢያንስ 4 ነገሮችን እናያለን።

አንደኛው፡ የሥላሴን መለኮትነት የምናይበት ነው። ይህም ጉዳይ ሥላሴን በመቀበል እና በመረዳት ረገድ ብዙዎች ከሚቸገሩበ ጉዳይ ጀርባ ያለ ዋነኛ ጥያቄ ነው። በዋናነትም የክርስቶስን እና የመንፈስ ቅዱስን አምላክነት የሚመለከተው ጥያቄ ነው። መጽሐፍ ቅዱስ አንድ አምላክ ብቻ እንዳለ አንድ መለኮታዊ ማንነት ብቻ እንዳለ ማስተማሩ ግልጽ ነው። ለምሳሌ፦

ዘዳግም 32፥ 39 “አሁንም እኔ ብቻዬን እኔ እንደ ሆንሁ፥ ከእኔም በቀር አምላክ እንደሌለ እዩ እኔ እገድላለሁ፥ አድንማለሁ፤ እኔ እመታለሁ፥ እፈውስማለሁ፤ ከእጄም የሚያድን የለም።”

ኢሳይያስ 43፥ 10 “ታውቁና ታምኑብኝ ዘንድ እኔም እንደሆንሁ ታስተውሉ ዘንድ፥ እናንተ የመረጥሁትም ባሪያዬ ምስክሮቼ ናችሁ ይላል እግዚአብሔር፤ ከእኔ በፊት አምላክ አልተሠራም ከእኔም በኋላ አይሆንም።”


እግዚአብሔር አንድ ብቻ ነው ብሎ የሚያስተምረው ያው አንዱ መጽሐፍ ቅዱስ መልሶ በዚያው አጽንዖት አብ እግዚአብሔር እንደሆነ ይነግረናል። ወልድንም እግዚአብሔር ነው ይለናል። መንፈስ ቅዱስንም ደግሞ እግዚአብሔር ነው ብሎ ያስተምረናል። ስለዚህ እነዚህ አካላት ያለምንም መደባለቅና መከፋፈል አንዱን እውነተኛ አምላክ መሆን አለባቸው።


እግዚአብሔር አንድም ሦስትም ነው። እርሱ አንድ... እግዚአብሔር አብ፣ እግዚአብሔር ወልድ፣ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው። ስለአንድነቱ ምንም ጥያቄና ጥርጥር ሊኖር አይችልም። ክርስቲያን የሆነ አማኝ ይህንን እውነት እንደ ማንኛውም አይሁዳዊ አጽንዖት የሚሰጠው እምነት ነው።  


ዘዳግም6፥ 4 "አምላካችን እግዚአብሔር አንድ እግዚአብሔር ነው”


ኢሳይያስ 45፥ 5 “እኔ እግዚአብሔር ነኝ ከእኔም በቀር አምላክ የለም ይላል" 


የመለኮት አንድነት ለወንጌል ስብከት መሠረታዊ ጉዳይ ነው፤ ያለና የሚኖረው አምላክ አንድ ነው፣ እርሱም የሚፈልገውና የሚገባው ሙሉ የሆነ የሰው ልጆች ሁሉ ታማኝነት ነው። ሁሉ ሊታመኑበት የሚገባ አንዱ እርሱ ብቻ ነውና። ነገር ግን ይህ አንድ አምላክ (አስቀድሞ እንደ እስራኤል አምላክ፣ ከዚያም ሥጋ በለበሰው ጌታ፣ ከዚያም በመንፈስ ቅዱስ) ራሱን በሦስት አካላት ማለትም በእነዚህ በየግላቸው ዘላለማዊ ህላዌነት ባላቸው ሦስቱ ሥላሴዎች ውስጥ ለዘላለም የሚኖር እንደሆነ በሚያሳይበት መንገድ ገለጧል። ስለዚህም ከሙታን የተነሣው ጌታ ኢየሱስ አህዛብ ሁሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እንዲጠመቁ በታላቁ ተልዕኮ አዟል፤ (ማቴ. 28፡19)።


ከዚህ በተቃራኒው ግን “ኢየሱስ ብቻ” የተሰኘ እንቅስቃሴ [Jesus Only Movement]፣ በመባል የሚታወቀው አንድ ብቻ ጰንጤቆስጣዊ እምነት፣ ከዚህ ያፈነገጠ አመለካከት አለው። ይህ እንቅስቃሴ በመለኮት ውስጥ ያለው አካል አንድ ብቻ ሲሆን እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ብሎ ያምናል። በቤተ ከርስቲያን ውስጥ የኖረውንና በአብ፣ በወልድ እና በመንፈስ ቅዱስ ስም የሚፈጸመውን የጥምቀት የሥላሴአዊ ቀመር ከመጠቀም ይልቅም እውነተኛው ጥምቀት “በኢየሱስ ስም” መከናወን እንዳለበት ተከታዮቹን ያስተምራል። በዚህ ኢየሱስ ብቻ በተሰኘ አስተምህሮ የሚታወቁ ተከታዮች የአብን ወይም የመንፈስ ቅዱስን መኖር ባይክዱም፣ እነዚህን ሚናዎች በመለኮት ውስጥ ካሉ የተለያዩ አካላት ይልቅ ኢየሱስ እንደተገለጠባቸው መገለጫዎቹ አድርገው ይተረጉሟቸዋል። ይህ አይነቱ እምነት ብዙ ጊዜ “ሞናርኪያኒዝም” አልያም “ሞዳሊዝም” ተብሎ ከሚታወቀው ሥነ-መለኮታዊ አቋም ጋር ይያያዛል፣ ይህም እግዚአብሔር በታሪክ ውስጥ በተለያዩ መንገዶች ወይም ቅርጾች ራሱን እንደገለጠ ይጠቁማል ባዮች ናቸው።


ሞናርኪያኒዝም በክርስትና ታሪክ ውስጥ ገና ከጠዋቱ ያቆጠቆጠ ኑፋቄአዊ የነገረ መለኮት ትምህርት ሲሆን፥ በአስተምህሮቱም የእግዚአብሔርን ሥሉስ መሆን እያደበዘዘ አንድነቱን (አንድ ብቻ መሆኑን) የሚያጎላ ነው፤ የሞናርኪያኒዝም ትምህርት ሦስት የተለያዩ፣ ማለትም አብ፣ ወልድ እና መንፈስ ቅዱስ የተባሉ አካላትን ያቀፈ አምላክነትን ከሚያሳየው ከትምህርተ ሥላሴ ጽንሰ አሳብ ጋር በእጅጉ ይቃረናል።ይህም ትምህርት የእግዚአብሔርን ማንነት እንዲሁም በእግዚአብሔር እና በኢየሱስ ክርስቶስ መካከል ያለውን ግንኙነት ለማብራራት የሚሞክር በ2ኛውና በ3ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ የተጀመረ እሳቤ ነው። ሞናርኪያኒዝም ከሚያነሳቸው ቁልፍ አሳቦቹ መካከል፦ አንደኛው፣ የእግዚአብሔር አንድነት (አንድ ብቻ መሆን) ነው፡- ሞናርክያኒዝም እግዚአብሔር አንድ የማይከፋፈል ማንነት መሆኑን አጽኖት ይሰጣል። ይህ አተያይ ብዙውን ጊዜ የአብ “ንጉሣዊ አገዛዝ” ተብሎ ይገለጻል፣ ይህም በአንድ ብቸኛ ታላቅ አምላክ ላይ ያለውን እምነት አጉልቶ የሚያሳይ ነው። ሁለተኛው፣ ክሪስቶሎጂያዊ አቋሙ ነው፡- ሞናርክያውያን ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አዳኝ ቢመለከቱትም ነገር ግን የሎጎስ (የቃሉን) ራሱን የቻለ ማነነት፣ ወይም ግላዊ ህልውናውን ይክዳሉ። ይልቁንም ለሞናርኪያኒዝም ኢየሱስ የተባለው ፍፁም አምላክ ቢሆንም ነገር ግን በማንነቱ ከእግዚአብሔር አብ የተለየ አካል አይደለም፣ ኢየሱስ ራሱ አብ ነው ብለው ያስተምራሉ። ሦስተኛው፣ በሞዳሊዝም እና በተለዋዋጭ ሞናርኪያኒዝም መካከል ያለው ተቃርኖ ነው፦ ሞናርክያኒዝም በሁለት ዋና ዋና ቅርንጫፎች ሊከፈል ይችላል። አንዱ፣ ከፍ ሲል የተጠቀሰው ሞዳሊዝም (ወይም ሞዳሊስት ሞናርኪያኒዝም) ሲሆን፡- ይህ አመለካከት እግዚአብሔር የሚገለጠው በሦስት ዓይነት ራሳቸውን በቻሉ አካላት ሳይሆን ይልቁንም በሦስት ዓይነት መንገዶች ወይም ቅርጾች (አብ፣ ወልድ እና መንፈስ ቅዱስ) እየሆነ ነው የሚለው ነው፤ ሌላኛው ደግሞ ተለዋዋጭ ሞናርኪያኒዝም ነው፣ ይህኛው አመለካከት ደግሞ ኢየሱስ ከእግዚአብሔር የተቀበለው፣ ወይም መለኮታዊ ሃይልን የተጎናጸፈ ሰው ብቻ መሆኑን ያሳያል፣ ትምህርቱም የክርስቶስ ሰብኣዊነት ላይ ብቻ አጽንዖት ይሰጣል። ሞናርክያኒዝም በጥንታዊው የክርስትና ሥነ-መለኮት፣ በተለይም በትምህርተ ሥላሴ ጽንሰ አሳብ ዙሪያ ተፈጥረዋል ላላቸው ተግዳሮቶች ምላሽ ለመስጠት ያሰበ አስተምህሮ ነው። ይህ እንቅስቃሴ አንድን አምላክን ብቻ ለማምላክ የነበረውን የጥንቶቹ ክርስቲያኖች እምነት ኋላ ላይ ስለ ሥላሴ በተሰጡ ትርጓሜዎች እንደተጣሰ ስለመሰለው የጥንት የሚለውን አንድን አምላክ ብቻ የማመንና የማምለክ ትውፊት ጠብቆ ለማቆየት ይጥራል።


ሞዳሊዝምም፣ በሚከተለው አስተምህሮተ ክርስቶስ አንድ ብቻ ክሪስቶሎጂ [Oneness Christology] በመባልም ይታወቃል፤ በመለኮት ውስጥ ምንም የተለያዩ አካላት የሉም የሚል ሥነ-መለኮታዊ አስተምህሮ ነው። ከዚህ ይልቅ ሞዳሊዝም እግዚአብሔር ራሱን እንዴት እንደገለጠ ሲያስተምር በሦስት የተለያዩ “ሞዶች” ወይም “ጭምብሎች” ወይም ገጸባህርያት እንደ አብ፣ እንደ ወልድ፣ ወይም እንደ መንፈስ ቅዱስ እየተወነ ተገለጠ የሚል አጉል ትምህርት ነው። በዚህ አተያይ መሰረት፣ እግዚአብሔር በባህሪው አንድ ነው ነገር ግን በተለያዩ ጊዜያት በተለያየ መልክ ይሰራል። ለምሳሌ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር እንደ አብ ሆኖ ታይቷል በአዲስ ኪዳን ደግሞ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆኖ እንደ ወልድ ተገለጧል አሁን ደግሞ እንደ መንፈስ ቅዱስ ሆኖ ይሰራል፣ እንጂ ከመጀመሪያ አንስቶ አንድ ብቻውን፣ ነጠላውን ነው ይላሉ። ይህ አተያይ እግዚአብሔር በመለኮታዊ ባሕርዩ አንድ እና በሦስት አካል የተገለጠ ነው ከሚለው ክርስቲያናዊ ከሆነው የሥላሴ አስተምህሮታዊ ኦርቶዶክሲ ጋር በእጅጉ ይቃረናል።


በጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ሞዳሊዝም የታየው በተለይም ሳቤሊየስ ከተባለ ጳጳስ አስተምህሮ ጋር በተያያዘ ነው። ጳጳሱም ሆነ አስተምህሮው ዋና በሆኑ የጥንት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ እንደ መናፍቅ እና እንደ ኑፋቄ ይቆጠራሉ። ምክንያቱም የአብ፣ የወልድን እና የመንፈስ ቅዱስን አንድነት፣ አካላዊ ልዩነቱንም የሚያጎላውን የሥላሴን ትውፊታዊ ግንዛቤ የሚክድ በመሆኑ ነው። በኖረው የቤተክርስቲያን የሥላሴ አስተምህሮ እና ከፍ ሲል በተጠቀሰው የሞዳሊዝም አተያይ የሳቤሊየስ የመንፈስ ልጆቹ በሆኑ “ኢየሱስ ብቻ” በተሰኘው ጰንጤ ቆስጣዊ እንቅስቃሴ መካከል ያለው ክርክር የእግዚአብሔርን መሰረታዊ ባህርይ እና የኢየሱስን ማንነት በተመለከተ በክርስትና ውስጥ የሚነሱ ጉልህ የሆኑ ሥነ-መለኮታዊ ልዩነቶችን የሚዳስስ ነው። ታሪካዊው የቤተክርስቲያን ትምህርተ ሥላሴ በሶስት አካላት መካከል ያለውን በሦስትነቱ አንድነቱ በአንድነትም ሦስትነት የሚብራራበትን ምጡቅ አንድነት ያለመከፋፈልና ያለመደባለቅ ሲያጎላ፣ “ኢየሱስ ብቻ” የተሰኘው የጰንጤ ቆስጤ እንቅስቃሴ ግን ይህንን ምጡቃዊ አስተምህሮ ገሸሽ አድርጎ ለራሱ የሚመቸውን ቀለል ያለ ምንገድ በመፈለግ ኢየሱስን የእግዚአብሔርና የመንፈስ ቅዱስ ብቸኛ መገለጫ አድርጎ በነጠላው ይወስደዋል፣ በዚህም ኑፋቄው መለኮትን አንድ ነጠላ አካል ብቻ ያደርገዋል። “ኢየሱስ ብቻ” ለሚሉ የሳቤሊየስ ልጆች አምላክ መልኩንና ባህርዩን እየቀያየረ ተውኔት እንደሚጫወት አይነት ነው፤ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር (አብ) ሆኖ የተወነው ራሱ በአዲስ ኪዳን ኢየሱስ (ወልድ) ሆኖ ተውኗል፣ አሁን ደግሞ በአማኞች ውስጥ ያው ኢየሱስ መንፈስ ቅዱስን ሆኖ እየተወነ ነው የሚል ሦስትነቱንና አንድነቱን ወደ ነጠላነት የቀየረ አስተምህሮ ነው። እንግዲህ እነዚህን ልዩነቶችና የኑፋቄውን ታሪካዊ መሰረት መረዳት በክርስቲያናዊ አንኳር አስተምህሮ እና እምነት ዙርያ ውይይት ለማድረግና የሳቱትን ለመመለስ ወሳኝ ነው። ቀጥሎ ያቀረብኳቸውን ነጥቦች ተመልከቱ፦


፩ኛ/ በቅዱሳት መጻሕፍት አብ አምላክ እንደሆነ በግልጽ የተነገረ ትምህርት ነው፡-


ዮሓንስ6፥ 37 “አብ የሚሰጠኝ ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል፥ ወደ እኔም የሚመጣውን ከቶ ወደ ውጭ አላወጣውም፤”


መጽሓፍ ቅዱስ አምላክ ስለሆነው እና አብ ተብሎ ስለሚጠራው ማንነት በግልጽ ይነግረናል። በአንዱ አምላክ ሥላሴአዊ ማንነት ውስጥ አብ ተብሎ የሚታወቅ ቀዳሚ አካል አለ። 


ማቴዎስ 6፥ 6 “አንተ ግን ስትጸልይ፥ ወደ እልፍኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ በስውር ላለው አባትህ ጸልይ፤ በስውር የሚያይ አባትህም በግልጥ ይከፍልሃል።”


ኤፌሶን 4፥ 6 “ከሁሉ በላይ የሚሆን በሁሉም የሚሠራ በሁሉም የሚኖር አንድ አምላክ የሁሉም አባት አለ።”


አብም የቅድስት ሥላሴ የመጀመሪያው ተጠሪ ሲሆን፣ ከወልድ እና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እኩል ነው።


ቆላስያስ 1፥ 2 “….ከእግዚአብሔር ከአባታችን ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ይሁን።”


1ጴጥሮስ 1፥ 2 “…እግዚአብሔር አብ አስቀድሞ እንዳወቃቸው በመንፈስም እንደሚቀደሱ፥ ይታዘዙና በኢየሱስ ክርስቶስ ደም ይረጩ ዘንድ ለተመረጡት…”


2ጴጥሮስ 1፥ 17 “¹⁷ ከገናናው ክብር። በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው የሚል ያ ድምፅ በመጣለት ጊዜ ከእግዚአብሔር አብ ክብርንና ምስጋናን ተቀብሎአልና፤”


ሁሉንም ማለት በሚቻልበት አኳዃን በተለይ የቅዱስ ጳውሎስን መልእክቶች ከተመለከታችሁ ለሚጽፍላቸው ሰዎች ሰላምታ ሲያቀርብ “በእግዚአብሔር አብ ስም ሰላም” በማለት መልእክቱን እንደሚጀምር ሁሉ መልእክቱን ሲያጠቃልልም ተሚዘጋው በሥላሴዎች በረከት ነው፤


2 ቆሮንቶስ 13፥ 14 “የጌታ የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ የእግዚአብሔርም ፍቅር የመንፈስ ቅዱስም ኅብረት ከሁላችሁ ጋር ይሁን። አሜን።”


ምክንያቱም መባረክ የሚችል በሕያውነት ያለ አንድ ነውና፦


ኤፌሶን 4፥ 4 “አንድ መንፈስ …አንድ ጌታ…አንድ አምላክ ..አባት” ነው። 


ስለዚህ አብ ራሱ እግዚአብሔር አምላክ እንደሆነ እናውቃለን። 


፪ኛ/ ወልድ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስም እግዚአብሔር አምላክ እንደሆነ የሚያስተምሩ በርካታ ጥቅሶችም አሉ።


ለምሳሌ፣ ነብዩ ኢሳይያስ ስለሚመጣው መሲሕ በተናገረበት በትንቢቱ ጌታ ኢየሱስን “ኃያል አምላክ” ብሎ ጠርቶታል።


ኢሳያስ 9፥ 6 “ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ ስሙም ድንቅ መካር፥ ኃያል አምላክ፥ የዘላለም አባት፥ የሰላም አለቃ ተብሎ ይጠራል።”


ተመልከቱ ስለሚወለደው ሕጻን በይፋ የተነገሩ፣ ማንነቱን የሚገልጹና የሚጠራባቸው ስያሜዎቹ አለም ከተፈጠረበት ጊዜ አንስቶ ማንም ያልተጠራባቸው ናቸው። መጽሓፍ ቅዱስ አምላክ ስለሆነው እና የእግዚአብሔር ልጅ ወልድ ተብሎ ስለሚጠራው ማንነት በግልጽ ይነግረናል። በአንዱ አምላክ ሥላሴአዊ ማንነት ውስጥ ወልድ ተብሎ የሚታወቅ ሌላ ሁለተኛ አካል አለ። 


ማርቆስ 1፥ 1 “የእግዚአብሔር ልጅ የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌል መጀመሪያ።”


ዮሓንስ 20፥ 31 “ነገር ግን ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ ታምኑ ዘንድ፥ አምናችሁም በስሙ ሕይወት ይሆንላችሁ ዘንድ ይህ ተጽፎአል።”


እርሱም ስለህዝቡ ኃጢአት የፍጻሜ ማስተሰረያውን ሊያቀርብ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ከድንግል ማሪያም ሥጋን ነስቶ የመጣው መሲሁ ሲሆን፣ የህዝቡንም መዳን ፍጹም ያደርግ ዘንድ በዚያው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ በ70 ዓ.ም ይጠባበቁት ለነበሩ ለቅዱሳኑ በዳግመኛ ምጻቱ ፓሮዥያ በክብርና በፍርድ የተመለሰው ነው።


እብራውያን 9፥ 28 “እንዲሁ ክርስቶስ ደግሞ፥ የብዙዎችን ኃጢአት ሊሸከም አንድ ጊዜ ከተሰዋ በኋላ፥ ያድናቸው ዘንድ ለሚጠባበቁት ሁለተኛ ጊዜ ያለ ኃጢአት ይታይላቸዋል።”


ወልድ ተብሎ የሚጠራው እርሱ ራሱ እግዚአብሔር ነው። እርሱም የቅድስት ስላሴ ሁለተኛ ተጠሪ ነው። ነገር ግን ደግሞ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እኩል ነው። እርሱ ስለ እኛ ልናየው እንዲቻለን በሥጋ የተገለጠ አምላክ ነው። እርሱ ለእኛና ስለ እኛ እውነተኛውን አምላክ የሚገልጥልን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሆነ መገለጥ ነው፣ እርሱን ስናይ እግዚአብሔርን እናያለን።


ዮሓንስ 1፥ 1 እና 14 “¹ በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ።….¹⁴ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን።”


ቆላስያስ1፥ 15 “እርሱም (ኢየሱስ) የማይታይ አምላክ ምሳሌ ነው።…ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኵር ነው።”


እግዚአብሔር ራሱ ካልሆነ በቀር እግዚአብሔርን ሊገልጥልን የተቻለው የለም። አሁን እዚህ ላይ ከአዲሱ መደበኛ የመጽሓፍ ቅዱስ ትርጉም አንድ አስገራሚ ጥቅስ ላሳያችሁ፦


ዮሃንስ 1፥ 18 “ከቶውንም እግዚአብሔርን ያየ ማንም የለም፤ ነገር ግን በአብ እቅፍ ያለው አንድያ ለጁ የሆነው አምላክ እርሱ ገለጠው።”


አዎ እርሱ (ልጁ) እግዚአሔር አምላክ ነው። የቶማስን የተጠራጣሪነት ታሪክ ታስታውሳላችሁን? ከሞት የተነሳውን ክርስቶስን ለመጀመሪያ ጊዜ በአይኖቹ አይቶ የተወጋውን ጉኑን በጣቶቹ በነካ ጊዜ የተናገረውን ቃል አታስታውሱም? እንዲህ ነበር ያለው:-


ዮሐንስ 20፥ 28 “ቶማስም፣ ጌታዬ አምላኬም ብሎ መለሰለት።”


ኢየሱስም ቶማስን መልሶ። “ስለ አየኸኝ አምነሃል፤” አለው፣ ይህም በትክክል መልሰሃል እኔም ማን እንደሆንሁ አሁን በደንብ ገብቶሃል! ማለት ነው። ኢየሱስ ቶማስን አላረመወም።


ዕብራውያን 1፥ 8 “ስለ ልጁ ግን፦ አምላክ ሆይ፥ ዙፋንህ እስከ ዘላለም ድረስ ይኖራል፤ የመንግሥትህ በትር የቅንነት በትር ነው።”


ተመልከቱ እዚህ ላይ እንደውም “አምላክ ሆይ፥” ብሎ ስለ ልጁ የሚናገር ራሱ እግዚአብሔር ነው። ጆን ስቶት Authentic Christianity በተሰኘው መጽሐፋቸው ገጽ 36 ላይ የኢየሱስን አምላክነት አስመልክቶ ጥያቄ አንስተው ሲመልሱ “ኢየሱስ የሚገባው አምልኮ ነው ወይስ አድናቆት ብቻ? በእውነት እርሱ አምላክ ከሆነ እንግዲያውስ አምልኳችን፣ በእርሱ ላይ መታመናችን እና እርሱን መታዘዛችን ይገባዋል። እርሱ አምላክ ካልሆነ ግን እንዲህ ያለውን አምልኮ ለእርሱ መስጠት ጣዖትን ማምለክ ይሆናል” ይላሉ። እንግዲህ ኢየሱስን አምላክ ብሎ በመጥራት ጉዳይ ቶማስንም እግዚአብሔርንም ተሳስተው ነበር ልንል እኛ ማነን?


፫ኛ/ መጽሓፍ ቅዱስ አምላክ ስለሆነው እና መንፈስ ቅዱስ ተብሎ ስለሚጠራው ማንነት በግልጽ ይነግረናል። በአንዱ አምላክ ማንነት ውስጥ መንፈስ ቅዱስ ተብሎ የሚታወቅ ሌላ ሦስተኛ አካል አለ። እርሱም የቅድስት ሥላሴ ሦስተኛ ተጠሪ ነው፤ ነገር ግን ደግሞ ከአብና ከወልድ ጋር እኩል ነው። ጳራቅሊጦስ የተባለው እርሱ አጽናኝችንና ረዳታችን ነው። እርሱም ከአብ ዘንድ የሆነ ስለ ክርስቶስ የሚመሰክረው ነው (ዮሓንስ 15፥ 26)። መንፈስ ቅዱስ ሁል ጊዜ ሲጠቀስ “እርሱ” ተብሎ በህላዌ ማንነቱ ይታወቃል እንጂ እንደ አንድ ነገር ወይም ቁስ “ይህ” አይባልም። (ዮሓንስ 14፥ 16-17፣ 26፤ ሓዋርያት 5፥ 32 ተመልከቱ)። 


መንፈስ ቅዱስ ተብሎ የሚጠራው ማንነት ራሱ አምላክ ነው። መንፈስ ቅዱስም አምላክ እንደሆነ የሚያስተምሩ ጥቅሶችም ደግሞ አሉ። በተለይ በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ 5 ላይ ሐናንያ እና ሰጲራ ከንብረታቸው ሽያጭ ከፊሉን ሸሽገው ለቤተክርስቲያን የሰጡት ገንዘብ ምን ያህል እንደሆነ በተጋለጡና መንፈስ ቅዱስን በዋሹ ጊዜ ጴጥሮስ ምን ብሎ እንደተናገራቸው ቃሉን ታስታውሳላችሁን? እንዲህ ነበር ያላቸው:-


ሐዋርያት ሥራ 5፥ 3-4 “ጴጥሮስም፦ ሐናንያ ሆይ፥ መንፈስ ቅዱስን ታታልልና ከመሬቱ ሽያጭ ታስቀር ዘንድ ሰይጣን በልብህ ስለ ምን ሞላ? ሳትሸጠው የአንተ አልነበረምን? ከሸጥኸውስ በኋላ በሥልጣንህ አልነበረምን? ይህን ነገር ስለ ምን በልብህ አሰብህ? እግዚአብሔርን እንጂ ሰውን አልዋሸህም አለው።”


ስለዚህ መንፈስ ቅዱስን መዋሸት እግዚአብሔርን ከመዋሸት ጋር አንድ ነው፣ ምንም ልዩነት የለውም። ምክንያቱም እርሱ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ አምላክ ነውና! ስለ እግዚአብሔር የተነገረ ነገር ስለመንፈስ ቅዱስም የተነገረ መሆኑን ስናይ መንፈስ ቅዱስ ራሱ እግዚአብሔር መሆኑን እናስተውላለን።


ሓዋርያት 3፥ 21 “እግዚአብሔር ከጥንት ጀምሮ በቅዱሳን ነቢያቱ አፍ የተናገረው፥…”


2ጴጥሮስ 1፥ 21 “²¹ ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና፥ ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ።”


መጽሓፍ ቅዱስ የአማኞች ሰውነት “የሕያው እግዚአብሔር ቤተመቅደስ” መሆኑን በሚናገርበት በዚያው ድምጸት መልሶ የአማኞች ሰውነት የመንፈስ ቅዱስ ቤተመቅደስ መሆኑን ይናገራል (1ቆሮንቶስ 6፥ 16 እና 19)። በአማኞች ዘንድ እንዲኖር የተሰጠው እርሱ ራሱ እግዚአብሔር የሆነው መንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር መንፈስ ደግሞም የክርስቶስ መንፈስ ነው፤ 

ሮሜ 8፥ 9 “እናንተ ግን የእግዚአብሔር መንፈስ በእናንተ ዘንድ ቢኖር፥ በመንፈስ እንጂ በሥጋ አይደላችሁም። የክርስቶስ መንፈስ የሌለው ከሆነ ግን ይኸው የእርሱ ወገን አይደለም”። 


ሁለተኛው፣ የሥላሴን አንድነት የምናይበት ነው። በተለይ በአለም አፈጣጠር ውስጥ ይህንን አንድነት በጉልህ እናያለን፡-


ዘፍጥረት 1፥ 26 “እግዚአብሔርም አለ፦ ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌአችን እንፍጠር፤ የባሕር ዓሦችንና የሰማይ ወፎችን፥ እንስሳትንና ምድርን ሁሉ፥ በምድር ላይ የሚንቀሳቀሱትንም ሁሉ ይግዙ”


ልብ በሉ፣ ሰውን እኔ ልፍጠረው አላለም። ይልቁንም "እኛ እንፍጠር!" ነው ያለው። ስላሴ የሆነው አምላክ በሰው ልጅ መፈጠር ውስጥ በአንድነት ተሳትፎ ያደርጋል። ይህ ስለ መላእክት አለመናገሩን እንዴት ልናውቅ እንችላለን? ተመልከቱ በዘፍጥረት 1፥ 1 ላይ ሰማይንና ምድርን የፈጠረ አምላክ እንዳለ ያሳያል። ያኔም በቁጥር 2 ላይ የእግዚአብሔር መንፈስ በውሃው ላይ ሰፍፎ ነበር ይለናል። በቆላስይስ መልዕክት ደግሞ ክርስቶስ ሰማይንና ምድርን እንደፈጠረ ተነግሮናል!


ቆላስይስ 1፥ 16 “የሚታዩትና የማይታዩትም፥ ዙፋናት ቢሆኑ ወይም ጌትነት ወይም አለቅነት ወይም ሥልጣናት፥ በሰማይና በምድር ያሉት ሁሉ በእርሱ ተፈጥረዋልና ከፍጥረት ሁሉ በፊት በኵር ነው፤ ሁሉ በእርሱና ለእርሱ ተፈጥሮአል፤”


ሥላሴዎች በመለኮታዊ አንድነት ተባብረው አብረው መሥራታቸው በቤተክርስቲያን ውስጥ ነገሮች እንዴት መሆንና መከናወን እንዳለባቸው የሚያሳይ ውብ ሥዕል ነው።


ዮሐንስ 17፥ 11 “ከዚህም በኋላ በዓለም አይደለሁም፥ እነርሱም በዓለም ናቸው፥ እኔም ወደ አንተ እመጣለሁ። ቅዱስ አባት ሆይ፥ እነዚህን የሰጠኸኝን እንደ እኛ አንድ እንዲሆኑ በስምህ ጠብቃቸው።”

ዮሐንስ 17፥ 20-21 “ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ፥ ከቃላቸው የተነሣ በእኔ ስለሚያምኑ ደግሞ እንጂ ስለ እነዚህ ብቻ አልለምንም፤ አንተ እንደ ላክኸኝ ዓለም ያምን ዘንድ፥ አንተ፥ አባት ሆይ፥ በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ እለምናለሁ።”


አንድነት እግዚአብሔር ለህዝቡ የሚፈልገው የከበረ ነገር ነው። ባፕቲስቶች ቢሆኑ፣ ሉተራውያን፣ ወንጌላውያን ቢሆኑ፣ ጴንጤቆስጤዎችና ተሐድሶዎች - ሁሉም ወንጌል አማኞች የኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌልን የመስበክ ዓላማ ይዘው በኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት እና በሥራው ዙሪያ አንድ ሆነዋል። እንግዲህ ክርስቲያናዊ አንድነት አስቀድሞ በሥላሴ ውስጥ ያለውና የሚኖረው አንድነት ነጸብራቅ መሆን አለበት።


ሦስተኛው፣ የሥላሴ ልዩ ልዩ አሰራር የምናይበት ነው። የሥላሴ አካላት የሚሰሩት አብረው ነው፣ ነገር ግን ሁልጊዜ ሁሉም አንድ ዓይነት ነገር ላያደርጉ ይችላሉ። ለምሳሌ ድነትን ተመልከቱ። አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ በድነት ስራ ውስጥ ያላቸው ሚና ልዩ ልዩ ነው፤ ይህ ልዩነት አንዱ ከሌላው ጋር በአሰራር ያለውን ልዩነት ወይም ተቃርኖ ማለት ሳይሆን ይልቁንም ልዩ ልዩ አሰራርን የሚያመለክት ነው። አስቀድሞ ከዘላለም በክርስቶስ የመረጠው ህዝቡ መዳንን እንዲያገኝ በሉዓላዊ ጥበብ፣ በመለኮታዊ ሀይል እና በፍቅር አብረው የሚሰሩ ሶስት የመለኮት አካላትን ተመልከቱ፤ አብ ከዘላለም ይመርጣል፣ ወልድ በቤዛኑቱ የአብን ፈቃድ ይፈጽማል፣ መንፈስ ቅዱስም ተሃድሶን በመስጠት የአብንና የወልድን ዓላማ ያስፈጽማል። ድነትን እውን ያደረጉ ሦስት የተለያዩ ሚናዎች፣ ግን ሁሉም ለአንድ ዓላማ ይሰራሉ።


የክርስቶስ አካል በሆነችው፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ፣ ብዙ ልዩ ልዩነቶች አሉ፣ ነገር ግን ደግሞ አንድነትም አለ። ጳውሎስ ይህንን ለማስረዳት የሰውን አካል እና የአካል ብልቶችን አንስቶ በምሳሌ ይጠቀማል። በፊታችንም እየሳለ የሰው አካል በይዘቱ ከክርስቶስ አካል አሠራር ጋር ባለው ትይዩነት ትምህርቱን ያስተላልፍበታል:-


1ቆሮንቶስ 12፥ 12 “ አካልም አንድ እንደ ሆነ ብዙም ብልቶች እንዳሉበት ነገር ግን የአካል ብልቶች ሁሉ ብዙዎች ሳሉ አንድ አካል እንደ ሆኑ፥ ክርስቶስ ደግሞ እንዲሁ ነው፤”


የሰው አካል እጅግ አስደናቂ የሆነ አይነተኛ የእግዚአብሔር ፍጥረት ነው። የአካሉ ተፈጥሮና እርስ በርሱ የተጋጠመበት ጅማት በሚያስደንቅ ሁኔታ ውስብስብ ነው፣ ነገር ግን ደግሞ ብልቶች አንዱ ከሌላው ጋር የተዋሃደ፣ ወደር የማይገኝለት መግባባት ትስስር እና መስተጋብር ያለው ነው። የሰው አካል ብልቶች ተስማምተው ሊሰሩ የማይችሉት በበሽታ ምክንያት ነው። በበሽታ ምክንያት አዕምሮው ካለበት ከማዘዣው ጭንቅላት ተገቢውን ምላሽ መስጠት የተሳነውን አካል ወይም የአካል ክፍል ማየት እጅግ አሳዛኝ ሁኔታ ነው።


1ቆሮንቶስ 12፥ 14-16 “አካል ብዙ ብልቶች እንጂ አንድ ብልት አይደለምና። እግር፦ እኔ እጅ አይደለሁምና የአካል ክፍል አይደለሁም ብትል፥ ይህን በማለትዋ የአካል ክፍል መሆንዋ ይቀራልን? ጆሮም፦ እኔ ዓይን አይደለሁምና የአካል ክፍል አይደለሁም ቢል፥ ይህን በማለቱ የአካል ክፍል መሆኑ ይቀራልን?”


እያንዳንዳችን በማህብረሰቡ ውስጥ ልዩ የሆነ ነገር ማበርከት እንዲቻለን እግዚአብሔር ሆን ብሎ ልዩ ልዩ አድርጎ ሰርቶናል። ሥላሴን በተመለከተም ያለው አሰራር በዚሁ ተመሳሳይ መንገድ ነው። እያንዳንዱ የሥላሴ አካል ሕይወታችንን በተመለከተ በአይነቱ የተለየ እና በአሰራሩ ልዩ የሆነ ነገርን ያበረክታል። ለምሳሌ ሮሜ 8፥ 28 ላይ እግዚአብሔር ነገርን ሁሉ ለበጎ ይሰራል ይላል። ቁጥር 34 ላይም ኢየሱስ ስለ እኛ ይማልዳል ብሎ ይናገራል። በቁጥር 26 ላይ ደግሞ መንፈስ ቅዱስ ይማልድልናል፣ እንዴት እንደምንጸልይም ይረዳናል ይላል። ይህ እንግዲህ የሚያሳየው በሕይወታችን ውስጥ ያለውን የሥላሴን ልዩ ልዩ አሰራር ነው።


እስካሁን የሥላሴን መለኮትነት፣ የሥላሴን አንድነት፣ በሥላሴ ውስጥ ያለውን ልዩ ልዩ አሰራር አይተናል።


አራተኛው ደግም በሥላሴ ውስጥ ያለውን መቀራረብ የምናይበት ነው።


ዮሐንስ 3፥ 35 “አባት ልጁን ይወዳል ሁሉንም በእጁ ሰጥቶታል።”


ዮሐንስ 14፥ 31 “ነገር ግን አብን እንድወድ ዓለም ሊያውቅ፥ አብም እንዳዘዘኝ፥ እንዲሁ አደርጋለሁ። ተነሡ፤ ከዚህ እንሂድ።”


ይህ የሚነግረን አምላካችን በግል የሚታወቅና የቅርብ መሆኑን ነው። እርሱ ከራሱ ጋር መገናኘት የሚችልና የሚወድ በህብረት ውስጥ ያለ አምላክ ነው። እግዚአብሔር በእርሱ ውስጥ እንዳለው አይነት ያማረ ቅርርብ ከእኛም ጋር ተመሳሳዩ ህብረት እንዲኖረው መፈለጉ ደግም እጅግ የከበረ ነገር ነው።


አንዱ አምላክ ቅድስት ሥላሴ ነው፣ ቅድስት ሥላልሴም አንዱን አምላክ ነው። መጽሐፍ ቅዱስም አንድ አምላክ እንዳለ፣ እርሱም በሦስት አካላት አብ፣ ወልድ እና መንፈስ ቅዱስ ሆኖ ለዘላለም ያለና የሚኖር እንደሆነ ማስተማሩ ግልጽ ነው። ሦስት አካላት እንጂ ሦስት አማልክት የሉም። ያለው ሥሉስ የሆነ አንድ አምላክ ነው። ታዲያ ይህንን ለሰዎች እንዴት እንዲገባቸው እንዴት ልናብራራው ይቻሉናል? ደካማ የሆነ የሰው ልጅ ስለ እግዚአብሔር ሊታወቅ የሚቻለውን ሁሉ ጠንቅቆ ሊያውቅ የሚችልበት ምንም መንገድ የሌለ መሆኑን በሚገባ ላስታውሳችሁ እወዳለሁ። ከፈለጋችሁ በአለም ሁሉ ወዳለ ቤተመጻህፍት ሂዱና የደረሳችሁበትን ያህል መጽሕፍትን ማንበብ፣ ስለ እግዚአብሔርም የሆነውን የተባለውን ነገር መቧጨር ትችላላችሁ። ያ ሁሉ እግዚአብሔርን ወደማወቅ አያደርስም። ጳውሎስ የተናገረውን ስሙ:-


ሮሜ 11፥ 34 “የጌታን ልብ ያወቀው ማን ነው? ወይስ አማካሪው ማን ነበር?”


ኢሳይያስም በዚህ መንገድ አስቀምጦታል:-


ኢሳይያስ 55፥ 8-9 “አሳቤ እንደ አሳባችሁ መንገዳችሁም እንደ መንገዴ አይደለምና፥ ይላል እግዚአብሔር፡፡ ሰማይ ከምድር ከፍ እንደሚል፥ እንዲሁ መንገዴ ከመንገዳችሁ አሳቤም ከአሳባችሁ ከፍ ያለ ነው።”


ዋናው ነገር ሥላሴን ሙሉ በሙሉ ለመረዳት ለሰው ልጅ እጅግ በጣም ከባድ ጉዳይ መሆኑ ነው። እንኳንም ከባድ፣ አይምሮንም የሚያልፍ ሆነ። ከመታወቅ የሚያልፈውን፣ መርምረው የማይደርሱበትን፣ ጠንቅቀንም አውቀን የምንጨርሰው አምላክ አናመልክም። ሥላሴ በእውነት ለእኛ በጣም ትልቅና አይምሮን የሚያልፍ ምጡቅ ርእሰ ጉዳይ ነው። እርሱን የምናስተያይበትና የምናመሳስልበት ማናቸውም ጉዳዮች በእውነቱ ፈጽመው ይፈርሳሉ።


የሥላሴን ትምህርት የምቀበለው በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ የተገለጠ ትምህርት መሆኑን ስላየሁ ነው እንጂ እኔ ፈጽሜና ጠንቅቄ ልረዳው የምችለው ስለሆነ አይደለም። በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ እኛን የማይገባን ነገር ያልገባን ስለሆነ ብቻ የእግዚአብሔር ቃል እውነትነቱ ያበቃል ማለት አይደለም። የእግዚአብሔር ቃል ብንረዳውም ባንረዳውም፣ ቢገባንም ባይገባንም እውነት ሆኖ የሚኖር ነው። እኛ ስለ ገባን የእግዚአብሔር ቃል እንደማይሆን ሁሉ እኛን ስላልገባን የእግዚአብሔር ቃል ከመሆን አይጎድልም።


በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ሚስጥር የሆኑና እንቆቅናሽ የሆኑ ነገሮች መኖራቸውን በተመለከተ ፈጽሞ አያሳስበኝም፣ የተገለጠው እንጂ ምስጢር ሆኖ የተሰወረው አያስጨንቀኝም፤ እስከምሞትበት ቀን ድረስ እንኳ በቅጡ ሳልረዳቸው የሚቀሩ ነገሮች በመኖራቸው ላይ ምንም ስጋት አይገባኝም። እኔ በዚህ ጉዳይ ተጨንቄ አላውቅም። ልረዳቸው የተገቡ ጉዳዮችን በተመለከተ ጌታ በፊቴ ባዘጋጀው ገበታዬ ላይ የሚበቃኝንና የተትረፈረፈ ማእድ አግኝቻለሁ! አሁን ግን እርሱ በዘላለማዊነቱ፣ በማይመረመረው፣ ሊታወቅ በማይችለውና ከመታወቅ በሚያልፈው ማንነቱ ከዘላለም በራሱ የሆነውን ሁሉ ለመመርመር ከሚሆን ደካማ መፍጨርጨር ይልቅ እግዚአብሔር እኔ እንድኖረውና እንድታዘዘው የተገባኝን፣ እርሱ በሰጠው መገለጥ ያዘዘውን ስለማድረግ የበለጠ ያሳስበኛል። እስቲ በማርቆስ ወንጌል ስለ ኢየሱስ ማንነት የተሰጡ አራት ምስክሮች አንስተን እያንዳንዳቸው ምን እንዱሚመሰክሩ፣ ከዚህም በላይ ሌላ ምንም ማስረጃ እንደማያስፈልገን እንመልከት:-


1. ማርቆስ ኢየሱስ እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ተናግሯል (ማር. 1፥ 1)።


 2. ነቢያትም ኢየሱስ ጌታ ነው ብለው መስክረዋል (ማር 1፥ 2-3)። 


 3. መጥምቁ ዮሐንስም ከእኔ በኋላ የሚመጣው ኢየሱስ ከእኔ ይልቅ የሚበረታ ነው ብሏል (ማር 1፥ 7-8)።


 4. እግዚአብሔር አብም ከሰማይ በሆነ ድምጹ ኢየሱስ የተወደደው የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ተናግሯል (ማር 1፥ 10-11)።


በመጨረሻም ለእምነትና ለሕይወት የተሰጠንን በቂ መገለጥ ስሙ:-


ዮሐንስ 20፥ 30-31 “ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ፤ ነገር ግን ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ ታምኑ ዘንድ፥ አምናችሁም በስሙ ሕይወት ይሆንላችሁ ዘንድ ይህ ተጽፎአል።”

gkr



From Blogger iPhone client